1|1|በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ በኾነው፡፡ 1|2|ምስጋና ለአላህ ይገባው የዓለማት ጌታ ለኾነው፤ 1|3|እጅግ በጣም ርኅሩህ በጣም አዛኝ 1|4|የፍርዱ ቀን ባለቤት ለኾነው፡፡ 1|5|አንተን ብቻ እንግገዛለን፤ አንተንም ብቻ እርዳታን እንለምናለን፡፡ 1|6|ቀጥተኛውን መንገድ ምራን፡፡ 1|7|የእነዚያን በነርሱ ላይ በጎ የዋልክላቸውን በነሱ ላይ ያልተቆጣህባቸውንና ያልተሳሳቱትንም ሰዎች መንገድ (ምራን፤ በሉ)፡፡ 2|1|አ.ለ.መ 2|2|ይህ መጽሐፍ (ከአላህ ለመኾኑ) ጥርጥር የለበትም፤ ለፈራህያን መሪ ነው፡፡ 2|3|ለነዚያ በሩቁ ነገር የሚያምኑ ሶላትንም ደንቡን ጠብቀው የሚሰግዱ ከሰጠናቸውም ሲሳይ የሚቸሩ ለኾኑት፤ 2|4|ለእነዚያም ወደ አንተ በተወረደውና ከአንተ በፊትም በተወረደው የሚያምኑ በመጨረሻይቱም (ዓለም) እነርሱ የሚያረጋግጡ ለኾኑት (መሪ ነው)፡፡ 2|5|እነዚያ ከጌታቸው በመመራት ላይ ናቸው፤ እነዚያም እነሱ ፍላጎታቸውን ያገኙ ናቸው፡፡ 2|6|እነዚያ የካዱት (ሰዎች) ብታስፈራራቸውም ባታስፈራራቸውም በነርሱ ላይ እኩል ነው፤ አያምኑም፡፡ 2|7|አላህ በልቦቻቸው ላይ በመስሚያቸውም ላይ አትሞባቸዋል፤ በዓይኖቻቸውም ላይ መሸፈኛ አልለ፤ ለነሱም ታላቅ ቅጣት አላቸው፡፡ 2|8|ከሰዎችም «በአላህና በመጨረሻው ቀን አምነናል» የሚሉ አልሉ፤ እነርሱም አማኞች አይደሉም፡፡ 2|9|አላህንና እነዚያን ያመኑትን (ሰዎች) ያታልላሉ፤ የማያውቁ ሲኾኑ ነፍሶቻቸውን እንጅ ሌላን አያታልሉም፡፡ 2|10|በልቦቻቸው ውስጥ (የንፍቅና) በሽታ አለባቸው፡፡ አላህም በሽታን ጨመረባቸው፡፡ ለነርሱም ይዋሹ በነበሩት ምክንያት አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 2|11|ለነርሱም «በምድር ላይ አታበላሹ» በተባሉ ጊዜ «እኛ አሳማሪዎች ብቻ ነን» ይላሉ፡፡ 2|12|ንቁ እነርሱ አጥፊዎቹ እነሱው ናቸው፤ ግን አያውቁም፡፡ 2|13|ለነሱም «ሰዎቹ እንዳመኑ እመኑ» በተባሉ ጊዜ «ቂሎቹ እንዳመኑ እናምናለን?» ይላሉ፡፡ አዋጅ ንቁ እነርሱ ቂሎቹ እነርሱው ናቸው፤ ግን አያውቁም፡፡ 2|14|እነዚያንም ያመኑትን በተገናኙ ጊዜ «አምነናል» ይላሉ፡፡ ወደ ሰይጣኖቻቸውም ባገለሉ ጊዜ «እኛ ከናንተ ጋር ነን፤ እኛ (በነሱ) ተሳላቂዎች ብቻ ነን» ይላሉ፡፡ 2|15|አላህ በነሱ ይሳለቅባቸዋል፤ በጥመታቸውም ውስጥ የሚዋልሉ ሲኾኑ ያዘገያቸዋል፡፡ 2|16|እነዚህ እነዚያ ስህተትን በቅንነት የገዙ ናቸው፡፡ ንግዳቸውም አላተረፈችም፤ ቀጥተኞችም አልኾኑም፡፡ 2|17|(በንፍቅና) ምሳሌያቸው እንደዚያ እሳትን እንዳነደደ ሰው በዙሪያው ያለውን ሁሉ ባበራች ጊዜም አላህ ብርሃናቸውን እንደወሰደባቸው በጨለማዎችም ውስጥ የማያዩ ኾነው እንደተዋቸው (ሰዎች) ብጤ ነው፡፡ 2|18|(እነሱ) ደንቆሮዎች፣ ዲዳዎች፣ ዕውሮች ናቸው፤ ስለዚህ እነርሱ አይመለሱም፡፡ 2|19|ወይም (ምሳሌያቸው) ከሰማይ እንደ ወረደ ዝናም (ባለቤቶች) ነው፤ በርሱ (በደመናው) ውስጥ ጨለማዎች፣ ነጎድጓድም፣ ብልጭታም ያሉበት ሲኾን ከመብረቆቹ ሞትን ለመፍራት ጣቶቻቸውን በጆሮቻቸው ውስጥ እንደሚያደርጉ ብጤ ነው፡፡ አላህም ከሓዲዎችን ከባቢ ነው፡፡ 2|20|ብልጭታው ዓይኖቻቸውን ሊነጥቅ ይቀርባል፡፡ ለነርሱ ባበራላቸው ቁጥር በርሱ ውስጥ ይኼዳሉ፡፡ በነሱም ላይ ባጨለመ ጊዜ ይቆማሉ፡፡ አላህም በሻ ኖሮ መስሚያቸውንና ማያዎቻቸውን በወሰደ ነበር፤ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና፡፡ 2|21|እናንተ ሰዎች ሆይ! የፈጠራችሁን እነዚያንም ከናንተ በፊት የነበሩትን (የፈጠረውን) ጌታችሁን ተገዙ፤ (ቅጣትን) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና፡፡ 2|22|(እርሱ) ያ ለናንተ ምድርን ምንጣፍ ሰማይንም ጣራ ያደረገ ነው፤ ከሰማይም (ከደመና) ውሃን ያወረደ በርሱም ከፍሬዎች ለናንተ ሲሳይን ያወጣ ነው፡፡ እናንተም (ፈጣሪነቱን) የምታውቁ ስትኾኑ ለአላህ ባላንጣዎችን አታድርጉ፡፡ 2|23|በባሪያችንም ላይ ካወረድነው በመጠራጠር ውስጥ ብትኾኑ ከብጤው አንዲትን ምዕራፍ አምጡ፡፡ እውነተኞችም እንደኾናችሁ ከአላህ ሌላ መስካሪዎቻችሁን ጥሩ፡፡ 2|24|(ይህንን) ባትሠሩ ፈጽሞም አትሠሩትምና ያችን መቀጣጠያዋ ሰዎችና ድንጋዮች የኾነችውን እሳት ተጠበቁ፤ ለከሓዲዎች ተደግሳለች፡፡ 2|25|እነዚያን ያመኑትንና መልካሞችንም የሠሩትን ለነርሱ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶች ያሏቸው መኾኑን አብስራቸው፡፡ ከርሷ ከፍሬ (ዓይነት) ሲሳይን በተመገቡ ቁጥር (ፍሬዎችዋ ስለሚመሳሰሉ) «ይህ ያ ከአሁን በፊት የተገመብነው ነው» ይላሉ፡፡ እርሱንም ተመሳሳይ ኾኖ ተሰጡት፡፡ ለነሱም በውስጧ ንጹህ የተደረጉ ሚስቶች አሏቸው፡፡ እነሱም በውስጧ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 2|26|አላህ ማንኛውንም ነገር ትንኝንም ኾነ (በትንሽነት ወይም በትልቅነት) ከበላይዋ የኾነንም ምሳሌ ለማድረግ አያፍርም፡፡ እነዚያ ያመኑትማ፤ እርሱ (ምሳሌው) ከጌታቸው (የተገኘ) እውነት መኾኑን ያውቃሉ፡፡ እነዚያም የካዱትማ «አላህ በዚህ ምንን ምሳሌ ሻ» ይላሉ፡፡ በርሱ (በምሳሌው) ብዙዎችን ያሳስታል በርሱም ብዙዎችን ያቀናል፡፡ በርሱም አመፀኞችን እንጅ ሌላን አያሳስትም፡፡ 2|27|እነዚያ የአላህን ቃል ኪዳን ከአጠበቀባቸው በኋላ የሚያፈርሱ እንዲቀጠልም በርሱ ያዘዘውን ነገር የሚቆርጡ በምድርም ላይ የሚያበላሹ እነዚያ እነርሱ ከሳሪዎቹ ናቸው፡፡ 2|28|ሙታን የነበራችሁ ስትኾኑ ሕያው ያደረጋችሁ ከዚያም የሚገድላችሁ ከዚያም ሕያው የሚያደርጋችሁ ሲኾን ከዚያም ወደርሱ የምትመለሱ ስትኾኑ በአላህ እንዴት ትክዳለችሁ! 2|29|እርሱ ያ በምድር ያለውን ሁሉ ለእናንተ የፈጠረ ነው፡፡ ከዚያም ወደ ሰማይ አሰበ፤ ሰባት ሰማያትም አደረጋቸው፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|30|(ሙሐመድ ሆይ) ጌታህ ለመላእክት፡- «እኔ በምድር ላይ ምትክን አድራጊ ነኝ፤» ባለ ጊዜ (የኾነውን አስታውስ፤ እነርሱም) «እኛ ከማመስገን ጋር የምናጠራህ ላንተም የምንቀድስ ስንኾን በርሷ ውስጥ የሚያጠፋንና ደሞችንም የሚያፈስን ታደርጋለህን?» አሉ፡፡ (አላህ) «እኔ የማታውቁትን ነገር አውቃለሁ» አላቸው፡፡ 2|31|አደምንም ስሞችን ሁሏንም አስተማረው፡፡ ከዚያም በመላእክት ላይ (ተጠሪዎቹን) አቀረባቸው፡፡ «እውነተኞችም እንደኾናችሁ የነዚህን (ተጠሪዎች) ስሞች ንገሩኝ» አላቸው፡፡ 2|32|«ጥራት ይገባህ፤ ከአስተማርከን ነገር በስተቀር ለኛ ዕውቀት የለንም፡፡ አንተ ዐዋቂው ጥበበኛው አንተ ብቻ ነህና» (አሉ)፡፡ 2|33|፡-«አደም ሆይ ስሞቻቸውን ንገራቸው» አለው፡፡ ስሞቻቸውን በነገራቸውም ጊዜ «እኔ የሰማያትንና የምድርን ሩቅ ምስጢር ዐውቃለሁ፤ የምትገልጹትንና ያንንም ትደብቁት የነበራችሁትን ዐውቃለሁ አላልኳችሁምን?» አላቸው፡፡ 2|34|ለመላእክትም «ለአደም ስገዱ» ባልን ጊዜ (አስታውስ) ፡፡ ሁሉም ወዲያውኑ ሰገዱ፤ ኢብሊስ (ዲያብሎስ) ብቻ ሲቀር እምቢ አለ፤ ኮራም ከከሓዲዎቹም ኾነ፡፡ 2|35|«አደም ሆይ! አንተ ከነሚስትህ በገነት ተቀመጥ፤ ከርሷም በፈለጋችሁት ስፍራ በሰፊው ተመገቡ፤ ግን ይህችን ዛፍ አትቅረቡ፤ ከበደለኞች ትኾናላችሁና» አልንም፡፡ 2|36|ከርሷም ሰይጣን አዳለጣቸው በውስጡም ከነበሩበት (ድሎት) አወጣቸው፡፡ «ከፊላችሁም ለከፊሉ ጠላት ሲኾን ውረዱ፤ ለናንተም በምድር ላይ እስከ ጊዜ (ሞታችሁ) ድረስ መርጊያና መጣቀሚያ አላችሁ» አልናቸው፡፡ 2|37|አደምም ከጌታው ቃላትን ተቀበለ፡፡ በርሱ ላይም (ጌታው ጸጸትን በመቀበል) ተመለሰለት፤ እነሆ እርሱ ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ነውና፡፡ 2|38|«ሁላችሁም ኾናችሁ ከርሷ ውረዱ፡፡ ከኔም የኾነ መመሪያ ቢመጣላችሁ ወዲያውኑ መመሪያዬን የተከተለ ሰው በነሱ ላይ ፍርሃት የለባቸውም፤ እነሱም አያዝኑም» አልናቸው፡፡ 2|39|እነዚያም (በመልክተኞቻችን) የካዱ በአንቀጾቻችንም ያስተባበሉ እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነርሱ በውስጧ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 2|40|የእስራኤል ልጆች ሆይ! ያችን በናንተ ላይ የለገስኳትን ጸጋዬን አስታውሱ፡፡ በቃል ኪዳኔም ሙሉ፤ በቃል ኪዳናችሁ እሞላለሁና፤ እኔንም ብቻ ፍሩ፡፡ 2|41|ከናንተ ጋር ያለውን (መጽሐፍ) የሚያረጋግጥ ሆኖ ባወረድኩትም (ቁርኣን) እመኑ፡፡ በርሱም የመጀመሪያ ከሓዲ አትሁኑ፡፡ በአንቀጾቼም ጥቂትን ዋጋ አትለውጡ፡፡ እኔንም ብቻ ተጠንቀቁ፡ 2|42|እውነቱንም በውሸት አትቀላቅሉ፡፡ እናንተም የምታውቁ ስትሆኑ እውነትን አትደብቁ፡፡ 2|43|ሶላትንም ደንቡን ጠብቃችሁ ስገዱ፡፡ ዘካንም (ግዴታ ምጽዋትን) ስጡ፡፡ (ለጌታችሁ) ከአጎንባሾች ጋርም አጎንብሱ፡፡ 2|44|እናንተ መጽሐፉን የምታነቡ ሆናችሁ ሰዎችን በበጎ ሥራ ታዛላችሁን? ነፍሶቻችሁንም ትረሳላችሁን? (የሥራችሁን መጥፎነት) አታውቁምን? 2|45|በመታገስና በሶላትም ተረዱ፡፡ እርሷም (ሶላት) በፈሪዎች ላይ እንጅ በሌላው ላይ በእርግጥ ከባድ ናት፡፡ 2|46|እነዚያ እነርሱ ጌታቸውን የሚገናኙ እነሱም ወደእርሱ ተመላሾች መኾናቸውን የሚያረጋግጡ በኾኑት (ላይ እንጅ ከባድ ናት)፡፡ 2|47|የእስራኤል ልጆች ሆይ! ያችን በናንተ ላይ የለገስኳትን ጸጋዬንና እኔም በዓለማት ላይ ያበለጥኳችሁ (አባቶቻችሁን በጊዜያቸው ከነበሩት ዓለማት ያበለጥኩዋቸው) መኾኔን አስታውሱ፡፡ 2|48|(ማንኛዋ) ነፍስም ከ(ሌላዋ) ነፍስ ምንንም የማትመነዳበትን፣ ከርሷም ምልጃን የማይቀበሉባትን፣ ከርሷም ቤዛ የማይያዝበትን፣ እነርሱም የማይረዱበትን ቀን ተጠንቀቁ፡፡ 2|49|ከፈርዖንም ቤተሰቦች (ከጎሶቹና ከሰራዊቱ) ብርቱን ቅጣት የሚያቀምሱዋችሁ ወንዶች ልጆቻችሁን የሚያርዱ ሴቶቻችሁንም የሚተው ሲኾኑ ባዳንናችሁ ጊዜ (የኾነውን አስታውሱ)፡፡ በዚሃችሁም ከጌታችሁ ታላቅ ፈተና አለበት፡፡ 2|50|በናንተም ምክንያት ባሕሩን በከፈልን ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ ወዲያውም አዳንናችሁ፡፡ የፈርዖንንም ቤተሰቦች እናንተ የምትመለከቱ ኾናችሁ አሰጠምናቸው፡፡ 2|51|ሙሳንም አርባን ሌሊት በቀጠርነው ጊዜ (የኾነውን አስታውሱ)፡፡ ከዚያም ከርሱ (መኼድ) በኋላ እናንተ በዳዮች ስትኾኑ ወይፈንን (አምላክ አድርጋችሁ) ያዛችሁ፡፡ 2|52|ከዚያም ከዚህ በኋላ እናንተ ታመሰግኑ ዘንድ ከናንተ ምሕረት አደረግን፡፡ 2|53|ሙሳንም መጽሐፍንና (እውነትና ውሸትን) መለያንም ትመሩ ዘንድ በሰጠነው ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ 2|54|ሙሳም ለሕዝቦቹ፡- «ሕዝቦቼ ሆይ! እናንተ ወይፈንን (አምላክ አድርጋችሁ) በመያዛችሁ ነፍሶቻችሁን በደላችሁ፡፡ ወደ ፈጣሪያችሁም ተመለሱ፤ ነፍሶቻችሁንም ግደሉ፤ ይሃችሁ በፈጣሪያችሁ ዘንድ ለናንተ በላጭ ነው» ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ በእናንተም ላይ ጸጸትን በመቀበል ተመለሰላችሁ፡፡ እነሆ እርሱ ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ነውና፡፡ 2|55|«ሙሳ ሆይ! አላህን በግልጽ እስከምናይ ድረስ ላንተ በፍጹም አናምንልህም» በላችሁም ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ እናንተም እየተመለከታችሁ መብረቅ ያዘቻችሁ፡፡ 2|56|ከዚያም ታመሰግኑ ዘንድ ከሞታችሁ በኋላ አስነሳናችሁ፡፡ 2|57|በናንተም ላይ ደመናን አጠለልን፡፡ በናተም ላይ (እንደ ነጭ ማር ያለ) መንናን እና ድርጭትን አወረድን፡፡ ከሰጠናችሁም ጣፋጮች «ብሉ (አልን)፡፡» አልበደሉንምም ግን ነፍሶቻቸውን ይበድሉ ነበር፡፡ 2|58|«ይህችንም ከተማ ግቡ፡፡ ከርሷም በሻችሁት ስፍራ ሰፊን (ምግብ) ተመገቡ፡፡ በሩንም ያጎነበሳችሁ ኾናችሁ ግቡ፤ (ጥያቄያችን የኃጢአታችን መርገፍ ነው) በሉም፡፡ ኃጢአቶቻችሁን ለናንተ እንምራለንና፡፡ በጎ ሠሪዎችንም (ምንዳን) እንጨምርላቸዋለን» ባልን ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ 2|59|እነዚያም የበደሉት ሰዎች ከዚያ ለነሱ ከተባሉት ሌላ ቃልን ለወጡ፡፡ በነዚያም በበደሉት ላይ ያመጹ በመሆናቸው ምክንያት መቅሠፍትን አወረድንባቸው፡፡ 2|60|ሙሳም ለሕዝቦቹ መጠጥን በፈለገ ጊዜ (የኾነውን አስታውሱ)፡፡ «ድንጋዩንም በበትርህ ምታ» አልነው፡፡ (መታውም) ከርሱም ዐሥራሁለት ምንጮች ፈለቁ፡፡ ሰዎቹ ሁሉ መጠጫቸውን በእርግጥ ዐወቁ፡፡ «ከአላህ ሲሳይ ብሉ፤ ጠጡም፤ አመጠኞችም ኾናችሁ በምድር ላይ አታበላሹ» (አልናቸው)፡፡ 2|61|ሙሳ ሆይ፡- «በአንድ (ዓይነት) ምግብ ላይ በፍጹም አንታገሥም፤ ስለዚህ ጌታህን ከዚያ ምድር ከምታበቅለው ሁሉ ከቅጠላቅጠል ከዱባዋም ከስንዴዋም ከምስርዋም ከሽንኩርቷም ለኛ ያወጣ ዘንድ ለኛ ለምንልን» ባላችሁም ጊዜ (የኾነውን አስታውሱ፡፡ ሙሳም፡- «ያንን እርሱ ዝቅተኛ የኾነውን በዚያ እርሱ በላጭ በኾነው ነገር ለውጥን ትፈልጋላችሁን? ወደ ከተማ ውረዱ፤ ለናንተም የጠየቃችሁት ነገር አላችሁ» አላቸው፡፡ በነርሱም ላይ ውርደትና ድኽነት ተመታባቸው፡፡ ከአላህም በኾነ ቁጣ ተመለሱ፡፡ ይህ እነርሱ በአላህ ታምራቶች ይክዱና ነቢያትንም ያለ ሕግ ይገድሉ ስለነበሩ ነው፡፡ ይህ በማመጻቸውና ወሰን የሚያልፉ በመኾናቸው ነው፡፡ 2|62|እነዚያ ያመኑ እነዚያም ይሁዳውያን የኾኑ፣ ክርስቲያኖችም፣ ሳቢያኖችም (ከእነርሱ) በአላህና በመጨረሻው ቀን ያመነ መልካምንም ሥራ የሠራ ለነርሱ በጌታቸው ዘንድ ምንዳቸው አላቸው፡፡ በነርሱም ላይ ፍርሃት የለባቸውም፤ እነሱም አያዝኑም፡፡ 2|63|ከበላያችሁም የጡርን ተራራ ያነሳን ኾነን የጠበቀ ቃልኪዳናችሁን በያዝን ጊዜ (የኾነውን አስታውሱ)፡፡ «ያንን የሰጠናችሁን በኀይል ያዙ፤ በውስጡ ያለውንም ነገር (ከእሳት) ትጠበቁ ዘንድ አስታውሱ» (አልን)፡፡ 2|64|ከዚያም ከዚህ በኋላ (ኪዳኑን) ተዋችሁ፡፡ በናንተም ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ ኖሮ በእርግጥ ከጠፊዎቹ በኾናችሁ ነበር፡፡ 2|65|እነዚያንም ከእናንተ ውስጥ በቅዳሜ ቀን (ዐሣን በማጥመድ) ወሰን ያለፉትንና ለነሱ «ወራዳዎች ስትኾኑ ዝንጀሮዎች ኹኑ» ያልናቸውን በእርግጥ ዐወቃችሁ፡፡ 2|66|(ቅጣቲቱንም) ለነዚያ በስተፊትዋ ለነበሩትና ለነዚያም ከበኋላዋ ላሉት (ሕዝቦች) መቀጣጫ ለፈራህያንም መገሰጫ አደረግናት፡፡ 2|67|ሙሳም ለሕዝቦቹ፡- «አላህ ላምን እንድታርዱ ያዛችኋል» ባለ ጊዜ (አስታወሱ)፡፡«መሳለቂያ አድርገህ ትይዘናለህን?» አሉት፡፡ «ከተሳላቂዎች ከመኾን በአላህ እጠበቃለሁ» አላቸው፡፡ 2|68|«ለኛ ጌታህን ጠይቅልን፤ እርሷ ምን እንደኾነች (ዕድሜዋን) ያብራራልን» አሉ፡፡ «እርሱ እርሷ ያላረጀች ጥጃም ያልኾነች በዚህ መካከል ልከኛ የኾነች ጊደር ናት ይላችኋል፤ የታዘዛችሁትንም ሥሩ» አላቸው፡፡ 2|69|«ለኛ ጌታህን ጠይቅልን፤ መልኳ ምን እንደኾነ ለኛ ይግለጽልን» አሉ፡፡ «እርሱ እርሷ መልኳ ደማቅ ተመልካቾችን የምታስደስት ዳለቻ ላም ናት ይላችኋል» አላቸው፡፡ 2|70|«ለኛ ጌታህን ጠይቅልን፤ እርሷ ምን እንደኾነች ይግለጽልን፤ ከብቶች በኛ ላይ ተመሳሰሉብን፡፡ እኛም አላህ የሻ እንደኾነ በእርግጥ ተመሪዎች ነን» አሉ፡፡ 2|71|«እርሱ እርሷ ያልተገራች ምድርን (በማረስ) የማታስነሳ እርሻንም የማታጠጣ (ከነውር) የተጠበቀች ልዩ ምልክት የሌለባት ናት ይላችኋል» አላቸው፡፡ «አሁን በትክክል መጣህ» አሉ፤ ሊሠሩ ያልተቃረቡም ሲኾኑ አረዷት ፡፡ 2|72|ነፍስነም በገደላችሁና በርሷም (ገዳይ) በተከራከራችሁ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ አላህም ትደብቁት የነበራችሁትን ሁሉ ገላጭ ነው፡፡ 2|73|«(በድኑን) በከፊሏም ምቱት» አልን፤ እንደዚሁ አላህ ሙታንን ያስነሳል፤ ታውቁም ዘንድ ታምራቶችን ያሳያችኋል፡፡ 2|74|ከዚያም ከዚህ በኋላ ልቦቻችሁ ደረቁ፤ እርሷም እንደ ድንጋዮች ወይም በድርቅና ይበልጥ የበረታች ናት፡፡ ከድንጋዮችም ከርሱ ጂረቶች የሚፈሱለት አልለ፡፡ ከነርሱም በእርግጥ የሚሰነጠቅና ከርሱ ውሃ (ምንጭ) የሚወጣው አልለ፡፡ ከነርሱም አላህን ከመፍራት የተነሳ ወደ ታች የሚወርድ አልለ፡፡ አላህም ከምትሠሩት ነገር ዘንጊ አይደለም፡፡ 2|75|(አይሁዶች) ከነሱ የኾኑ ጭፍሮች የአላህን ቃል የሚሰሙና ከዚያም ከተረዱት በኋላ እነርሱ እያወቁ የሚለውጡት ሲኾኑ ለናንተ ማመናቸውን ትከጅላላችሁን? 2|76|እነዚያንም ያመኑትን ባገኙ ጊዜ «አምነናል» ይላሉ፡፡ ከፊላቸውም ወደ ከፊሉ ባገለለ «ጊዜ አላህ በናንተ ላይ በገለጸላቸሁ ነገር እጌታችሁ ዘንድ በርሱ እንዲከራከሩዋችሁ ትነግሩዋቸዋላችሁን? አታውቁምን?» ይላሉ፡፡ 2|77|አላህ የሚደብቁትንና የሚገልጹትን የሚያውቅ መኾኑን አያውቁምን? 2|78|ከነሱም መጽሐፉን የማያውቁ መሃይማናን አሉ፡፡ ግን ከንቱ ምኞቶችን (ይመኛሉ)፤ እነርሱም የሚጠራጠሩ እንጂ ሌላ አይደሉም፡፡ 2|79|ለነዚያም መጽሐፉን በእጆቻቸው ለሚጽፉና ከዚያም በርሱ ጥቂትን ዋጋ ሊገዙበት «ይህ ከአላህ ዘንድ ነው» ለሚሉ ወዮላቸው፡፡ ለነርሱም ከዚያ እጆቻቸው ከጻፉት ወዮላቸው፡፡ ለነሱም ከዚያ ከሚያፈሩት (ኃጢኣት) ወዮላቸው፡፡ 2|80|«እሳትም የተቆጠሩን ቀኖች እንጂ አትነካንም» አሉ፡፡ «አላህ ዘንድ ቃል ኪዳን ይዛችኋልን? (ይህ ከኾነ) አላህም ኪዳኑን አያፈርስም፤ በእውነቱ በአላህ ላይ የማታውቁትን ትናገራላችሁ» በላቸው፡፡ 2|81|አይደለም (ትነካችኋለች)፤ መጥፎን (ክሕደትን) የሠራ በርሱም ኃጠኣቱ የከበበችው ሰው እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነርሱ በውስጧ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 2|82|እነዚያም ያመኑት በጎ ሥራዎችንም የሠሩት እነዚያ የገነት ጓዶች ናቸው፡፡ እነርሱ በውስጧ ዘላለም ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 2|83|የእስራኤል ልጆችንም ጥብቅ ኪዳን አላህን እንጂ ሌላን አታምልኩ፤ በወላጆችም በጎን ሥራ (አድርጉ)፤ በዝምድና ባለቤቶችም፣ በየቲሞችም (አባት የሌላቸው ልጆች) በምስኪኖችም (በጎ ዋሉ)፤ ለሰዎችም መልካምን ተናገሩ፤ ሶላትንም ደንቡን ጠብቃችሁ ስገዱ፤ ዘካንም ስጡ በማለት በያዝንባቸው ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ ከዚያም ከናንተ ጥቂቶች ሲቀሩ ሸሻችሁ እናንተም (ኪዳንን) የምትተዉ ናችሁ፡፡ 2|84|ደሞቻችሁን አታፍስሱ ነፍሶቻችሁንም (ከፊላችሁን) ከአገሮቻችሁ አታውጡ የምንል ስንኾን የጠበቀ ቃል ኪዳናችሁን በያዝንባችሁ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ ከዚያም (በኪዳኑ) አረጋገጣችሁ፤ እናንተም ትመሰክራላችሁ፡፡ 2|85|ከዚያም እናንተ እነዚያ ነፍሶቻችሁን የምትገድሉ ከናንተም የኾኑ ጭፍሮችን በኃጢአትና በመበደል በነርሱ ላይ የምትረዳዱ ስትኾኑ ከአገሮቻቸው የምታወጡ ምርኮኞችም ኾነው ቢመጡዋችሁ የምትበዡ ናችሁ፡፡ እርሱ (ነገሩ) እነርሱን ማውጣት በእናንተ ላይ የተከለከለ ነው፡፡ በመጽሐፉ ከፊል ታምናላችሁን? በከፊሉም ትክዳላችሁን? ከእናንተም ይህንን የሚሠራ ሰው ቅጣት በቅርቢቱ ሕይወት ውርደት እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ በትንሣኤ ቀንም ወደ ብርቱ ቅጣት ይመለሳሉ፡፡ አላህም ከምትሠሩት ሥራ ሁሉ ዘንጊ አይደለም፡፡ 2|86|እነዚህ እነዚያ ቅርቢቱን ሕይወት በመጨረሻይቱ አገር የገዙ ናቸው፡፡ ከነሱም ቅጣቱ አይቀልላቸውም፤ እነሱም አይርረዱም፡፡ 2|87|ሙሳንም መጽሐፍን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ ከበኋላውም መልክትኞችን አስከታተልን፡፡ የመርየምን ልጅ ዒሳንም ግልጽ ታምራቶችን ሰጠነው፡፡ በቅዱሱ መንፈስም አበረታነው፡፡ ነፍሶቻችሁ በማትወደው ነገር መልክተኛ በመጣላችሁ ቁጥር (ከመከተል) ትኮራላችሁን? ከፊሉን አስተባበላችሁ፤ ከፊሉንም ትገድላላችሁ፡፡ 2|88|«ልቦቻችንም ሽፍኖች ናቸው» አሉ፤ አይደለም አላህ በክሕደታቸው ምክንያት ረገማቸው ጥቂትንም ብቻ ያምናሉ፡፡ 2|89|ከነሱም ጋር ያለውን (መጽሐፍ) አረጋጋጭ የኾነ መጽሐፍ ከአላህ ዘንድ በመጣላቸው ጊዜ (ከመምጣቱ) በፊት በነዚያ በካዱት ላይ ይረዱበት የነበሩ ሲኾኑ ያወቁት ነገር በመጣላቸው ጊዜ በርሱ ካዱ፡፡ የአላህም ርግማን በከሓዲዎች ላይ ይኹን፡፡ 2|90|ነፍሶቻቸውን በርሱ የሸጡበት ነገር ከፋ! (እርሱም) አላህ ከባሮቹ በሚሻው ሰው ላይ ከችሮታው (ራእይን) ማውረዱን በመመቅኘት አላህ ባወረደው ነገር መካዳቸው ነው፡፡ በቁጣ ላይም ቁጣ (የተረጋገጠባቸው ሲኾኑ) ተመለሱ፡፡ ለከሓዲዎችም አዋራጅ ቅጣት አላቸው፡፡ 2|91|አላህም ባወረደው (ሁሉ) ለእነርሱ «እመኑ» በተባሉ ጊዜ «በኛ ላይ በተወረደው (መጽሐፍ ብቻ) እናምናለን» ይላሉ፡፡ ከርሱ ኋላ ባለው (ቁርአን) እርሱ ከነሱ ጋር ላለው (መጽሐፍ) አረጋጋጭ እውተኛ ሲኾን ይክዳሉ፡፡ «አማኞች ከኾናችሁ ከአሁን በፊት የአላህን ነቢያት ለምን ገደላችሁ?» በላቸው፡፡ 2|92|ሙሳም በታምራቶች በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ ከዚያም ከበኋላው እናንተ በዳዮች ስትኾኑ ወይፈንን (አምላክ አድርጋችሁ) ያዛችሁ፡፡ 2|93|የጡርንም ጋራ ከበላያችሁ ያነሳን ስንኾን (በኦሪት ሕግ እንድትሠሩ) ኪዳናችሁን በያዝን ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ «የሰጠናችሁን በኀይል ያዙ፤ ስሙም፤» (አልን)፡፡«ሰማን አመጽንም» አሉ፡፡ የወይፈኑንም ውዴታ በክሕደታቸው ምክንያት በልቦቻቸው ውስጥ ተጠጡ፡፡ «አማኞች እንደኾናችሁ እምነታችሁ በርሱ የሚያዛችሁ ነገር ከፋ!» በላቸው፡፡ 2|94|«የመጨረሻይቱ አገር (ገነት) አላህ ዘንድ ከሰው ሁሉ ሌላ የተለየች ስትኾን ለእናንተ ብቻ እንደኾነች እውነተኞች ከኾናችሁ ሞትን ተመኙ» በላቸው፡፡ 2|95|እጆቻቸውም ባሳለፉት (በሠሩት) ምክንያት ምን ጊዜም ፈጽሞ አይመኙትም፤ አላህም በዳዮችን ዐዋቂ ነው፡፡ 2|96|ከሰዎችም ሁሉ ከእነዚያም (ጣዖትን) ከአጋሩት ይበልጥ በሕይወት ላይ የሚጓጉ ኾነው በእርግጥ ታገኛቸዋለህ፡፡ አንዳቸው ሺሕ ዓመት ዕድሜ ቢሰጥ ይወዳል፡፡ እርሱም ዕድሜ መሰጠቱ ከቅጣት የሚያርቀው አይደለም፡፡ አላህም የሚሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 2|97|ለጂብሪል (ለገብርኤል) ጠላት የኾነ ሰው (በቁጭት ይሙት) በላቸው፡፡ እርሱ (ቁርኣኑን) ከበፊቱ ለነበሩት (መጻሕፍት) አረጋጋጭ ለምእመናን መሪና ብስራት ሲኾን በአላህ ፈቃድ በልብህ ላይ አውርዶታልና፡፡ 2|98|ለአላህና ለመላእክቱ ለመልክተኞቹም ለጂብሪልም ለሚካልም (ሚካኤል) ጠላት የኾነ ሰው አላህ ለ(እነዚህ) ከሓዲዎች ጠላት ነው፡፡ 2|99|ወዳንተም ግልጽ የኾኑትን አንቀጾች በእርግጥ አውርደናል፡፡ በርሷም አመጸኞች እንጂ ሌላው አይክድም፤ 2|100|ቃል ኪዳንንም ቃል በገቡ ቁጥር ከእነርሱ ከፊሉ ይጥለዋልን? (ያፈርሰዋልን?)፤ ይልቁንም አብዛኞቻቸው አያምኑም፡፡ 2|101|እነርሱ ጋርም ላለው (መጽሐፍ) አረጋጋጭ የኾነ መልክተኛ ከአላህ ዘንድ በመጣላቸው ጊዜ ከነዚያ መጽሐፍን ከተሰጡት ከፊሉ እነርሱ እንደማያውቁ ኾነው የአላህን መጽሐፍ ከጀርባዎቻቸው ኋላ ጣሉ፡፡ 2|102|ሰይጣናትም በሱለይማን (ሰሎሞን) ዘመነ መንግስት የሚያነቡትን (ድግምት) ተከተሉ፡፡ ሱለይማንም አልካደም፤ (ድግምተኛ አልነበረም)፤ ግን ሰይጣናት ሰዎችን ድግምትን የሚያስተምሩ ሲኾኑ ካዱ፡፡ ያንንም በባቢል በሁለቱ መላእክት በሃሩትና ማሩት ላይ የተወረደውን ነገር (ያስተምሩዋቸዋል)፡፡ «እኛ መፈተኛ ነንና አትካድ» እስከሚሉም ድረስ አንድንም አያስተምሩም፡፡ ከእነሱም በሰውየውና በሚስቱ መካከል በርሱ የሚለዩበትን ነገር ይማራሉ፡፡ እነርሱም በአላህ ፈቃድ ካልኾነ በርሱ አንድንም ጎጂዎች አይደሉም፡፡ የሚጎዳቸውንና የማይጠቅማቸውንም ይማራሉ፡፡ የገዛውም ሰው ለርሱ በመጨረሻይቱ አገር ምንም እድል የሌለው መኾኑን በእርግጥ ዐወቁ፡፡ ነፍሶቻቸውንም በርሱ የሸጡበት ዋጋ ከፋ! የሚያውቁ በኾኑ ኖሮ (ባልሠሩት ነበር)፡፡ 2|103|እነርሱም (አይሁዶች) ባመኑና በተጠነቀቁ ኖሮ (በተመነዱ ነበር)፡፡ የሚያውቁ ቢኾኑ ከአላህ ዘንድ የኾነው ምንዳ (ነፍሶቻቸውን ከሚሸጡበት) በላጭ ነው፡፤ 2|104|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! (ለነቢዩ) ራዒና አትበሉ፡፡ ተመለከትን በሉም፡፡ ስሙም፤ ለከሓዲዎችም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 2|105|እነዚያ ከመጽሐፉ ባለቤቶችና ከአጋሪዎቹም የካዱት በናንተ ላይ ከጌታችሁ የኾነ መልካም ነገር መወረዱን አይወዱም፡፡ አላህም በችሮታው (በነቢይነት) የሚሻውን ይመርጣል፡፡ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 2|106|ከአንቀጽ ብንለውጥ ወይም እርሷን ብናስረሳህ ከርሷ የሚበልጥን ወይም ብጤዋን እናመጣለን፤ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ከሃሊ (ቻይ) መኾኑን አታውቅምን? 2|107|አላህ የሰማያትና የምድር ንግሥና ለርሱ ብቻ መኾኑን አታውቅምን? ለእናንተም ከአላህ ሌላ ዘመድና ረዳት ምንም የላችሁም፡፡ 2|108|በእውነቱ ከአሁን በፊት ሙሳ እንደተጠየቀ ብጤ መልክተኛችሁን ልትጠይቁ ትፈልጋላችሁን? በእምነትም ክህደትን የሚለውጥ ሰው ትክክለኛውን መንገድ በእርግጥ ተሳሳተ፡፡ 2|109|ከመጽሐፉ ባለቤቶች ብዙዎች እውነቱ ከተገለጸላቸው በኋላ ከነፍሶቻቸው በኾነው ምቀኝነት ከእምነታችሁ በኋላ ከሓዲዎች አድርገው ሊመልሱዋችሁ ተመኙ፡፡ አላህም ትዕዛዙን እስከሚያመጣ ድረስ ይቅርታ አድርጉ፤ እለፏቸውም፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ከሃሊ ነውና፡፡ 2|110|ሶላትንም አስተካክላችሁ ስገዱ፡፡ ዘካንም ስጡ፡፡ ለነፍሶቻችሁም ከበጎ ሥራ የምታስቀድሙትን አላህ ዘንድ ታገኙታላችሁ፡፡ አላህ የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነውና፡፡ 2|111|«ገነትንም አይሁድን ወይም ክርስቲያኖችን የኾነ ሰው እንጂ ሌላ አይገባትም» አሉ፡፡ ይህቺ (ከንቱ) ምኞታቸው ናት፡፡ «እውነተኞች እንደኾናችሁ አስረጃችሁን አምጡ» በላቸው፡፡ 2|112|አይደለም (ሌላውም ይገባታል) እርሱ በጎ ሠሪ ኾኖ ፊቱን ለአላህ የሰጠ ሰው ለርሱ በጌታው ዘንድ ምንዳው አለው፡፡ በነሱም ላይ ፍርሃት የለባቸውም፤ እነሱም አያዝኑም፡፡ 2|113|እነርሱ መጽሐፉን የሚያነቡ ሲኾኑ አይሁዶች፡- ክርስቲያኖች በምንም ላይ አይደሉም አሉ፡፡ ክርስቲያኖችም፡- አይሁዶች በምንም ላይ አይደሉም አሉ፡፡ እንደዚሁ እነዚያ የማያውቁት (አጋሪዎች) የንግግራቸውን ብጤ አሉ፡፡ አላህም በዚያ በርሱ ይለያዩበት በነበሩት ነገር በትንሣኤ ቀን በመካከላቸው ይፈርዳል፡፡ 2|114|የአላህንም መስጊዶች በውስጣቸው ስሙ እንዳይወሳ ከከለከለና እርሷንም በማበላሸት ከሮጠ ሰው ይበልጥ በዳይ ማነው? እነዚያ ፈሪዎች ኾነው እንጂ ለእነርሱ በቅርቢቱ ዓለም ውርደት አላቸው፡፡ ለነርሱም በመጨረሻይቱ አገር ታላቅ ቅጣት አላቸው፡፡ 2|115|ምሥራቁም ምዕራቡም የአላህ ነው (ፊቶቻችሁን) ወደ የትም ብታዞሩ የአላህ ፊት እዚያ ነው፡፡ አላህ ችሮታው ሰፊ ዐዋቂ ነውና፡፡ 2|116|አላህም ልጅ አለው አሉ፡፡ (ከሚሉት) ጥራት ተገባው፡፡ አይደለም በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የርሱ ነው፡፡ ሁሉም ለርሱ ታዛዦች ናቸው፡፡ 2|117|ሰማያትንና ምድርን ያለብጤ ፈጣሪ ነው፤ ነገርንም (ማስገኘት) በሻ ጊዜ ለርሱ የሚለው፡- «ኹን ነው፤» ወዲያውም ይኾናል፡፡ 2|118|እነዚያም የማያውቁት (አንተ መልክተኛ ስለመኾንህ) አላህ አያናግረንም ኖሮአልን? ወይም (ለእውነተኛነትህ) ታምር አትመጣልንም ኖሮአልን? አሉ፡፡ እንደዚሁ እነዚያ ከነሱ በፊት የነበሩት እንደ ንግግራቸው ብጤ ብለዋል፡፡ ልቦቻቸው (በክሕደት) ተመሳሰሉ፡፡ ለሚያረጋግጡ ሕዝቦች አንቀጾችን በእርግጥ አብራርተናል፡፡ 2|119|እኛ አብሳሪና አስፈራሪ ኾነህ በውነት ላክንህ፡፡ ከእሳትም ጓዶች አትጠየቅም፡፡ 2|120|አይሁዶችና ክርስቲያኖችም ሃይማኖታቸውን እስከምትከተል ድረስ ካንተ ፈጽሞ አይወዱም፡፡ «የአላህ መምራት (ትክክለኛው) መምራት እርሱ ብቻ ነው» በላቸው፡፡ ከዚያም እውቀቱ ከመጣልህ በኋላ ዝንባሌያቸውን ብትከተል ለአንተ ከአላህ (የሚከለክልልህ) ዘመድና ረዳት ምንም የለህም፡፡ 2|121|እነዚያ መጽሐፉን የሰጠናቸው ተገቢ ንባቡን ያነቡታል፡፡ እነዚያ በርሱ ያምናሉ፤ በርሱም የሚክዱ እነዚያ እነርሱ ከሳሪዎቹ ናቸው፡፡ 2|122|የእስራኤል ልጆች ሆይ! ያችን በናንተ ላይ የለገስኳትን ጸጋዬንና እኔም በዓለማት ላይ ያበለጥኳችሁ መኾኔን አስታውሱ፡፡ 2|123|(አማኝ) ነፍስም ከ(ከሓዲ) ነፍስ ምንንም የማትጠቅምበትን፣ ከርሷም ቤዛ የማይወሰድበትን፣ ምልጃም ለርሷ የማትጠቅምበትን፣ እነርሱም የማይረዱበትን ቀን ተጠንቀቁ፡፡ 2|124|ኢብራሂምንም ጌታው በቃላት (በሕግጋት) በፈተነውና በፈጸማቸው ጊዜ (አስታውስ)፤ «እኔ ለሰዎች መሪ አድራጊህ ነኝ» አለው፡፡ «ከዘሮቼም (አድርግ)» አለ፡፡ ቃል ኪዳኔ በዳዮቹን አያገኝም አለው፡፡ 2|125|ቤቱንም ለሰዎች መመለሻና ጸጥተኛ ባደረግን ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ከኢብራሂምም መቆሚያ መስገጃን አድርጉ፡፡ ወደ ኢብራሂምና ወደ ኢስማዒልም ቤቴን ለዘዋሪዎቹና ለተቀማጮቹም ለአጎንባሾች ሰጋጆቹም አጥሩ ስንል ቃል ኪዳን ያዝን፡፡ 2|126|ኢብራሂም ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ጌታዬ ሆይ! ይህንን ጸጥተኛ አገር አድርግ፡፡ ቤተሰቦቹንም ከነሱ በአላህና በመጨረሻው ቀን ያመነውን ሰው ከፍሬዎች ስጠው፡፡ (አላህም) የካደውንም ሰው፤ (እሰጠዋለሁ)፡፡ ጥቂትም እጠቅመዋለሁ፤ ከዚያም ወደ እሳት ቅጣት አስጠጋዋለሁ፤ ምን ትከፋም መመለሻ! (አለ)፡፡ 2|127|ኢብራሂምና ኢስማኢልም «ጌታችን ሆይ! ከእኛ ተቀበል፡፡ አንተ ሰሚውና ዐዋቂው አንተ ነህና» የሚሉ ሲኾኑ ከቤቱ መሠረቶቹን ከፍ ባደረጉ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 2|128|«ጌታችን ሆይ! ላነተ ታዛዦችም አድርገን፡፡ ከዘሮቻችንም ላንተ ታዛዦች ሕዝቦችን (አድርግ)፡፡ ሕግጋታችንንም አሳየን፤ (አሳውቀን)፡፡ በኛም ላይ ተመለስን፤ አንተ ጸጸትን ተቀባዩ ሩኅሩኅ አንተ ብቻ ነህና፡፡» 2|129|«ጌታችን ሆይ! በውስጣቸውም ከነሱው የኾነን መልክተኛ በነርሱ ላይ አንቀጾችህን የሚያነብላቸውን መጽሐፍንና ጥበብንም የሚያስተምራቸውን (ከክህደት) የሚያጠራቸውንም ላክ፤ አንተ አሸናፊው ጥበበኛው አንተ ብቻ ነህና» (የሚሉም ሲኾኑ)፡፡ 2|130|ከኢብራሂምም ሕግጋት ነፍሱን ያቄለ ሰው ካልኾነ በስተቀር የሚያፈገፍግ ማነው? (የለም)፤ በቅርቢቱም ዓለም በእርግጥ መረጥነው፡፡ በመጨረሻይቱም ዓለም እርሱ ከመልካሞቹ ነው፡፡ 2|131|ጌታው ለርሱ ታዘዝ ባለው ጊዜ (መረጠው)፡፡ ለዓለማት ጌታ ታዘዝኩ አለ፡፡ 2|132|በርሷም (በሕግጋቲቱ) ኢብራሂም ልጆቹን አዘዘ፡፡ ያዕቁብም (እንደዚሁ ልጆቹን አዘዘ)፡፡ «ልጆቼ ሆይ! አላህ ለናንተ ሃይማኖትን መረጠ፤ ስለዚህ እናንተ ሙስሊሞች ኾናችሁ እንጂ አትሙቱ» (አላቸው)፡፡ 2|133|ያዕቁብን ሞት በመጣበት ጊዜ ለልጆቹ ከኔ በኋላ ማንን ትገዛላችሁ ባለ ጊዜ ቀራቢዎች ነበራችሁን? (እነርሱም) አምላክህንና የአባቶችህን የኢብራሂምን የኢስማዒልንና የኢስሐቅንም አምላክ አንድ የኾነውን አምላክ እኛ ለርሱ ፍፁም ታዛዦች ኾነን እናመልካለን አሉ፡፡ 2|134|ይህች (የተወሳችው) በእርግጥ ያለፈች ሕዝብ ናት፡፡ ለርሷ የሠራችው (ምንዳ) አላት፡፡ ለናንተም የሠራችሁት (ምንዳ) አላችሁ፡፡ ይሠሩትም ከነበሩት አትጠየቁም፡፡ 2|135|«አይሁድን ወይም ክርስቲያኖችን ኹኑ፤ (ቅኑን መንገድ) ትመራላችሁና» አሉም፡፡ «አይደለም የኢብራሂምን ሃይማኖት ቀጥተኛ ሲኾን እንከተላለን፤ ከአጋሪዎችም አልነበረም» በላቸው፡፡ 2|136|«በአላህና ወደኛ በተወረደው (ቁርኣን) ወደ ኢብራሂምም ወደ ኢስማዒልና ወደ ኢስሐቅም ወደ ያዕቁብና ወደ ነገዶቹም በተወረደው በዚያም ሙሳና ዒሳ በተሰጡት በዚያም ነቢያት ሁሉ ከጌታቸው በተሰጡት ከነርሱ በአንድም መካከል የማንለይ ስንኾን አመንን፤ እኛም ለርሱ (ለአላህ) ታዛዦች ነን» በሉ፡፡ 2|137|በርሱ ባመናችሁበት ብጤ ቢያምኑ በእርግጥ ተመሩ፡፡ ቢዞሩም እነርሱ በጭቅጭቅ ውስጥ ብቻ ናቸው፡፡ እነርሱንም አላህ ይበቃሃል፤ እርሱም ሰሚው ዐዋቂው ነው፡፡ 2|138|የአላህን (የተፈጥሮ) መንክር (እምነት) ያዙ፡፡ በመንከርም ከአላህ ይበልጥ ያማረ ማነው? (ማንም የለም) እኛም ለርሱ ብቻ ተገዢዎች ነን (በሉ)፡፡ 2|139|እርሱ (አላህ) ጌታችንና ጌታችሁ ሲኾን ለኛም ሥራችን ያለን ስንኾን ለናንተም ሥራችሁ ያላችሁ ስትኾኑ እኛም ለርሱ ፍጹም ታዛዦች ስንኾን በአላህ (ሃይማኖት) ትከራከሩናላችሁን? በላቸው፡፡ 2|140|ወይም ኢብራሂም ኢስማዒልም ኢስሐቅም ያዕቁብም ነገዶቹም አይሁዶች ወይም ክርስቲያኖች ነበሩ ትላላችሁን? «እናንተ ታውቃላችሁን? ወይንስ አላህ?» በላቸው፡፡ እርሱም ዘንድ ከአላህ የኾነችን ምስክርነት ከደበቀ ሰው ይበልጥ በዳይ ማነው? አላህም ከምትሠሩት ሁሉ ዘንጊ አይደለም፡፡ 2|141|ይህቺ በእርግጥ ያለፈች ሕዝብ ናት፤ ለእርሷ የሠራችው አላት፤ ለናንተም የሠራችሁት አላችሁ፤ ይሠሩትም ከነበሩት አትጠየቁም፡፡ 2|142|ከሰዎቹ ቂሎቹ «ከዚያች በርሷ ላይ ከነበሩባት ቂብላቸው ምን አዞራቸው?» ይላሉ፤ «ምሥራቁም ምዕራቡም የአላህ ነው፤ የሻውን ሰው ወደ ቀጥተኛው መንገድ ይመራል» በላቸው፡፡ 2|143|እንደዚሁም (እንደመራናችሁ) በሰዎች ላይ መስካሪዎች ልትሆኑና መልክተኛውም በናንተ ላይ መስካሪ ይሆን ዘንድ ምርጥ ሕዝቦች አደረግናችሁ፡፡ ያችንም በርሷ ላይ የነበርክባትን አቅጣጫ መልክተኛውን የሚከተለውን ሰው ወደ ክህደት ከሚመለሰው ሰው ልናውቅ (ልንገልጽ) እንጅ ቂብላ አላደረግናትም፡፡ እርሷም በነዚያ አላህ በመራቸው ሰዎች ላይ በስተቀር በእርግጥ ከባድ ናት፡፡ አላህም እምነታችሁን (ስግደታችሁን) የሚያጠፋ አይደለም፤ አላህ ለሰዎች በጣም ርኅሩኅ አዛኝ ነውና፡፡ 2|144|የፊትህን ወደ ሰማይ መገላበጥ በእርግጥ እናያለን፡፡ ወደምትወዳትም ቂብላ እናዞርሃለን፡፡ ስለዚህ ፊትህን ወደ ተከበረው መስጊድ (ወደ ካዕባ) አግጣጫ አዙር፡፡ የትም ስፍራ ብትኾኑም (ስትሰግዱ) ፊቶቻችሁን ወደርሱ አግጣጫ አዙሩ፡፡ እነዚያም መጽሐፉን የተሰጡት እርሱ ከጌታቸው ሲኾን እውነት መሆኑን ያውቃሉ፡፡ አላህም ከምትሠሩት ሥራ ዘንጊ አይደለም፡፡ 2|145|እነዚያንም መጽሐፍን የተሰጡትን በአስረጅ ሁሉ ብትመጣቸው ቂብላህን አይከተሉም፡፡ አንተም ቂብላቸውን ተከታይ አይደለህም፡፡ ከፊላቸውም የከፊሉን ቂብላ ተከታይ አይደሉም፡፡ ከዕውቀትም (ከራዕይ) ከመጣልህ በኋላ ዝንባሌያቸውን ብትከተል አንተ ያን ጊዜ ከበዳዮች ነህ፡፡ 2|146|እነዚያ መጽሐፍን የሰጠናቸው ወንዶች ልጆቻቸውን እንደሚያውቁ (ሙሐመድን) ያውቁታል፡፡ ከነሱም የተለዩ ክፍሎች እነርሱ የሚያወቁ ሲኾኑ እውነቱን በእርግጥ ይደብቃሉ፡፡ 2|147|(ይህ) ከጌታህ የኾነ እውነት ነው፤ ከተጠራጣሪዎቹም አትሁን፡፡ 2|148|ለሁሉም እርሱ (በስግደት ፊቱን) የሚያዞርባት አግጣጫ አለችው፡፡ ወደ መልካም ሥራዎችም ተሽቀዳደሙ፡፡ የትም ስፍራ ብትኾኑ አላህ እናንተን የተሰበሰባችሁ ኾናችሁ ያመጣችኋል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና፡፡ 2|149|ከየትም (ለጉዞ) ከወጣህበት ስፍራ ፊትሀን ወደ ተከበረው መስጊድ አግጣጫ አዙር፡፡ እርሱም ከጌታህ የኾነ እርግጠኛ እውነት ነው፡፡ አላህም ከምትሠሩት ሥራ ዘንጊ አይደለም፡፡ 2|150|ከየትም ከወጣህበት ስፍራ ፊትህን ወደ ተከለለው መስጊድ አግጣጫ አዙር፡፡ በየትም ስፍራ ብትኾኑ ለሰዎቹ እነዚያ ከነሱ የበደሉት ሲቀሩ (ሃይማኖታችንን ይክዳሉ ቂብላችንን ይከተላሉ በማለት) በናንተ ላይ መከራከሪያ እንዳይኖራቸው ፊቶቻችሁን ወደ አግጣጫው አዙሩ፡፡ አትፍሩዋቸውም፤ ፍሩኝም፤ (በዚህም ያዘዝኳችሁ መከራከሪያ እንዳይኖራቸው) በናንተም ላይ ጸጋየን እንድሞላላችሁና (ወደ እውነትም) እንድትመሩ ነው፡፡ 2|151|በውስጣችሁ ከናንተው የኾነን በናንተ ላይ አንቀጾቻችንን የሚያነብላችሁና የሚያጠራችሁ፣ መጽሐፍንና ጥበብንም የሚያስተምራችሁ፣ ታውቁት ያልነበራችሁትንም ነገር የሚያሳውቃችሁ የኾነን መልክተኛ እንደላክን (ጸጋን ሞላንላችሁ)፡፡ 2|152|አስታውሱኝም፤ አስታውሳችኋለሁና ለኔም አመስግኑ፤ አትካዱኝም፡፡ 2|153|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በመታገስና በሶላት ተረዱ፡፡ አላህ (በእርዳታው) ከታጋሾች ጋር ነውና፡፡ 2|154|በአላህ መንገድ (ለሃይማኖቱ) የሚገደሉትን ሰዎችም «ሙታን ናቸው» አትበሉ፡፡ በእውነቱ ሕያዋን ናቸው፤ ግን አታውቁም፡፡ 2|155|ከፍርሃትና ከረኃብም በጥቂት ነገር፣ ከገንዘቦችና ከነፍሶችም፣ ከፍራፍሬዎችም በመቀነስ በእርግጥ እንሞክራችኋለን፡፡ ታጋሾችንም (በገነት) አብስር፡፡ 2|156|እነዚያን መከራ፤ በነካቻቸው ጊዜ «እኛ ለአላህ፤ ነን እኛም ወደርሱ ተመላሾች» ነን የሚሉትን (አብስር)፡፡ 2|157|እነዚያ በእነርሱ ላይ ከጌታቸው የኾኑ ምሕረቶች ችሮታም አልሉ፡፡ እነርሱም (ወደ እውነት) ተመሪዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 2|158|ሶፋና መርዋ ከአላህ (ትዕዛዝ መፈጸሚያ) ምልክቶች ናቸው፡፡ ቤቱን (ካዕባን) በሐጅ ወይም በዑምራህ ሥራ የጎበኘ ሰው በሁለቱ (መካከል) በመመላለሱ በርሱ ላይ ኃጢአት የለበትም፡፡ መልካምንም ሥራ በፈቃደኛነት የሠራ ሰው (አላህ ይመነዳዋል)፤ አላህ አመስጋኝ ዐዋቂ ነውና፡፡ 2|159|እነዚያ ከአንቀጾችና ከቅን መምሪያ ያወረድነውን ለሰዎች በመጽሐፉ ከገለጽነው በኋላ የሚደብቁ፤ እነዚያ አላህ ይረግማቸዋል፤ ረጋሚዎችም ሁሉ ይረግሟቸዋል፡፡ 2|160|እነዚያ (ከመደበቅ) የተጸጸቱና (ሥራቸውን) ያሳመሩም (የደበቁትን) የገለጹም ብቻ ሲቀሩ፡፡ እነዚህም በነሱ ላይ (ጸጸታቸውን) እቀበላለሁ፤ እኔም ጸጸትን በጣም ተቀባይ አዛኙ ነኝ፡፡ 2|161|እነዚያ የካዱ እነርሱ ከሐዲዎች ኾነውም የሞቱ እነዚያ በነርሱ ላይ የአላህና የመላእክት የሰዎችም ሁሉ እርግማን አለባቸው፡፡ 2|162|በውስጧ (በርግማንዋ ውስጥ) ሁልጊዜ ዘውታሪዎች ሲኾኑ ቅጣቱ ከነሱ አይቀለልም እነርሱም አይቅቆዩም (ጊዜ አይስሰጡም)፡፡ 2|163|አምላካችሁም አንድ አምላክ ብቻ ነው፤ ከርሱ በቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ (እርሱ) እጅግ በጣም ርኅሩህ አዛኝ ነው፡፡ 2|164|ሰማያትንና ምድርን በመፍጠር ሌሊትንና ቀንንም በማተካካት፣ በዚያቸም ሰዎችን በሚጠቅም ነገር (ተጭና) በባህር ላይ በምትንሻለለው ታንኳ፣ አላህም ከሰማይ ባወረደው ውሃና በርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው በማድረጉ፣ በርሷም ውስጥ ከተንቀሳቃሽ ሁሉ በመበተኑ፣ ነፋሶችንም (በየአግጣጫው) በማገለባበጥ፣ በሰማይና በምድር መካከል በሚነዳውም ደመና ለሚያውቁ ሕዝቦች እርግጠኛ ምልክቶች አሉ፡፡ 2|165|ከሰዎችም ከአላህ ሌላ ባለንጣዎችን (ጣዖታትን) አላህን እንደሚወዱ የሚወዷቸው ኾነው የሚይዙ አልሉ፡፡ እነዚያ ያመኑትም አላህን በመውደድ (ከነርሱ) ይበልጥ የበረቱ ናቸው፡፡ እነዚያም የበደሉት ሰዎች ቅጣትን (በትንሣኤ ቀን) ባዩ ጊዜ ኀይል ሁሉ ለአላህ ብቻ መኾኑንና አላህም ቅጣቱ ብርቱ መኾኑን (በአዱኛ ዓለም) ቢያውቁ ኖሮ (ባላንጣዎችን በመያዛቸው በተጸጸቱ ነበር)፡፡ 2|166|እነዚያ አስከታዮቹ ቅጣትን ያዩ ሲኾኑ ከእነዚያ ከተከታዮች በተጥራሩና በእነርሱም (መካከል) ምክንያቶች በተቆረጡ ጊዜ (የሚኾኑትን ባወቁ ኖሮ በተጸጸቱ ነበር)፡፡ 2|167|እነዚያም የተከተሉት «ለእኛ (ወደ ቅርቢቱ ዓለም) አንዲት ጊዜ መመለስ በኖረችንና ከእኛ እንደተጥራሩ ከእነርሱ በተጥራራን እንመኛለን» ይላሉ፡፡ እንደዚሁ አላህ ሥራዎቻቸውን በነርሱ ላይ ጸጸቶች አድርጎ ያሳያቸዋል፡፡ እነርሱም ከእሳት ወጪዎች አይደሉም፡፡ 2|168|እናንተ ሰዎች ሆይ! በምድር ካለው ነገር የተፈቀደ ጣፋጭ ሲኾን ብሉ፡፡ የሰይጣንንም እርምጃዎች አትከታተሉ፡፡ እርሱ ለእናንተ ግልጽ ጠላት ነውና፡፡ 2|169|(እርሱ) የሚያዛችሁ በኃጢኣትና በጸያፍ ነገር በአላህም ላይ የማታውቁትን እንድትናገሩ ብቻ ነው፡፡ 2|170|ለእነርሱም «አላህ ያወረደውን ተከተሉ» በተባሉ ጊዜ «አይደለም አባቶቻችንን በርሱ ላይ ያገኘንበትን ነገር እንከተላለን» ይላሉ፡፡ አባቶቻቸው ምንም የማያውቁና (ወደ እውነት) የማይመሩም ቢኾኑ (ይከተሉዋቸዋልን?) 2|171|የነዚያም የካዱት (እና ወደ ቅን መንገድ የሚጠራቸው ሰው) ምሳሌ እንደዚያ ድምጽንና ጥሪን በስተቀር ሌላን በማይሰማ (እንስሳ) ላይ እንደሚጮህ ብጤ ነው፡፡ (እነርሱ) ደንቆሮዎች፣ ዲዳዎች፣ ዕውሮች ናቸው፤ ስለዚህ እነርሱ አያውቁም፡፡ 2|172|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከነዚያ ከሰጠናችሁ ጣፋጮች ብሉ፡፡ ለአላህም እርሱን ብቻ የምትገዙ እንደኾናችሁ አመስግኑ፡፡ 2|173|በናንተ ላይ እርም ያደረገው በክትንና ደምን፣ የእሪያ ሥጋንም፣ በእርሱም (ማረድ) ከአላህ ስም ሌላ የተነሳበትን ነገር ብቻ ነው፡፡ ሽፍታና ወሰን አላፊ ሳይኾን (ለመብላት) የተገደደ ሰውም በርሱ ላይ ኃጢኣት የለበትም አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 2|174|እነዚያ አላህ ከመጽሐፍ ያወረደውን የሚደብቁ በርሱም (በመደበቃቸው) ጥቂትን ዋጋ የሚገዙ እነዚያ በሆዶቻቸው ውስጥ እሳትን እንጂ አይበሉም፡፡ አላህም በትንሣኤ ቀን አያናግራቸውም፤ (ከኃጢኣት) አያጠራቸውምም፡፡ ለነርሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 2|175|እነዚያ ጥመትን በቅንነት ቅጣትንም በምሕረት የገዙ ናቸው፡፡ በእሳት ላይም ምን ታጋሽ አደረጋቸው! 2|176|ይህ (ቅጣት) አላህ መጽሐፍን በእውነት ያወረደ በመኾኑ ምክንያት (እና በርሱ በመካዳቸው) ነው፡፡ እነዚያም በመጽሐፉ የተለያዩት (ከእውነት) በራቀ ጭቅጭቅ ውስጥ ናቸው፡፡ 2|177|መልካም ሥራ ፊቶቻችሁን ወደ ምሥራቅና ምዕራብ አቅጣጫ ማዞር አይደለም፡፡ ግን መልካም ሥራ በአላህና በመጨረሻው ቀን፣ በመላእክትም፣ በመጻሕፍትም፣ በነቢያትም፣ ያመነ ሰው ገንዘብንም ከመውደዱ ጋር ለዝምድና ባለቤቶችና ለየቲሞች ለምስኪኖችም፣ ለመንገደኞችም፣ ለለማኞችም፣ ለጫንቃዎችም (ማስለቀቅ) የሰጠ ሰውና ሶላትንም ደንቡን ጠብቆ የሰገደ፣ ዘካንም የሰጠ፣ ቃል ኪዳንም በገቡ ጊዜ በኪዳናቸው የሞሉ (ሰዎች ሥራ) ነው፡፡ በችግር በበሽታና በጦር ጊዜም ታጋሾችን (እናወድሳለን)፡፡ እነዚህ እነዚያ እውነትን የያዙ ናቸው፡፡ እነዚያም ተጠንቃቂዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 2|178|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በተገደሉ ሰዎች ማመሳሰል በናንተ ላይ ተጻፈ፡፡ ነጻ በነጻ ባሪያም በባሪያ ሴትም በሴት (ይገደላሉ)፡፡ ለእርሱም (ለገዳዩ) ከወንድሙ (ደም) ትንሽ ነገር ምሕረት የተደረገለት ሰው (በመሓሪው ላይ ጉማውን) በመልካም መከታተል ወደርሱም (ወደ መሓሪው) ገዳዩ በመልካም አኳኋን መክፈል አለባቸው፡፡ ይህ ከጌታችሁ የኾነ ማቃለልና እዝነት ነው፡፡ ከዚህም በኋላ ሕግን የተላለፈ ሰው ለርሱ አሳማሚ ቅጣት አለው፡፡ 2|179|ለእናንተም ባለ አእምሮዎች ሆይ! በማመሳሰል (ሕግ) ውስጥ ሕይወት አላችሁ፡፡ ትጠነቀቁ ዘንድ (ገዳይን መግደል ተደነገገላችሁ)፡፡ 2|180|አንዳችሁን ሞት በመጣበት ጊዜ ሀብትን ቢተው ለወላጆችና ለቅርብ ዘመዶች በበጎ መናዘዝ በናንተ ላይ ተጻፈ፡፡ (ይህ) በጥንቁቆቹ ላይ እርግጠኛ ድንጋጌ ተደነገገ፡፡ 2|181|(ኑዛዜውን) ከሰማውም በኋላ የለወጠው ሰው ኃጢአቱ በነዚያ በሚለውጡት ላይ ብቻ ነው፡፡ አላህ ሰሚ ዐዋቂ ነውና፡፡ 2|182|ከተናዛዢም በኩል (ከውነት) መዘንበልን ወይም (ከሢሶ በመጨመር) ኃጢኣትን ያወቀና በመካከላቸው ያስታረቀ ሰው በእርሱ ላይ ኃጢኣት የለበትም፡፡ አላህ በጣም መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 2|183|እናንተ ያመናችሁ ሆይ ጾም በነዚያ ከናንተ በፊት በነበሩት (ሕዝቦች) ላይ እንደ ተጻፈ በናንተም ላይ ተጻፈ (ተደነባ) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና፡፡ 2|184|የተቆጠሩን ቀኖች (ጹሙ)፡፡ ከእናንተም ውሰጥ በሽተኛ ወይም በጉዞ ላይ የኾነ ሰው ከሌሎች ቀኖች ቁጥሮችን መጾም አለበት፡፡ በእነዚያም ጾምን በማይችሉት ላይ ቤዛ ድኻን ማብላት አለባቸው፡፡ (ቤዛን በመጨመር) መልካምንም ሥራ የፈቀደ ሰው እርሱ (ፈቅዶ መጨመሩ) ለርሱ በላጭ ነው፡፡ መጾማችሁም ለናንተ የበለጠ ነው፤ የምታውቁ ብትኾኑ (ትመርጡታላችሁ)፡፡ 2|185|(እንድትጾሙ የተጻፈባችሁ) ያ በርሱ ውስጥ ለሰዎች መሪ ከቅን መንገድና (እውነትን ከውሸት) ከሚለዩም ገላጮች (አንቀጾች) ሲኾን ቁርኣን የተወረደበት የረመዳን ወር ነው፡፡ ከእናንተም ወሩን ያገኘ ሰው ይጹመው፡፡ በሽተኛ ወይም በጉዞ ላይ የኾነም ሰው ከሌሎች ቀኖች ቁጥሮችን (በልኩ) መጾም አለበት፡፡ አላህ በእናንተ ገሩን (ነገር) ይሻል፡፡ በእናንተም ችግሩን አይሻም፡፡ ቁጥሮችንም ልትሞሉ አላህንም ቅኑን መንገድ ስለመራችሁ ታከብሩትና ታመሰግኑት ዘንድ (ይህን ደነገግንላችሁ)፡፡ 2|186|ባሮቼም ከእኔ በጠየቁህ ጊዜ (እንዲህ በላቸው)፡- እኔ ቅርብ ነኝ፡፡ የለማኝን ጸሎት በለመነኝ ጊዜ እቀበለዋለሁ፡፡ ስለዚህ ለኔ ይታዘዙ፤ በኔም ይመኑ፤ እነሱ ሊመሩ ይከጀላልና፡፡ 2|187|በጾም ሌሊት ወደ ሴቶቻችሁ መድረስ ለናንተ ተፈቀደላችሁ፡፡ እነርሱ ለናንተ ልብሶች ናቸው፤ እናንተም ለነርሱ ልብሶች ናችሁ፡፡ አላህ እናንተ ነፍሶቻችሁን የምትበድሉ መኾናችሁን ዐወቀ፡፡ በእናንተም ላይ ተመለሰላችሁ፡፡ ከእናንተም ይቅርታ አደረገ፡፡ አሁን ተገናኙዋቸው፡፡ አላህም ለናንተ የጻፈላችሁን ነገር (ልጅን) ፈልጉ፡፡ ከጎህ የኾነው ነጩ ክርም ከጥቁሩ ክር (ከሌሊት ጨለማ) ለእናንተ እስከሚገልጽላችሁ ድረስ ብሉ፤ ጠጡም፡፡ ከዚያም ጾምን እስከ ሌሊቱ ድረስ ሙሉ፡፡ እናንተም በመስጊዶች ተቀማጮች ስትኾኑ አትገናኙዋቸው፡፡ ይህች የአላህ ሕግጋት ናትና (ለመተላለፍ) አትቅረቧት፡፡ እንደዚሁ አላህ አንቀጾቹን ለሰዎች ያብራራል፡፡ እነርሱ (የተከለከሉትን) ሊጠነቀቁ ይከጀላልና፡፡ 2|188|ገንዘቦቻችሁንም በመካከላችሁ በከንቱ (ያለ አግባብ) አትብሉ፡፡ እናንተም የምታውቁ ስትኾኑ ከሰዎች ገንዘቦች ከፊልን በኃጢኣት ትበሉ ዘንድ ወደ ዳኞች አትጣሏት፡፡ 2|189|(ሙሐመድ ሆይ!) ከለጋ ጨረቃዎች (መለዋወጥ) ይጠየቁሃል፡፡ እነርሱ ለሰዎች ጥቅም ለሐጅም (ማወቂያ) ጊዜያቶች (ምልክቶች) ናቸው በላቸው፡፡ መልካም ሥራም ቤቶችን ከጀርባዎቻቸው በመምጣታችሁ አይደለም፡፡ ግን የመልካም ሥራ ባለቤት የተጠነቀቀ ሰው ነው፡፡ ቤቶችንም ከደጃፎቻቸው በኩል ግቡ፤ አላህንም ፍሩ ልትድኑ ይከጀላልና (በላቸው)፡፡ 2|190|እነዚያንም የሚጋደሉዋችሁን (ከሓዲዎች) በአላህ መንገድ ተጋደሉ፡፡ ወሰንንም አትለፉ፤ አላህ ወሰን አላፊዎን አይወድምና፡፡ 2|191|ባገኛችኋቸውም ስፍራ ሁሉ ግደሉዋቸው፡፡ ከአወጧችሁም ስፍራ አውጧቸው፡፡ መከራም ከመግደል ይበልጥ የበረታች ናት፡፡ በተከበረው መስጊድም ዘንድ በርሱ ውስጥ እስከሚጋደሉዋችሁ ድረስ አትጋደሉዋቸው፡፡ ቢጋደሉዋችሁም ግደሉዋቸው፤ የከሓዲዎች ቅጣት እንደዚህ ነው፡፡ 2|192|ቢከለከሉም አላህ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 2|193|ሁከት እስከማይገኝና ሃይማኖት ለአላህ ብቻ እስከሚኾን ድረስ ተጋደሉዋቸው፡፡ ቢከለክሉም ወሰንን ማለፍ፤ በበዳዮች ላይ እንጂ የለም (ወሰን አትለፉባቸው)፡፡ 2|194|የተከበረው ወር በተከበረው ወር አንጻር ነው፡፡ ክብሮችም ሁሉ ተመሳሳዮች ናቸው፡፡ በእናንተም ላይ (በተከበረው ወር) ወሰን ያለፈባችሁን ሰው በናንተ ላይ ወሰን ባለፈው ብጤ በርሱ ላይ ወሰን እለፉበት፡፡ አላህንም ፍሩ አላህ ከሚፈሩት ጋር መኾኑንም ዕወቁ፡፡ 2|195|በአላህም መንገድ ለግሱ፡፡ በእጆቻችሁም (ነፍሶቻችሁን) ወደ ጥፋት አትጣሉ፡፡ በጎ ሥራንም ሥሩ፤ አላህ በጎ ሠሪዎችን ይወዳልና፡፡ 2|196|ሐጅንና ዑምራንም ለአላህ ሙሉ፡፡ ብትታገዱም ከሀድይ (ከመሥዋእት) የተገራውን (መሰዋት) አለባችሁ፡፡ ሀድዩም እስፍራው እስከሚደርስ ድረስ ራሶቻችሁን አትላጩ፡፡ ከናንተም ውስጥ በሽተኛ ወይም በራሱ ሁከት ያለበት የኾነ ሰው (ቢላጭ) ከጾም ወይም ከምጽዋት ወይም ከመሥዋዕት ቤዛ አለበት፡፡ ጸጥታም ባገኛችሁ ጊዜ እስከ ሐጅ በዑምራ የተጣቀመ ሰው ከሀድይ የተገራውን (መሠዋት) አለበት፡፡ ያላገኘም ሰው ሶስትን ቀኖች በሐጅ ወራት፤ ሰባትም በተመለሳችሁ ጊዜ መጾም አለበት፡፡ ይህች ሙሉ ዐሥር (ቀናት) ናት፡፡ ይህም (ሕግ) ቤተሰቦቹ ከቅዱሱ መስጊድ አቅራቢያ ላልኾኑ ነው፡፡ አላህንም ፍሩ፤ አላህም ቅጣተ ብርቱ መኾኑን እወቁ፡፡ 2|197|ሐጅ (ጊዜያቱ) የታወቁ ወሮች ናቸው፡፡ በእነርሱም ውስጥ ሐጅን (እንዲሠራ) ነፍሱን ያስገደደ ሰው በሐጅ ውስጥ ሴትን መገናኘት ማመጽም ክርክርም የለም፡፡ ከበጎም ሥራ የምትሠሩትን ሁሉ አላህ ያውቀዋል፡፡ ተሰነቁም፤ ከስንቅም ሁሉ በላጩ ጥንቃቄ (አላህን መፍራት) ነው፡፡ የአእምሮዎችም ባለቤቶች ሆይ! ፍሩኝ፡፡ 2|198|(በሐጅ ጊዜ በንግድ ሥራ) ከጌታችሁ ትርፍን በመፈለጋችሁ በናንተ ላይ ኃጢኣት የለባችሁም፡፡ ከዐረፋትም በጎረፋችሁ ጊዜ መሸዐረልሐራም ዘንድ አላህን አውሱ፡፡ (ለሐጅ) ስለመራችሁም አውሱት፡፡ ከመምራቱ በፊትም በእርግጥ ከተሳሳቾች ነበራችሁ፡፡ 2|199|ከዚያም (ቁረይሾች ሆይ!) ሰዎቹ ከጎረፉበት ስፍራ ጉረፉ፤ (ተመለሱ)፡፡ አላህንም ምሕረትን ለምኑ፤ አላህ እጅግ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 2|200|የሐጅ ሥራዎቻችሁንም በፈጸማችሁ ጊዜ አባቶቻችሁን እንደምታወሱ ወይም ይበልጥ የበረታን ማውሳት አላህን አውሱ፡፡ ከሰዎችም ውስጥ፡- «ጌታችን ሆይ! በምድረዓለም መልካም ዕድልን ስጠን» የሚል ሰው አለ፡፡ ለርሱም በመጨረሻይቱ አገር ከዕድል ምንም የለውም፡፡ 2|201|ከእነርሱም ውስጥ፡- «ጌታችን ሆይ! በምድረ ዓለም ደግን ነገር (ጸጋን) በመጨረሻይቱም አገር ደግን ነገር (ገነትን) ስጠን፤ የእሳትንም ቅጣት ጠብቀን» የሚሉ ሰዎች አልሉ፡፡ 2|202|እነዚያከሠሩት በጎ ሥራ ለነርሱ እድል አላቸው፡፡ አላህም ምርመራው ፈጣን ነው፡፡ 2|203|በተቆጠሩ ቀኖችም ውስጥ (በሚና ጠጠሮችን ስትወረውሩ) አላህን አውሱ፡፡ በሁለት ቀኖችም ውስጥ (በመኼድ) የተቻኮለ ሰው በርሱ ላይ ኃጢኣት የለበትም፡፡ የቆየም ሰው በርሱ ላይ ኃጢኣት የለበትም፡፡ (ይህም) አላህን ለፈራ ሰው ነው፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ እናንተ ወደርሱ የምትሰበሰቡ መኾናችሁንም ዕወቁ፡፡ 2|204|ከሰዎችም ውስጥ እርሱ ክርክረ ብርቱ ሲኾን በቅርቢቱ ሕይወት ንግግሩ የሚደንቅህና በልቡ ውስጥ ባለው ነገር ላይ አላህን የሚያስመሰክር ሰው አልለ፡፡ 2|205|(ካንተ) በዞረም ጊዜ በምድር ላይ በውስጧ ሊያበላሽና አዝመራንና እንስሳዎችን ሊያጠፋ ይሮጣል፡፡ አላህም ማበላሸትን አይወድም፡፡ 2|206|ለእርሱ «አላህን ፍራ» በተባለም ጊዜ፤ ትዕቢቱ በኃጢኣት (ሥራ) ላይ ትገፈፋዋለች፡፡ ገሀነምም በቂው ናት፤ (እርሷም) በእርግጥ የከፋች ምንጣፍ ናት፡፡ 2|207|ከሰዎችም ውስጥ የአላህን ውዴታ ለመፈለግ ነፍሱን የሚሸጥ ሰው አልለ፡፡ አላህም ለባሮቹ በጣም ርኅሩህ ነው፡፡ 2|208|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ሁላችሁም በመታዘዝ ውስጥ ግቡ፡፡ የሰይጣንንም እርምጃዎች አትከተሉ፤ እርሱ ለእናንተ ግልጽ ጠላት ነውና፡፡ 2|209|ግልጽ ማስረጃዎችም ከመጡላችሁ በኋላ ብትዘነበሉ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ መኾኑን እወቁ፡፡ 2|210|አላህ (ቅጣቱ)ና መላእክቱ ከደመና በኾኑ ጥላዎች ውስጥ ሊመጡዋቸው እንጂ አይጠባበቁም፡፡ ነገሩም ተፈጸመ፤ ነገሮችም ሁሉ ወደ አላህ ይመለሳሉ፡፡ 2|211|የእስራኤልን ልጆች ከግልጽ ተዓምር ስንትን እደሰጠናቸው ጠይቃቸው፡፡ የአላህንም ጸጋ ከመጣችለት በኋላ የሚለውጥ ሰው አላህ ቅጣተ ብርቱ ነው፡፡ 2|212|ለእነዚያ ለካዱት ከእነዚያ ካመኑት የሚሳለቁ ሲኾኑ ቅርቢቱ ሕይወት ተሸለመችላችው፡፡ እነዚያም የተጠነቀቁት በትንሣኤ ቀን ከበላያቸው ናቸው፡፡ አላህም ለሚሻው ሰው ያለ ግምት ይሰጣል፡፡ 2|213|ሰዎቹ ሁሉ አንድ ሕዝብ ነበሩ፤ (ተለያዩ)፡፡ አላህም ነቢያትን አብሳሪዎችና አስፈራሪዎች አድርጎ ላከ፡፡ ከእነርሱም ጋር መጻሕፍትን በሰዎቹ መካከል በዚያ በርሱ በተለያዩበት ነገር ይፈርድ ዘንድ በእውነት አወረደ፡፡ በእርሱም (በሃይማኖት) ግልጽ አስረጂዎች ከመጡላቸው በኋላ በመካከላቸው ለኾነው ምቀኝነት እነዚያው የተሰጡት እንጂ አልተለያዩበትም፡፡ አላህም እነዚያን ያመኑትን ሰዎች ለእዚያ ከእውነት በርሱ ለተለያዩበት በፍቃዱ መራቸው፡፡ አላህም የሚሻውን ሰው ወደ ቀጥተኛው መንገድ ይመራል፡፡ 2|214|በእውነቱ የእነዚያ ከበፊታችሁ ያለፉት (ምእምናን መከራ) ብጤ ሳይመጣችሁ ገነትን ልትገቡ ታስባላችሁን? መልክተኛውና እነዚያ ከርሱ ጋር ያመኑት «የአላህ እርዳታ መቼ ነው?» እስከሚሉ ድረስ መከራና ጉዳት ነካቻቸው፤ ተርበደበዱም፡፡ ንቁ! የአላህ እርዳታ በእርግጥ ቅርብ ነው (ተባሉም)፡፡ 2|215|ምንን (ለማንም) እንደሚለግሱ ይጠይቁሃል፡፡ ከመልካም ነገር የምትለግሱት፤ ለወላጆችና ለቅርብ ዘመዶች፣ ለየቲሞችም፣ ለድሆችም፣ ለመንገደኞችም ነው፡፡ ከበጎ ነገርም ማንኛውንም ብትሠሩ አላህ እርሱን ዐዋቂ ነው በላቸው፡፡ 2|216|መጋደል እርሱ ለእናንተ የተጠላ ሲሆን በእናንተ ላይ ተጻፈ፡፡ አንዳች ነገርን እርሱ ለናንተ የበለጠ ሲሆን የምትጠሉት መኾናችሁ ተረጋገጠ፡፡ አንዳችንም ነገር እርሱ ለናንተ መጥፎ ሲሆን የምትወዱት መሆናችሁ ተረጋገጠ፡፡ አላህም (የሚሻላችሁን) ያውቃል ግን እናንተ አታውቁም፡፡ 2|217|ከተከበረው ወር (ከረጀብ) በርሱ ውስጥ ከመጋደል ይጠይቁሃል፡፡ በላቸው «በርሱ ውስጥ መጋደል ታላቅ (ኀጢአት) ነው፡፡ ግን ከአላህ መንገድ (ሰዎችን) መከላከል፣ በርሱም መካድ፣ ከተከበረውም መስጊድ (ማገድ) ባለቤቶቹንም ከርሱ ማውጣት አላህ ዘንድ ይበልጥ ታላቅ (ወንጀል) ነው፡፡ ፈተናም (ማጋራት) ከመግደል ይበልጥ ከባድ ነው፡፡ (ከሐዲዎች) ቢችሉ ከሃይማኖታችሁ እስከሚመልሳችሁ ድረስ የሚዋጉዋችሁ ከመሆን አይቦዝኑም፡፡ ከእናንተ ውስጥም ከሃይማኖቱ የሚመለስና እርሱም ከሐዲ ሆኖ የሚሞት ሰው እነዚያ (በጎ) ሥራቸው በቅርቢቱም በመጨረሻይቱም አገር ተበላሸች፡፡ እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነርሱ በርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡» 2|218|እነዚያ ያመኑትና እነዚያም (ከአገራቸው) የተሰደዱት በአላህም መንገድ ላይ የተጋደሉት እነዚያ የአላህን እዝነት ይከጅላሉ፡፡ አላህም እጅግ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 2|219|አእምሮን ከሚቃወም መጠጥና ከቁማር ይጠይቁሃል፡፡ «በሁለቱም ውስጥ ታላቅ ኃጢኣትና ለሰዎች ጥቅሞች አሉባቸው፡፡ ግን ኃጢኣታቸው ከጥቅማቸው በጣም ትልቅ ነው» በላቸው፡፡ ምንን እንደሚመጸውቱም (መጠኑን) ይጠይቁሃል፡፡ «ትርፍን (መጽውቱ)» በላቸው፡፡ እንደዚሁ ታስተነትኑ ዘንድ አላህ ለናንተ አንቀጾችን ይገልጽላችኋል፡፡ 2|220|በቅርቢቱ ዓለምና በመጨረሻይቱ ታስተነትኑ ዘንድ (ይገለጽላችኋል)፡፡ ከየቲሞችም ይጠይቁሃል፡፡ «ለእነርሱ (ገንዘባቸውን በማራባት) ማሳመር በላጭ ነው፡፡ ብትቀላቀሏቸውም ወንድሞቻችሁ ናቸው፡፡ አላህም የሚያጠፋውን ከሚያበጀው (ለይቶ) ያውቃል፡፡ አላህም በሻ ኖሮ ባስቸገራችሁ ነበር፤ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና» በላቸው፡፡ 2|221|(በአላህ) አጋሪ የሆኑ ሴቶች እስከሚያምኑ ድረስ አታግቡዋቸው፡፡ ከአጋሪይቱ ምንም ብትደንቃችሁም እንኳ ያመነችው ባሪያ በእርግጥ በላጭ ናት፡፡ ለአጋሪዎቹም እስከሚያምኑ ድረስ አትዳሩላቸው፡፡ ከአጋሪው (ጌታ) ምንም ቢደንቃችሁ ምእምኑ ባሪያ በላጭ ነው፡፡ እነዚያ (አጋሪዎች) ወደ እሳት ይጣራሉ፡፡ አላህም በፈቃዱ ወደ ገነትና ወደ ምሕረት ይጠራል፡፡ ሕግጋቱንም ለሰዎች ይገልጻል እነርሱ ሊገሰጹ ይከጀላልና፡፡ 2|222|ከወር አበባም ይጠይቁሃል፡፡ እርሱ አስጠያፊ ነው፡፡ ሴቶችንም በወር አበባ ጊዜ ራቋቸው፡፡ ንጹሕ እስከሚኾኑም ድረስ አትቅረቡዋቸው፡፡ ንጹሕ በኾኑም ጊዜ አላህ ካዘዛችሁ ስፍራ ተገናኙዋቸው፡፡ አላህ (ከኃጢኣት) ተመላሾችን ይወዳል፤ ተጥራሪዎችንም ይወዳል በላቸው፡፡ 2|223|ሴቶቻችሁ ለናንተ እርሻ ናቸው፡፡ እርሻችሁንም በፈለጋችሁት ኹነታ ድረሱ፡፡ ለነፍሶቻችሁም (መልካም ሥራን) አስቀድሙ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ እናንተም ተገናኝዎቹ መኾናችሁን ዕወቁ፡፡ ምእመናንንም (በገነት) አብስር፡፡ 2|224|መልካም እንዳትሠሩ፣ አላህንም እንዳትፈሩ፣ በሰዎችም መካከል እንዳታስታርቁ አላህን ለመሐላዎቻችሁ ግርዶ አታድርጉ፡፡ አላህም ሰሚ አዋቂ ነው፡፡ 2|225|በመሐላዎቻችሁ በውድቁ (ሳታስቡ በምትምሉት) አላህ አይዛችሁም፡፡ ግን ልቦቻችሁ ባሰቡት ይይዛችኋል፡፡ አላህም በጣም መሐሪ ታጋሽ ነው፡፡ 2|226|ለእነዚያ ከሴቶቻቸው (ላይቀርቡ) ለሚምሉት አራትን ወሮች መጠበቅ አለባቸው፡፡ (ከመሐላቸው) ቢመለሱም አላህ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 2|227|መፍታትንም ቁርጥ አሳብ ቢያደርጉ (ይፍቱ)፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|228|የተፈቱ ሴቶችም ነፍሶቻቸውን (ከማግባት) ሦስትን ቁርእ ይጠብቁ፡፡ በአላህና በመጨረሻውም ቀን የሚያምኑ ቢኾኑ አላህ በማሕፀኖቻቸው ውስጥ የፈጠረውን ሊደብቁ ለነርሱ አይፈቀድላቸውም፡፡ ባሎቻቸውም በዚህ ውስጥ እርቅን ቢፈልጉ በመማለሳቸው ተገቢዎች ናቸው፡፡ ለእነርሱም (ለሴቶች) የዚያ በእነርሱ ላይ ያለባቸው (ግዳጅ) ብጤ በመልካም አኑዋኑዋር (በባሎቻቸው ላይ መብት) አላቸው፡፡ ለወንዶችም (ጣጣቸውን ስለሚሸከሙ) በእነሱ ላይ ብልጫ አላቸው፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 2|229|ፍች ሁለት ጊዜ ነው፤ (ከዚህ በኋላ) በመልካም መያዝ ወይም በበጎ አኳኋን ማሰናበት ነው፡፡ የአላህንም ሕግጋት አለመጠበቃቸውን ካላወቁ በስተቀር ከሰጣችኃቸው ነገር ምንንም ልትወስዱ ለእናንተ (ለባሎች) አይፈቀድላችሁም፡፡ የአላህንም ሕግጋት አለመጠበቃቸውን ብታውቁ በእርሱ (ነፍሷን) በተበዠችበት ነገር በሁለቱም ላይ ኃጢኣት የለም፡፡ ይህች የአላህ ሕግጋት ናት፤ አትተላለፏትም፡፡ የአላህንም ሕግጋት የሚተላለፉ እነዚያ እነርሱ በዳዮች ናቸው፡፡ 2|230|(ሦስተኛ) ቢፈታትም ከዚህ በኋላ ሌላን ባል እስከምታገባ ድረስ ለርሱ አትፈቀድለትም፡፡ (ሁለተኛው ባል) ቢፈታትም የአላህን ሕግጋት መጠበቃቸውን ቢያውቁ በመማለሳቸው በሁለቱም ላይ ኃጢኣት የለባቸውም፡፡ ይህችም የአላህ ሕግጋት ናት ለሚያውቁ ሕዝቦች ያብራራታል፡፡ 2|231|ሴቶችን በፈታችሁና (የዒዳ) ጊዜያቸውን በደረሱ ጊዜ በመልካም ያዙዋቸው፤ (ተማለሷቸው) ወይም በመልካም ኹኔታ አሰናብቱዋቸው፡፡ ለመጉዳትም ወሰን ታልፋባቸው ዘንድ አትያዙዋቸው፤ ይህንንም የሚሠራ ሰው ነፍሱን በእርግጥ በደለ፡፡ የአላህንም አንቀጾች ማላገጫ አድርጋችሁ አትያዙ፡፡ የአላህንም ጸጋ በናንተ ላይ ያደረገውን ከመጽሐፍና ከጥበብም በርሱ የሚገስጻችሁ ሲኾን በናንተ ላይ ያወረደውን አስታውሱ፡፡ አላህንም ፍሩ፤ አላህም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ መኾኑን ዕወቁ፡፡ 2|232|ሴቶችንም በፈታችሁና ጊዜያቸውን በደረሱ ጊዜ በመካከላቸው በሕግ በተዋደዱ ጊዜ ባሎቻቸውን ከማግባት አታስተጓጉሏቸው፡፡ ይህ (መከልከል) ከእናንተ በአላህና በመጨረሻው ቀን የሚያምን ሰው በርሱ ይገሰጽበታል፡፡ ይህ ሁኔታችሁ ለእናንተ በላጭ ነው፤ (ከመጠርጠር) አጥሪም ነው፡፡ አላህም ያውቃል፤ እናንተ ግን አታውቁም፡፡ 2|233|እናቶችም ልጆቻቸውን ሙሉ የኾኑን ሁለት ዓመታት ያጥቡ፡፡ (ይህም) ማጥባትን መሙላት ለሻ ሰው ነው፡፡ ለእርሱም በተወለደለት (አባት) ላይ ምግባቸውና ልብሳቸው በችሎታው ልክ አለበት፡፡ ነፍስ ችሎታዋን እንጂ አትገደድም፡፡ ወላጂት (እናት) በልጅዋ ምክንያት ለርሱ የተወለደለትም (አባት) በልጁ ምክንያት አይጎዳዱ፡፡ በወራሽም ላይ እንደዚሁ ብጤ አለበት፡፡ (ወላጆቹ) ከሁለቱም በኾነ መዋደድና መመካከር (ልጁን ከጡት) መነጠልን ቢፈልጉ በሁለቱም ላይ ኃጢኣት የለባቸውም፡፡ ልጆቻችሁንም ለሌሎች አጥቢዎች ማስጠባትን ብትፈልጉ ልትሰጡ የሻችሁትን በመልካም ኹኔታ በሰጣችሁ ጊዜ (በማስጠባታችሁ) በእናንተ ላይ ኃጢኣት የለባችሁም፡፡ አላህንም ፍሩ፤ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች መኾኑን ዕወቁ፡፡ 2|234|እነዚያም ከናንተ ውስጥ የሚሞቱና ሚስቶችን የሚተዉ (ሚስቶቻቸው) በነፍሶቻቸው አራት ወሮች ከዐስር (ቀናት ከጋብቻ) ይታገሱ፡፡ ጊዜያቸውንም በጨረሱ ጊዜ በነፍሶቻቸው በታወቀ ሕግ በሠሩት ነገር በእናንተ ላይ ኃጢአት የለባችሁም፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጥ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|235|ሴቶችንም ከማጨት በርሱ ባሸሞራችሁበት ወይም በነፍሶቻችሁ ውስጥ (ለማግባት) በደበቃችሁት በናንተ ላይ ኃጢኣት የለባችሁም፡፡ አላህ እናንተ በእርግጥ የምታስታውሷቸው መኾናችሁን ዐወቀ፡፡ (ስለዚህ ማሸሞርንና ማሰብን ፈቀደላችሁ፡፡) ግን በሕግ የታወቀን ንግግር የምትነጋገሩ ካልኾናችሁ በስተቀር፤ ምስጢርን (ጋብቻን) አትቃጠሩዋቸው፡፡ የተጻፈውም (ዒዳህ) ጊዜውን እስከሚደርስ ድረስ ጋብቻን ለመዋዋል ቁርጥ ሐሳብ አታድርጉ፡፡ አላህም በነፍሶቻችሁ ያለውን ነገር የሚያውቅ መኾኑን ዕወቁ፤ ተጠንቀቁትም፡፡ አላህም መሓሪ ታጋሽ መኾኑን ዕወቁ፡፡ 2|236|ሴቶችን ሳትነኳቸው (ሳትገናኙ)፤ ወይም ለነሱ መህርን ሳትወስኑላቸው ብትፈቷቸው በናንተ ላይ ኃጢኣት የለባችሁም፡፡ (ዳረጎት በመስጠት መፍታት ትችላላችሁ፡፡) ጥቀሟቸውም፡፡ በሀብታም ላይ ችሎታው በድኀም ላይ ችሎታው (አቅሙ የሚፈቅደውን መስጠት) አለበት፡፡ መልካም የኾነን መጥቀም በበጎ ሠሪዎች ላይ የተረጋገጠን፤ (ጥቀሟቸው)፡፡ 2|237|ለእነርሱም መወሰንን በእርግጥ የወሰናችሁላቸው ስትኾኑ ሳትነኳቸው በፊት ብተፈቷቸው ካልማሩዋችሁ ወይም ያ የጋብቻው ውል በእጁ የኾነው (ባልየው) ካልማረ በስተቀር የወሰናችሁት ግማሹ አላቸው፡፡ ምሕረትም ማድረጋችሁ ወደ አላህ ፍራቻ በጣም የቀረበ ነው፡፡ በመካከላችሁም ችሮታን አትርሱ፤ አላህ የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነውና፡፡ 2|238|በሶላቶች (በተለይ) በመካከለኛይቱም ሶላት ላይ ተጠባበቁ፡፡ ታዛዦች ኾናችሁም ለአላህ ቁሙ፡፡ 2|239|ብትፈሩም እግረኞች ወይም ጋላቢዎች ኾናችሁ (ስገዱ)፡፡ ጸጥተኞችም በኾናችሁ ጊዜ ታውቁት ያልነበራችሁትን እንደ አሳወቃችሁ አላህን አውሱ (ስገዱ)፡፡ 2|240|እነዚያ ከናንተ ውስጥ የሚሞቱ ሚስቶችንም የሚተዉ፤ ለሚስቶቻቸው (ከቤታቸው) የማይወጡ ሲኾኑ ዓመት ድረስ መጠቀምን ኑዛዜን (ይናዘዙ)፡፡ በፈቃዳቸው ቢወጡም በሕግ ከታወቀው ነገር በነፍሶቻቸው በሠሩት በእናንተ (በሟቹ ዘመዶች) ላይ ኃጢኣት የለባችሁም አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 2|241|ለተፈቱ ሴቶችም በችሎታ መጠን ዳረጎት አላቸው፡፡ አላህን በሚፈሩ ላይ ተደንግጓል፡፡ 2|242|እንደዚሁ አላህ አንቀጾቹን ታውቁ ዘንድ ለናንተ ያብራራላችኋል፡፡ 2|243|ወደ እነዚያ እነርሱ ብዙ ሺሕ ኾነው ሞትን ለመፍራት ከሀገሮቻቸው ወደ ወጡት ሰዎች ዕውቀትህ አልደረሰምን? አላህም ለነርሱ «ሙቱ» አላቸው፤ (ሞቱም)፡፡ ከዚያም ሕያው አደረጋቸው፡፡ አላህም በሰዎች ላይ ባለችሮታ ነው፤ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያመሰግኑም፡፡ 2|244|በአላህም መንገድ (ሃይማኖት) ተጋደሉ፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ መኾኑን ዕወቁ፡፡ 2|245|ያ ለአላህ መልካም ብድርን የሚያበድርና ለእርሱ (አላህ) ብዙ እጥፎች አድርጎ የሚያነባብርለት ማነው? አላህም ይጨብጣል፤ ይዘረጋልም፤ ወደ እርሱም ትመለሳላችሁ፡፡ 2|246|ከእስራኤል ልጆች ከሙሳ በኋላ ወደ ነበሩት ጭፍሮች ለነቢያቸው (ለሳሙኤል)፡- «ለእኛ ንጉሥን አስነሳልን በአላህ መንገድ እንዋጋለን፤» ባሉ ጊዜ አላየህምን? (አላወቅህምን?)፡-«መዋጋት ቢጻፍባችሁ አትዋጉም ይኾናል» አላቸው፡፡ «ከሀገሮቻችንና ከልጆቻችን የተባረርን ስንኾን በአላህ መንገድ የማንዋጋ ለእኛ ምን አለን?» አሉ፡፡ በእነርሱ ላይ መዋጋት በተጻፈባቸውም ጊዜ ከእነርሱ ጥቂቶች ሲቀሩ አፈገፈጉ፡፡ አላህም በዳዮቹን ዐዋቂ ነው፡፡ 2|247|ነቢያቸውም ለእነርሱ፡- «አላህ ጧሉትን (ሳኦልን) ንጉሥ አድርጎ በእርግጥ ላከላችሁ» አላቸው፡፡ (እነርሱም)፡- «እኛ ከእርሱ ይልቅ በንግሥና ተገቢዎች ስንኾን ከሀብትም ስፋትን ያልተሰጠ ሲኾን ለእርሱ በኛ ላይ እንዴት ንግሥና ይኖረዋል?» አሉ፡፡ (ነቢያቸውም)፡-«አላህ በእናንተ ላይ መረጠው፡፡ በዕውቀትና በአካልም ስፋትን ጨመረለት፡፡ አላህም ንግሥናውን ለሚሻው ሰው ይሰጣል፡፡ አላህም ችሮታው ሰፊ ዐዋቂ ነው» አላቸው፡፡ 2|248|ነቢያቸውም ለእነርሱ፡- «የንግሥናው ምልክት ከጌታችሁ የኾነ እርጋታ የሙሳ ቤተሰብና የሃሩን ቤተሰብ ከተውትም ቅርስ በውስጡ ያለበት መላእክት የሚሸከሙት ኾኖ ሳጥኑ ሊመጣላችሁ ነው፡፡ አማኞች ብትኾኑ በዚህ ለእናንተ እርግጠኛ ምልክት አልለ» አላቸው፡፡ 2|249|ጧሉትም በሠራዊቱ (ታጅቦ) በወጣ ጊዜ፡- «አላህ በወንዝ (ውሃ) ፈታኛችሁ ነው ከርሱም የጠጣ ሰው ከእኔ አይደለም፡፡ ያልቀመሰውም ሰው በእጁ መዝገንን የዘገነ ሰው ብቻ ሲቀር እርሱ ከኔ ነው» አለ፡፡ ከእነርሱም ጥቂቶች ሲቀሩ ከርሱ ጠጡ፡፡ እርሱና እነዚያም ከእርሱ ጋር ያመኑት (ወንዙን) ባለፉት ጊዜ፡- «ጃሎትንና ሠራዊቱን በመዋጋት ለኛ ዛሬ ችሎታ የለንም» አሉት፡፡ እነዚያ እነርሱ አላህን ተገናኝዎች መኾናቸው የሚያረጋግጡት፡- «ከጥቂት ጭፍራ በአላህ ፈቃድ ብዙን ጭፍራ ያሸነፈች ብዙ ናት፤ አላህም ከታጋሾች ጋር ነው» አሉ፡፡ 2|250|ለጃሎትና ለሠራዊቱ በተሰለፉም ጊዜ፡- «ጌታችን ሆይ! በእኛ ላይ ትዕግስትን አንቧቧ፤ ጫማዎቻችንንም አደላድል፤ በከሓዲያን ሕዝቦችም ላይ እርዳን» አሉ፡፡ 2|251|በአላህም ፈቃድ ድል መቷቸው፡፡ ዳውድም ጃሉትን (ዳዊት ጎልያድን) ገደለ፡፡ ንግሥናንና ጥበብንም (ነቢይነትን) አላህ ሰጠው፡፡ ከሚሻውም ነገር ሁሉ አሳወቀው፡፡ አላህም ሰዎችን ከፊላቸውን በከፊሉ መመለሱ ባልነበረ ኖሮ ምድር በተበላሸች ነበር፤ ግን አላህ በዓለማት ላይ የችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 2|252|እነዚህ (አንቀጾች) በውነት በአንተ ላይ የምናነባቸው ሲኾኑ የአላህ አንቀጾች ናቸው፤ አንተም በእርግጥ ከመልክተኞቹ ነህ፡፡ 2|253|እነዚህን መልክተኞች ከፊላቸውን በከፊሉ ላይ አበለጥን፡፡ ከእነርሱ ውስጥ አላህ ያነጋገረው አልለ፡፡ ከፊሎቻቸውንም በደረጃዎች ከፍ አደረገ፡፡ የመርየምን ልጅ ዒሳንም ግልጽ ታምራቶችን ሰጠነው፡፡ በቅዱሱ መንፈስም አበረታነው፡፡ አላህም በሻ ኖሮ እነዚያ ከእነርሱ (ከመልክተኞቹ) በኋላ የነበሩት ግልጽ ታምራቶች ከመጡላቸው በኋላ ባልተጋደሉ ነበር፡፡ ግን ተለያዩ፡፡ ከእነርሱም ውስጥ ያመነ ሰው አልለ፡፡ ከነርሱም ውስጥ የካደ ሰው አልለ፡፡ አላህም በሻ ኖሮ ባልተዋጉ (ባልተለያዩ) ነበር፡፡ ግን አላህ የሚሻውን ይሠራል፡፡ 2|254|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በርሱ ውስጥ ሽያጭ (መበዠት)፣ ወዳጅነትም፣ ምልጃም የሌለበት ቀን ከመምጣቱ በፊት ከሰጠናችሁ ነገር ለግሱ፡፡ ከሓዲዎችም በዳዮቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 2|255|አላህ ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ ሕያው ራሱን ቻይ ነው፡፡ ማንገላጀትም እንቅልፍም አትይዘውም፡፡ በሰማያት ውስጥና በምድር ውስጥ ያለው ሁሉ የርሱ ብቻ ነው፡፡ ያ እርሱ ዘንድ በፈቃዱ ቢኾን እንጅ የሚያማልድ ማነው? (ከፍጡሮች) በፊታቸው ያለውንና ከኋላቸው ያለውን ሁሉ ያውቃል፡፡ በሻውም ነገር እንጂ ከዕውቀቱ በምንም ነገር አያካብቡም (አያውቁም)፡፡ መንበሩ ሰማያትንና ምድርን ሰፋ፡፡ ጥበቃቸውም አያቅተውም፡፡ እርሱም የሁሉ በላይ ታላቅ ነው፡፡ 2|256|በሃይማኖት ማስገደድ የለም፡፡ ቅኑ መንገድ ከጠማማው በእርግጥ ተገለጠ፡፡ በጣዖትም የሚክድና በአላህ የሚያምን ሰው ለርሷ መበጠስ የሌላትን ጠንካራ ዘለበት በእርግጥ ጨበጠ፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|257|አላህ የእነዚያ ያመኑት ሰዎች ረዳት ነው፡፡ ከጨለማዎች ወደ ብርሃን ያወጣቸዋል፡፡ እነዚያም የካዱት ረዳቶቻቸው ጣዖታት ናቸው፡፡ ከብርሃን ወደ ጨለማዎች ያወጧቸዋል፡፡ እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፤ እነርሱ በውስጧ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 2|258|ወደዚያ አላህ ንግሥናን ስለሰጠው ኢብራሂምን በጌታው ነገር ወደ ተከራከረው ሰው አላየህምን ኢብራሂም «ጌታዬ ያ ሕያው የሚያደርግና የሚገድል ነው» ባለ ጊዜ «እኔ ሕያው አደርጋለሁ እገድላለሁም» አለ፡፡ ኢብራሂም፡- «አላህ ፀሐይን ከምሥራቅ በኩል ያመጣል (አንተ) ከምዕራብ በኩል አምጣት» አለው፡፡ ያም የካደው ሰው ዋለለ፤ (መልስ አጣ) አላህም በዳዮች ሕዝቦችን አይመራም፡፡ 2|259|ወይም ያንን በከተማ ላይ እርሷ በጣራዎችዋ ላይ የወደቀች ስትኾን ያለፈውን ሰው ብጤ (አላየህምን)፡- «ይህችን (ከተማ) ከሞተች በኋላ አላህ እንዴት ሕያው ያደርጋታል» አለ፡፡ አላህም ገደለው መቶ ዓመትን (አቆየውም)፡፡ ከዚያም አስነሳው፡- «ምን ያህል ቆየህ» አለው፡፡ «አንድ ቀን ወይም የቀንን ከፊል ቆየሁ» አለ፡፡ «አይደለም መቶን ዓመት ቆየህ፡፡ ወደ ምግብህና ወደ መጠጥህም ያልተለወጠ ሲኾን ተመልከት፡፡ ወደ አህያህም ተመልከት፡፡ ለሰዎችም አስረጅ እናደርግህ ዘንድ (ይህንን ሠሰራን)፡፡ ወደ ዐፅሞቹም እንዴት እንደምናስነሳት ከዚያም ሥጋን እንደምናለብሳት ተመልከት» አለው፡፡ ለርሱም (በማየት) በተገለጸለት ጊዜ፡- «አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ መኾኑን ዐውቃለሁ» አለ፡፡ 2|260|ኢብራሂምም «ጌታዬ ሆይ! ሙታንን እንዴት ሕያው እንደምታደርግ አሳየኝ» ባለ ጊዜ (አስታውስ፡፡) አላህ ፡- «አላመንክምን» አለው፡፡ «አይደለም (አምኛለሁ)፤ ግን ልቤ እንዲረጋ» ነው አለ፡፡ (አላህም)፡- «ከበራሪዎች (ከወፎች) አራትን ያዝ፡፡ ወደ አንተም ሰብስባቸው፡፡ (ቆራርጣቸውም)፤ ከዚያም በየኮረብታው ሁሉ ላይ ከነርሱ ቁራጭን አድርግ፡፡ ከዚያም ጥራቸው፤ ፈጥነው ይመጡሃልና፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ መኾኑን ዕወቅ» አለው፡፡ 2|261|የእነዚያ ገንዘቦቻቸውን በአላህ መንገድ የሚለግሱ ሰዎች (ልግስና) ምሳሌ በየዘለላው ሁሉ መቶ ቅንጣት ያለባቸውን ሰባት ዘለላዎች እንደ አበቀለች አንዲት ቅንጣት ብጤ ነው፡፡ አላህም ለሚሻው ሰው (ከዚህ በላይ) ያነባብራል፡፡ አላህም ችሮታው ሰፊ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|262|እነዚያ ገንዘቦቻቸውን በአላህ መንገድ የሚለግሱ ከዚያም የሰጡትን ነገር መመጻደቅንና ማስከፋትን የማያስከትሉ ለእነርሱ በጌታቸው ዘንድ ምንዳቸው አላቸው፡፡ በእነርሱም ላይ ፍርሃት የለባቸውም፤ እነርሱም አያዝኑም፡፡ 2|263|መልካም ንግግርና ምሕረት ማድረግ ማስከፋት ከሚከተላት ምጽዋት በላጭ ነው፡፡ አላህም ተብቃቂ ታጋሽ ነው፡፡ 2|264|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እንደዚያ ገንዘቡን ለሰዎች ማሳየት ሲል እንደሚሰጠውና በአላህና በመጨረሻውም ቀን እንደማያምነው ሰው ምጽዋቶቻችሁን በመመጻደቅና በማስከፋት አታበላሹ፡፡ ምሳሌውም በላዩ ዐፈር እንዳለበት ለንጣ ድንጋይ ኃይለኛም ዝናብ እንዳገኘውና ምልጥ አድርጎ እንደተወው ብጤ ነው፡፡ ከሠሩት ነገር በምንም ላይ (ሊጠቀሙ) አይችሉም፡፡ አላህም ከሓዲያንን ሕዝቦች አይመራም፡፡ 2|265|የእነዚያም የአላህን ውዴታ ለመፈለግና ለነፍሶቻቸው (እምነትን) ለማረጋገጥ ገንዘቦቻቸውን የሚለግሱ ሰዎች ምሳሌ በተስተካከለች ከፍተኛ ስፍራ ላይ እንዳለች አትክልት፣ ብዙ ዝናብ እንደነካት ፍሬዋንም እጥፍ ኾኖ እንደሰጠች፣ ዝናብም ባይነካት ካፊያ እንደሚበቃት ብጤ ነው፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 2|266|(ከእናንተ) አንዳችሁ ለርሱ ከዘምባባና ከወይኖች በስርዋ ወንዞች የሚፈሱባት አትክልት ልትኖረው፣ በውስጧም ለርሱ ከየፍሬው ሁሉ ሊኖረው እርጅናም ሊነካውና ለርሱ ደካማዎች ዝርያዎች ያሉት ሲኾን በውስጡ እሳት ያለበት ውርጭ ሊያገኛትና ልትቃጠል ይወዳልን እንደዚሁ አላህ አንቀጾችን ለእናንተ ያብራራል፤ ልታስተነትኑ ይከጀላልና፡፡ 2|267|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ካፈራችሁትና ከዚያም ለእናንተ ከምድር ካወጣንላችሁ ከመልካሙ ለግሱ፡፡ መጥፎውንም (ለመስጠት) አታስቡ፡፡ በእርሱ ዓይኖቻችሁን ጨፍናችሁ እንጂ የማትወስዱት ስትኾኑ ከእርሱ (ከመጥፎው) ትሰጣላችሁን አላህም ተብቃቂ ምስጉን መኾኑን ዕወቁ፡፡ 2|268|ሰይጣን (እንዳትለግሱ) ድኽነትን ያስፈራራችኋል፡፡ በመጥፎም ያዛችኋል፡፡ አላህም ከርሱ የኾነን ምሕረትና ችሮታን ይቀጥራችኋል፡፡ አላህም ችሮታው ሰፊ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|269|ለሚሻው ሰው ጥበብን ይሰጣል፤ ጥበብንም የሚስሰጥ ሰው ብዙን መልካም ነገር በእርግጥ ተሰጠ፡፡ የአእምሮዎች ባለቤቶች እንጂ (ሌላው) አይገሰጽም፡፡ 2|270|ከምጽዋትም ማንኛውንም የለገሳችሁትን ወይም ከስለት የተሳላችሁትን አላህ ያውቀዋል፡፡ ለበዳዮችም ከረዳቶች ምንም የላቸውም፡፡ 2|271|ምጽዋቶችን ብትገልጹ እርሷ ምንኛ መልካም ናት፡፡ ብትደብቋትና ለድኾች ብትሰጧትም እርሱ ለናንተ በላጭ ነው፡፡ ከኃጢአቶቻችሁም ከእናንተ ያብሳል፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|272|እነርሱን ማቅናት በአንተ ላይ የለብህም፡፡ ግን አላህ የሚሻውን ሰው ያቀናል፡፡ ከገንዘብም የምትለግሱት (ምንዳው) ለነፍሶቻችሁ ነው፡፡ የአላህንም ፊት (ውዴታውን) ለመፈለግ እንጂ አትለግሱም፡፡ ከገንዘብም የምትለግሱት ሁሉ (ምንዳው) ወደናንተ ይሞላል፡፡ እናንተም አትበደሉም፡፡ 2|273|(የምትመጸውቱት) ለእነዚያ በአላህ መንገድ (ለመታገል ሲሉ) ለታገዱት ድኾች ነው፡፡ በምድር መኼድን አይችሉም፡፡ (ልመናን) ከመጥጠበቃቸው (የተነሳ) የማያውቅ ሰው ሀብታሞች ናቸው ብሎ ይጠረጥራቸዋል፡፡ በምልክታቸው ታውቃቸዋለህ፡፡ ሰዎችን በችክታ አይለምኑም፡፡ ከገንዘብም የምትለግሱት አላህ እርሱን ዐዋቂ ነው፡፡ 2|274|እነዚያ ገንዘቦቻቸውን በሌሊትና በቀን በድብቅም በግልጽም የሚለግሱ ለእነርሱ በጌታቸው ዘንድ ምንዳቸው አላቸው፡፡ በእነርሱም ላይ ፍርሃት የለባቸውም እነርሱም አያዝኑም፡፡ 2|275|እነዚያ አራጣን የሚበሉ ያ ሰይጣን ከመንካቱ የተነሳ የሚጥለው ሰው (ከአውድቁ) እንደሚነሳ ብጤ እንጅ (ከመቃብራቸው) አይነሱም፡፡ ይህ እነርሱ መሸጥ የአራጣ ብጤ ብቻ ነው በማለታቸው ነው፡፡ ግን መሸጥን አላህ ፈቅዷል፡፡ አራጣንም እርም አድርጓል፡፡ ከጌታውም ግሳጼ የመጣለትና የተከለከለ ሰው ለርሱ (ከመከልከሉ በፊት) ያለፈው አለው፡፡ ነገሩም ወደ አላህ ነው፤ (አራጣን ወደ መብላት) የተመለሰም ሰው እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነርሱ በውስጧ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 2|276|አላህ አራጣን (በረከቱን) ያጠፋል፡፡ ምጽዋቶችንም ያፋፋል፡፡ አላህም ኃጠኢተኛ ከሓዲን ሁሉ አይወድም፡፡ 2|277|እነዚያ ያመኑ፡፡ መልካም ሥራዎችንም የሠሩ፡፡ ሶላትንም ያስተካከሉ፡፡ ዘካንም የሰጡ ለነርሱ በጌታቸው ዘንድ ምንዳቸው አላቸው፡፡ በእነርሱም ላይ ፍርሃት የለባቸውም እነርሱም አያዝኑም፡፡ 2|278|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ፡፡ ከአራጣም የቀረውን ተዉ፡፡ አማኞች እንደኾናችሁ (ተጠንቀቁ)፡፡ 2|279|(የታዘዛችሁትን) ባትሠሩም ከአላህና ከመልክተኛው በኾነች ጦር (መወጋታችሁን) ዕወቁ፡፡ ብትጸጸቱም ለእናንተ የገንዘቦቻችሁ ዋናዎች አሏችሁ፡፡ አትበድሉም አትበደሉምም፡፡ 2|280|የድኽነት ባለቤት የኾነም (ባለዕዳ) ሰው ቢኖር እማግኘት ድረስ ማቆየት ነው፡፡ (በመማር) መመጽወታችሁም ለእናንተ በላጭ ነው፡፡ የምታውቁ ብትኾኑ (ትሠሩታላችሁ)፡፡ 2|281|በእርሱም ውስጥ ወደ አላህ የምትመለሱበትንና ከዚያም እነርሱ የማይበደሉ ሲሆኑ ነፍስ ሁሉ የሠራችውን ሥራ የምትሞላበትን ቀን ተጠንቀቁ፡፡ 2|282|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ በዕዳ በተዋዋላችሁ ጊዜ ጻፉት፡፡ ጸሐፊም በመካከላችሁ በትክክል ይጻፍ፡፡ ጸሐፊም አላህ እንደ አሳወቀው መጻፍን እንቢ አይበል፡፡ ይጻፍም፡፡ ያም በርሱ ላይ ዕዳው ያለበት ሰው በቃሉ ያስጽፍ፡፡ አላህንም ጌታውን ይፍራ፡፡ ከእርሱም (ካለበት ዕዳ) ምንንም አያጉድል፡፡ ያም በርሱ ላይ ዕዳው ያለበት ቂል፣ ወይም ደካማ፣ ወይም በቃሉ ማስጻፍን የማይችል ቢኾን ዋቢው በትክክል ያስጽፍለት፡፡ ከወንዶቻችሁም ሁለትን ምስክሮች አስመስክሩ፡፡ ሁለትም ወንዶች ባይኾኑ ከምስክሮች ሲኾኑ ከምትወዱዋቸው የኾኑን አንድ ወንድና አንደኛዋ ስትረሳ አንደኛይቱ ሌላዋን ታስታውሳት ዘንድ ሁለት ሴቶች (ይመስክሩ)፡፡ ምስክሮችም በተጠሩ ጊዜ እንቢ አይበሉ፡፡ (ዕዳው) ትንሽ ወይም ትልቅ ቢኾንም እስከ ጊዜው ድረስ የምትጽፉት ከመኾን አትሰልቹ፡፡ እንዲህ ማድረጋችሁ አላህ ዘንድ በጣም ትክክል ለምስክርነትም አረጋጋጭ ላለመጠራጠራችሁም በጣም ቅርብ ነው፡፡ ግን በመካከላችሁ እጅ በጅ የምትቀባበሏት ንግድ ብትኾን ባትጽፉዋት በናንተ ላይ ኃጢኣት የለባችሁም፡፡ በተሻሻጣችሁም ጊዜ አስመስክሩ፡፡ ጸሐፊም ምስክርም (ባለ ጉዳዩ ጋር) አይጎዳዱ፡፡ (ይህንን) ብትሠሩም እርሱ በእናንተ (የሚጠጋ) አመጽ ነው፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህም ያሳውቃችኋል፡፡ አላህም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|283|በጉዞም ላይ ብትኾኑና ጸሐፊን ባታገኙ የተጨበጡ መተማመኛዎችን ያዙ፡፡ ከፊላችሁም ከፊሉን ቢያምን ያ የታመነው ሰው አደራውን ያድርስ፡፡ አላህንም ጌታውን ይፍራ፡፡ ምስክርነትንም አትደብቁ፡፡ የሚደብቃትም ሰው እርሱ ልቡ ኃጢኣተኛ ነው፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 2|284|በሰማያት ውስጥና በምድርም ውስጥ ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ በነፍሶቻችሁ ውስጥ ያለውን ብትገልጹ ወይም ብትደብቁት አላህ በርሱ ይቆጣጠራችኋል፡፡ ለሚሻውም ሰው ይምራል፡፡ የሚሻውንም ሰው ይቀጣል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 2|285|መልክተኛው ከጌታው ወደ ርሱ በተወረደው አመነ፡፡ ምእምኖቹም (እንደዚሁ)፡፡ ሁሉም በአላህ፣ በመላዕክቱም፣ በመጻሕፍቱም፣ በመልክተኞቹም ከመልክተኞቹ «በአንድም መካከል አንለይም» (የሚሉ ሲኾኑ) አመኑ፡፡ «ሰማን፤ ታዘዝንም፡፡ ጌታችን ሆይ! ምሕረትህን (እንሻለን)፡፡ መመለሻም ወዳንተ ብቻ ነው» አሉም፡: 2|286|አላህ ነፍስን ከችሎታዋ በላይ አያስገድዳትም፡፡ ለርስዋ የሠራችው አላት፡፡ በርስዋም ላይ ያፈራችው (ኀጢአት) አለባት፡፡ (በሉ)፡- ጌታችን ሆይ! ብንረሳ ወይም ብንስት አትያዘን፤ (አትቅጣን)፡፡ ጌታችን ሆይ! ከባድ ሸክምን ከእኛ በፊት በነበሩት ላይ እንደጫንከው በእኛ ላይ አትጫንብን፡፡ ጌታችን ሆይ! ለኛም በርሱ ችሎታ የሌለንን ነገር አታሸክመን፡፡ ከእኛም ይቅርታ አድርግ ለእኛም ምሕረት አድርግ፡፡ እዘንልንም፤ ዋቢያችን አንተ ነህና፡፡ በከሓዲዎች ሕዝቦች ላይም እርዳን፡፡ 3|1|አ.ለ.መ (አሊፍ ላም ሚም)፤ 3|2|አላህ ከርሱ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ (እርሱ) ሕያው ሁሉን ነገር አስተናባሪ ነው፡፡ 3|3|ከርሱ በፊት ያሉትን መጻሕፍት የሚያረጋግጥ ሲኾን መጽሐፉን (ቁርኣንን) ባንተ ላይ ከፋፍሎ በእውነት አወረደ፡፡ ተውራትንና ኢንጂልንም አውርዷል፡፡ 3|4|(ከቁርኣን) በፊት ለሰዎች መሪ አድርጎ (አወረዳቸው)፡፡ ፉርቃንንም አወረደ፡፡ እነዚያ በአላህ ተዓምራቶች የካዱ ለእነርሱ ብርቱ ቅጣት አላቸው፡፡ አላህም አሸናፊ የመበቀል ባለቤት ነው፡፡ 3|5|አላህ በምድርም በሰማይም ምንም ነገር በርሱ ላይ አይሰወርም፡፡ 3|6|እርሱ ያ በማሕጸኖች ውስጥ እንደሚሻ አድርጎ የሚቀርጻችሁ ነው፡፡ ከእርሱ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 3|7|እርሱ ያ በአንተ ላይ መጽሐፉን ያወረደ ነው፡፡ ከእርሱ (ከመጽሐፉ) ግልጽ የኾኑ አንቀጾች አልሉ፡፡ እነሱ የመጽሐፉ መሠረቶች ናቸው፡፡ ሌሎችም ተመሳሳዮች አልሉ፡፡ እነዚያማ በልቦቻቸው ውስጥ ጥመት ያለባቸው ሰዎች ማሳሳትን ለመፈለግና ትችቱን ለመፈለግ ከርሱ የተመሳሰለውን ይከታተላሉ፡፡ (ትክክለኛ) ትችቱንም አላህ ብቻ እንጅ ሌላ አያውቀውም፡፡ በዕውቀትም የጠለቁት «በርሱ አምነናል፤ ሁሉም ከጌታችን ዘንድ ነው» ይላሉ፡፡ የአእምሮ ባለቤቶችም እንጅ (ሌላው) አይገሰጽም፡፡ 3|8|(እነሱም ይላሉ)፡- «ጌታችን ሆይ! ቅኑን መንገድ ከመራኸን በኋላ ልቦቻችንን አታዘምብልብን፡፡ ከአንተ ዘንድ የኾነን ችሮታም ለኛ ስጠን፡፡ አንተ በጣም ለጋስ ነህና፡፡» 3|9|«ጌታችን ሆይ! አንተ በርሱ (ለመምጣቱ) ጥርጥር የሌለበት በኾነ ቀን ሰውን ሁሉ ሰብሳቢ ነህ፡፡ ምንጊዜም አላህ ቀጠሮውን አያፈርስምና፡፡» 3|10|እነዚያ የካዱት ሰዎች ገንዘቦቻቸውና ልጆቻቸው ከአላህ (ቅጣት) ምንም አያስጥሉዋቸውም፡፡ እነዚያም እነርሱ የእሳት ማገዶዎች ናቸው፡፡ 3|11|(ልማዳቸው ሁሉ) እንደፈርዖን ቤተሰብና እንደእነዚያ ከበፊታቸው እንደነበሩት ሕዝቦች ልማድ ነው፡፡ በአንቀጾቻችን አስተባበሉ፡፡ አላህም በኃጢአቶቻቸው ያዛቸው፡፡ አላህም ቅጣተብርቱ ነው፡፡ 3|12|ለእነዚያ ለካዱት ሰዎች በላቸው፡- «በቅርብ ጊዜ ትሸነፉላችሁ፡፡ ወደ ገሀነምም ትሰበሰባላችሁ፡፡ ምንጣፊቱም ምን ትከፋ!» 3|13|(የበድር ቀን) በተጋጠሙት ሁለት ጭፍሮች ለናንተ በእርግጥ ተዓምር አልለ፡፡ አንደኛዋ ጭፍራ በአላህ መንገድ ትጋደላለች፡፡ ሌላይቱም ከሓዲ ናት፡፡ ከሓዲዎቹ (አማኞቹን) በዓይን አስተያየት እጥፋቸውን ኾነው ያዩዋቸዋል፡፡ አላህም በርዳታው የሚሻውን ሰው ያበረታል፡፡ በዚህ ውስጥ ለማስተዋል ባለቤቶች በእርግጥ መገሰጫ አለበት፡፡ 3|14|ከሴቶች፣ ከወንዶች ልጆችም፣ ከወርቅና ከብር፣ ከተካመቹ ገንዘቦችም፣ ከተሰማሩ ፈረሶችም፣ ከግመል ከከብትና ከፍየልም፣ ከአዝመራም የኾኑ ፍላጎቶችን መውደድ ለሰዎች ተሸለመ፡፡ ይህ ሁሉ የቅርቢቱ ሕይወት መጠቀሚያ ነው፡፡ አላህም እርሱ ዘንድ መልካም መመለሻ (ገነት) አለ፡፡ 3|15|«ከዚህ ሁሉ ነገር የሚበልጥን ልንገራችሁን» በላቸው፡፡ (እርሱም) «ለእነዚያ ለተጠነቀቁት ሰዎች በጌታቸው ዘንድ በሥራቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶች በውስጧ ሁልጊዜ ነዋሪዎች ሲኾኑ ንጹሕ የተደረጉ ሚስቶችም፣ ከአላህም የኾነ ውዴታ አላቸው፡፡ አላህም ባሮቹን ተመልካች ነው፡፡» 3|16|(እነርሱም) እነዚያ፡- «ጌታችን ሆይ! እኛ አመንን ኀጢአቶቻችንንም ለእኛ ማር፤ የእሳትንም ቅጣት ጠብቀን» የሚሉ ናቸው፡፡ 3|17|ታጋሾች እውነተኞችም ታዛዦችም ለጋሶችና በሌሊት መጨረሻዎች ምሕረትን ለማኞች ናቸው፡፡ 3|18|አላህ በማስተካከል የቆመ (አስተናባሪ) ሲኾን ከእርሱ በስተቀር ሌላ አምላክ የሌለ መኾኑን መሰከረ፡፡ መላእክቶችና የዕውቀት ባለቤቶችም (እንደዚሁ መሰከሩ)፡፡ ከእርሱ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 3|19|አላህ ዘንድ (የተወደደ) ሃይማኖት ኢስላም ብቻ ነው፡፡ እነዚያም መጽሐፉን የተሰጡት ሰዎች በመካከላቸው ላለው ምቀኝነት ዕውቀቱ ከመጣላቸው በኋላ እንጅ አልተለያዩም፡፡ በአላህም አንቀጾች የሚክድ አላህ ምርመራው ፈጣን ነው፡፡ 3|20|ቢከራከሩህም፡- «ፊቴን ለአላህ ሰጠሁ፤ የተከተሉኝም ሰዎች (እንደዚሁ ለአላህ ሰጡ)» በላቸው፡፡ ለእነዚያም መጽሐፍን ለተሰጡት ሰዎችና ለመሐይሞቹ፡- «ሰለማችሁን» በላቸው፡፡ ቢሰልሙም በእርግጥ ተመሩ፡፡ እምቢ ቢሉም በአንተ ላይ ያለብህ ማድረስ ብቻ ነው፡፡ አላህም ባሮቹን ተመልካች ነው፡፡ 3|21|እነዚያ በአላህ አንቀጾች የሚክዱ ነቢያትንም ያለ አግባብ የሚገድሉ ከሰዎችም ውስጥ እነዚያን በትክክለኛነት የሚያዙትን የሚገድሉ በአሳማሚ ቅጣት አብስራቸው፡፡ 3|22|እነዚያ በቅርቢቱና በመጨረሻይቱ ዓለም ሥራዎቻቸው የተበላሹ ናቸው፡፡ ለእነርሱም ምንም ረዳቶች የሏቸውም፡፡ 3|23|ወደ እነዚያ ከመጽሐፉ (ትምህርት) ዕድልን ወደ ተሰጡት ሰዎች አላየህምን ወደ አላህ መጽሐፍ በመካከላቸው ይፈርድ ዘንድ ይጠራሉ፡፡ ከዚያም ከእነሱ ገሚሶቹ እነርሱ (እውነቱን) የተዉ ኾነው ይሸሻሉ፡፡ 3|24|ይኸ እነርሱ «እሳት የተቆጠሩ ቀኖችን እንጅ አትነካንም» በማለታቸው ነው፡፡ በሃይማኖታቸውም ይቀጣጥፉት የነበሩት ነገር አታለላቸው፡፡ 3|25|በርሱ (መምጣት) ጥርጥር የሌለበት በኾነው ቀን በሰበሰብናቸውና ነፍስ ሁሉ የሠራችውን ሥራ በተሞላች ጊዜ እንዴት ይኾናሉ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 3|26|(ሙሐመድ ሆይ!) በል፡- «የንግስና ባለቤት የኾንክ አላህ ሆይ! ለምትሻው ሰው ንግሥናን ትሰጣለህ፡፡ ከምትሻውም ሰው ንግሥናን ትገፍፋለህ፡፡ የምትሻውንም ሰው ታልቃለህ፡፡ የምትሻውንም ሰው ታዋርዳለህ፡፡ መልካም ነገር ሁሉ በእጅህ (በችሎታህ) ነው፤ አንተ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነህና፡፡» 3|27|ሌሊቱን በቀን ውስጥ ታስገባለህ፡፡ ቀኑንም በሌሊቱ ውስጥ ታስገባለህ፡፡ ሕያውንም ከሙት ውስጥ ታወጣለህ፡፡ ሙትንም ከሕያው ውስጥ ታወጣለህ፡፡ ለምትሻውም ሰው ያለግምት ትሰጣለህ፡፡ 3|28|ምእምናን ከሓዲዎችን ከምእምናን ሌላ ረዳቶች አድርገው አይያዙ፡፡ ይኼንንም የሚሠራ ሰው ከአላህ (ሃይማኖት) በምንም ውስጥ አይደለም፡፡ ከእነርሱ መጥጠበቅን ብትጠበቁ እንጂ፡፡ አላህም ነፍሱን (ቁጣውን) ያስጠነቅቃችኋል፡፡ መመለሻም ወደ አላህ ብቻ ነው፡፡ 3|29|«በደረቶቻችሁ ውስጥ ያለውን ነገር ብትደብቁ ወይም ብትገልፁት አላህ ያውቀዋል፡፡ በሰማያት ያለውንና በምድርም ያለውን ሁሉ ያውቃል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው» (በል)፡፡ 3|30|ነፍስ ሁሉ ከመልካም ነገር የሠራችውን የቀረበ ኾኖ የምታገኝበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ ከመጥፎም የሠራችው በርስዋና በርሱ (በኀጢአትዋ) መካከል በጣም የሰፋ ርቀት ቢኖር ትመኛለች፡፡ አላህ ነፍሱን ያስጠነቅቃችኋል፡፡ አላህም ለባሮቹ ሩኅሩኅ ነው፡፡ 3|31|በላቸው፡- «አላህን የምትወዱ እንደኾናችሁ ተከተሉኝ፤ አላህ ይወዳችኋልና፡፡ ኀጢኣቶቻችሁንም ለናንተ ይምራልና፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡» 3|32|«አላህንና መልክተኛውን ታዘዙ፡፡ ብትሸሹም አላህ ከሓዲዎችን አይወድም» በላቸው፡፡ 3|33|አላህ አደምን፣ ኑሕንም፣ የኢብራሂምንም ቤተሰብ፣ የዒምራንንም ቤተሰብ በዓለማት ላይ መረጠ፡፡ 3|34|ከፊልዋ ከከፊሉ የኾነች ዝርያ አድርጎ (መረጣት)፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 3|35|የዒምራን ባለቤት (ሐና) «ጌታዬ ሆይ! እኔ በሆዴ ውስጥ ያለውን (ፅንስ ከሥራ) ነጻ የተደረገ ሲኾን ለአንተ ተሳልኩ፡፡ ከእኔም ተቀበል አንተ ሰሚው ዐዋቂው ነህና» ባለች ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 3|36|በወለደቻትም ጊዜ፡- «ጌታዬ ሆይ! እኔ ሴት ኾና ወለድኋት፡፡» አላህም የወለደችውን ዐዋቂ ነው፡፡ «ወንድም እንደ ሴት አይደለም፡፡ እኔም መርየም ብዬ ስም አወጣሁላት፡፡ እኔም እስዋንም ዝርያዋንም ከተረገመው ሰይጣን በአንተ እጠብቃቸዋለሁ» አለች፡፡ 3|37|ጌታዋም በደህና አቀባበል ተቀበላት፡፡ በመልካም አስተዳደግም አፋፋት፡፡ ዘከሪያም አሳደጋት፤ ዘከሪያ በርሷ ላይ በምኹራቧ በገባ ቁጥር እርስዋ ዘንድ ሲሳይን አገኘ፡፡ «መርየም ሆይ! ይህ ለአንቺ ከየት ነው» አላት፡፡ «እርሱ ከአላህ ዘንድ ነው፡፡ አላህ ለሚሻው ሰው ሲሳዩን ያለ ድካም ይሰጣል» አለችው፡፡ 3|38|እዚያ ዘንድ ዘከሪያ ጌታውን ለመነ፡፡ «ጌታዬ ሆይ! ከአንተ ዘንድ መልካም ዘርን ለኔ ስጠኝ አንተ ጸሎትን ሰሚነህና» አለ፡፡ 3|39|እርሱም በጸሎት ማድረሻው ክፍል ቆሞ ሲጸልይ መላእክት ጠራችው፡፡ «አላህ በየሕያ ከአላህ በኾነ ቃል የሚያረጋግጥ ጌታም ድንግልም ከደጋጎቹ ነቢይም ሲኾን ያበስርሃል» በማለት (መላእክት ጠራችው)፡፡ 3|40|«ጌታዬ ሆይ! እኔ እርጅና በእርግጥ የደረሰብኝ ስኾን ባልተቤቴም መሐን ስትሆን ለእኔ እንዴት ልጅ ይኖረኛል አለ፡፡ (መልአኩም) እንደዚሁ አላህ የሚሻውን ነገር ይሠራል» አለው፡፡ 3|41|«ጌታዬ ሆይ! ለእኔ ምልክትን አድርግልኝ» አለ፡፡ «ምልክትህ ሦስት ቀን በጥቅሻ ቢኾን እንጅ ሰዎችን አለማናገርህ ነው፡፡ ጌታህንም በብዙ አውሳ፡፡ በማታና በጧትም አወድሰው» አለው፡፡ 3|42|መላእክትም ያሉትን (አስታውስ)፡፡ «መርየም ሆይ! አላህ በእርግጥ መረጠሸ፡፡ አነጻሽም፡፡ በዓለማት ሴቶችም ላይ መረጠሽ፡፡» 3|43|«መርየም ሆይ! ለጌታሽ ታዘዢ፡፡ ስገጂም፡፡ ከአጎንባሾቹም ጋር አጎንብሺ፡፡» 3|44|ይኸ ወደ አንተ የምናወርደው የኾነ ከሩቅ ወሬዎች ነው፡፡ መርየምንም ማን እንደሚያሳድግ ብርኦቻቸውን (ለዕጣ) በጣሉ ጊዜ እነሱ ዘንድ አልነበርክም፡፡ በሚከራከሩም ጊዜ እነሱ ዘንድ አልነበርክም፡፡ 3|45|መላእክት ያሉትን (አስታውስ)፡- «መርየም ሆይ! አላህ ከርሱ በኾነው ቃል ስሙ አልመሲሕ ዒሳ የመርየም ልጅ በዚህ ዓለምና በመጨረሻውም ዓለም የተከበረ ከባለሟሎችም በኾነ (ልጅ) ያበስርሻል፡፡» 3|46|«በሕፃንነቱና በከፈኒሳነቱ ሰዎቹን ያነጋግራል፡፡ ከመልካሞቹም ነው» (አላት)፡፡ 3|47|፡-ጌታዬ ሆይ! ሰው ያልነካኝ ስኾን ለኔ እንዴት ልጅ ይኖረኛል አለች፡፡ ነገሩ እንዳልሽው ነው፡፡ አላህ የሚሻውን ይፈጥራል፡፡ አንዳችን በሻ ጊዜ ለርሱ ኹን ይለዋል፤ ወዲውኑም ይኾናል አላት፡፡ 3|48|ጽሕፈትንና ጥበብንም ተውራትንና ኢንጂልንም ያስተምረዋል፡፡ 3|49|ወደ እስራኤልም ልጆች መልክተኛ ያደርገዋል፡፡ (ይላልም)፡- «እኔ ከጌታዬ ዘንድ በተዓምር ወደ እናንተ መጣሁ፡፡ እኔ ለናንተ ከጭቃ እንደ ወፍ ቅርፅ እፈጥራለሁ፡፡ በርሱም እተነፍስበታለሁ፡፡ በአላህም ፈቃድ ወፍ ይኾናል፡፡ በአላህም ፈቃድ ዕውር ኾኖ የተወለደን፣ ለምጸኛንም አድናለሁ፡፡ ሙታንንም አስነሳለሁ፡፡ የምትበሉትንና በቤታችሁ የምታደልቡትንም ሁሉ እነግራችኋለሁ፡፡ የምታምኑ እንደኾናችሁ ለእናንተ በዚህ ውስጥ በእርግጥ ተዓምር አለበት፡፡» 3|50|«ከተውራትም ከእኔ በፊት ያለውን ያረጋገጥሁ ስኾን የዚያንም በእናንተ ላይ እርም የተደረገውን ከፊል ለእናንተ እፈቅድ ዘንድ (መጣኋችሁ) ከጌታችሁም በኾነ ታምር መጣሁዋችሁ፡፡ አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም፡፡» 3|51|«አላህ ጌታዬና ጌታችሁ ነው፤ ስለዚህ ተገዙት፤ ይህ ቀጥተኛ መንገድ ነው» (አላቸው)፡፡ 3|52|ዒሳ ከነርሱ ክህደት በተሰማውም ጊዜ፡- «ወደ አላህ (ተጨምረው) ረዳቶቼ እነማን ናቸው» አለ፤ ሐዋርያት፡- «እኛ የአላህ ረዳቶች ነን፤ በአላህ አምነናል፤ እኛም ትክክለኛ ታዛዦች መኾናችንን መስክር» አሉ፡፡ 3|53|«ጌታችን ሆይ! ባወረድኸው አመንን፤ መልክተኛውንም ተከተልን፤ ከመስካሪዎችም ጋር መዝግበን» (አሉ)፡፡ 3|54|(አይሁዶችም) አደሙ አላህም አድማቸውን መለሰባቸው፡፡ አላህም ከአድመኞች ሁሉ በላጭ ነው፡፡ 3|55|አላህም ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ዒሳ ሆይ! እኔ ወሳጂህ ወደ እኔም አንሺህ ነኝ፡፡ ከነዚያም ከካዱት ሰዎች አጥሪህ ነኝ እነዚያንም የተከተሉህን እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ ከነዚያ ከካዱት በላይ አድራጊ ነኝ፡፡ ከዚያም መመለሻችሁ ወደእኔ ነው፡፡ በርሱ ትለያዩበትም በነበራችሁት ነገር በመካከላችሁ እፈርዳለሁ፡፡ 3|56|«እነዚያማ የካዱትን ሰዎች በቅርቢቱ ዓለምና በመጨረሻይቱ ዓለም ብርቱን ቅጣት እቀጣቸዋለሁ፡፡ ለእነርሱም ምንም ረዳቶች የሏቸውም፡፡» 3|57|እነዚያም ያመኑትማ መልካም ሥራዎችንም የሠሩት ምንዳዎቻቸውን ይሞላላቸዋል፡፡ አላህም በዳዮችን አይወድም፡፡ 3|58|ይህ ከተዓምራቶችና ጥበብን ከያዘው ተግሳጽ ሲኾን በአንተ ላይ እናነበዋለን፡፡ 3|59|አላህ ዘንድ የዒሳ ምሳሌ እንደ አዳም ብጤ ነው፡፡ ከዐፈር ፈጠረው፡፡ ከዚያም ለርሱ (ሰው) «ኹን» አለው፤ ኾነም፡፡ 3|60|ይህ ከጌታህ ዘንድ የኾነ እውነት ነው፡፡ ከተጠራጣሪዎቹም አትኹን፡፡ 3|61|ዕውቀቱም ከመጣልህ በኋላ በርሱ (በዒሳ) የተከራከሩህን ሰዎች «ኑ፤ ልጆቻችንንና ልጆቻችሁን፣ ሴቶቻችንንና ሴቶቻችሁንም፣ ነፍሶቻችንንና ነፍሶቻችሁንም እንጥራ፡፡ ከዚያም አጥብቀን አላህን እንለምን፤ የአላህንም ቁጣ በውሸታሞቹ ላይ እናድርግ» በላቸው፡፡ 3|62|ይህ እርሱ በእርግጥ እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ አምላክም ከአላህ በስተቀር ምንም የለም፡፡ አላህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 3|63|(ከማመን) እንቢ ቢሉም አላህ አጥፊዎቹን በእርግጥ ዐዋቂ ነው፡፡ 3|64|የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! በእኛና በእናንተ መካከል ትክክል ወደ ኾነች ቃል ኑ፡፡ (እርሷም) አላህን እንጅ ሌላን ላንገዛ፣ በርሱም ምንንም ላናጋራ፣ ከፊላችንም ከፊሉን ከአላህ ሌላ አማልክት አድርጎ ላይይዝ ነው፤ በላቸው፡፡ እምቢ ቢሉም፡- እኛ ሙስሊሞች መኾናችንን መስክሩ በሏቸው፡፡ 3|65|እናንተ የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! በኢብራሂም ለምን ትከራከራላችሁ ተውራትና ኢንጂልም ከርሱ በኋላ እንጅ አልተወረዱም፡፡ ልብ አታደርጉምን በላቸው፡፡ 3|66|ንቁ! እናንተ እነዚያ ለእናንተ በርሱ ዕውቀት ባላችሁ ነገር የተከራከራችሁ ናችሁ፡፡ ታዲያ ለእናንተ በርሱ ዕውቀት በሌላችሁ ነገር ለምን ትከራከራላችሁ አላህም ያውቃል፡፡ እናንተ ግን አታውቁም፡፡ 3|67|ኢብራሂም ይሁዳዊም ክርስቲያንም አልነበረም፡፡ ግን ወደ ቀጥተኛው ሃይማኖት የተዘነበለ ሙስሊም ነበረ፡፡ ከአጋሪዎችም አልነበረም፡፡ 3|68|ከሰው ሁሉ በኢብራሂም ተገቢዎቹ እነዚያ የተከተሉትና ይህ ነቢይ እነዚያም ያመኑት ናቸው፡፡ አላህም የምእምናን ረዳት ነው፡፡ 3|69|ከመጽሐፉ ባለቤቶች የኾኑ ጭፍሮች ነፍሶቻቸውን እንጂ የማያሳስቱ ሲኾኑ ሊያሳስቱዋችሁ ተመኙ ግን አያውቁም፡፡ 3|70|የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! እናንተ የምታውቁ ስትኾኑ በአላህ አንቀጾች ለምን ትክዳላችሁ 3|71|«የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! እውነቱን በውሸት ለምን ትቀላቅላላችሁ እውነቱንም እናንተ የምታውቁ ስትኾኑ ለምን ትደብቃላችሁ» 3|72|ከመጽሐፉ ባለቤቶች የኾኑ ጭፍሮችም አሉ፡- «በነዚያ በአመኑት ላይ በተወረደው (ቁርኣን) በቀኑ መጀመሪያ ላይ እመኑበት፡፡ በመጨረሻውም ካዱት፡፡ እነርሱ ሊመለሱ ይከጀላልና፡፡» 3|73|እናንተ የተሰጣችሁትን ብጤ አንድም ሰው መሰጠቱን ወይም እጌታችሁ ዘንድ የሚከራከሩዋችሁ መኾንን ሃይማኖታችሁን ለተከተለ ሰው ቢኾን እንጂ አትመኑ (አትግለጹ አሉ)፡፡ «መምሪያው የአላህ መምሪያ ብቻ ነው» በላቸው፡፡ «ችሮታ በአላህ እጅ ነው፡፡ ለሚሻው ይሰጠዋል፡፡ አላህም ችሮታው ሰፊ ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 3|74|በችሮታው (በነቢይነት) የሚሻውን ይመርጣል፡፡ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 3|75|ከመጽሐፉ ሰዎችም በብዙ ገንዘብ ብታምነው ወዳንተ የሚመልስ ሰው አልለ፡፡ ከእነሱም በአንድ ዲናር እንኳ ብታምነው፤ ሁል ጊዜ በርሱ ላይ የምትጠባበቅ ካልኾንክ በስተቀር የማይመልስ ሰው አልለ፡፡ «ይህ በመሃይምናን (በምናደርገው) በእኛ ላይ ምንም መንገድ የለብንም» ስለሚሉ ነው፡፡ እነርሱ እያወቁም በአላህ ላይ ውሸትን ይናገራሉ፡፡ 3|76|አይደለም (አለባቸው እንጅ)፡፡ በቃል ኪዳኑ የሞላና የተጠነቀቀ ሰው አላህ ጥንቁቆችን ይወዳል፡፡ 3|77|እነዚህ በአላህ ቃል ኪዳንና በመሐላዎቻቸው ጥቂትን ዋጋ የሚለውጡ እነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም ምንም ዕድል የላቸውም፡፡ በትንሣኤ ቀንም አላህ አያነጋግራቸውም፡፡ ወደ እነርሱም አይመለከትም አያነጻቸውምም፡፡ ለነሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 3|78|ከእነሱም እርሱ ከመጽሐፉ ያይደለ ሲኾን ከመጽሐፉ መኾኑን እንድታስቡ በመጽሐፉ ምላሶቻቸውን የሚያጣምሙ ክፍሎች አሉ፡፡ እርሱ ከአላህ ዘንድ ያልኾነ ሲኾን «እርሱ ከአላህ ዘንድ ነውም» ይላሉ፡፡ እነርሱ የሚያውቁ ሲኾኑም በአላህ ላይ ውሸትን ይናገራሉ፡፡ 3|79|ለማንም ሰው አላህ መጽሐፍንና ጥበብን ነቢይነትንም ሊሰጠውና ከዚያም ለሰዎች «ከአላህ ሌላ ለእኔ ባሮች ኾኑ» ሊል አይገባውም፡፡ «ግን መጽሐፍን የምታስተምሩ በነበራችሁትና የምታጠኑም በነበራችሁት በዕውቀታችሁ ሠሪዎች ኹኑ» (ይላቸዋል)፡፡ 3|80|መላእክትንና ነቢያትንም አማልክቶች አድርጋችሁ እንድትይዙ ሊያዛችሁ (አይገባውም)፡፡ እናንተ ሙስሊሞች ከኾናችሁ በኋላ በክህደት ያዛችኋልን 3|81|አላህ የነቢያትን ቃል ኪዳን ከመጽሐፍና ከጥበብ ሰጥቻችሁ ከዚያም «ከእናንተ ጋር ላለው (መጽሐፍ) የሚያረጋግጥ መልክተኛ ቢመጣላችሁ በርሱ በእርግጥ እንደምታምኑበት በእርግጥም እንድትረዱት ሲል በያዘ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ አረጋገጣችሁን በዚህም ላይ ኪዳኔን ያዛችሁምን» አላቸው፡፡ «አረጋገጥን» አሉ፡፡ «እንግዲያስ መስክሩ፤ እኔም ከእናንተ ጋር ከመስካሪዎቹ ነኝ» አላቸው፡፡ 3|82|ከዚህም በኋላ የሸሹ ሰዎች እነዚያ እነሱ አመጸኞቹ ናቸው፡፡ 3|83|በሰማያትና በምድር ያሉ ሁሉ፤ በውድም በግድም ለርሱ የታዘዙ ወደርሱም የሚመለሱ ሲኾኑ (ከሓዲዎች) ከአላህ ሃይማኖት ሌላን ይፈልጋሉን 3|84|«በአላህ አመንን፡፡ በእኛ ላይ በተወረደውም (በቁርኣን)፣ በኢብራሂምና በኢስማዒልም፣ በኢስሓቅም፣ በያዕቆብም፣ በነገዶችም ላይ በተወረደው፤ ለሙሳና ለዒሳም ለነቢያትም ሁሉ ከጌታቸው በተሰጠው (አመንን)፡፡ ከእነርሱ መካከል አንድንም አንለይም፡፡ እኛ ለእርሱ ታዛዦች ነን» በል፡፡ 3|85|ከኢስላም ሌላ ሃይማኖትን የሚፈልግ ሰው ፈጽሞ ከርሱ ተቀባይ የለውም፡፡ እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከከሳሪዎቹ ነው፡፡ 3|86|ከእምነታቸውና መልክተኛውም እውነት መኾኑን ከመሰከሩ የተብራሩ አንቀጾችም ከመጡላቸው በኋላ የካዱን ሕዝቦች አላህ እንዴት ያቀናል! አላህ በዳዮችንም ሕዝቦች አያቀናም፡፡ 3|87|እነዚያ ቅጣታቸው የአላህና የመላእክት የሰዎችም ሁሉ ርግማን በእነሱ ላይ መኾን ነው፡፡ 3|88|በውስጧ ዘውታሪዎች ሲኾኑ ቅጣቱም ከነሱ ላይ አይቃለልላቸውም፡፡ እነሱም ቀን አይስሰጡም፡፡ 3|89|እነዚያ ከዚህ በኋላ ንስሓ የገቡና (ሥራቸውን) ያሳመሩ ሲቀሩ፡፡ (እነዚህንስ ይምራቸዋል)፤ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 3|90|እነዚያ ከእምነታቸው በኋላ የካዱ ከዚያም ክህደትን የጨመሩ ጸጸታቸው ፈጽሞ ተቀባይ የላትም፡፡ እነዚያም የተሳሳቱ እነርሱ ናቸው፡፡ 3|91|እነዚያ የካዱና እነርሱም በክህደታቸው ላይ እንዳሉ የሞቱ ከእነሱ ከአንዳቸው በምድር ሙሉ የኾነ ወርቅ (ቢኖረውና) በርሱ ቢበዥበትም እንኳ ፈጽሞ ተቀባይን አያገኝም፡፡ እነዚያ ለእነርሱ የሚያሰቃይ ቅጣት አላቸው፡፡ ለነርሱም ምንም ረዳቶች የሏቸውም፡፡ 3|92|የምትወዱትን እስከምትለግሱ ድረስ በጎን ሥራ (ዋጋውን) አታገኙም፡፡ ከምንም ነገር ብትለግሱ አላህ ያውቀዋል፡፡ 3|93|ተውራት ከመወረድዋ በፊት እስራኤል በራሱ ላይ እርም ካደረገው ነገር በስተቀር ምግብ ሁሉ ለእስራኤል ልጆች የተፈቀደ ነበር፡፡ እውነተኞችም እንደኾናችሁ ተውራትን አምጡ አንብቡዋትም በላቸው፡፡ 3|94|ከዚህም በኋላ በአላህ ላይ ውሸትን የቀጣጠፉ ሰዎች እነዚያ እነርሱ በደለኞች ናቸው፡፡ 3|95|«አላህ እውነትን ተናገረ፡፡ የኢብራሂምንም መንገድ ወደ እውነት ያዘነበለ ሲኾን ተከተሉ፡፡ ከአጋሪዎቹም አልነበረም» በላቸው፡፡ 3|96|ለሰዎች (መጸለያ) መጀመሪያ የተኖረው ቤት ብሩክና ለዓለማት ሁሉ መመሪያ ሲኾን ያ በበካህ (በመካ) ያለው ነው፡፡ 3|97|በውስጡ ግልጽ የኾኑ ተዓምራቶች የኢብራሒምም መቆሚያ አልለ፡፡ ወደ ውስጡ የገባ ሰው ጸጥተኛ ይኾናል፡፡ ለአላህም በሰዎች ላይ ወደርሱ መኼድን በቻለ ሁሉ ላይ ቤቱን መጎብኘት ግዴታ አለባቸው፡፡ የካደም ሰው አላህ ከዓለማት ሁሉ የተብቃቃ ነው፡፡ 3|98|«የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! አላህ በምትሠሩት ሁሉ ላይ ዐዋቂ ሲኾን በአላህ ተዓምራት ለምን ትክዳላችሁ» በላቸው፡፡ 3|99|«የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! እናንተ መስካሪዎች ኾናችሁ ከአላህ መንገድ መጥመሟን የምትፈልጓት ስትኾኑ ያመነን ሰው ለምን ትከለክላላችሁ አላህም ከምትሰሩት ነገር ሁሉ ዘንጊ አይደለም» በላቸው፡፡ 3|100|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከነዚያ መጽሐፉን ከተሰጡት ሰዎች ከፊሉን ብትታዘዙ ከእምነታችሁ በኋላ ከሓዲዎች አድርገው ይመልሱዋችኋል፡፡ 3|101|የአላህም አንቀጾች በእናንተ ላይ የሚነበቡ ሲኾኑ መልክተኛውም በውስጣችሁ ያለ ሲኾን እናንተ እንዴት ትክዳላችሁ በአላህም የሚጠበቅ ሰው ወደ ቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ ተመራ፡፡ 3|102|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ተገቢውን መጠንቀቅ ተጠንቀቁት፡፡ እናንተም ሙስሊሞች ኾናችሁ እንጅ አትሙቱ፡፡ 3|103|የአላህንም (የማመን) ገመድ ሁላችሁም ያዙ፡፡ አትለያዩም፡፡ ጠበኞችም በነበራችሁ ጊዜ በእናንተ ላይ (የዋለውን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ፡፡ በልቦቻችሁም መካከል አስማማ፡፡ በጸጋውም ወንድማማቾች ኾናችሁ፡፡ በእሳት ጉድጓድ አፋፍም ላይ ነበራችሁ፡፡ ከእርስዋም አዳናችሁ፡፡ እንደዚሁ ትመሩ ዘንድ አላህ ለእናንተ አንቀጾቹን ያብራራል፡፡ 3|104|ከናንተም ወደ በጎ ነገር የሚጠሩ በመልካም ሥራም የሚያዙ ከክፉ ነገርም የሚከለክሉ ሕዝቦች ይኑሩ፡፡ እነዚያም እነሱ የሚድኑ ናቸው፡፡ 3|105|እንደነዚያም ግልጽ ተዓምራት ከመጣላቸው በኋላ እንደተለያዩትና እንደ ተጨቃጨቁት አትኹኑ፡፡ እነዚያም ለእነርሱ ታላቅ ቅጣት አላቸው፡፡ 3|106|ፊቶች የሚያበሩበትን ፊቶችም የሚጠቁሩበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ እነዚያ ፊቶቻቸው የጠቆሩትማ «ከእምነታችሁ በኋላ ካዳችሁን ትክዱት በነበራችሁት ነገር ቅጣቱን ቅመሱ» (ይባላሉ)፡፡ 3|107|እነዚያም ፊቶቻቸው ያበሩትማ በአላህ ችሮታ (ገነት) ውስጥ ናቸው፡፡ እነርሱ በውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 3|108|ይህች በአንተ ላይ በእውነት የምናነባት ስትኾን የአላህ ተዓምራት ናት፡፡ አላህም ለዓለማት በደልን የሚሻ አይደለም፡፡ 3|109|በሰማያት ያለውና በምድር ያለውም ሁሉ የአላህ ነው፡፡ ነገሮችም ሁሉ ወደ አላህ ብቻ ይመለሳሉ፡፡ 3|110|ለሰዎች ከተገለጸች ሕዝብ ሁሉ በላጭ ኾናችሁ በጽድቅ ነገር ታዛላችሁ፤ ከመጥፎም ነገር ታዛላችሁ፤ በአላህም (አንድነት) ታምናላችሁ፡፡ የመጽሐፉም ሰዎች ባመኑ ኖሮ ለነርሱ የተሻለ በኾነ ነበር፡፡ ከነርሱ አማኞች አሉ፡፡ አብዛኞቻቸው ግን አመጸኞች ናቸው፡፡ 3|111|ማስከፋትን እንጅ ፈጽሞ አይጎዱዋችሁም፡፡ ቢዋጉዋችሁም ጀርባዎችን ያዙሩላችኋል (ይሸሻሉ)፡፡ ከዚያም አይረዱም፡፡ 3|112|የትም በተገኙበት ስፍራ ከአላህ በኾነ ቃል ኪዳን ከሰዎችም በኾነ ቃል ኪዳን (የተጠበቁ) ካልኾኑ በስተቀር በነርሱ ላይ ውርደት ተመታችባቸው፡፡ ከአላህም በኾነ ቁጣ ተመለሱ፡፡ በእነርሱም ላይ ድኽነት ተመታችባቸው፡፡ ይኸ እነርሱ በአላህ ተዓምራት ይክዱ ስለ ነበሩና ነቢያትንም ያለ ሕግ ይገድሉ ስለነበሩ ነው፡፡ ይህ በማመጻቸውና ወሰንን ይተላለፉ ስለነበሩ ነው፡፡ 3|113|(የመጽሐፉ ሰዎች ሁሉ) እኩል አይደሉም፡፡ ከመጽሐፉ ሰዎች ቀጥ ያሉ በሌሊት ሰዓቶች እነርሱ የሚሰግዱ ኾነው የአላህን አንቀጾች የሚያነቡ ሕዝቦች አሉ፡፡ 3|114|በአላህና በመጨረሻው ቀን ያምናሉ፡፡ በጽድቅ ነገርም ያዛሉ፡፡ ከመጥፎ ነገርም ይከለክላሉ፡፡ በበጎ ሥራዎችም ይጣደፋሉ፡፡ እነዚያም ከመልካሞቹ ናቸው፡፡ 3|115|ከበጎ ሥራ ማንኛውንም ቢሠሩ አይካዱትም፡፡ አላህም ጥንቁቆቹን ዐዋቂ ነው፡፡ 3|116|እነዚያ የካዱት ሰዎች ገንዘቦቻቸውና ልጆቻቸው ከአላህ (ቅጣት) እነርሱን ምንንም አያድኑዋቸውም፡፡ እነዚያም የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነርሱ በእርስዋ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 3|117|የዚያ በዚህች በቅርቢቱ ሕይወት የሚለግሱት ነገር ምሳሌ በውስጧ ውርጭ ያለባት ነፋስ ነፍሶቻቸውን የበደሉን ሕዝቦች አዝመራ እንደነካችና እንዳጠፋችው ብጤ ነው፡፡ አላህም አልበደላቸውም ግን ነፍሶቻቸውን ይበድላሉ፡፡ 3|118|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከእናንተ ሌላ ምስጢረኛን አትያዙ፡፡ ማበላሸትን አይገቱላችሁም፡፡ ጉዳታችሁን ይወዳሉ፡፡ ጥላቻይቱ ከአፎቻቸው በእርግጥ ተገለጸች፡፡ ልቦቻቸውም የሚደብቁት ይበልጥ ትልቅ ነው፡፡ ልብ የምታደርጉ እንደኾናችሁ ለእናንተ ማብራሪያዎችን በእርግጥ ገለጽን፡፡ 3|119|እነሆ እናንተ እነዚያ የምትወዱዋቸው ናችሁ፡፡ (እነሱ) ግን አይወዱዋችሁም፡፡ በመጽሐፉም በሁሉም ታምናላችሁ፡፡ ባገኙዋችሁም ጊዜ «አምነናል» ይላሉ፡፡ ባገለሉም ጊዜ ከቁጭታቸው የተነሳ በእናንተ ላይ ዐጽቆቻቸውን ይነክሳሉ፡፡ «በቁጭታችሁ ሙቱ፤ አላህ ልቦች የቋጠሩትን ዐዋቂ ነውና» በላቸው፡፡ 3|120|ደግ ነገር ብትነካችሁ ታስከፋቸዋለች፡፡ መጥፎም ነገር ብታገኛችሁ በእርሷ ይደሰታሉ፡፡ ብትታገሱና ብትጠነቀቁም ተንኮላቸው ምንም አይጎዳችሁም፡፡ አላህ በሚሠሩት ሁሉ (በዕውቀቱ) ከባቢ ነውና፡፡ 3|121|ለምእምኖቹም ለውጊያ ሥራዎችን የምታዘጋጅ ኾነህ ከቤተሰብህ በማለድክ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 3|122|ከእናንተ ሁለት ጭፍሮች አላህ ረዳታቸው ሲኾን ለመፍራት ባሰቡ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ በአላህም ላይ ብቻ ምእምናኖች ይመኩ፡፡ 3|123|በበድርም እናንተ ጥቂቶች ኾናችሁ ሳለ አላህ በእርግጥ ረዳችሁ፡፡ አላህንም ታመሰግኑ ዘንድ ፍሩት፡፡ 3|124|ለምእምናን «ጌታችሁ በሦስት ሺህ መላእክት የተወረዱ ሲኾኑ ቢረዳችሁ አይበቃችሁምን» በምትል ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 3|125|«አዎን ብትታገሱና ብትጠነቀቁ ከዚህም ፍጥነታቸው (ጠላቶቻችሁ) ቢመጡባችሁ ጌታችሁ ምልክት ባላቸው አምስት ሺህ መላእክት ይረዳችኋል፡፡» 3|126|አላህም (እርዳታውን) ለእናንተ ብስራትና ልቦቻችሁ በእርሱ እንዲረኩ እንጂ አላደረገውም፡፡ ድልም መንሳት አሸናፊ ጥበበኛ ከኾነው አላህ ዘንድ እንጅ ከሌላ አይደለም፡፡ 3|127|(ድልን ያጎናጸፋችሁ) ከእነዚያ ከካዱት ከፊልን ሊቆርጥ (ሊያጠፋ) ወይም ሊያዋርዳቸውና ያፈሩ ኾነው እንዲመለሱ ነው፡፡ 3|128|(አላህ) በእነርሱ ላይ ይቅርታ እስኪያደርግ ወይም እነርሱ በዳዮች ናቸውና እስኪቀጣቸው ድረስ ላንተ ከነገሩ ምንም የለህም፡፡ 3|129|በሰማያት ያለው በምድርም ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው ይምራል፤ የሚሻውንም ሰው ይቀጣል፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 3|130|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አራጣን የተነባበሩ እጥፎች ሲኾኑ አትብሉ፡፡ ትድኑም ዘንድ አላህን ፍሩ፡፡ 3|131|ያችንም ለከሓዲዎች የተደገሰችውን እሳት ተጠንቀቁ፡፡ 3|132|ይታዘንላችሁም ዘንድ አላህንና መልክተኛውን ታዘዙ፡፡ 3|133|ከጌታችሁ ወደ ኾነችም ምሕረትና ስፋትዋ እንደ ሰማያትና ምድር ወደ ኾነች ገነት አላህን ለሚፈሩ የተዘጋጀች ስትኾን ተቻኮሉ፡፡ 3|134|ለእነዚያ በድሎትም ኾነ በችግር ለሚለግሱት፣ ቁጭትንም ገቺዎች ከሰዎችም ይቅርታ አድራጊዎች ለኾኑት (ተደግሳለች)፡፡ አላህም በጎ ሠሪዎችን ይወዳል፡፡ 3|135|ለእነዚያም መጥፎ ሥራን በሠሩ ወይም ነፍሶቻቸውን በበደሉ ጊዜ አላህን የሚያስታውሱና ለኀጢአቶቻቸው ምሕረትን የሚለምኑ ለኾኑት ከአላህም ሌላ ኀጢአቶችን የሚምር አንድም የለ፡፡ (በስሕተት) በሠሩትም ላይ እነርሱ የሚያውቁ ሲኾኑ የማይዘወትሩ ለኾኑት (ተደግሳለች)፡፡ 3|136|እነዚያ ምንዳቸው ከጌታቸው ምሕረትና በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ በሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶችም ናቸው፡፡ የሠሪዎችም ምንዳ (ገነት) ምንኛ አማረች!፡፡ 3|137|ከእናንተ በፊት ድርጊቶች በእርግጥ አልፈዋል፡፡ በምድርም ላይ ኺዱ፡፡ የአስተባባዮችም ፍጻሜ እንዴት እንደነበረ ተመልከቱ፡፡ 3|138|ይህ ለሰዎች ገላጭ፤ ለጥንቁቆች መሪና ገሳጭ ነው፡፡ 3|139|እናንተም የበላዮች ስትኾኑ ምእመናን እንደኾናችሁ አትስነፉ፤ አትዘኑም፡፡ 3|140|ቁስል ቢያገኛችሁ ሰዎቹንም መሰሉ ቁስል አግኝቷቸዋል፡፡ ይኽችንም ቀናት በሰዎች መካከል እናዘዋውራታለን፡፡ (እንድትገሰጹና) አላህም እነዚያን ያመኑትን እንዲያውቅ (እንዲለይ) ከእናንተም ሰማዕታትን እንዲይዝ ነው፡፡ አላህም በዳዮችን አይወድም፡፡ 3|141|አላህም እነዚያን ያመኑትን (ከኀጢአት) ሊያነጻና ከሓዲዎችንም ሊያጠፋ ነው፡፡ 3|142|በእውነቱ አላህ ከናንተ እነዚያን የታገሉትን ሳያውቅ (ሳይለይ) ታጋሾቹንም ሳያውቅ ገነትን ልትገቡ አሰባችሁን 3|143|(በጦርነት ላይ) መሞትንም ሳታገኙት በፊት በርግጥ የምትመኙት ነበራችሁ፡፡ እናንተም የምትመለከቱ ስትኾኑ በርግጥ አያችሁት (ታዲያ ለምን ሸሻችሁ) 3|144|ሙሐመድም ከበፊቱ መልክተኞች በእርግጥ ያለፉ የኾነ መልክተኛ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ ታዲያ ቢሞት ወይም ቢገደል ወደ ኋላችሁ ትገለበጣላችሁን ወደኋላው የሚገለበጥም ሰው አላህን ምንም አይጎዳም፡፡ አላህም አመስጋኞቹን በእርግጥ ይመነዳል፡፡ 3|145|ለማንኛይቱም ነፍስ በአላህ ፍርድ ቢኾን እንጅ ልትሞት አይገባትም፡፡ (ጊዜውም) ተወስኖ ተጽፏል፡፡ የቅርቢቱንም ምንዳ የሚፈልግ ሰው ከእርስዋ እንሰጠዋለን፡፡ የመጨረሻይቱንም ምንዳ የሚፈልግ ሰው ከእርስዋ እንሰጠዋለን፤ አመስጋኞችንም በእርግጥ እንመነዳለን፡፡ 3|146|ከነቢይም ብዙ ሊቃውንት ከርሱ ጋር ኾነው የተዋጉ ብዙ ናቸው፡፡ በአላህም መንገድ ለሚደርስባቸው ነገር አልፈሩም፤ አልደከሙምም፡፡ (ለጠላት) አልተዋረዱምም፡፡ አላህም ትዕግስተኞችን ይወዳል፡፡ 3|147|ንግግራቸውም «ጌታችን ሆይ! ኃጢአቶቻችንንና በነገራችን ሁሉ ወሰን ማለፋችንን ለእኛ ማር፣ ይዞታችንንም አደላድል፣ በከሓዲዎችም ሕዝቦች ላይ እርዳን» ማለታቸው እንጅ ሌላ አልነበረም፡፡ 3|148|አላህም የቅርቢቱን ምንዳና የመጨረሻይቱን መልካም ምንዳ ሰጣቸው፡፡ አላህም በጎ አድራጊዎችን ይወዳል፡፡ 3|149|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እነዚያን የካዱትን ሰዎች ብትታዘዙ ወደ ኋላችሁ ይመልሱዋችኋል፡፡ ከሳሪዎች ኾናችሁም ትገለበጣላችሁ፡፡ 3|150|(አይረዷችሁም)፤ ይልቁን አላህ ብቻ ረዳታችሁ ነው፡፡ እርሱም ከረዳቶች ሁሉ በላጭ ነው፡፡ 3|151|በእነዚያ በካዱት ሰዎች ልቦች ውስጥ አላህ በእርሱ አስረጅ ያላወረደበትን ነገር በአላህ በማጋራታቸው ምክንያት ፍርሃትን እንጥላለን፡፡ መኖሪያቸውም እሳት ናት፡፡ የበዳዮችም መኖሪያ ምን ትከፋ! 3|152|አላህም በፈቃዱ በምትጨፈጭፏቸው ጊዜ ኪዳኑን በእርግጥ አረጋገጠላችሁ፡፡ የምትወዱትንም ነገር ካሳያችሁ በኋላ በፈራችሁ በትዕዛዙም በተጨቃጨቃችሁና ባመጻችሁ ጊዜ (እርዳታውን ከለከላችሁ)፡፡ ከእናንተ ውስጥ ቅርቢቱን ዓለም የሚሻ አለ፡፡ ከእናንተም የመጨረሻይቱን ዓለም የሚሻ አልለ፡፡ ከዚያም ሊሞክራችሁ ከእነርሱ አዞራችሁ፡፡ በእርግጥም ከእናንተ ይቅርታ አደረገላችሁ፡፡ አላህም በምእምናን ላይ የችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 3|153|መልክተኛው ከኋላችሁ የሚጠራችሁ ሲኾን ርቃችሁ በምትሸሹና በአንድም ላይ የማትዞሩ በኾናችሁ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ ባመለጣችሁና በደረሰባችሁም ነገር እንድታዝኑ በሐሳብ ላይ ሐሳብን መነዳችሁ፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 3|154|ከዚያም ከጭንቅ በኋላ ጸጥታን ከእናንተ ከፊሎችን የሚሸፍንን እንቅልፍ በእናንተ ላይ አወረደ፡፡ ከፊሎቹም ነፍሶቻቸው በእርግጥ አሳሰቧቸው፡፡ እውነት ያልኾነውን የመሃይምነትን መጠራጠር በአላህ ይጠራጠራሉ፤ «ከነገሩ ለእኛ ምንም የለንም» ይላሉ፡፡ «ነገሩ ሁሉም ለአላህ ነው» በላቸው፡፡ ለአንተ የማይገልጹትን በነፍሶቻቸው ውስጥ ይደብቃሉ፡፡ «ከነገሩ ለእኛ አንዳች በነበረን ኖሮ እዚህ ባልተገደልን ነበር» ይላሉ፡፡ «በቤታችሁ ውስጥ በኾናችሁም ኖሮ እነዚያ በእነርሱ ላይ መገደል የተጻፈባቸው ወደ መውደቂያቸው በወጡ ነበር» በላቸው፡፡ አላህ (ፍርዱን ሊፈጽምና) በደረቶቻችሁም ውስጥ ያለውን ሊፈትን በልቦቻችሁም ውስጥ ያለውን ነገር ሊገልጽ (ይህን ሠራ)፡፡ አላህም በደረቶች ውስጥ ያለን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 3|155|እነዚያ ሁለቱ ጭፍሮች በተገናኙ ቀን ከእናንተ የሸሹት ሰዎች በዚያ በሠሩት ከፊል ምክንያት ያሳሳታቸው ሰይጣን ነው፡፡ አላህም ከነሱ በእርግጥ ይቅር አለ፡፡ አላህ መሓሪ በቅጣት የማይቸኩል ነውና፡፡ 3|156|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እንደነዚያ እንደ ካዱትና ስለ ወንድሞቻቸው በምድር ላይ በተጓዙ ወይም ዘማቾች በኾኑ ጊዜ «እኛ ዘንድ በነበሩ ኖሮ ባልሞቱም ባልተገደሉም ነበር» እንደሚሉት አትኹኑ፡፡ አላህ ይህንን በልቦቻቸው ውስጥ ጸጸት ያደርግባቸው ዘንድ (ይህንን አሉ)፡፡ አላህም ሕያው ያደርጋል፤ ይገድላልም፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 3|157|በአላህም መንገድ ብትገደሉ ወይም፤ ብትሞቱ ከአላህ የኾነው ምሕረትና እዝነት (እነርሱ) ከሚሰበስቡት ሀብት በእርግጥ በላጭ ነው፡፡ 3|158|ብትሞቱም ወይም ብትገደሉ በእርግጥ ወደ አላህ ብቻ ትሰበሰባላችሁ፡፡ 3|159|ከአላህም በኾነች ችሮታ ለዘብክላቸው፡፡ ዐመለ መጥፎ ልበ ደረቅም በኾንክ ኖሮ ከዙሪያህ በተበተኑ ነበር፡፡ ከእነርሱም ይቅር በል፡፡ ለእነርሱም ምሕረትን ለምንላቸው፡፡ በነገሩም ሁሉ አማክራቸው፡፡ ቁርጥ ሐሳብም ባደረግህ ጊዜ በአላህ ላይ ተመካ፡፡ አላህ በርሱ ላይ ተመኪዎችን ይወዳልና፡፡ 3|160|አላህ ቢረዳችሁ ለእናንተ አሸናፊ የለም፡፡ ቢያዋርዳችሁም ያ ከርሱ (ማዋረድ) በኋላ የሚረዳችሁ ማነው በአላህም ላይ ብቻ ምእምናን ይመኩ፡፡ 3|161|ለነቢይም ሰለባን መደበቅ አይገባውም፡፡ ሰለባንም የሚደብቅ ሰው በትንሣኤ ቀን በደበቀው ነገር (ተሸክሞ) ይመጣል፡፡ ከዚያም ነፍስ ሁሉ የሥራዋን ዋጋ ትሞላለች፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 3|162|የአላህን ውዴታ የተከተለ ሰው ከአላህ በኾነ ቁጣ እንደ ተመለሰና መኖሪያው ገሀነም እንደ ኾነ ሰው ነውን መመለሻውም ምን ይከፋ! 3|163|እነርሱ አላህ ዘንድ ባለ ደረጃዎች ናቸው፡፡ አላህም የሚሠሩትን ነገር ተመልካች ነው፡፡ 3|164|አላህ በምእምናን ላይ ከጎሳቸው የኾነን፤ በእነርሱ ላይ አንቀጾቹን የሚያነብ፣ የሚጠራቸውም፣ መጽሐፍንና ጥበብን የሚያስተምራቸውም የኾነን መልእክተኛ በውስጣቸው በላከ ጊዜ፤ በእርግጥ ለገሰላቸው፡፡ እነርሱም ከዚያ በፊት በግልጽ ስህተት ውስጥ ነበሩ፡፡ 3|165|ሁለት ብጤዎችዋን በእርግጥ ያገኛችሁ የኾነች መከራ (መጠቃት) ባገኘቻችሁ ጊዜ «ይህ ከየት ነው» አላችሁን «እርሱ ከነፍሶቻችሁ ዘንድ ነው፡፡» አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና በላቸው፡፡ 3|166|ሁለቱ ጭፍሮችም በተጋጠሙ ቀን የደረሰባችሁ በአላህ ፈቃድ ነው፡፡ ምእምናንንም (ሊፈትንና) ሊገልጽ ነው፡፡ 3|167|እነዚያንም የነፈቁትንና ለነርሱ «ኑ፤ በአላህ መንገድ ተጋደሉ፤ ወይም ተከላከሉ፤» የተባሉትን ሊገልጽ ነው፡፡ «መዋጋት (መኖሩን) ብናውቅ ኖሮ በተከተልናችሁ ነበር» አሉ፡፡ እነርሱ ያን ጊዜ ከእምነት ይልቅ ወደ ክህደት የቀረቡ ናቸው፡፡ በልቦቻቸው የሌለውን በአፎቻቸው ይናገራሉ፡፡ አላህም የሚደብቁትን ዐዋቂ ነው፡፡ 3|168|እነዚያ (ከትግል) የቀሩ ሲኾኑ ለወንድሞቻቸው፡- «በታዘዙን ኖሮ ባልተገደሉ ነበር» ያሉ ናቸው፡፡ «እውነተኞች እንደኾናችሁ ከነፍሶቻችሁ ላይ ሞትን ገፍትሩ» በላቸው፡፡ 3|169|እነዚያን በአላህ መንገድ የተገደሉትን ሙታን አድርገህ አትገምታቸው፡፡ በእርግጥ እነርሱ እጌታቸው ዘንድ ሕያዋን ናቸው፤ ይመገባሉ፡፡ 3|170|አላህ ከችሮታው በሰጣቸው ነገር ተደሳቾች ሲኾኑ (ይመገባሉ)፡፡ በነዚያም ከኋላቸው ገና በእነርሱ ባልተከተሉት በእነርሱ ላይ ፍርሃት ባለመኖሩና እነርሱም የማያዝኑ በመኾናቸው ይደሰታሉ፡፡ 3|171|ከአላህ በኾነ ጸጋና ልግስና አላህም የምእምናንን ምንዳ የማያጠፉ በመኾኑ ይደሰታሉ፡፡ 3|172|እነዚያ መቁሰል ካገኛቸው በኋላ ለአላህና ለመልክተኛው የታዘዙት ከእነሱ ለነዚያ በጎ ለሠሩትና ለተጠነቀቁት ታላቅ ምንዳ አላቸው፡፡ 3|173|እነዚያ ሰዎቹ ለእነርሱ፡- «ሰዎች ለእናንተ (ጦርን) አከማችተዋልና ፍሩዋቸው» ይሉዋቸውና (ይህም) እምነትን የጨመረላቸው «በቂያችንም አላህ ነው ምን ያምርም መጠጊያ!» ያሉ ናቸው፡፡ 3|174|ከአላህም በኾነ ጸጋና ችሮታ ክፉ ነገር ያልነካቸው ኾነው ተመለሱ፡፡ የአላህንም ውዴታ ተከተሉ፤ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 3|175|እንዲህ የሚላችሁ ሰይጣን ብቻ ነው፡፡ ወዳጆቹን ያስፈራራችኋል፡፡ አትፍሩዋቸውም፡፡ ምእምናንም እንደኾናችሁ ፍሩኝ፡፡ 3|176|እነዚያም በክህደት የሚቻኮሉት አያሳዝኑህ፡፡ ከነርሱ ፈጽሞ አላህን በምንም አይጎዱምና፡፡ አላህ በመጨረሻይቱ ዓለም ለእነሱ ዕድልን ላያደርግ ይሻል፡፡ ለእነርሱም ታላቅ ቅጣት አላቸው፡፡ 3|177|እነዚያ ክህደትን በእምነት የለወጡ አላህን በምንም ነገር ፈጽሞ አይጎዱትም፡፡ ለእነሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 3|178|እነዚያ የካዱት ሰዎች እነርሱን ማዘግየታችንን ለነፍሶቻቸው ደግ ነገር ነው ብለው አያስቡ፡፡ እነርሱን የምናዘገያቸው ኃጢኣትን እንዲጨምሩ ብቻ ነው፡፡ ለነሱም አዋራጅ ስቃይ አላቸው፡፡ 3|179|አላህ መጥፎውን ከመልካሙ እስከሚለይ ድረስ ምእምናንን እናንተ በርሱ ላይ ባላችሁበት (ኹኔታ) ላይ የሚተው አይደለም፡፡ አላህም ሩቁን ነገር የሚያሳውቃችሁ አይደለም፡፡ ግን አላህ ከመልክተኞቹ የሚሻውን ይመርጣል፡፡ በአላህና በመልክተኞቹም እመኑ፡፡ ብታምኑና ብትጠነቀቁም ለናንተ ታላቅ ምንዳ አላችሁ፡፡ 3|180|እነዚያም አላህ ከችሮታው በሰጣቸው ገንዘብ የሚነፍጉ እርሱ ለእነሱ ደግ አይምሰላቸው፡፡ ይልቁንም፤ እርሱ ለነሱ መጥፎ ነው፡፡ ያንን በርሱ የነፈጉበትን በትንሣኤ ቀን (እባብ ኾኖ) ይጠለቃሉ፡፡ የሰማያትና የምድርም ውርስ ለአላህ ብቻ ነው፡፡ አላህም በሚሠሩት ሁሉ ውስጥ ዐዋቂ ነው፡፡ 3|181|የእነዚያን «አላህ ድኻ ነው እኛ ግን ከበርቴዎች ነን» ያሉትን ሰዎች ቃል አላህ በእርግጥ ሰማ፡፡ ያንን ያሉትንና ነቢያትን ያለ ሕግ መግደላቸውን በእርግጥ እንጽፋለን፡፡ «የእሳትንም ስቃይ ቅመሱ» እንላቸዋለን፡፡ 3|182|ያ (ስቃይ) እጆቻችሁ ባሳለፉት ሥራ ነው፡፡ አላህም ለባሮቹ በዳይ ባለመኾኑ ነው፡፡ 3|183|እነዚያ ለማንኛውም መልክተኛ «እሳት የምትበላው የኾነን ቁርባን እስከሚያመጣልን ድረስ ላናምን አላህ ወደኛ አዟል» ያሉ ናቸው፡፡«መልክተኞች ከእኔ በፊት በተዓምራትና በዚያም ባላችሁት (ቁርባን) በእርግጥ መጥተውላችኋል፡፡ እውነተኞች ከኾናችሁ ታዲያ ለምን ገደላችኋቸው» በላቸው፡፡ 3|184|ቢያስተባብሉህም ከአንተ በፊት በግልጽ ተዓምራትና በጽሑፎች፣ በብሩህ መጽሐፍም የመጡት መልክተኞች በእርግጥ ተስተባብለዋል፡፡ 3|185|ነፍስ ሁሉ ሞትን ቀማሽ ናት፡፡ ምንዳዎቻችሁንም የምትሞሉት በትንሣኤ ቀን ብቻ ነው፡፡ ከእሳትም የተራቀና ገነትን የተገባ ሰው በእርግጥ ምኞቱን አገኘ፡፡ ቅርቢቱም ሕይወት የመታለያ መሳሪያ እንጅ ሌላ አይደለችም፡፡ 3|186|በገንዘቦቻችሁና በነፍሶቻችሁ በእርግጥ ትፈተናላችሁ፡፡ ከእነዚያም ከእናንተ በፊት መጽሐፍን ከተሰጡትና ከእነዚያም ከአጋሩት ብዙን ማሰቃየት ትሰማላችሁ፡፡ ብትታገሱና ብትጠነቀቁ ይህ ከጥብቅ ነገሮች ነው፡፡ 3|187|አላህ የነዚያን መጽሐፉን የተሰጡትን ቃል ኪዳን ለሰዎች በእርግጥ ታብራሩታላችሁ አትደብቁትምም በማለት የያዘባቸውን (አስታውሱ)፡፡ በጀርባዎቻቸውም ኋላ ጣሉት፡፡ በርሱም ጥቂትን ዋጋ ገዙ፡፡ የሚገዙትም ነገር ከፋ! 3|188|እነዚያን በሠሩት ነገር የሚደሰቱትንና ባልሠሩትም መመስገንን የሚወዱትን አታስብ፤ ከቅጣት በመዳን ላይ ናቸው ብለህ አታሰባቸው፡፡ ለእነሱ አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 3|189|የሰማያትና የምድር ንግሥና ለአላህ ብቻ ነው፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 3|190|ሰማያትንና ምድርን በመፍጠር ሌሊትና ቀንንም በመተካካት ለባለ አእምሮዎች በእርግጥ ምልክቶች አሉ፡፡ 3|191|(እነርሱም) እነዚያ ቆመው፣ ተቀምጠውም፣ በጎኖቻቸው ተጋድመውም አላህን የሚያወሱ በሰማያትና በምድር አፈጣጠርም የሚያስተነትኑ፡- «ጌታችን ሆይ! ይኸን በከንቱ አልፈጠርከውም፤ ጥራት ይገባህ፤ ከእሳትም ቅጣት ጠብቀን» የሚሉ ናቸው፡፡ 3|192|«ጌታችን ሆይ! አንተ እሳት የምታገባውን ሰው በእርግጥ አዋረድከው፤ ለበደለኞችም ምንም ረዳቶች የሉዋቸውም፡፡» 3|193|«ጌታችን ሆይ! እኛ በጌታችሁ እመኑ በማለት ወደ እምነት የሚጠራን ጠሪ ሰማን፡፡ አመንም፡፡ ጌታችን ሆይ! ኃጢአቶቻችንንም ለኛ ማር፡፡ ክፉ ሥራዎቻችንንም ከኛ አብስ፡፡ ከንጹሖቹም ሰዎች ጋር ግደለን፤» 3|194|«ጌታችን ሆይ! በመልክተኞችህም ላይ ተስፋ ቃል ያደረግክልንን ስጠን፡፡ በትንሣኤ ቀንም አታዋርደን፡፡ አንተ ቀጠሮን አታፈርስምና» (የሚሉ ናቸው)፡፡ 3|195|ጌታቸውም «እኔ ከእናንተ ከወንድ ወይም ከሴት የሠሪን ሥራ አላጠፋም፡፡ ከፊላችሁ ከከፊሉ ነው፤ በማለት ለነርሱ ልመናቸውን ተቀበለ፡፡ እነዚያም የተሰደዱ ከአገሮቻቸውም የተባረሩ በመንገዴም የተጠቁ የተጋደሉም የተገደሉም ክፉ ሥራዎቻቸውን ከእነርሱ በእርግጥ አብሳለሁ፡፡ በሥሮቻቸውም ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በእርግጥ አገባቸዋለሁ፡፡ ከአላህ ዘንድ የኾነን ምንዳ (ይመነዳሉ)፡፡ አላህም እርሱ ዘንድ መልካም ምንዳ አልለ፡፡ » 3|196|የእነዚያ የካዱት ሰዎች በአገሮች መንፈላሰስ አያታልህ፡፡ 3|197|አነስተኛ ጥቅም ነው፡፡ ከዚያም መኖሪያቸው ገሀነም ናት፡፡ ምን ትከፋም ምንጣፍ! 3|198|ግን እነዚያ ጌታቸውን የፈሩ ለእነሱ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶች በውስጧ ዘውታሪዎች ሲኾኑ ከአላህ ዘንድ (የተሰጡ) መስተንግዶዎች አሏቸው፡፡ አላህም ዘንድ ያለው (ምንዳ) ለበጎ ሠሪዎች በላጭ ነው፡፡ 3|199|ከመጽሐፉም ባለቤቶች ለአላህ ፈሪዎች በአላህ አንቀጾችም ጥቂትን ዋጋ የማይለወጡ ሲኾኑ በአላህና በዚያ ወደ እናንተ በተወረደው በዚያም ወደእነርሱ በተወረደው የሚያምኑ ሰዎች አልሉ፡፡ እነዚያ ለእነርሱ በጌታቸው ዘንድ ምንዳቸው አላቸው፡፡ አላህ ምርመራው ፈጣን ነው፡፡ 3|200|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ታገሱ ተበራቱም፡፡ (በጦር ኬላ ላይ) ተሰለፉም፡፡ ትድኑም ዘንድ አላህን ፍሩ፡፡ 4|1|እናንተ ሰዎች ሆይ! ያንን ከአንዲት ነፍስ (ከአዳም) የፈጠራችሁን ከእርስዋም መቀናጆዋን (ሔዋንን) የፈጠረውን ከእነርሱም ብዙ ወንዶችንና ሴቶች የበተነውን ጌታችሁን ፍሩ፡፡ ያንንም በርሱ የምትጠያየቁበትን አላህንና ዝምድናዎችንም (ከመቁረጥ) ተጠንቀቁ፡፡ አላህ በእናንተ ላይ ተጠባባቂ ነውና፡፡ 4|2|የቲሞችንም ገንዘቦቻቸውን ስጡ፡፡ መጥፎውንም በመልካሙ አትለውጡ፡፡ ገንዘቦቻቸውንም ወደ ገንዘቦቻችሁ (በመቀላቀል) አትብሉ እርሱ ታላቅ ኃጢአት ነውና፡፡ 4|3|በየቲሞችም (ማግባት) አለማስተካከላችሁን ብትፈሩ (ዝሙትንና ከተወሰነላችሁ በላይ ማግባትንም ፍሩ)፡፡ ከሴቶች ለእናንተ የተዋበላችሁን ሁለት ሁለት ሦስት ሦስትም አራት አራትም አግቡ፡፡ አለማስተካከልንም ብትፈሩ አንዲትን ብቻ ወይም እጆቻችሁ ንብረት ያደረጉትን ያዙ፡፡ ይህ ወደ አለመበደል በጣም የቀረበ ነው፡፡ 4|4|ሴቶችንም መህሮቻቸውን በደስታ ስጡ፡፡ ለእናንተም ከእርሱ አንዳችን ነገር ነፍሶቻቸው ቢለግሱ መልካም ምስጉን ሲኾን ብሉት፡፡ 4|5|ቂሎችንም ያችን አላህ ለእናንተ መተዳደሪያ ያደረጋትን ገንዘቦቻችውን (የያዛችሁላቸውን) አትስጡዋቸው፡፡ ከርሷም መግቡዋቸው አልብሱዋቸውም፡፡ ለእነሱም መልካምን ንግግር ተናገሩ፡፡ 4|6|የቲሞችንም ጋብቻን እስከደረሱ ጊዜ ድረስ ፈትኑዋቸው፡፡ ከእነርሱም ቅንነትን ብታውቁ ገንዘቦቻቸውን ወደ እነርሱ ስጡ፡፡ በማባከንና ማደጋቸውንም በመሽቀዳደም አትብሏት፡፡ (ከዋቢዎች) ሀብታምም የኾነ ሰው ይከልከል፡፡ ድሃም የኾነ ሰው (ለድካሙ) በአግባብ ይብላ፡፡ ገንዘቦቻቸውንም ወደ እነርሱ በሰጣችሁ ጊዜ በእነርሱ ላይ አስመስክሩ፡፡ ተጠባባቂነትም በአላህ በቃ፡፡ 4|7|ለወንዶች ወላጆችና የቅርብ ዘመዶች ከተዉት (ንብረት) ፋንታ (ድርሻ) አላቸው፡፡ ለሴቶችም ወላጆችና የቅርብ ዘመዶች ከተዉት ከእርሱ ካነሰው ወይም ከበዛው ፋንታ አላቸው፡፡ የተወሰነ ድርሻ (ተደርጓል)፡፡ 4|8|ክፍያንም (ወራሽ ያልኾኑ) የዝምድና ባለቤቶችና የቲሞች፣ ምስኪኖችም በተገኙበት ጊዜ ከእርሱ ዳርጓቸው፡፡ መልካምንም ንግግር ተናገሩዋቸው፡፡ 4|9|እነዚያም ከኋላቸው ደካሞችን ዝርያዎች ቢተው ኖሮ በእነርሱ ላይ የሚፈሩ (በየቲሞች ላይ) ይጠንቀቁ፡፡ አላህንም ይፍሩ፡፡ (ለተናዛዡ) ትክክለኛንም ቃል ይናገሩ፡፡ 4|10|እነዚያ የየቲሞችን ገንዘብ በመበደል የሚበሉ በሆዶቻቸው ውስጥ የሚበሉት እሳትን ብቻ ነው፡፡ እሳትንም በእርግጥ ይገባሉ፡፡ 4|11|አላህ በልጆቻችሁ (ውርስ በሚከተለው) ያዛችኋል፡፡ ለወንዱ የሁለት ሴቶች ድርሻ ብጤ አለው፡፡ (ሁለት ወይም) ከሁለት በላይም የኾኑ ሴቶች ብቻ ቢኾኑ ለእነሱ (ሟቹ) ከተወው ረጀት (ድርሻ) ከሦስት ሁለት እጁ አላቸው፡፡ አንዲትም ብትኾን ለርሷ ግማሹ አላት፡፡ ለአባትና ለእናቱም ለእርሱ ልጅ እንዳለው ከሁለቱ ለያንዳንዱ ከስድስት አንድ አላቸው፡፡ ለእርሱም ልጅ ባይኖረውና ወላጆቹ ቢወርሱት ለእናቱ ሲሶው አላት፡፡ ለእርሱም ወንድሞችና እኅቶች ቢኖሩት ለናቱ ከስድስት አንድ አላት፡፡ (ይህም የተባለው) በርሷ ከተናዘዘባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡ አባቶቻችሁና ልጆቻችሁ ለእናንተ በመጥቀም ማንኛቸው ይበልጥ ቅርብ እንደኾኑ አታውቁም፡፡ (ይኽም) ከአላህ የተደነገገ ነው፤ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡ 4|12|ለእናንተም ሚስቶቻችሁ ከተዉት ንብረት ለእነርሱ ልጅ ባይኖራቸው ግማሹ አላችሁ፡፡ ለእነሱም ልጅ ቢኖራቸው ከተዉት ሀብት ከአራት አንድ አላችሁ፡፡ (ይህም) በእርሷ ከሚናዘዙባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡ ለናንተም ልጅ ባይኖራችሁ ከተዋችሁት ንብረት ለእነርሱ (ለሚስቶች) ከአራት አንድ አላቸው፡፡ ለእናንተም ልጅ ቢኖራችሁ ከተዋችሁት ንብረት ለእነርሱ ከስምንት አንድ አላቸው (ይህም በርሷ ከምትናዘዙባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡) ወላጅም ልጅም የሌለው በጎን ወራሾች የሚወርስ ወንድ ወይም ሴት ቢገኝ ለእርሱም (ለሟቹ) ወንድም ወይም እኅት (ከእናቱ በኩል ብቻ የኾነ) ቢኖር ከሁለቱ ለያንዳንዳቸው ከስድስት አንድ አላቸው፡፡ ከዚህም (ከአንድ) የበዙ ቢኾኑ እነርሱ በሲሶው ተጋሪዎች ናቸው፡፡ (ይህም ወራሾችን) የማይጎዳ ኾኖ በእርሷ ከሚናዘዙባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡ ከአላህም የኾነን ኑዛዜ (ያዛችኋል)፡፡ አላህም ዐዋቂ ቻይ ነው፡፡ 4|13|እነዚህ የአላህ ውሳኔዎች ናቸው፡፡ አላህንና መልክተኛውንም የሚታዘዙ ሰዎች ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ ያገባቸዋል፡፡ ይህም ትልቅ ዕድል ነው፡፡ 4|14|አላህንና መልክተኛውንም የሚያምጽ ወሰኖቹንም የሚተላለፍ በውስጧ ዘውታሪ ሲኾን እሳትን ያገባዋል፡፡ ለርሱም አዋራጅ ቅጣት አለው፡፡ 4|15|እነዚያም ከሴቶቻችሁ መጥፎን ሥራ (ዝሙትን) የሚሠሩ በእነርሱ ላይ ከናንተ አራትን (ወንዶች) አስመስክሩባቸው፡፡ ቢመሰክሩም ሞት እስከሚደርስባቸው ወይም አላህ ለእነርሱ መንገድን እስከሚያደርግ ድረስ በቤቶች ውሰጥ ያዙዋቸው (ጠብቁዋቸው)፡፡ 4|16|እነዚያንም ከእናንተ ውስጥ (ዝሙትን) የሚሠሩዋትን አሰቃዩዋቸው፡፡ ቢጸጸቱና ሥራቸውንም ቢያሳምሩ ከእነርሱ ተገቱ (አታሰቃዩዋቸው)፡፡ አላህ ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ነውና፡፡ 4|17|ጸጸትን መቀበል በአላህ ላይ የሚገባው ለእነዚያ ኀጢአትን በስህተት ለሚሠሩና ከዚያም ከቅርብ ጊዜ ለሚጸጸቱት ብቻ ነው፡፡ እነዚያንም አላህ በእነርሱ ላይ ጸጸትን ይቀበላል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|18|ጸጸትንም መቀበል ለእነዚያ ኀጢአቶችን ለሚሠሩ አንዳቸውንም ሞት በመጣበት ጊዜ «እኔ አሁን ተጸጸትኩ» ለሚልና ለነዚያም እነርሱ ከሓዲዎች ኾነው ለሚሞቱ አይደለችም፡፡ እነዚያ ለእነሱ አሳማሚን ቅጣት አዘጋጅተናል፡፡ 4|19|እናንተ ያመናችሁ ሰዎች ሆይ! ሴቶችን ያስገደዳችሁ ኾናችሁ ልትወርሱና ግልጽን መጥፎ ሥራ ካልሠሩ በስተቀር ከሰጣችኋቸው ከፊሉን ልትወስዱ ልታጉላሏቸውም ለእናንተ አይፈቀድም፡፡ በመልካምም ተኗኗሩዋቸው፡፡ ብትጠሉዋቸውም (ታገሱ)፡፡ አንዳችን ነገር ብትጠሉ አላህም በእርሱ ብዙ ደግ ነገርን ሊያደርግ ይቻላልና፡፡ 4|20|በሚስትም ስፍራ ሚስትን ለመለወጥ ብትፈልጉ ለአንደኛይቱ (ለምትፈታው) ብዙን ገንዘብ የሰጣችኋት ስትኾኑ ከርሱ ምንንም አትውሰዱ፡፡ በመበደልና ግልጽ በኾነ ኀጢአት ትወስዱታላችሁን 4|21|ከፊላችሁ ወደ ከፊሉ በእርግጥ የደረሰ ሲኾንና ከእናንተ ላይም (ሴቶች) የጠበቀ ኪዳንን የያዙባችሁ ሲኾኑ እንዴት ትወስዱታላችሁ! 4|22|ከሴቶችም አባቶቻችሁ ያገቡዋቸውን አታግቡ፡፡ (ትቀጡበታላችሁ)፡፡ ያለፈው ሲቀር፡፡ እርሱ መጥፎና የተጠላ ሥራ ነውና፡፡ መንገድነቱም ከፋ! 4|23|እናቶቻችሁ፣ ሴት ልጆቻችሁም፣ እኅቶቻችሁም፣ አክስቶቻችሁም፣ የሹሜዎቻችሁም፣ የወንድም ሴቶች ልጆችም፣ የእኅት ሴቶች ልጆችም፣ እነዚያም ያጠቡዋችሁ እናቶቻችሁ፣ ከመጥባት የኾኑትም እኅቶቻችሁ፣ የሚስቶቻችሁም እናቶች፣ እነዚያም በጉያዎቻችሁ ያሉት የእነዚያ በእነርሱ የገባችሁባቸው ሚስቶቻችሁ ሴቶች ልጆች፣ (ልታገቧቸው) በእናንተ ላይ እርም ተደረጉባችሁ፡፡ በእነርሱም (በሚስቶቻችሁ) ያልገባችሁባቸው ብትኾኑ (በፈታችኋቸው ጊዜ ሴቶች ልጆቻቸውን ብታገቡ) በእናንተ ላይ ኀጢአት የለባችሁም፡፡ የእነዚያ ከጀርባዎቻችሁ የኾኑት ወንዶች ልጆቻችሁ ሚስቶችም በሁለት እኅትማማቾችም መካከል መሰብሰብ (እንደዚሁ እርም ነው)፡፡ ግን ከዚህ በፊት ያለፈው ሲቀር (እርሱንስ ተምራችኋል) አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 4|24|ከሴቶችም (በባል) ጥብቆቹ እጆቻቸሁ (በምርኮ) የያዙዋቸው ሲቀሩ በእናንተ ላይ እርም ናቸው፡፡ (ይህን) አላህ በናንተ ላይ ጻፈ፡፡ ከዚሃችሁም (ከተከለከሉት) ወዲያ ጥብቆች ኾናችሁ ዝሙተኞች ሳትኾኑ በገንዘቦቻችሁ ልትፈልጉ ለእናንተ ተፈቀደ፡፡ ከእነሱም በርሱ (በመገናኘት) የተጠቀማችሁባቸውን ሴቶች መህሮቻቸውን ግዴታ ሲኾን ስጧቸው፡፡ ከመወሰንም በኋላ በተዋደዳችሁበት ነገር በእናንተ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡ 4|25|ከናንተም ውስጥ ጥብቆች ምእምናት የኾኑትን ለማግባት ሀብትን ያልቻለ ሰው እጆቻችሁ ንብረት ካደረጓቸው ከምእምናት ወጣቶቻችሁ (ባሪያን ያግባ)፡፡ አላህም እምነታችሁን ዐዋቂ ነው፡፡ ከፊላችሁ ከከፊሉ (የተራባ) ነው፡፡ (ባሮችን) በጌቶቻቸውም ፈቃድ አግቡዋቸው፡፡ መህሮቻቸውንም በመልካም መንገድ ስጧቸው፡፡ ጥብቆች ኾነው ዝሙተኞች ያልኾኑ የስርቆሽ ወዳጆችንም ያልያዙ ሲኾኑ (አግቧቸው)፡፡ በማግባት በተጠበቁም ጊዜ መጥፎን ሥራ ቢሠሩ በእነርሱ ላይ ከቅጣት በነጻዎቹ ላይ ያለው ግማሽ አለባቸው፡፡ ይኸ (ባሪያን ማግባት) ከናንተ ዝሙትን ለፈራ ሰው ነው፡፡ 4|26|አላህ (የሃይማኖታችሁን ሕግጋት) ሊያብራራላችሁ ከእናንተ በፊትም የነበሩትን ነቢያት ደንቦች ሊመራችሁ በእናንተም ላይ ጸጸትን ሊቀበል ይሻል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|27|አላህም በእናንተ ላይ ጸጸትን ሊቀበል ይሻል፡፡ እነዚያም ፍላጎታቸውን የሚከተሉት (ከውነት) ትልቅን መዘንበል እንድትዘነበሉ ይፈልጋሉ፡፡ 4|28|አላህ ከእናንተ ሊያቃልልላችሁ ይሻል፡፡ ሰውም ደካማ ኾኖ ተፈጠረ፡፡ 4|29|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ገንዘቦቻችሁን በመካከላችሁ ያለ አግባብ አትብሉ፡፡ ግን ከእናንተ በመዋደድ የኾነችውን ንግድ (ብሉ)፡፡ ነፍሶቻችሁንም አትግደሉ፡፡ አላህ ለእናንተ አዛኝ ነውና፡፡ 4|30|ወሰን በማለፍና በመበደልም ይህንን የሠራ ሰው እሳትን እናገባዋለን፡፡ ይኸም በአላህ ላይ ገር ነው፡፡ 4|31|ከእርሱ ከተከለከላችሁት ታላላቆቹን (ኀጢአቶች) ብትርቁ (ትናንሾቹን) ኀጢአቶቻችሁን ከእናንተ እናብሳለን፡፡ የተከበረንም ስፍራ (ገነትን) እናገባችኋለን፡፡ 4|32|አላህም ከፊላችሁን በከፊሉ ላይ በእርሱ ያበለጠበትን ጸጋ አትመኙ፡፡ ለወንዶች ከሠሩት ሥራ እድል አላቸው፡፡ ለሴቶችም ከሠሩት ሥራ ዕድል አላቸው፡፡ አላህንም ከችሮታው ለምኑት፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 4|33|ለሁሉም (ለወንዶችና ለሴቶች) ወላጆችና የቅርብ ዘመዶች ከተዉት ሀብት ጠቅላይ ወራሾችን አድርገናል፡፡ እነዚያንም (ለመረዳዳትና ለመዋረስ) በመሐላዎቻችሁ የተዋዋላችኋቸውን ድርሻቸውን (ከስድስት አንድ) ስጧቸው፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 4|34|ወንዶች በሴቶች ላይ ቋሚዎች (አሳዳሪዎች) ናቸው፡፡ አላህ ከፊላቸውን በከፊሉ ላይ በማብለጡና (ወንዶች) ከገንዘቦቻቸው (ለሴቶች) በመስጠታቸው ነው፡፡ መልካሞቹም ሴቶች (ለባሎቻቸው) ታዛዦች አላህ ባስጠበቀው ነገር ሩቅን ጠባቂዎች ናቸው፡፡ እነዚያንም ማመጸቸውን የምትፈሩትን ገስጹዋቸው፡፡ በመኝታዎችም ተለዩዋቸው፡፡ (ሳካ ሳታደርሱ) ምቱዋቸውም፡፡ ቢታዘዟችሁም (ለመጨቆን) በእነርሱ ላይ መንገድን አትፈልጉ፤ አላህ የበላይ ታላቅ ነውና፡፡ 4|35|(እናንተ ዋቢዎች) የመካከላቸውንም ጭቅጭቅ ብታውቁ ከቤተሰቦቹ ሽማግሌን ከቤተሰቦችዋም ሽማግሌን ላኩ፡፡ ማስታረቅን ቢሹ አላህ በመካከላቸው ያስማማል፡፡ አላህ ግልጽን ዐዋቂ ውስጥንም ዐዋቂ ነውና፡፡ 4|36|አላህንም ተገዙ፡፡ በእርሱም ምንንም አታጋሩ፡፡ በወላጆችና በቅርብ ዝምድና ባለቤትም፣ በየቲሞችም፣ በምስኪኖችም፣ በቅርብ ጎረቤትም፣ በሩቅ ጎረቤትም፣ በጎን ባልደረባም፣ በመንገደኛም፣ እጆቻችሁም ንብረት ባደረጓቸው (ባሮች)፣ መልካምን (ሥሩ)፤ አላህ ኩራተኛ ጉረኛ የኾነን ሰው አይወድም፡፡ 4|37|እነዚያ የሚሰስቱ ሰዎችንም በመሰሰት የሚያዙ አላህም ከችሮታው የሰጣቸውን ጸጋ የሚደብቁ (ብርቱን ቅጣት ይቀጥጣሉ)፡፡ ለከሓዲዎችም አዋራጅን ቅጣት አዘጋጅተናል፡፡ 4|38|እነዚያም ለሰዎች ይውልኝ ሲሉ ገንዘቦቻቸውን የሚሰጡ በአላህና በመጨረሻውም ቀን የማያምኑ (ይቀጥጣሉ)፡፡ ሰይጣንም ለእርሱ ጓደኛው የኾነ ሰው ጓደኛነቱ ከፋ! 4|39|በአላህና በመጨረሻውም ቀን ባመኑ አላህ ከሰጣቸውም (ሲሳይ) በለገሱ ኖሮ በነርሱ ላይ ምን (ጉዳት) ነበረ አላህም በነርሱ (ኹነታ) ዐዋቂ ነው፡፡ 4|40|አላህ የብናኝን ክብደት ያህል አይበድልም፡፡ መልካም ሥራ ብትኾንም ይደራርባታል፡፡ ከእርሱም ዘንድ ታላቅን ምንዳ ይሰጣል፡፡ 4|41|ከሕዝቦችም ሁሉ መስካሪን ባመጣን ጊዜ አንተንም በእነዚህ ላይ መስካሪ አድርገን በምናመጣህ ጊዜ (የከሓዲዎች ኹኔታ) እንዴት ይኾን 4|42|በዚያ ቀን እነዚያ የካዱትና መልክተኛውን ያልታዘዙት በእነሱ ምድር ብትደፋባቸው ይመኛሉ፡፡ ከአላህም ወሬን አይደብቁም፡፡ 4|43|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እናንተ የሰከራችሁ ኾናችሁ የምትሉትን ነገር እስከምታውቁ የረከሳችሁም ስትኾኑ መንገድን አላፊዎች ካልኾናችሁ በስተቀር (አካላታችሁን) እስከምትታጠቡ ድረስ ስግደትን አትቅረቡ፡፡ በሽተኞች ወይም በጉዞ ላይ ብትኾኑም፥ ወይንም ከእናንተ አንዱ ከዓይነምድር ቢመጣ፥ ወይንም ሴቶችን ብትነካኩና ውሃን ባታገኙ፣ ንጹሕ የኾነን የምድር ገጽ አስቡ፡፡ ፊቶቻችሁንና እጆቻችሁንም (በርሱ) አብሱ፡፡ አላህ ይቅር ባይ መሓሪ ነውና፡፡ 4|44|ወደነዚያ ከመጽሐፉ (ዕውቀት) ዕድልን ወደ ተሰጡት አላየህምን ጥመትን (በቅንነት) ይገዛሉ፡፡ መንገድንም እንድትሳሳቱ ይፈልጋሉ፡፡ 4|45|አላህም ጠላቶቻችሁን ዐዋቂ ነው፡፡ ጠባቂነትም በአላህ በቃ፡፡ ረዳትነትም በአላህ በቃ፡፡ 4|46|ከነዚያ አይሁዳውያን ከኾኑት ሰዎች ንግግሮችን ከስፍራዎቹ የሚያጣምሙ አልሉ፡፡ «ሰማንም አመጽንም የማትሰማም ስትኾን ስማ» ይላሉ፡፡ በምላሶቻቸውም ለማጣመምና ሃይማኖትንም ለመዝለፍ ራዒና ይላሉ፡፡ እነሱም «ሰማን ታዘዝንም ስማም ተመልከተንም» ባሉ ኖሮ ለነሱ መልካምና ትክክለኛ በኾነ ነበር፡፡ ግን በክህደታቸው አላህ ረገማቸው፡፡ ጥቂትንም እንጅ አያምኑም፡፡ 4|47|እናንተ መጽሐፉን የተሰጣችሁ ሆይ! ፊቶችን ሳናብስና በጀርባዎች ላይ ሳንመልሳቸው ወይም የሰንበትን ባለቤቶች (ያፈረሱትን) እንደረገምን ሳንረግማቸው በፊት ከእናንተ ጋር ያለውን የሚያረጋግጥ ኾኖ ባወረድነው (ቁርኣን) እመኑ፡፡ የአላህም ትዕዛዝ ተፈጻሚ ነው፡፡ 4|48|አላህ በእርሱ ማጋራትን በፍጹም አይምርም፡፡ ከዚህ ሌላ ያለውንም (ኀጢአት) ለሚሻው ሰው ይምራል፡፡ በአላህም የሚያጋራ ሰው ታላቅን ኀጢአት በእርግጥ ቀጠፈ፡፡ 4|49|ወደእነዚያ ነፍሶቻቸውን ወደ ሚያጠሩት (የሚያወድሱት) አላየህምን አይደለም፤ አላህ የሚፈልገውን ያጠራል፡፡ የተምር ፍሬ ክር ያህልም አይበደሉም፡፡ 4|50|በአላህ ላይ ውሸትን እንዴት እንደሚቀጣጥፉ ተመልከት፡፡ ግልጽ ወንጀልም በርሱ (በመቅጠፍ) በቃ፡፡ 4|51|ወደ እነዚያ ከመጽሐፉ ዕድልን ወደ ተሰጡት አላየኸምን በድግምትና በጣዖት ያምናሉ፡፡ ለእነዚያም ለካዱት፡- እናንተ በመንገድ (በሃይማኖት) ከእነዚያ ካመኑት ይበልጥ የቀናችሁ ናችሁ ይላሉ፡፡ 4|52|እነዚያ አላህ የረገማቸው ናቸው፡፡ አላህም የረገመው ሰው ለእርሱ ፈጽሞ ረዳትን አታገኝለትም፡፡ 4|53|በእውነቱ ለእነሱ ከንግሥናው ፋንታ አላቸውን ያን ጊዜ ለሰዎች በተምር ፍሬ ላይ ያለችውን ነጥብ ያህል አይሰጡም ነበር፡፡ 4|54|ይልቁንም ሰዎችን (ሙሐመድን) አላህ ከችሮታው በሰጣቸው ነገር ላይ ይመቀኛሉን ለኢብራሂምም ቤተሰቦች መጽሐፍንና ጥበብን በእርግጥ ሰጠን ታላቅንም ንግሥና ሰጠናቸው፡፡ 4|55|ከእነሱም (ከይሁዶች) በእርሱ ያመነ አለ፡፡ ከእነርሱም ከእርሱ ያፈገፈ አለ፡፡ አቃጣይነትም በገሀነም በቃ፡፡ 4|56|እነዚያን በተአምራታችን የካዱትን በእርግጥ እሳትን እናገባቸዋለን፡፡ ስቃይን እንዲቀምሱ ቆዳዎቻቸው በተቃጠሉ ቁጥር ሌሎችን ቆዳዎች እንለውጥላቸዋለን፡፡ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና፡፡ 4|57|እነዚያንም ያመኑትንና መልካም ሥራዎችን የሠሩትን ከስራቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች ዘልዓለም በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ በእርግጥ እናገባቸዋለን፡፡ ለእነሱ በውስጥዋ ንጹሕ ሚስቶች አሉዋቸው፡፡ የምታስጠልልን ጥላም እናገባቸዋለን፡፡ 4|58|አላህ አደራዎችን ወደ ባለቤቶቻቸው እንድታደርሱ ያዛችኋል፡፡ በሰዎችም መካከል በፈረዳችሁ ጊዜ በትክክል እንድትፈርዱ (ያዛችኋል)፡፡ አላህ በርሱ የሚገሥጻችሁ ነገር ምን ያምር! አላህ ሰሚ ተመልካች ነው፡፡ 4|59|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ መልክተኛውንና ከእናንተም የስልጣን ባለቤቶችን ታዘዙ፡፡ በማንኛውም ነገር ብትከራከሩ በአላህና በመጨረሻው ቀን የምታምኑ ብትኾኑ (የተከራከራችሁበትን ነገር) ወደ አላህና ወደ መልክተኛው መልሱት፡፡ ይህ የተሻለ መጨረሻውም ያማረ ነው፡፡ 4|60|ወደ እነዚያ እነርሱ በአንተ ላይ በተወረደውና ከአንተ በፊትም በተወረደው አምነናል ወደሚሉት፤ አላየህምን በእርሱ እንዲክዱ በእርግጥ የታዘዙ ሲኾኑ ወደ ጣዖት መፋረድን ይፈልጋሉ፡፡ ሰይጣንም (ከእውነት) የራቀን መሳሳት ሊያሳስታቸው ይፈልጋል፡፡ 4|61|ለእነርሱም፡- «አላህ ወደ አወረደው (ቁርኣን)ና ወደ መልክተኛው ኑ» በተባሉ ጊዜ መናፍቃን ከአንተ መሸሽን ሲሸሹ ታያቸዋለህ፡፡ 4|62|እጆቻቸውም ባስቀደሙት (ጥፋት) መከራ በደረሰችባቸውና ከዚያም «ደግን ሐሳብና ማስማማትን እንጅ ሌላ አልሻንም» በማለት በአላህ የሚምሉ ኾነው በመጡህ ጊዜ እንዴት ይኾናሉ 4|63|እነዚህ እነዚያ አላህ በልቦቻቸው ውስጥ ያለውን ሁሉ የሚያውቅባቸው ናቸው፡፡ እነርሱንም ተዋቸው ገሥጻቸውም፡፡ ለእነርሱም በነፍሶቻቸው ውስጥ ስሜት ያለውን ቃል ተናገራቸው፡፡ 4|64|ማንንም መልክተኛ በአላህ ፈቃድ ሊታዘዙት እንጅ አልላክንም፡፡ እነሱም ነፍሶቻቸውን በበደሉ ጊዜ ወደ አንተ ቢመጡና አላህንም ምሕረትን በለመኑ መልክተኛውም ለነርሱ ምሕረትን በለመነላቸው ኖሮ አላህን ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ኾኖ ባገኙት ነበር፡፡ 4|65|በጌታህም እምላለሁ በመካከላቸው በተከራከሩበት ፍርድ እስከሚያስፈርዱህ ከዚያም ከፈረድከው ነገር በነፍሶቻቸው ውስጥ ጭንቀትን እስከማያገኙና ፍጹም መታዘዝንም እስከሚታዘዙ ድረስ አያምኑም፤ (ምእመን አይኾኑም)፡፡ 4|66|እኛም በእነርሱ ላይ፡- «ነፍሶቻችሁን ግደሉ ወይም ከአገሮቻችሁ ውጡ» ማለትን በጻፍን ኖሮ ከነሱ ጥቂቶቹ እንጅ ባልሠሩት ነበር፡፡ እነርሱም በእርሱ የሚገሰጹበትን ነገር በሠሩ ኖሮ ለነሱ መልካምና (በእምነታቸው ላይ) ለመርጋትም በጣም የበረታ በኾነ ነበር፡፡ 4|67|ያን ጊዜም ከእኛ ዘንድ ታላቅን ምንዳ በሰጠናቸው ነበር፡፡ 4|68|ቀጥተኛውንም መንገድ በእርግጥ በመራናቸው ነበር፡፡ 4|69|አላህንና መልክተኛውንም የሚታዘዝ ሰው እነዚያ ከእነዚያ አላህ በእነርሱ ላይ ከለገሳቸው ከነቢያት፣ ከጻድቃንም፣ ከሰማዕታትም፣ ከመልካሞቹ ጋር ይኾናሉ፡፡ የእነዚያም ጓደኝነት አማረ፡፡ 4|70|ይህ ችሮታ ከአላህ ነው፡፡ አዋቂነትም በአላህ በቃ፡፡ 4|71|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ጥንቃቄያችሁን ያዙ፡፡ ክፍልፍልም Ñድ ሆናችሁ (ለዘመቻ) ውጡ፡፡ ወይም ተሰብስባችሁ ውጡ፡፡ 4|72|ከእናንተም ውስጥ በእርግጥ (ከዘመቻ) ወደ ኋላ የሚንጓደድ ሰው አልለ፡፡ አደጋም ብታገኛችሁ ከእነሱ ጋር ተጣጅ ባልኾንኩ ጊዜ አላህ በእኔ ላይ በእርግጥ ለገሰልኝ ይላል፡፡ 4|73|ከአላህም የኾነ ችሮታ ቢያገኛችሁ በእናንተና በእርሱ መካከል ፍቅር እንዳልነበረች ሁሉ «ታላቅ ዕድልን አገኝ ዘንድ ከነሱ ጋር በኾንኩ ወይ ምኞቴ!» ይላል፡፡ 4|74|እነዚያም ቅርቧን ሕይወት በመጨረሻይቱ ሕይወት የሚለውጡ በአላህ መንገድ ይጋደሉ፡፡ በአላህም መንገድ የሚጋደል፣ የሚገደልም ወይም የሚያሸንፍ ታላቅ ምንዳን በእርግጥ እንሰጠዋለን፡፡ 4|75|በአላህ መንገድና ከወንዶች ከሴቶችና ከልጆችም የኾኑትን ደካሞች እነዚያን፡- «ጌታችን ሆይ! ከዚች ባለቤቶችዋ በዳይ ከኾኑት ከተማ አውጣን ከአንተም ዘንድ ለእኛ አሳዳሪን አድርግልን ከአንተ ዘንድም ለእኛ ረዳትን አድርግልን» የሚሉትን (ለማዳን) የማትጋደሉት ለእናንተ ምን አላችሁ 4|76|እነዚያ ያመኑት ሰዎች በአላህ መንገድ ይጋደላሉ፡፡ እነዚያ የካዱትም በጣዖት መንገድ ይጋደላሉ፡፡ የሰይጣንንም ጭፍሮች ተጋደሉ፡፡ የሰይጣን ተንኮል ደካማ ነውና፡፡ 4|77|ወደእነዚያ ለእነርሱ፡- እጆቻችሁን (ከመጋደል) ሰብስቡ፣ ሶላትንም ደንቡን ጠብቃችሁ ስገዱ፣ ግዴታ ምጽዋትም ስጡ ወደ ተባሉት አላየህምን በእነርሱም ላይ መጋደል በተጻፈ ጊዜ ከእነሱ ከፊሎቹ ወዲያውኑ ሰዎችን አላህን እንደሚፈሩ ወይም የበለጠ ፍራቻን ይፈራሉ፡፡ «ጌታችን ሆይ! በእኛ ላይ መጋደልን ለምን ደነገግክ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ አታቆየንም ኖሮአልን» ይላሉም፡፡ «የቅርቢቱ ሕይወት ጥቅም አነስተኛ ነው፡፡ መጨረሻይቱም ዓለም አላህን ለሚፈራ ሰው በላጭ ናት፡፡ በተምር ፍሬ ውስጥ ያለን ክር ያህል እንኳ አትበደሉም» በላቸው፡፡ 4|78|«የትም ስፍራ ብትኾኑ በጠነከሩ ሕንጻዎች ውስጥ ብትኾኑም እንኳ ሞት ያገኛችኋል፡፡ ደግም ነገር ብታገኛቸው ይህች ከአላህ ዘንድ ናት» ይላሉ፡፡ መከራም ብታገኛቸው «ይህቺ ከአንተ ዘንድ ናት» ይላሉ፡፡ «ሁሉም (ደጉም ክፉውም) ከአላህ ዘንድ ነው» በላቸው፡፡ ለእነዚህም ሰዎች ንግግርን ሊረዱ የማይቀርቡት ምን አላቸው 4|79|ከደግ ነገር የሚያገኝህ ከአላህ (ችሮታ) ነው፡፡ ከመከራም የሚደርስብህ ከራስህ (ጥፋት የተነሳ) ነው፡፡ ለሰዎችም ሁሉ መልክተኛ ኾነህ ላክንህ፡፡ መስካሪም በአላህ በቃ፡፡ 4|80|መልክተኛውን የሚታዘዝ ሰው በእርግጥ አላህን ታዘዘ፡፡ ከትእዛዝም የሸሸ ሰው (አያሳስብህ)፡፡ በእነሱ ላይ ጠባቂ አድርገን አልላክንህምና፡፡ 4|81|«(ነገራችን) መታዘዝ ነው» ይላሉም፤ ከአንተም ዘንድ በወጡ ጊዜ ከነርሱ ከፊሎቹ ከዚያ (በፊትህ) ከሚሉት ሌላን (በልቦቻቸው) ያሳድራሉ፡፡ አላህም የሚያሳድሩትን ነገር ይጽፋል፡፡ ስለዚህ ተዋቸው፡፡ በአላህም ላይ ተጠጋ፡፡ መጠጊያም በአላህ በቃ፡፡ 4|82|ቁርኣንን አያስተነትኑምን ከአላህ ሌላ ዘንድ በነበረ ኖሮ በርሱ ውስጥ ብዙን መለያየት ባገኙ ነበር፡፡ 4|83|ከጸጥታ ወይም ከፍርሃት አንዳች (ወሬ) በመጣላቸውም ጊዜ እርሱን ያጋንናሉ፡፡ ወደ መልክተኛውና ከእነርሱ ወደ ትዕዛዙ ባለቤቶች (ወደ ዐዋቂዎቹ) በመለሱት ኖሮ እነዚያ ከእነርሱ (ነገሩን) የሚያውጣጡት ባወቁት ነበር፡፡ በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ ኖሮ ከጥቂቶች በስተቀር ሰይጣንን በተከተላችሁ ነበር፡፡ 4|84|በአላህም መንገድ ተጋደል፡፡ ራስህን እንጅ ሌላን አትገደድም፡፡ ምእምናንንም (በመጋደል ላይ) አደፋፍር፡፡ አላህ የእነዚያን የካዱትን ኀይል ሊከለክል ይከጀላል፡፡ አላህም በኀይል በመያዙ የበረታ ቅጣቱም የጠነከረ ነው፡፡ 4|85|መልካም መታደግን የሚታደግ ሰው ለእርሱ ከርስዋ ዕድል ይኖረዋል፡፡ መጥፎ መታደግንም የሚታደግ ሰው ለእርሱ ከርስዋ ድርሻ ይኖረዋል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 4|86|በሰላምታ በተከበራችሁም ጊዜ ከእርሷ ይበልጥ ባማረ (ሰላምታ) አክብሩ፡፡ ወይም (እርሷኑ) መልሷት፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ተቆጣጣሪ ነውና፡፡ 4|87|አላህ ከእርሱ በስተቀር አምላክ የለም፡፡ ወደ ትንሣኤ ቀን በርሱ ጥርጥር የሌለበት ሲኾን በእርግጥ ይሰበስባችኋል፡፡ በንግግርም ከአላህ ይበልጥ እውነተኛ ማነው 4|88|በመናፍቃንም (ነገር) አላህ በሥራዎቻቸው ወደ ክህደት የመለሳቸው ሲኾኑ ሁለት ክፍሎች የኾናችሁት ለናንተ ምን አላችሁ አላህ ያጠመመውን ሰው ልታቀኑ ታስባላችሁን አላህም ያሳሳተውን ሰው ለእርሱ መንገድን ፈጽሞ አታገኝለትም፡፡ 4|89|(እነርሱ) እንደ ካዱ ብትክዱና እኩል ብትኾኑ ተመኙ! በአላህም ሃይማኖት እስከሚሰደዱ ድረስ ከነሱ ወዳጆችን አትያዙ፡፡ (ከእምነት) ቢያፈገፍጉም ያዙዋቸው፤ (ማርኩዋቸው)፡፡ ባገኛችሁበትም ስፍራ ግደሉዋቸው፡፡ ከእነሱም ወዳጅንና ረዳትን አትያዙ፡፡ 4|90|እነዚያ በእናንተና በእነርሱ መካከል ቃል ኪዳን ወዳላቸው ሕዝቦች የሚጠጉና ወይም እናንተን ለመጋደል ወይም ወገኖቻቸውን ለመጋደል ልቦቻቸው የተጨነቁ ኾነው የመጧዋችሁ ሲቀሩ፤ (እነዚያንስ አትጋደሉዋቸው)፡፡ አላህም በሻ ኖሮ በእናንተ ላይ ኀይል በሰጣቸውና በተጋደሉዋችሁ ነበር፡፡ ቢተዋችሁና ባይጋደሉዋችሁም ወደ እናንተም እርቅን ቢያቀርቡ አላህ ለእናንተ በነሱ ላይ (የመጋደል) መንገድን አላደረገም፡፡ 4|91|ሌሎች ከእናንተ ለመዳን ከወገኖቻቸውም ለመዳን የሚፈልጉን ታገኛላችሁ፡፡ ወደ እውከት እንዲመለሱ በተጠሩ ቁጥር በርሷ ውስጥ ይመለሳሉ፡፡ ባይተውዋችሁና እርቅንም ባያቀርቡላችሁ፣ እጆቻቸውንም ባይሰበስቡ፣ ባገኛችኋቸው ስፍራ ማርኩዋቸው፡፡ ግደሉዋቸውም፡፡ እነዚያንም ለእናንተ በነሱ ላይ ግልጽ ማስረጃን አድርገናል፡፡ 4|92|ለምእመንም በስሕተት ካልኾነ በቀር ምእመንን መግደል አይገባውም፡፡ ምእመንንም በስህተት የገደለ ሰው ያመነችን ጫንቃ (ባሪያ) ነጻ ማውጣትና ወደ ቤተሰቦቹም የምትሰጥ ጉማ ምሕረት ካላደረጉለት በስተቀር (መክፈል) አለበት፡፡ እርሱ (ተገዳዩ) ምእመን ሲኾን ለእናንተ ጠላት ከኾኑትም ሕዝቦች ቢኾን ያመነችን ጫንቃ ነጻ ማውጣት (ብቻ) አለበት፡፡ በእናንተና በእነሱ መካከል ቃል ኪዳን ካላቸውም ሕዝቦች ቢኾን ወደ ቤተሰቦቹ በእጅ የምትሰጥ ጉማና ያመነችን ጫንቃ ነጻ ማውጣት አለበት፡፡ ያላገኘ ሰውም ተከታታዮችን ሁለት ወሮች መጾም አለበት፡፡ አላህ መጸጸትን ለመቀበል (ደነገገላችሁ)፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|93|ምእመንንም አስቦ የሚገድል ሰው ቅጣቱ በውስጧ ዘውታሪ ሲኾን ገሀነም ናት፡፡ አላህም በርሱ ላይ ተቆጣ፡፡ ረገመውም፡፡ ለእርሱም ከባድ ቅጣትን አዘጋጀ፡፡ 4|94|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በአላህ መንገድ (ለመጋደል) በተጓዛችሁ ጊዜ አስረግጡ፡፡ ሰላምታንም ወደናንተ ላቀረበ ሰው የቅርቢቱን ሕይወት ጥቅም የምትፈልጉ ኾናችሁ ምእመን አይደለህም አትበሉ፡፡ አላህም ዘንድ ብዙ ዘረፋዎች አሉ፡፡ ከዚህ በፊት እንደዚሁ ነበራችሁ፡፡ አላህም በእናንተ ላይ ለገሰ ስለዚህ አስተውሉ፡፡ አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነውና፡፡ 4|95|ከምእመናን የጉዳት ባለቤት ከኾኑት በቀር ተቀማጮቹና በአላህ መንገድ በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸው የሚታገሉት አይተካከሉም፡፡ በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸው የሚታገሉትን አላህ በተቀማጮቹ ላይ በደረጃ አበለጠ፡፡ ለሁሉም አላህ መልካሚቱን (ገነት) ተስፋ ሰጠ፡፡ ታጋዮቹንም በተቀማጮቹ ላይ አላህ በታላቅ ምንዳ አበለጠ፡፡ 4|96|ከእርሱ ዘንድ በኾኑ ደረጃዎች (አበለጠ)፡፡ ምሕረትንም አደረገ፡፡ እዝነትም አዘነላቸው፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 4|97|እነዚያ (ለእምንት ባለመሰደድ) ነፍሶቻቸውን በዳዮች ኾነው መላእክት (በበድር) የገደሉዋቸው (መላእክት ለነርሱ) «በምን ነገር ላይ ነበራችሁ» አሏቸው፡፡ «በምድር ውስጥ ደካሞች ነበርን» አሉ፡፡ «የአላህ ምድር ትሰደዱባት ዘንድ ሰፊ አልነበረችምን» አሉዋቸው፡፡ እነዚያም መኖሪያቸው ገሀነም ናት፡፡ በመመለሻነትም ከፋች! 4|98|ግን ከወንዶችና ከሴቶች ከሕፃኖችም ሲኾኑ (ለመውጣት) መላን የማይችሉና መንገድንም የማይምመሩ ደካሞች (ቅጣት የለባቸውም) 4|99|እነዚያም አላህ ከእነርሱ ይቅርታ ሊያደርግ ይሻል፡፡ አላህም ይቅር ባይ መሓሪ ነው፡፡ 4|100|በአላህም መንገድ የሚሰደድ ሰው በምድር ውስጥ ብዙ መሰደጃንና ምቾትን ያገኛል፡፡ ወደ አላህና ወደ መልክተኛውም ስደተኛ ኾኖ ከቤቱ የሚወጣ ከዚያም (በመንገድ) ሞት የሚያገኘው ሰው ምንዳው በእርግጥ አላህ ዘንድ ተረጋገጠ፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 4|101|በምድርም ላይ በተጓዛችሁ ጊዜ እነዚያ የካዱት ያውኩናል ብላችሁ ብትፈሩ ከሶላት (ባለ አራት ረከዓት የኾኑትን) ብታሳጥሩ በናንተ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ ከሓዲዎች ለእናንተ በእርግጥ ግልጽ ጠላቶች ናቸውና፡፡ 4|102|በውስጣቸውም በኾንክና ሶላትን ለእነርሱ ባስገደድካቸው ጊዜ ከእነሱ አንዲት ጭፍራ ካንተ ጋር ትቁም፡፡ መሣሪያዎቻቸውንም ይያዙ፡፡ በግንባራቸውም በተደፉ ጊዜ ከስተኋላችሁ ይኹኑ፡፡ (እነዚህ ይኺዱና) ያልሰገዱትም ሌሎቹ ጭፍሮች ይምጡ፡፡ ከአንተም ጋር ይስገዱ፡፡ ጥንቃቄያቸውንና መሣሪያዎቻቸውንም ይያዙ፡፡ እነዚያ የካዱት ከመሣሪያዎቻችሁና ከጓዞቻችሁ ብትዘነጉና በእናንተ ላይ አንዲትን መዘንበል ቢዘነበሉ ተመኙ፡፡ ከዝናብም የኾነ ችግር በእናንተ ቢኖር ወይም ሕመምተኞች ብትኾኑ መሣሪያዎቻችሁን ብታስቀምጡ በናንተ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ ጥንቃቄያችሁንም ያዙ፡፡ አላህ ለከሓዲዎች አዋራጅን ቅጣት አዘጋጀ፡፡ 4|103|ሶላትንም በፈጸማችሁ ጊዜ ቆማችሁም ተቀምጣችሁም በጎኖቻችሁም ላይ ተጋድማችሁ አላህን አውሱ፡፡ በረጋችሁም ጊዜ ሶላትን (አሟልታችሁ) ስገዱ፡፡ ሶላት በምእምናን ላይ በጊዜያት የተወሰነች ግዴታ ናትና፡፡ 4|104|ሰዎቹንም በመፈለግ አትስነፉ፡፡ (ስትቆስሉ) የምትታመሙ ብትኾኑ እናንተ እንደምትታመሙ እነሱም ይታመማሉ፡፡ የማይከጅሉትንም ከአላህ ትከጅላላችሁ፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|105|እኛ በሰዎች መካከል አላህ ባሳወቀህ ልትፈርድ ወደ አንተ መጽሐፉን በእውነት አወረድን፡፡ ለከዳተኞችም ተከራካሪ አትኹን፡፡ 4|106|አላህንም ምሕረትን ለምን፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 4|107|ከእነዚያም ነፍሶቻቸውን ከሚበድሉት ላይ አትከራከር፡፡ አላህ ከዳተኛ ኃጢአተኛ የኾነን ሰው አይወድምና፡፡ 4|108|ከሰው ይደበቃሉ፡፡ አላህም እርሱ (በዕውቀቱ) ከእነሱ ጋር ሲኾን ከንግግር የማይወደውን ነገር (በልቦቻቸው) በሚያሳድሩ ጊዜ (ከእርሱ) አይደበቁም፡፡ አላህም በሚሠሩት ሁሉ (በዕውቀቱ) ከባቢ ነው፡፡ 4|109|እነሆ እናንተ እነዚያ በቅርቢቱ ሕይወት ከነሱ የተከራከራችሁ ናችሁ፡፡ በትንሣኤ ቀን አላህን ስለእነሱ የሚከራከር ማን ነው ወይስ ለእነሱ ኃላፊና መመኪያ የሚኾን ማን ነው 4|110|መጥፎም የሚሠራ ሰው ወይም ነፍሱን የሚበድል ከዚያም (ተጸጽቶ) አላህን ምሕረት የሚለምን አላህን መሓሪ አዛኝ ኾኖ ያገኘዋል፡፡ 4|111|ኀጢአትንም የሚሠራ ሰው የሚሠራው ጥፋት በራሱ ላይ ነው፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፤ 4|112|ኀጢአትን ወይም አበሳን የሚሠራም ሰው ከዚያም በእርሱ ንጹሕን ሰው የሚሰድብ ቅጥፈትንና ግልጽ አበሳን በቁርጥ ተሸከመ፡፡ 4|113|የአላህም ችሮታና እዝነቱ ባንተ ላይ ባልነበረ ኖሮ ከእነሱ የኾኑ ጭፍሮች ሊያሳስቱህ ባሰቡ ነበር፡፡ ነፍሶቻቸውንም እንጅ ሌላን አያሳስቱም፡፡ በምንም አይጐዱህም፡፡ አላህም በአንተ ላይ መጽሐፍንና ጥበብን አወረደ፡፡ የማታውቀውንም ሁሉ አስተማረህ፡፡ የአላህም ችሮታ በአንተ ላይ ታላቅ ነው፡፡ 4|114|ከውይይታቸው በምጽዋት ወይም በበጎ ሥራ ወይም በሰዎች መካከል በማስታረቅ ከሚያዙ ሰዎች ውይይት በስተቀር በብዙው ውስጥ ደግ ነገር የለበትም፡፡ ይኸንንም (የተባለውን) የአላህን ውዴታ ለመፈለግ የሚሠራ ሰው ታላቅ ምንዳን እንሰጠዋለን፡፡ 4|115|ቅኑም መንገድ ለእርሱ ከተገለጸ በኋላ መልክተኛውን የሚጨቃጨቅና ከምእምኖቹ መንገድ ሌላ የኾነን የሚከተል ሰው (በዚህ ዓለም) በተሾመበት (ጥመት) ላይ እንሾመዋለን፤ ገሀነምንም እናገባዋለን፡፡ መመለሻይቱም ከፋች! 4|116|አላህ በርሱ የማጋራትን (ወንጀል) አይምርም፡፡ ከዚህም ወዲያ ያለውን ለሚሻው ሰው ይምራል፡፡ በአላህም የሚያጋራ ሰው (ከእውነት) የራቀን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ፡፡ 4|117|ከእርሱ ሌላ እንስታትን እንጅ አይገዙም፡፡ አመጸኛ ሰይጣንንም እንጅ ሌላን አይግገዙም፡፡ 4|118|«አላህ የረገመውን ከባሮችህም የተወሰነን ድርሻ በእርግጥ እይዛለሁ» ያለውን (ሰይጣን እንጅ ሌላን አይከተሉም)፡፡ 4|119|በእርግጥ አጠማቸዋለሁም፡፡ (ከንቱን) አስመኛቸዋለሁም፡፡ አዛቸውምና የእንስሶችን ጆሮዎች ይተለትላሉ፡፡ አዛቸውምና የአላህን ፍጥረት ይለውጣሉ፤ (ያለውን ይከተላሉ)፡፡ ከአላህም ሌላ ሰይጣንን ረዳት አድርጎ የሚይዝ ሰው ግልጽ ክስረትን በአርግጥ ከሰረ፡፡ 4|120|(የማይፈጸመውን) ተስፋ ይሰጣቸዋል፡፡ ያስመኛቸዋልም፡፡ ሰይጣንም ለማታለል እንጅ አይቀጥራቸውም፡፡ 4|121|እነዚያ መኖሪያቸው ገሀነም ናት፡፡ ከርስዋም መሸሻን አያገኙም፡፡ 4|122|እነዚያም ያመኑና በጎ ሥራዎችን የሠሩ በሥራቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች ዘላለም በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ እናገባቸዋለን፡፡ አላህ እውነተኛን ተስፋ ሰጣቸው፡፡ በንግግርም ከአላህ ይበልጥ እውነተኛ ማን ነው 4|123|(ነገሩ) በምኞታችሁና በመጽሐፉ ሰዎች ምኞት አይደለም፡፡ መጥፎን የሚሠራ ሰው በእርሱ ይቀጣል፡፡ ለእርሱም ከአላህ ሌላ ጠባቂንም ረዳትንም አያገኝም፡፡ 4|124|ከወንድ ወይም ከሴት እርሱ አማኝ ኾኖ ከበጎ ሥራዎች አንዳችን የሚሠራም ሰው እነዚያ ገነትን ይገባሉ፡፡ በተምር ፍሬ ላይ ያለችን ነጥብ ያክል እንኳ አይበደሉም፡፡ 4|125|እርሱ መልካም ሠሪ ኾኖ ፊቱን ለአላህ ከሰጠና የኢብራሂምንም መንገድ ቀጥተኛ ሲኾን ከተከተለ ሰው ይበልጥ ሃይማኖቱ ያማረ ማን ነው አላህም ኢብራሂምን ፍጹም ወዳጅ አድርጐ ያዘው፡፡ 4|126|በሰማያት ያለውና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ በዕውቀት ከባቢ ነው፡፡ 4|127|በሴቶችም ነገር ያስተቹሃል፡፡ አላህ በእነርሱ ይነግራችኋል፡፡ ያም በመጽሐፉ በእናንተ ላይ የሚነበበው በእነዚያ ለእነርሱ (ከውርስ) የተጻፈላቸውን በማትሰጧቸውና ልታገቧቸው በማትፈልጉት የቲሞች ሴቶች (ይህንን እንዳታደርጉ) ከሕፃናትም ለኾኑት ደካሞች መብታቸውን እንድትሰጡ ለየቲሞችም በትክክል አንድትቆሙ (ይነግራችኋል) በላቸው፡፡ ከበጎም ሥራ ማናቸውንም ብትሠሩ አላህ እርሱን ዐዋቂ ነው፡፡ 4|128|ሴትም ከባልዋ ጥላቻን ወይም ፊቱን ማዞርን ብታውቅ በመካከላቸው መስማማትን ቢስማሙ በሁለቱ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ መታረቅም መልካም ነው፡፡ ነፍሶችም ንፍገት ተጣለባቸው፡፡ መልካምም ብትሠሩ ብትጠነቀቁም አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 4|129|በሴቶችም መካከል ምንም እንኳ ብትጓጉ (በፍቅር) ለማስተካከል አትችሉም፡፡ እንደ ተንጠለጠለችም አድርጋችሁ ትተዋት ዘንድ (ወደምትወዷት) መዘንበልን ሁሉ አትዘንበሉ፡፡ ብታበጁም ብትጠነቀቁም አላህ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 4|130|ቢለያዩም አላህ ሁሉንም በችሮታው ያብቃቃቸዋል፡፡ አላህም ችሮታው ሰፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|131|በሰማያት ያለውና በምድርም ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ እነዚያንም ከበፊታችሁ መጽሐፍን የተሰጡትን እናንተንም አላህን ፍሩ በማለት በእርግጥ አዘዝን፡፡ ብትክዱም በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ (አትጐዱትም)፡፡ አላህም ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡ 4|132|በሰማያት ያለውና በምድርም ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ መመከያም በአላህ በቃ፡፡ 4|133|ሰዎች ሆይ!(አላህ) ቢሻ ያስወግዳችኋል፡፡ ሌሎችንም ያመጣል፡፡ አላህም በዚህ ላይ ቻይ ነው፡፡ 4|134|የቅርቢቱን ዓለም ምንዳ የሚፈልግ የኾነ ሰው አላህ ዘንድ የቅርቢቱና የመጨረሻይቱ ምንዳ አልለ፡፡ አላህም ሰሚ ተመልካች ነው፡፡ 4|135|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በትክክል (ፍትሕ) ቀዋሚዎች በነፈሶቻችሁ ወይም በወላጆችና በቅርብ ዘመዶች ላይ ቢኾንም እንኳ ለአላህ መስካሪዎች ኹኑ፡፡ ሀብታም ወይም ድኻ ቢኾን አላህ በእነርሱ (ከእናንተ) ይበልጥ ተገቢ ነው፡፡ እንዳታደሉም ዝንባሌን አትከተሉ፡፡ ብታጠምሙም ወይም (መመስከርን) ብትተው አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 4|136|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በአላህና በመልክተኛው በዚያም በመልክተኛው ላይ ባወረደው መጽሐፍ በዚያም ከበፊቱ ባወረደው መጽሐፍ እመኑ፡፡ በአላህና በመላእክቱም፣ በመጽሐፎቹም፣ በመልክተኞቹም፣ በመጨረሻውም ቀን፣ የካደ ሰው (ከእውነት) የራቀን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ፡፡ 4|137|እነዚያ (በሙሳ) ያመኑና ከዚያም (ወይፈንን በመገዛት) የካዱ ከዚያም (በእርሱ) ያመኑ ከዚያም (በዒሳ) የካዱ ከዚያም (በሙሐመድ) ክሕደትን የጨመሩ አላህ ለእነሱ የሚምራቸውና ቅኑን መንገድ የሚመራቸው አይደለም፡፡ 4|138|መናፍቃንን ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት ያላቸው መኾኑን አብስራቸው፡፡ 4|139|እነዚያ ከምእምናን ሌላ ከሓዲዎችን ወዳጆች አድርገው የሚይዙ እነሱ ዘንድ ልቅናን ይፈልጋሉን ልቅናውም ሁሉ ለአላህ ብቻ ነው፡፡ 4|140|በእናንተም ላይ በመጽሐፉ ውስጥ የአላህን አንቀጾች በርሷ ሲካድባትና በርሷም ሲላገጥባት በሰማችሁ ጊዜ በሌላ ወሬ ውስጥ እስከሚገቡ ድረስ ከእነሱ ጋር አትቀመጡ፡፡ ማለትን በእርግጥ አወረደ፡፡ እናንተ ያንጊዜ ብጤያቸው ናችሁና፡፡ አላህ መናፍቃንን እና ከሓዲዎችን በሙሉ በገሀነም ውስጥ ሰብሳቢ ነውና፡፡ 4|141|እነዚያ በእናንተ (የጊዜን መዘዋወር) የሚጠባበቁ ናቸው፡፡ ለእናንተም ከአላህ የኾነ አሸናፊነት «ቢኖራችሁ ከእናንተ ጋር አልነበርንምን» ይላሉ፡፡ ለከሓዲዎችም ዕድል ቢኖር «(ከአሁን በፊት) በእናንተ ላይ አልተሾምንምን (እና አልተውናችሁምን) ከምእምናንም (አደጋ) አልከለከልናችሁምን» ይላሉ፡፡ አላህም በትንሣኤ ቀን በመካከላችሁ ይፈርዳል፡፡ አላህም ለከሓዲዎች በምእምናን ላይ መንገድን በፍጹም አያደርግም፡፡ 4|142|መናፍቃን አላህን ያታልላሉ፡፡ እርሱም አታላያቸው ነው፡፡ (ይቀጣቸዋል)፡፡ ወደ ሶላትም በቆሙ ጊዜ ታካቾች ስዎችን የሚያሳዩ ኾነው ይቆማሉ፡፡ አላህንም ጥቂትን እንጅ አያወሱም፡፡ 4|143|በዚህ መካከል ወላዋዮች ኾነው (ያሳያሉ)፡፡ ወደእነዚህም ወደእነዚያም አይደሉም፡፡ አላህም ያሳሳተውን ሰው ለእርሱ (የቅንነት) መንገድን በፍፁም አታገኝለትም፡፡ 4|144|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከምእምናን ሌላ ከሓዲዎችን ወዳጆች አድርጋችሁ አትያዙ፤ ለአላህ በናንተ ላይ ግልጽ ማስረጃዎችን ልታደርጉ ትፈልጋላችሁን 4|145|መናፍቃን በእርግጥ ከእሳት በታችኛው አዘቅት ውስጥ ናቸው፡፡ ለእነሱም ረዳትን አታገኝላቸውም፡፡ 4|146|እነዚያ የተመለሱ (ሥራቸውን) ያሳመሩም፤ በአላህም የተጠበቁ፤ ሃይማኖታቸውንም ለአላህ ፍጹም ያደረጉ ሲቀሩ፡፡ እነዚያስ ከምእምናን ጋር ናቸው፡፡ ለምእምናንም አላህ ታላቅን ምንዳ በእርግጥ ይሰጣል፡፡ 4|147|ብታመሰግኑና ብታምኑ አላህ እናንተን በመቅጣት ምን ያደርጋል አላህም ወረታን መላሽ ዐዋቂ ነው፡፡ 4|148|አላህ ከንግግር በክፉው መጮህን ከተበደለ ሰው (ጩኸት) በቀር አይወድም፡፡ አላህ ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 4|149|ደግ ነገርን ብትገልጹ ወይም ብትደብቁት ወይም ከመጥፎ ነገር (ከበደል) ይቅርታ ብታደርጉ አላህ ይቅር ባይ ኃያል ነው፡፡ 4|150|እነዚያ በአላህና በመልክተኞቹ የሚክዱ፣ በአላህና በመልክተኞቹም መካከል መለየትን የሚፈልጉ፣ «በከፊሉም እናምናለን በከፊሉም እንክዳለን» የሚሉ፣ በዚህም መካከል መንገድን ሊይዙ የሚፈልጉ፤ 4|151|እነዚያ በውነት ከሓዲዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ ለከሓዲዎችም አዋራጅን ቅጣት አዘጋጅተናል፡፡ 4|152|እነዚያም በአላህና በመልክተኞቹ ያመኑ ከነርሱም በአንድም መካከል ያልለዩ እነዚያ ምንዳዎቻቸውን በእርግጥ ይሰጣቸዋል፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 4|153|የመጽሐፉ ሰዎች በነሱ ላይ ከሰማይ መጽሐፍን እንድታወርድ ይጠይቁሃል፡፡ ከዚያም የከበደን (ነገር) ሙሳን በእርግጥ ጠይቀዋል፡፡ «አላህንም በግልጽ አሳየን» ብለዋል፡፡ በበደላቸውም መብረቅ ያዘቻቸው፡፡ ከዚያም ተዓምራቶች ከመጡላቸው በኋላ ወይፈኑን (አምላክ አድርገው) ያዙ፡፡ ከዚያም ይቅር አልን፡፡ ሙሳንም ግልጽ ስልጣንን ሰጠነው፡፡ 4|154|በቃል ኪዳናቸውም ምክንያት የጡርን ተራራ ከበላያቸው አነሳን፡፡ ለእነሱም «ደጃፉን አጎንባሾች ኾናችሁ ግቡ» አልን፡፡ ለእነርሱም «በሰንበት ቀን ትዕዛዝን አትተላልፉ» አልን፡፡ ከእነሱም ከባድን ቃል ኪዳን ያዝን፡፡ 4|155|ቃል ኪዳናቸውንም በማፍረሳቸው፣ በአላህም አንቀጾች በመካዳቸው፣ ነቢያትንም ያለ አግባብ በመግደላቸውና «ልቦቻችን ሽፍኖች ናቸው» በማለታቸው ምክንያት (ረገምናቸው)፡፡ በእውነቱ በክህደታቸው ምክንያት አላህ በርሷ (በልቦቻቸወ) ላይ አተመ፡፡ ስለዚህ ጥቂትን እንጅ አያምኑም፡፡ 4|156|በመካዳቸውም በመርየም ላይ ከባድ ቅጥፈትን በመናገራቸውም ምክንያት (ረገምናቸው)፡፡ 4|157|«እኛ የአላህን መልክተኛ የመርየምን ልጅ አልመሲሕ ዒሳን ገደልን» በማለታቸውም (ረገምናቸው)፡፡ አልገደሉትም አልሰቀሉትምም፡፡ ግን ለእነሱ (የተገደለው ሰው በዒሳ) ተመሰለ፡፡ እነዚያም በእርሱ ነገር የተለያዩት ከእርሱ (መገደል) በመጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ ጥርጣሬን ከመከተል በስተቀር በእርሱ ነገር ምንም ዕውቀት የላቸውም፡፡ በእርግጥም አልገደሉትም፡፡ 4|158|ይልቁንስ አላህ (ኢሳን) ወደርሱ አነሳው፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|159|ከመጽሐፉም ሰዎች ከመሞቱ በፊት በእርሱ (በዒሳ) በእርግጥ የሚያምን እንጅ (አንድም) የለም፡፡ በትንሣኤም ቀን በነሱ ላይ መስካሪ ይኾናል፡፡ 4|160|ከእነዚያ ይሁዳውያን ከኾኑትም በተገኘው በደል ሰዎችንም ከአላህ መንገድ በብዙ በመከልከላቸው ምክንያት ለእነሱ ተፈቅደው የነበሩትን ጣፋጮች ምግቦች በእነርሱ ላይ እርም አደረግንባቸው፡፡ 4|161|ከእርሱ በቁርጥ የተከለከሉ ሲኾኑ አራጣንም በመያዛቸውና የሰዎችን ገንዘቦች ያለ አግባብ (በጉቦ) በመብላታቸውም ምክንያት (የተፈቀደላቸውን እርም አደረግንባቸው)፡፡ ከእነሱም ለከሓዲዎቹ አሳማሚን ቅጣት አዘጋጀን፡፡ 4|162|ግን ከነርሱ ውስጥ በዕውቀት የጠለቁትና ምእምናኖቹ በአንተ ላይ በተወረደውና ከአንተም በፊት በተወረደው መጽሐፍ የሚያምኑ ሲኾኑ ሶላትንም ደንቡን ጠብቀው ሰጋጆችን (እናመሰግናለን)፡፡ ዘካንም ሰጪዎቹ በአላህና በመጨረሻዎቹም ቀን አማኞቹ እነዚያ ታላቅ ምንዳን በእርግጥ እንሰጣቸዋለን፡፡ 4|163|እኛ ወደ ኑሕና ከርሱ በኋላ ወደ ነበሩት ነቢያት እንዳወረድን ወደ አንተም አወረድን፡፡ ወደ ኢብራሂምም፣ ወደ ኢስማዒልም፣ ወደ ኢስሓቅም፣ ወደ ያዕቆብም፣ ወደ ነገዶቹም፣ ወደ ዒሳም፣ ወደ አዩብም፣ ወደ ዩኑስም፣ ወደ ሃሩንና፣ ወደ ሱለይማንም አወረድን፡፡ ለዳውድም ዘቡርን ሰጠነው፡፡ 4|164|ከዚህም በፊት በአንተ ላይ በእርግጥ የተረክናቸውን መልክተኞች ባንተ ላይም ያልተረክናቸውን መልክተኞች (እንደላክን ላክንህ)፡፡ አላህም ሙሳን ማነጋገርን አነጋገረው፡፡ 4|165|ከመልክተኞቹ በኋላ ለሰዎች በአላህ ላይ አስረጅ እንዳይኖር አብሳሪዎችና አስፈራሪዎች የኾኑን መልክተኞች (ላክን)፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|166|ግን አላህ ባንተ ላይ ባወረደው ይመሰክራል፡፡ በዕውቀቱ አወረደው፡፡ መላእክቱም ይመሰክራሉ፡፡ መስካሪም በአላህ በቃ፡፡ 4|167|እነዚያ የካዱት ከአላህም መንገድ ያገዱት (ከእውነት) የራቀን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳቱ፡፡ 4|168|እነዚያ የካዱ የበደሉም አላህ የሚምራቸውና (ቅን) መንገድን የሚመራቸው አይደለም፡፡ 4|169|ግን በውስጧ ዘለዓለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ የገሀነምን መንገድ (ይመራቸዋል)፡፡ ይህም በአላህ ላይ ገር ነው፡፡ 4|170|እናንተ ሰዎች ሆይ! መልክተኛው እውነትን ከጌታችሁ አመጣላችሁ፡፡ እመኑም ለናንተ የተሻለ (ይኾናል)፡፡ ብትክዱም (አትጐዱትም)፡፡ በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነውና፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 4|171|እናንተ የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! በሃይማኖታችሁ ወሰንን አትለፉ፡፡ በአላህም ላይ እውነትን እንጅ አትናገሩ፡፡ የመርየም ልጅ አልመሲሕ ዒሳ የአላህ መልክተኛ ወደ መርየም የጣላት «የኹን» ቃሉም ከእርሱ የኾነ መንፈስም ብቻ ነው፡፡ በአላህና በመልክተኞቹም እመኑ፡፡ « (አማልክት) ሦስት ናቸው» አትበሉም፡፡ ተከልከሉ፤ ለእናንተ የተሻለ ይኾናልና፡፡ አላህ አንድ አምላክ ብቻ ነው፡፡ ለእርሱ ልጅ ያለው ከመኾን የጠራ ነው፡፡ በሰማያትና በምድር ያለ ሁሉ የርሱ ነው፡፡ መመኪያም በአላህ በቃ፡፡ 4|172|አልመሲሕ (ኢየሱስ) ለአላህ ባሪያ ከመኾን ፈጽሞ አይጠየፍም፡፡ ቀራቢዎች የኾኑት መላእክትም (አይጠየፉም)፡፡ እርሱን ከመገዛት የሚጠየፍና የሚኮራም ሰው (አላህ) ሁሉንም ወደ እርሱ በእርግጥ ይሰበስባቸዋል፡፡ 4|173|እነዚያማ ያመኑት መልካሞችንም የሠሩት ምንዳዎቻቸውን ይሞላላቸዋል፡፡ ከችሮታውም ይጨምርላቸዋል፡፡ እነዚያን የተጠየፉትንና የኮሩትንማ አሳማሚን ቅጣት ይቀጣቸዋል፡፡ ከአላህም ሌላ ለእነሱ ዝምድንና ረዳትን አያገኙም፡፡ 4|174|እናንተ ሰዎች ሆይ! ከጌታችሁ ዘንድ በእርግጥ አስረጅ መጣላችሁ፤ ወደእናንተም ገላጭ የኾነን ብርሃን (ቁርኣንን) አወረድን፡፡ 4|175|እነዚያማ በአላህ ያመኑ በርሱም የተጠበቁ ከሱ በኾነው እዝነትና ችሮታ ውስጥ በእርግጥ ያስገባቸዋል፡፡ ወደእርሱም ቀጥተኛ መንገድን ይመራቸዋል፡፡ 4|176|ይጠይቁሃል በላቸው፡- «ወላጅና ልጅ ሳይኖረው በሚወረስ ሰው አላህ ይነግራችኋል፡፡ ለእርሱ ልጅ የሌለው ሰው ቢሞት ለእርሱም እኅት ብትኖረው ለእርስዋ ከተወው ረጀት ግማሹ አላት፡፡ እርሱም ለርሷ ልጅ የሌላት እንደኾነች (በሙሉ) ይወርሳታል፡፡ ሁለት (እኅቶች ወይም ከሁለት በላይ) ቢኾኑም ከተወው ረጀት ከሦስት ሁለት እጁ አላቸው፡፡ ወንድሞች (ና እኅቶች) ወንዶችና ሴቶች ቢኾኑም ለወንዱ የሁለት ሴቶች ድርሻ ብጤ አለው፡፡ አላህ እንዳትሳሳቱ ለእናንተ ያብራራል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡» 5|1|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በቃል ኪዳኖች ሙሉ፡፡ በእናንተ ላይ የሚነበበው ብቻ ሲቀር፡፡ የግመል፣ የከብት፣ የበግና የፍየል እንስሳዎች እናንተ በሐጅ ሥራ ላይ ኾናችሁ ማደንን የተፈቀደ ሳታደረጉ ለእናንተ ተፈቀዱ፡፡ አላህ የሚሻውን ይፈርዳል፡፡ 5|2|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! የአላህ (ክልክል ያደረጋቸውን) ምልክቶች የተፈቀዱ አታድርጉ፡፡ የተከበረውንም ወር በመጋደል አትድፈሩ፡፡ ወደ መካ የሚነዱትን መስዋዕትና የሚታበቱባቸውንም ገመዶች ከጌታቸው ችሮታንና ውዴታን ፈልገው ወደ ተከበረው ቤት አሳቢዎችንም ሰዎች (አትንኩ)፡፡ ከሐጅም ሥራ በወጣችሁ ጊዜ ዐድኑ፡፡ ከተከበረው መስጊድ ስለከለከሉዋችሁ ሰዎችን መጥላትም (በነሱ ላይ) ወሰን እንድታልፉ አይገፋፋችሁ፡፡ በበጎ ነገርና አላህን በመፍራትም ተረዳዱ፡፡ ግን በኃጢአትና ወሰንን በማለፍ አትረዳዱ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና፡፡ 5|3|በክት፣ ፈሳሽ ደምም፣ የእሪያ (አሣማ) ሥጋም፣ በርሱ ከአላህ (ስም) ሌላ የተነሳበትም፣ የታነቀችም፣ ተደብድባ የተገደለችም፣ ተንከባላ የሞተችም፣ በቀንድ ተውግታ የሞተችም፣ ከርሷ አውሬ የበላላትም (ከእነዚህ በሕይወት ደርሳችሁ) ያረዳችሁት ብቻ ሲቀር ለጣዖታትም የታረደው በአዝላምም ዕድልን መፈለጋችሁ በእናንተ ላይ እርም ተደረገ፡፡ ይህ ድርጊት አመጽ ነው፡፡ ዛሬ እነዚያ የካዱት ከሃይማኖታችሁ ተስፋ ቆረጡ፡፡ ስለዚህ አትፍሩዋቸው፡፡ ፍሩኝም፡፡ ዛሬ ሃይማኖታችሁን ለናንተ ሞላሁላችሁ፡፡ ጸጋዬንም በናንተ ላይ ፈጸምኩ፡፡ ለእናንተም ኢስላምን ከሃይማኖት በኩል ወደድኩ፡፡ በረኃብ ወቅት ወደ ኃጢአት ያዘነበለ ሳይሆን (እርም የኾኑትን ለመብላት) የተገደደ ሰውም (ይብላ)፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 5|4|ለእነርሱ ምን እንደተፈቀደላቸው ይጠይቁሃል፡፡ በላቸው፡- «ለእናንተ መልካሞች ሁሉና እነዚያም ከአዳኞች አሰልጣኞች ኾናችሁ ያስተማራችኋቸው (ያደኑት) ተፈቀደላችሁ፡፡ አላህ ከአስተማራችሁ ዕውቀት ታስተምሯቸዋላችሁ፡፡ ለእናንተም ከያዙላችሁ ነገር ብሉ፡፡ በርሱም ላይ የአላህን ስም አውሱ፡፡ አላህንም ፍሩ አላህ ምርመራው ፈጣን ነውና፡፡» 5|5|ዛሬ መልካሞች ሁሉ ለናንተ ተፈቀዱ፡፡ የእነዚያም መጽሐፍን የተሰጡት ሰዎች ምግብ (ያረዱት) ለእናንተ የተፈቀደ ነው፡፡ ምግባችሁም ለነሱ የተፈቀደ ነው፡፡ ከምእመናት ጥብቆቹም ከእነዚያ ከእናንተ በፊት መጽሐፍን ከተሰጡት ሴቶች ጥብቆቹም፤ ዘማዊዎችና (ዝሙተኞች) የምስጢር ወዳጅ ያዢዎች ሳትኾኑ ጥብቆች ኾናችሁ መህሮቻቸውን በሰጣችኋቸው ጊዜ (ልታገቡዋቸው የተፈቀዱ ናቸው)፡፡ ከእምነትም የሚመለስ ሰው በእርግጥ ሥራው ተበላሸ፡፡ በመጨረሻም ቀን እርሱ ከከሳሪዎቹ ነው፡፡ 5|6|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ወደ ሶላት በቆማችሁ (ለመቆም ባሰባችሁ) ጊዜ ፊቶቻችሁን፣ እጆቻችሁንም እስከ ክርኖች እጠቡ፡፡ ራሶቻችሁንም (በውሃ) አብሱ፡፡ እግሮቻችሁንም እስከ ቁርጭምጭሚቶች (እጠቡ)፡፡ (ሴት ጋር በመገናኘት ወይም በሌላ ምክንያት «ጀናባ») ብትኾኑ (ገላችሁን) ታጠቡ፡፡ በሽተኞች ወይም በጉዞ ላይ ብትኾኑም ወይም ከእናንተ አንዳችሁ ከዓይነ ምድር ቢመጣ ወይም ሴቶችን ብትነካኩና ውሃን ባታገኙ ንጹሕን የምድር ገጽ አስቡ ፡፡ ከሱም ፊቶቻችሁንና እጆቻችሁን አብሱ፡፡ አላህ በእናንተ ላይ ምንም ችግር ሊያደርግ አይሻም፡፡ ግን ታመሰግኑ ዘንድ ሊያጠራችሁና ጸጋውን በእናንተ ላይ ሊሞላ ይሻል፡፡ 5|7|በእናንተም ላይ (የለገሰውን) የአላህን ጸጋ ያንንም ሰምተናል ታዘናልም ባላችሁ ጊዜ በርሱ ያጠበቀባችሁን ቃል ኪዳኑን አስታውሱ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ በደረቶች ውስጥ ያለውን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 5|8|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ለአላህ ቀጥተኞች በትክክል መስካሪዎች ኹኑ፡፡ ሕዝቦችንም መጥላት ባለማስተካከል ላይ አይገፋፋችሁ፡፡ አስተካክሉ፡፡ እርሱ (ማስተካከል) ለአላህ ፍራቻ በጣም የቀረበ ነው፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 5|9|እነዚያንም ያመኑትንና በጎ ሥራዎችን የሠሩትን አላህ (ገነትን) ተስፋ አደረገላቸው፡፡ ለእነርሱ ምሕረትና ታላቅ ምንዳ አላቸው፡፡ 5|10|እነዚያም የካዱና በተአምራቶቻችን ያስተባበሉ እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ 5|11|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ሕዝቦች እጆቻቸውን ወደ እናንተ ሊዘረጉ ባሰቡና እጆቻቸውን ከእናንተ ላይ በከለከላችሁ ጊዜ በናንተ ላይ (የዋለላችሁን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ ምእመናንም በአላህ ላይ ይመኩ፡፡ 5|12|አላህም የእስራኤልን ልጆች የጠበቀ ቃል ኪዳን በእርግጥ ያዘባቸው፡፡ ከነርሱም ዐስራ ሁለትን አለቆች አስነሳን፡፡ አላህም አላቸው፤ «እኔ ከናንተ ጋር ነኝ፤ ሶላትን ብታስተካክሉ ግዴታ ምጽዋትንም ብትሰጡ በመልክተኞቼም ብታምኑ ብትረዱዋቸውም ለአላህም መልካም ብድርን ብታበድሩ ኀጢአቶቻችሁን ከናንተ በእርግጥ አብሳለሁ፡፡ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶችም በእርግጥ አገባችኋለሁ፡፡ ከዚህም በኋላ ከእናንተ የካደ ሰው ቀጥተኛውን መንገድ በእርግጥ ተሳሳተ፡፡» 5|13|ቃል ኪዳናቸውንም በማፍረሳቸው ረገምናቸው፡፡ ልቦቻቸውንም ደረቆች አደረግን፡፡ ቃላትን ከቦታዎቻቸው ይለውጣሉ፡፡ በርሱም ከታዘዙበት ነገር ፈንታን ተው፡፡ ከእነሱም ጥቂቶች ሲቀሩ ከነርሱ የኾነን ክዳት የምታውቅባቸው ከመኾን አትወገድም፡፡ ከእነርሱም ይቅርታ አድርግ እለፋቸውም፡፡ አላህ መልካም ሠሪዎችን ይወዳልና፡፡ 5|14|ከእነዚያም እኛ ክርስቲያኖች ነን ካሉት የጠበቀ ቃል ኪዳናቸውን ያዝን፡፡ በእርሱም ከታዘዙበት ነገር ፈንታን ተውት፡፡ ስለዚህ እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ በመካከላቸው ጠብንና ጥላቻን ጣልንባቸው፡፡ አላህም ይሠሩት የነበሩትን ሁሉ በእርግጥ ይነግራቸዋል፡፡ 5|15|የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! ከመጽሐፉ ትሸሽጉት ከነበራችሁት ነገር ብዙውን ለእናንተ የሚገልጽ ከብዙውም የሚተው ሲኾን መልክተኛችን (ሙሐመድ) በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ ከአላህ ዘንድ ብርሃንና ገላጭ መጽሐፍ በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ 5|16|አላህ ውዴታውን የተከተሉትን ሰዎች የሰላምን መንገዶች በእርሱ ይመራቸዋል፡፡ በፈቃዱም ከጨለማዎች ወደ ብርሃን ያወጣቸዋል፡፡ ወደ ቀጥተኛም መንገድ ይመራቸዋል፡፡ 5|17|እነዚያ አላህ እርሱ የመርየም ልጅ አልመሲሕ ነው ያሉ በእርግጥ ካዱ፡፡ የመርየምን ልጅ አልመሲሕን እናቱንም በምድር ያለንም ሁሉ ለማጥፋት ቢሻ ከአላህ ማዳንን የሚችል ማነው በላቸው፡፡ የሰማያትና የምድር የመካከላቸውም ንግሥና የአላህ ብቻ ነው፡፡ የሚሻውን ይፈጥራል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 5|18|አይሁዶችና ክርስቲያኖችም «እኛ የአላህ ልጆችና ወዳጆቹ ነን» አሉ፡፡ «ታዲያ በኃጢአቶቻችሁ ለምን ያሰቃያችኋል አይደላችሁም እናንተ ከፈጠራቸው ሰዎች ናችሁ» በላቸው፡፡ ለሚሻው ሰው ይምራል፡፡ የሚሻውንም ሰው ይቀጣል፡፡ የሰማያትና የምድርም በመካከላቸውም ያለው ሁሉ ንግሥና የአላህ ብቻ ነው፡፡ መመለሻም ወደርሱ ብቻ ነው፡፡ 5|19|እናንተ የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! «አብሳሪና አስፈራሪ አልመጣልንም» እንዳትሉ ከመልክተኞች በመቋረጥ ጊዜ ላይ ሲኾን (ሕጋችንን) የሚያብራራ ኾኖ መልክተኛችን በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ አብሳሪና አስፈራሪም በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 5|20|ሙሳም ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡- «ሕዝቦቼ ሆይ የአላህን ጸጋ በውስጣችሁ ነቢያትን ባደረገና ነገሥታትንም ባደረጋችሁ ከዓለማትም ለአንድም ያልሰጠውን ችሮታ በሰጣችሁ ጊዜ በእናንተ ላይ (ያደረገውን ጸጋ) አስታውሱ፡፡» 5|21|«ሕዝቦቼ ሆይ! ያችን አላህ ለእናንተ ያደረጋትን የተቀደሰችውን መሬት ግቡ፡፡ ወደ ኋላችሁም አትመለሱ፡፡ ከሳሪዎች ኾናችሁ ትመለሳላችሁና፡፡» 5|22|«ሙሳ ሆይ! በርስዋ ውስጥ ኀያላን ሕዝቦች አሉ፡፡ ከርስዋም እስከሚወጡ ድረስ እኛ ፈጽሞ አንገባትም፡፡ ከርስዋም ቢወጡ እኛ ገቢዎች ነን» አሉ፡፡ 5|23|ከእነዚያ (አላህን) ከሚፈሩትና አላህ በእነርሱ ላይ ከለገሰላቸው የኾኑ ሁለት ሰዎች «በእነርሱ (በኀያሎቹ) ላይ በሩን ግቡ፡፡ በገባችሁትም ጊዜ እናንተ አሸናፊዎች ናችሁ፡፡ ምእመናንም እንደኾናችሁ በአላህ ላይ ተመኩ» አሉ፡፡ 5|24|«ሙሳ ሆይ! በውስጧ እስካሉ ድረስ እኛ ፈጽሞ ምን ጊዜም አንገባትም፡፡ ስለዚህ ኺድ አንተና ጌታህ ተጋደሉም እኛ እዚህ ተቀማጮች ነን» አሉ፡፡ 5|25|«ጌታዬ ሆይ እኔ ራሴንና ወንድሜን በቀር (ላስገድድ) አልችልም፡፡ በእኛና በአመጸኞቹም ሕዝቦች መካከል ለይ» አለ፡፡ 5|26|እርስዋም (የተቀደሰችው መሬት) በእነርሱ ላይ አርባ ዓመት እርም ናት፡፡ በምድረ በዳ ይንከራተታሉ፡፡ «በአመጸኞችም ሕዝቦች ላይ አትዘን» አለው፡፡ 5|27|በነርሱም ላይ የአደምን ሁለት ልጆች ወሬ ቁርባንን ባቀረቡና (አላህ) ከአንደኛቸው ተቀብሎ ከሌላው ባልተቀበለ ጊዜ (የኾነውን) በእውነት አንብብላቸው፡፡ «በእርግጥ እገድልሃለሁ» አለው፡፡ (ተገዳዩ) «አላህ የሚቀበለው እኮ ከጥንቁቆቹ ብቻ ነው» አለ፡፡ 5|28|«ልትገድለኝ እጅህን ወደኔ ብትዘረጋ እኔ ልገድልህ እጄን ወዳንተ የምዘረጋ አይደለሁም፡፡ እኔ የዓለማትን ጌታ አላህን እፈራለሁና» አለ፡፡ 5|29|«እኔ በኃጢአቴና በኃጢአትህ ልትመለስና ከእሳት ጓዶች ልትኾን እሻለሁ፤ ይኽም የበደለኞች ቅጣት ነው» (አለ)፡፡ 5|30|ነፍሱም ወንድሙን መግደልን ለርሱ ሸለመችለት፤(አነሳሳችው፤)፡፡ ገደለውም፡፡ ከከሳሪዎቹም ኾነ፡፡ 5|31|የወንድሙንም ሬሳ እንዴት እንደሚሸሽግ ያሳየው ዘንድ አላህ መሬትን የሚጭር ቁራን ላከለት፡፡ «ወይ እኔ የወንድሜን ሬሳ እሸሽግ ዘንድ እንደዚህ ቁራ ብጤ መኾን አቃተኝን» አለ፡፡ ከጸጸተኞችም ኾነ፡፡ 5|32|በዚህ ምክንያት በእስራኤል ልጆች ላይ እነሆ ያለ ነፍስ (መግደል) ወይም በምድር ላይ ያለማጥፋት (ካልሆነ በስተቀር) ነፍስን የገደለ ሰው ሰዎቹን ሁሉ እንደገደለ ነው፤ ሕያው ያደረጋትም ሰው ሰዎቹን ሁሉ ሕያው እንዳደረገ ነው ማለትን ጻፍን፡፡ መልክተኞቻችንም በግልጽ ተዓምራት በእርግጥ መጡዋቸው፡፡ ከዚያም ከዚህ በኋላ ከእነሱ ብዙዎቹ በምድር ላይ ወሰንን አላፊዎች ናቸው፡፡ 5|33|የእነዚያ አላህንና መልክተኛውን የሚዋጉ በምድርም ላይ ለማጥፋት የሚተጉ ሰዎች ቅጣት መገደል ወይም መሰቀል ወይም እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን በማፈራረቅ መቆረጥ ወይም ከአገር መባረር ነው፡፡ ይህ በነሱ በቅርቢቱ ዓለም ውርደት ነው፡፡ በመጨረሻይቱም ለእነርሱ ከባድ ቅጣት አላቸው፡፡ 5|34|እነዚያ በእነርሱ ላይ ከመቻላችሁ (ከመወሰናችሁ) በፊት የተጸጸቱ ሲቀሩ፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ መኾኑን እወቁ፡፡ 5|35|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ፡፡ ወደርሱም መቃረቢያን (መልካም ሥራን) ፈልጉ፡፡ ትድኑ ዘንድም በእርሱ መንገድ ታገሉ፡፡ 5|36|እነዚያ የካዱት ሰዎች በምድር ላይ ያለው ሁሉ ከእርሱም ጋር ብጤው ከትንሣኤ ቀን ቅጣት በእርሱ ሊበዡበት ለእነርሱ በኖራቸው ኖሮ ከእነሱ ተቀባይን ባላገኙ ነበር፡፡ ለእነሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 5|37|ከእሳት ሊወጡ ይፈልጋሉ፡፡ እነርሱም ከርስዋ ወጪዎች አይደሉም፡፡ ለእነርሱም ዘውታሪ ቅጣት አላቸው፡፡ 5|38|ሰራቂውንና ሰራቂይቱንም በሠሩት ነገር ለቅጣት ከአላህ የኾነን መቀጣጫ እጆቻቸውን ቁረጡ፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 5|39|ከበደሉም በኋላ የተጸጸተና ሥራውን ያሳመረ አላህ ጸጸቱን ከእርሱ ይቀበለዋል፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 5|40|የሰማያትና የምድር ንግሥና የሱ (የአላህ) ብቻ መኾኑን አላወቅክምን የሚሻውን ሰው ይቀጣል፡፡ ለሚሻውም ሰው ይምራል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 5|41|አንተ መልክተኛ ሆይ! እነዚያ በክሕደት የሚቻኮሉት ከእነዚያ ልቦቻቸው ያላመኑ ሲኾኑ በአፎቻቸው «አመንን» ካሉትና ከእነዚያም አይሁድ ከኾኑት ሲኾኑ አያሳዝኑህ፡፡ (እነርሱ) ውሸትን አዳማጮች ናቸው፡፡ ለሌሎች ወዳንተ ላልመጡ ሕዝቦች አዳማጮች ናቸው፡፡ ንግግሮችን ከቦታቸው ሌላ ያጣምማሉ፡፡ «ይህንን (የተጣመመውን) ብትስሰጡ ያዙት፡፡ ባትስሰጡትም ተጠንቀቁ» ይላሉ፡፡ አላህም መፈተኑን የሚሻበትን ሰው ለእርሱ ከአላህ (ለመከላከል) ምንንም አትችልም፡፡ እነዚህ እነዚያ አላህ ልቦቻቸውን ማጥራትን ያልሻላቸው ናቸው፡፡ ለእነርሱ በቅርቢቱ ዓለም ውርደት አላቸው፡፡ ለእነርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከባድ ቅጣት አላቸው፡፡ 5|42|ውሸትን አዳማጮች እርምን በላተኞች ናቸው፡፡ ወደአንተ ቢመጣም በመካከላቸው ፍረድ፡፡ ወይም ተዋቸው፡፡ ብትተዋቸውም ምንም አይጎዱህም፡፡ ብትፈርድም በመካከላቸው በትክክል ፍረድ፡፡ አላህ በትክክል ፈራጆችን ይወዳልና፡፡ 5|43|እነርሱም ዘንድ ተውራት እያለች በውስጧ የአላህ ፍርድ ያለባት ስትኾን እንዴት ያስፈርዱሃል! ከዚያም ከዚህ በኋላ እንዴት ይሸሻሉ! እነዚያም በፍጹም ምእምናን አይደሉም፡፡ 5|44|እኛ ተውራትን በውስጥዋ መምሪያና ብርሃን ያለባት ስትኾን አወረድን፡፡ እነዚያ ትዕዛዝን የተቀበሉት ነቢያት በእነዚያ አይሁዳውያን በኾኑት ላይ በርሷ ይፈርዳሉ፡፡ ሊቃውንቱና ዐዋቂዎቹም ከአላህ መጽሐፍ እንዲጠብቁ በተደረጉትና በርሱም ላይ መስካሪዎች በኾኑት (ይፈርዳሉ)፡፡ ሰዎችንም አትፍሩ፡፡ ፍሩኝም፡፡ በአንቀጾቼም አነስተኛን ዋጋ አትለውጡ፡፡ አላህም ባወረደው ነገር ያልፈረደ ሰው እነዚያ ከሓዲዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 5|45|በእነርሱም ላይ በውስጧ «ነፍስ በነፍስ ዓይንም በዓይን አፍንጫም በአፍንጫ ጆሮም በጆሮ ጥርስም በጥርስ (ይያዛል)፡፡» ቁስሎችንም ማመሳሰል አለባቸው ማለትን ጻፍን፡፡ በእርሱም የመጸወተ (የማረ) ሰው እርሱ ለርሱ (ለሠራው ኃጢአት) ማስተሰሪያ ነው፡፡ አላህም ባወረደው ነገር የማይፈርድ ሰው፤ እነዚያ በደለኞቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 5|46|በፈለጎቻቸውም (በነቢያቶቹ ፈለግ) ላይ የመርየምን ልጅ ዒሳን ከተውራት በስተፊቱ ያለውን አረጋጋጭ ሲኾን አስከተልን፡፡ ኢንጂልንም በውስጡ ቀጥታና ብርሃን ያለበት በስተፊቱ ያለችውን ተውራትንም የሚያረጋግጥ ለጥንቁቆችም መሪና ገሳጭ ሲኾን ሰጠነው፡፡ 5|47|የኢንጅልም ባለቤቶች በውስጡ አላህ ባወረደው ሕግ ይፍረዱ፡፡ አላህም ባወረደው የማይፈርድ ሰው እነዚያ አመጸኞች እነርሱ ናቸው፡፡ 5|48|ወደ አንተም መጽሐፉን ከበፊቱ ያለውን መጽሐፍ አረጋጋጭና በእርሱ ላይ ተጠባባቂ ሲኾን በእውነት አወረድን፡፡ በመካከላቸውም አላህ ባወረደው ሕግ ፍረድ፡፡ እውነቱም ከመጣልህ በኋላ ዝንባሌዎቻቸውን አትከተል፡፡ ከእናንተ ለሁሉም ሕግንና መንገድን አደረግን፡፡ አላህም በሻ ኖሮ አንድ ሕዝብ ባደረጋችሁ ነበር፡፡ ግን በሰጣችሁ ሕግጋት ሊሞክራችሁ (ለያያችሁ)፡፡ በጎ ሥራዎችንም (ለመሥራት) ተሽቀዳደሙ፤ መመለሻችሁ በጠቅላላ ወደ አላህ ነው፡፡ በእርሱም ትለያዩበት የነበራችሁትን ነገር ይነግራችኋል፡፡ 5|49|በመካከላቸውም አላህ ባወረደው ሕግ ፍረድ፡፡ ፍላጎቶቻቸውንም አትከተል፡፡ አላህም ወደ አንተ ካወረደው ከከፊሉ እንዳያሳስቱህ ተጠንቀቃቸው (ማለትን አወረድን)፡፡ ቢዞሩም አላህ የሚሻው በከፊሉ ኃጢአታቸው ሊቀጣቸው መኾኑን ዕወቅ፡፡ ከሰዎቹም ብዙዎቹ አመጸኞች ናቸው፡፡ 5|50|የማይምንነትን ፍርድ ይፈልጋሉን ለሚያረጋግጡም ሰዎች ከአላህ ይበልጥ ፍርዱ ያማረ ማን ነው 5|51|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አይሁዶችንና ክርስቲያኖችን ረዳቶች አድርጋችሁ አትያዙ፡፡ ከፊላቸው ለከፊሉ ረዳቶች ናቸው፡፡ ከእናንተም ውስጥ ረዳቶች የሚያደርጋቸው ሰው እርሱ ከነርሱ ነው፡፡ አላህ አመጸኞችን ሕዝቦች አያቀናም፡፡ 5|52|እነዚያንም በልቦቻቸው ውስጥ (የንፍቅና) በሽታ ያለባቸውን ሰዎች «የጊዜ መለዋወጥ እንዳያገኘን እንፈራለን የሚሉ» ሲኾኑ በእነርሱ (ለመረዳት) ሲቻኮሉ ታያቸዋለህ፡፡ አላህም ድል መንሳትን ወይም ከእርሱ ዘንድ የኾነን ነገር (ማጋለጥን) ሊያመጣ በነፍሶቻቸው ውስጥ በደበቁትም ነገር ተጸጻቾች ሲሆኑ ተረጋገጠ፡፡ 5|53|እነዚያም ያመኑት ሰዎች፡- «እነዚያ እነርሱ ከእናንተ ጋር ነን ብለው የጠነከረ መሐላቸውን በአላህ የማሉት እነዚህ ናቸውን» ይላሉ፡፡ ሥራዎቻቸው ተበላሹ፡፡ ከሳሪዎችም ኾኑ፡፡ 5|54|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከእናንተ ውስጥ ከሃይማኖቱ የሚመለስ ሰው አላህ (በእነርሱ ስፍራ) የሚወዳቸውንና የሚወዱትን፣ በምእመናን ላይ ትሑቶች፣ በከሓዲዎች ላይ ኀያላን የኾኑን በአላህ መንገድ የሚታገሉን የወቃሽን ወቀሳ የማይፈሩን ሕዝቦች በእርግጥ ያመጣል፡፡ ይኸ የአላህ ችሮታ ነው፤ ለሚሻው ሰው ይሰጠዋል፤ አላህም ችሮታው ሰፊ ዐዋቂ ነው፡፡ 5|55|ረዳታችሁ አላህና መልክተኛው እነዚያም ያመኑት ብቻ ናቸው፡፡ (እነርሱ) እነዚያ ሶላትን በደንቡ የሚሰግዱ እነርሱም ያጎነበሱ ኾነው ምጽዋትን የሚሰጡ ናቸው፡፡ 5|56|አላህንና መልክተኛውን እነዚያንም ያመኑትን የሚወዳጅ ሰው (ከአላህ ጭፍሮች ይኾናል)፡፡ የአላህም ጭፍሮች እነርሱ አሸናፊዎች ናቸው፡፡ 5|57|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከእነዚያ ከበፊታችሁ መጽሐፍን ከተሰጡት እነዚያን ሃይማኖታችሁን ማላገጫና መጫወቻ አድርገው የያዙትን ከሓዲዎችንም ረዳቶች አድርጋችሁ አትያዙ፡፡ ምእምናንም እንደኾናችሁ አላህን ፍሩ፡፡ 5|58|ወደ ሶላትም በጠራችሁ ጊዜ (ጥሪይቱን) መሳለቂያና መጫወቻ አድርገው ይይዟታል፡፡ ይህ እነርሱ የማያውቁ ሕዝቦች በመኾናቸው ነው፡፡ 5|59|«የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! በአላህና ወደኛ በተወረደው በፊትም በተወረደው ለማመናችን አብዛኞቻችሁም አመጸኞች ለመኾናችሁ እንጅ (ሌላን ነገር) ከኛ ትጠላላችሁን» በላቸው፡፡ 5|60|«አላህ ዘንድ ቅጣቱ ከዚህ የከፋ ነገር ልንገራችሁን» በላቸው፡፡ (እርሱም) «አላህ የረገመው ሰው በእርሱም ላይ ተቆጣበት፡፡ ከእነርሱም ዝንጀሮዎችንና ከርከሮዎችን ያደረገው ጣዖትንም የተገዛ ሰው (ሃይማኖት) ነው፡፡ እነዚያ በጣም በከፋ ስፍራ ናቸው፡፡» ከቀጥተኛውም መንገድ በጣም የተሳሳቱ ናቸው፡፡ 5|61|በመጡዋችሁም ጊዜ (ወደእናንተ) ከክህደት ጋር በእርግጥ የገቡ እነርሱም ከርሱ ጋር በእርግጥ የወጡ ሲኾኑ «አምነናል» ይላሉ፡፡ አላህም ይደብቁት የነበሩትን ነገር በጣም ዐዋቂ ነው፡፡ 5|62|ከእነርሱም ብዙዎቹን በኃጢአትና በበደል እርምንም በመብላታቸው የሚጣደፉ ሲኾኑ ታያለህ፡፡ ይሠሩት የነበሩት ነገር በጣም ከፋ! 5|63|ቀሳውስቱና ሊቃውንቱ ከኃጢአት ንግግራቸውና እርምን ከመብላታቸው አይከለክሏቸውም ኖሮአልን ይሠሩት የነበሩት ነገር በጣም ከፋ! 5|64|አይሁዶችም «የአላህ እጅ የታሰረች ናት» አሉ፡፡ እጆቻቸው ይታሰሩ ባሉትም ነገር ይረገሙ፡፡ አይደለም (የአላህ) እጆቹ የተዘረጉ ናቸው፡፡ እንደሚሻ ይለግሳል፡፡ ከጌታህም ወደ አንተ የተወረደው (ቁርኣን) ከእነሱ ብዙዎቹን ትዕቢትንና ክህደትን በእርግጥ ይጨምራቸዋል፡፡ በመካከላቸውም ጠብንና ጥላቻን እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ ጣልን፡፡ ለጦር እሳትን ባያያዙ (ባጫሩ) ቁጥር አላህ ያጠፋታል፡፡ በምድርም ውስጥ ለማበላሸት ይሮጣሉ፡፡ አላህም አበላሺዎችን አይወድም፡፡ 5|65|የመጽሐፉም ባለቤቶች ባመኑና (ከክህደትም) በተጠነቀቁ ኖሮ ከእነሱ ኃጢኣቶቻቸውን በእርግጥ ባበስንና የመጠቀሚያ ገነቶችንም በእርግጥ ባገባናቸው ነበር፡፡ 5|66|እነርሱም ተውራትንና ኢንጂልን ከጌታቸውም ወደእነሱ የተወረደውን መጽሐፍ ባቋቋሙ (በሠሩበት) ኖሮ ከበላያቸውና ከእግሮቻቸው ሥር በተመገቡ ነበር፡፡ ከእነሱ ውስጥ ትክክለኞች ሕዝቦች አልሉ፡፡ ከእነሱም ብዙዎቹ የሚሠሩት ነገር ከፋ! 5|67|አንተ መልክተኛ ሆይ! ከጌታህ ወዳንተ የተወረደውን አድርስ፡፡ ባትሠራም መልክቱን አላደረስክም፡፡ አላህም ከሰዎች ይጠብቅሃል፡፡ አላህ ከሓዲዎችን ሕዝቦች አያቀናምና፡፡ 5|68|«እናንተ የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! ተውራትንና ኢንጂልን ከጌታችሁም ወደእናንተ የተወረደውን እስከምታቆሙ (እስከምትሠሩባቸው) ድረስ በምንም ላይ አይደላችሁም» በላቸው፡፡ ከጌታህም ወደ አንተ የተወረደው ቁርኣን ከእነሱ ብዙዎቹን ትዕቢትንና ክህደትን በእርግጥ ይጨምርባቸዋል፡፡ በከሓዲያን ሕዝቦችም ላይ አትዘን፡፡ 5|69|እነዚያ ያመኑና እነዚያም አይሁዳውያን የኾኑ፣ ሳቢያኖችም፣ ክርስቲያኖችም (ከነርሱ) በአላህና በመጨረሻው ቀን ያመነና መልካምን ሥራ የሠራ ሰው በነርሱ ላይ ፍርሃት የለባቸውም፡፡ እነርሱም አያዝኑም፡፡ 5|70|የእስራኤልን ልጆች የጠበቀ ቃል ኪዳን በእርግጥ ያዝንባቸው፡፡ ወደእነሱም መልክተኞችን ላክን፡፡ ነፍሶቻቸው በማትወደው ነገር መልእክተኛ በመጣላቸው ቁጥር ከፊሉን አስተባበሉ፤ ከፊሉንም ይገድላሉ፡፡ 5|71|ፈተናም አለመኖርዋን ጠረጠሩ፡፡ ታወሩም፣ ደነቆሩም፣ ከዚያም አላህ ከነርሱ ላይ ጸጸትን ተቀበለ፡፡ ከዚያም ከእነሱ ብዙዎቹ ታወሩ፣ ደነቆሩም፡፡ አላህም የሚሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 5|72|እነዚያ «አላህ እርሱ የመርየም ልጅ አልመሲሕ ነው» ያሉ በእርግጥ ካዱ፡፡ አልመሲህም አለ፡- «የእስራኤል ልጆች ሆይ! ጌታዬንና ጌታችሁን አላህን ተገዙ፡፡» እነሆ! በአላህ የሚያጋራ ሰው አላህ በርሱ ላይ ገነትን በእርግጥ እርም አደረገ፡፡ መኖሪያውም እሳት ናት፡፡ ለበዳዮችም ምንም ረዳቶች የሏቸውም፡፡ 5|73|እነዚያ «አላህ የሦስት ሦስተኛ ነው» ያሉ በእርግጥ ካዱ፡፡ ከአምላክም አንድ አምላክ እንጅ ሌላ የለም፡፡ ከሚሉትም ነገር ባይከለከሉ ከነሱ እነዚያን የካዱትን አሳማሚ ቅጣት በእርግጥ ይነካቸዋል፡፡ 5|74|ወደ አላህ አይመለሱምና ምሕረትን አይለምኑትምን አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 5|75|የመርየም ልጅ አልመሲሕ ከበፊቱ መልክተኞች በእርግጥ ያለፉ የኾነ መልክተኛ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ እናቱም በጣም እውነተኛ ናት፡፡ (ሁለቱም) ምግብን የሚበሉ ነበሩ፤ አንቀጾችን ለነርሱ (ለከሓዲዎች) እንዴት እንደምናብራራ ተመልከት ከዚያም (ከእውነት) እንዴት እንደሚመለሱ ተመልከት፡፡ 5|76|«ከአላህ ሌላ ለእናንተ መጉዳትንና መጥቀምን የማይችልን ትገዛላችሁን» በላቸው፡፡ አላህም እርሱ ሰሚው ዐዋቂ ነው፡፡ 5|77|«እናንተ የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! በሃይማኖታችሁ ከእውነት ሌላ የኾነን (ማለፍ) ወሰንን አትለፉ፡፡ በፊትም በእርግጥ የተሳሳቱትንና ከቀጥተኛው መንገድም (አሁን) የተሳሳቱን ሕዝቦች ከንቱ ዝንባሌዎች አትከተሉ» በላቸው፡፡ 5|78|ከእስራኤል ልጆች እነዚያ የካዱት በዳውድና በመርየም ልጅ በዒሳ ምላስ ተረገሙ፡፡ ይህ ትእዛዝን በመጣሳቸውና ወሰንን የሚያልፉ በመኾናቸው ነው፡፡ 5|79|ከሠሩት መጥፎ ነገር አይከላከሉም ነበር፡፡ ይሠሩት የነበሩት ነገር በእርግጥ ከፋ! 5|80|ከእነሱ ብዙዎቹን እነዚያን የካዱትን ሲወዳጁ ታያለህ፡፡ በእነሱ ላይ አላህ የተቆጣባቸው በመኾኑ ለእነርሱ ነፍሶቻቸው ያስቀደሙት ሥራ በጣም ከፋ፡፡ እነሱም በቅጣት ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 5|81|በአላህና በነቢዩ ወደርሱም በተወረደው ቁርኣን የሚያምኑ በኾኑ ኖሮ ወዳጆች አድርገው ባልያዙዋቸው ነበር፡፡ ግን ከነርሱ ብዙዎቹ አመጠኞች ናቸው፡፡ 5|82|አይሁዶችንና እነዚያን ያጋሩትን ለእነዚያ ለአመኑት በጠላትነት ከሰዎች ሁሉ ይበልጥ የበረቱ ኾነው በእርግጥ ታገኛለህ፡፡ እነዚያንም «እኛ ክርስቲያኖች ነን» ያሉትን ለእነዚያ ለአመኑት በወዳጅነት በእርግጥ ይበልጥ የቀረቧቸው ኾነው ታገኛለህ፡፡ ይህ ከእነሱ ውስጥ ቀሳውስትና መነኮሳት በመኖራቸውና እነሱም የማይኮሩ በመኾናቸው ነው፡፡ 5|83|ወደ መልክተኛውም የተወረደውን (ቁርኣን) በሰሙ ጊዜ እውነቱን ከማወቃቸው የተነሳ ዓይኖቻቸው እንባን ሲያፈሱ ታያለህ፡፡ «ጌታችን ሆይ! አመንን ከመስካሪዎቹም ጋር ጻፈን » ይላሉ፡፡ 5|84|«በአላህና ከውነትም በመጣልን ነገር የማናምን ጌታችንም ከመልካም ሰዎች ጋር ሊያስገባን የማንከጅል ለኛ ምን አለን» (ይላሉ)፡፡ 5|85|ባሉትም ምክንያት አላህ በስሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ መነዳቸው፡፡ ይህም የበጎ ሠሪዎች ዋጋ ነው፡፡ 5|86|እነዚያም የካዱና በአንቀጾቻችን ያስተባበሉ እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ 5|87|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህ ለናንተ የፈቀደላችሁን ጣፋጮች እርም አታድርጉ፡፡ ወሰንንም አትለፉ፡፡ አላህ ወሰን አላፊዎችን አይወድምና፡፡ 5|88|አላህም ከሰጣችሁ ሲሳይ የተፈቀደ ጣፋጭ ሲኾን ብሉ፡፡ ያንንም እናንተ በርሱ አማኞች የኾናችሁበትን አላህን ፍሩ፡፡ 5|89|አላህ በመሐላዎቻችሁ በውድቁ አይዛችሁም፡፡ ግን መሐላዎችን (ባሰባችሁት) ይይዛችኋል፡፡ ማስተሰሪያውም ቤተሰቦቻችሁን ከምትመግቡት ከመካከለኛው (ምግብ) ዐስርን ምስኪኖች ማብላት ወይም እነሱን ማልበስ ወይም ጫንቃን ነጻ ማውጣት ነው፤ (ከተባሉት አንዱን) ያላገኘም ሰው ሦስት ቀኖችን መጾም ነው፤ ይህ በማላችሁ ጊዜ የመሐላዎቻችሁ ማካካሻ ነው፡፡ መሐላዎቻችሁንም ጠብቁ፡፡ እንደዚሁ አላህ ለናንተ አንቀጾችን ያብራራል፡፡ እናንተ ልታመሰግኑ ይከጀላልና፡፡ 5|90|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! የሚያሰክር መጠጥ ቁማርም ጣዖታትም አዝላምም ከሰይጣን ሥራ የኾኑ እርኩስ ብቻ ናቸው፡፡ (እርኩስን) ራቁትም ልትድኑ ይከጀላልና፡፡ 5|91|ሰይጣን የሚፈልገው በሚያሰክር መጠጥና በቁማር በመካከላችሁ ጠብንና ጥላቻን ሊጥል አላህን ከማውሳትና ከስግደትም ሊያግዳችሁ ብቻ ነው፡፡ ታዲያ እናንተ (ከእነዚህ) ተከልካዮች ናችሁን (ተከልከሉ)፡፡ 5|92|አላህንም ተገዙ፡፡ መልክተኛውንም ታዘዙ፡፡ ተጠንቀቁም፡፡ ብትሸሹም፤ በመልክተኛችን ላይ ያለበት ግልጽ ማድረስ ብቻ መኾኑን ዕወቁ፡፡ 5|93|በእነዚያ ባመኑትና በጎ ሥራዎችን በሠሩት ላይ (ክህደትን) በተጠነቀቁና ባመኑ መልካም ሥራዎችንም በሠሩ ከዚያም (የሚያሰክርንና ቁማርን) በተጠነቀቁና ባመኑ ከዚያም (ከተከለከለው ሁሉ) በተጠነቀቁና (ሥራን) ባሳመሩ ጊዜ (ከመከልከሉ በፊት) በተመገቡት ነገር ኃጢአት የለባቸውም፡፡ አላህም በጎ ሠሪዎችን ይወዳል፡፡ 5|94|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! (በሐጅ ጊዜ) እጆቻችሁና ጦሮቻችሁ በሚያገኙት ታዳኝ አውሬ አላህ ይሞክራችኋል፡፡ በሩቅ ኾኖ የሚፈራውን ሰው አላህ ሊገልጽ (ይሞክራችኋል)፡፡ ከዚያም በኋላ ወሰንን ያለፈና ያደነ ሰው ለርሱ አሳማሚ ቅጣት አለው፡፡ 5|95|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እናንት በሐጅ ሥራ ውስጥ ስትኾኑ አውሬን አትግደሉ፡፡ ከእናንተም እያወቀ የገደለው ሰው ቅጣቱ ከእናንተ ሁለት የትክክለኛነት ባለቤቶች የሚፈርዱበት የኾነ ወደ ካዕባ ደራሽ መሥዋዕት ሲኾን ከቤት እንስሳዎች የገደለውን ነገር ብጤ መስጠት ወይም ምስኪኖችን ማብላት ወይም የዚህን ልክ መጾም ማካካሻ ነው፡፡ (ይኽም) የሥራውን ከባድ ቅጣት እንዲቀምስ ነው፡፡ (ሳይከለከል በፊት) ካለፈው ነገር አላህ ይቅርታ አደረገ፡፡ (ወደ ጥፋቱም) የተመለሰም ሰው አላህ ከርሱ ይበቀላል፡፡ አላህም አሸናፊ የመበቀል ባለቤት ነው፡፡ 5|96|የባሕር ታዳኝና ምግቡ ለእናንተም ለመንገደኞችም መጠቀሚያ ይኾን ዘንድ ለናንተ ተፈቀደ፡፡ በሐጅም ላይ እስካላችሁ ድረስ የየብስ አውሬ በናንተ ላይ እርም ተደረገ፡፡ ያንንም ወደርሱ የምትሰበሰቡበትን አላህን ፍሩ፡፡ 5|97|ከዕባን፣ የተከበረውን ቤት፣ ክልክል የኾነውንም ወር፣ መስዋዕቱንና ባለ ምልክቶቹንም መንጋዎች አላህ ለሰዎች መቋቋሚያ አደረገ፡፡ ይህ አላህ በሰማያት ያለውን ሁሉ በምድርም ያለውን ሁሉ የሚያውቅ መኾኑን አላህም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ መኾኑን እንድታውቁ ነው፡፡ 5|98|አላህ ቅጣተ ብርቱ መኾኑን አላህም መሓሪ አዛኝ መኾኑን እወቁ፡፡ 5|99|በመልክተኛው ላይ ማድረስ እንጅ ሌላ የለበትም፡፡ አላህም የምትገልጹትን ነገር የምትደብቁትንም ሁሉ ያውቃል፡፡ 5|100|«የመጥፎው (ገንዘብ) ብዛት ቢያስደንቃችሁም እንኳ መጥፎውና ጥሩው አይስተካከሉም፡፡ ባለልቦች ሆይ! አላህንም ፍሩ፤ እናንተ ልትድኑ ይከጀላልና፤» በላቸው፡፡ 5|101|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ለእናንተ ቢገለጹ ከሚያስከፏችሁ ነገሮች አትጠይቁ፡፡ ቁርኣንም በሚወርድበት ጊዜ ከእርሷ ብትጠይቁ ለናንተ ትገለጻለች፤ ከእርሷ አላህ ይቅርታ አደረገ፡፡ አላህም መሓሪ ታጋሽ ነው፡፡ 5|102|ከናንተም በፊት ሕዝቦች በእርግጥ ጠየቋት፡፡ ከዚያም በእርሷ (ምክንያት) ከሓዲዎች ኾኑ፡፡ 5|103|ከበሒራ ከሳኢባም ከወሲላም ከሓምም አላህ ምንንም (ሕግ) አላደረገም፡፡ ግን እነዚያ የካዱት በአላህ ላይ ውሸትን ይቀጣጥፋሉ፡፡ አብዛኞቻቸውም አያውቁም፡፡ 5|104|ለእነርሱም አላህ ወደ አወረደውና ወደ መልክተኛው ኑ በተባሉ ጊዜ «አባቶቻችንን በርሱ ላይ ያገኘንበት ነገር ይበቃናል» ይላሉ፡፡ አባቶቻቸው ምንም የማያውቁና የማይመሩ ቢኾኑም (ይኸንን ማለት ይበቃቸዋልን) 5|105|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ነፍሶቻችሁን (ከእሳት) ያዙ፤ (ጠብቁ)፡፡ በተመራችሁ ጊዜ የተሳሳተ ሰው አይጎዳችሁም፡፡ የሁላችሁም መመለሻ ወደ አላህ ብቻ ነው፡፡ ትሠሩትም የነበራችሁትን ሁሉ ይነግራችኋል፡፡ 5|106|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አንዳችሁን ሞት በመጣበት ጊዜ በኑዛዜ ወቅት የመካከላችሁ ምስክርነት ከእናንተ ሁለት የትክክለኛነት ባለቤቶች የኾኑ ሰዎች ወይም በምድር ብትጓዙና የሞት አደጋ ብትነካችሁ ከሌሎቻችሁ የኾኑ ሁለት ሌሎች ሰዎች (መመስከር) ነው፡፡ ብትጠራጠሩ ከሶላት (ከዐሱር) በኋላ ታቆሟቸውና (የሚመሰክርለት ሰው) የዝምድና ባለቤት ቢኾንም እንኳ «በርሱ ዋጋን አንገዛም የአላህንም ምስክርነት አንደብቅም፤ ያን ጊዜ (ደብቀን ብንገኝ) እኛ ከኃጢአተኞች ነን» ብለው በአላህ ስም ይምላሉ፡፡ 5|107|እነርሱም ኃጢአትን (በውሸት መስክረው) የተገቡ መኾናቸው ቢታወቅ ከእነዚያ (ለሟቹ) ቅርቦች በመኾን (ውርስ) ከተገባቸው የኾኑ ሁለት ሌሎች ሰዎች በስፍራቸው (በምስክሮች ስፍራ) ይቆሙና «ምስክርነታችን ከእነሱ ምስክርነት ይልቅ እውነት ነው ወሰንም አላለፍንም ያን ጊዜ እኛ ከበዳዮች ነን» ሲሉ በአላህ ይምላሉ፡፡ 5|108|ይህ ምስክርነትን በተገቢዋ ላይ ለማምጣታቸው ወይም ከመሐላዎቻቸው በኋላ የመሐላዎችን (ወደ ወራሾች) መመለስን ለመፍራት በጣም የቀረበ ነው፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ ስሙም፡፡ አላህም አመጸኞች ሕዝቦችን አይመራም፡፡ 5|109|አላህ መልክተኞቹን የሚሰበስብበትንና «ምን መልስ ተሰጣችሁ» የሚልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ «ለእኛ ምንም ዕውቀት የለንም አንተ ሩቆችን በጣም ዐዋቂ አንተ ብቻ ነህ» ይላሉ፡፡ 5|110|አላህ በሚል ጊዜ (አስታውስ)፡- «የመርየም ልጅ ዒሳ ሆይ! በአንተና በእናትህ ላይ (የዋልኩላችሁን) ጸጋዬን አስታውስ፡፡ በሕፃንነትና በከፈኒሳነት (የበሰለ ሰው ኾነህ) ሰዎችን የምትናገር ስትኾን በቅዱስ መንፈስ (በገብሬል) ባበረታሁህ ጊዜ፤ ጽሕፈትንና ጥበብንም ተውራትንና ኢንጂልንም ባስተማርኩህ ጊዜ፣ ከጭቃም የወፍ ቅርጽ ብጤ በፈቃዴ በምትሠራና በውስጧ በምትነፋ በፈቃዴም ወፍ በምትኾን ጊዜ፣ ዕውርም ኾኖ የተወለደንና ለምጻምንም በፈቃዴ በምታሽር ጊዜ፣ ሙታንንም በፈቃዴ (ከመቃብራቸው) በምታወጣ ጊዜ፣ የእስራኤልንም ልጆች በተአምራት በመጣህባቸውና ከእነሱ እነዚያ የካዱት ይህ ግልጽ ድግምት እንጅ ሌላ አይደለም ባሉ ጊዜ፣ (ሊገድሉህ ሲያስቡህ) ከአንተ ላይ በከለከልኩልህም ጊዜ (ያደረግሁልህን ውለታ አስታውስ)፡፡» 5|111|ወደ ሐዋርያትም «በኔና በመልክተኛዬ እመኑ» በማለት ባዘዝኩ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «አመንን፤ እኛ ሙስሊሞች መኾናችንን መስክር» አሉ፡፡ 5|112|ሐዋርያት፡- «የመርየም ልጅ ዒሳ ሆይ! ጌታህ በእኛ ላይ ከሰማይ ማእድን ሊያወርድልን ይችላልን» ባሉ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «ምእመናን እንደ ኾናችሁ አላህን ፍሩ» አላቸው፡፡ 5|113|«ከእርሷ ልንበላ ልቦቻችንም ሊረኩ እውነት ያልከንም መኾንህን ልናውቅና በእርሷም ላይ ከመስካሪዎች ልንኾን እንፈልጋለን» አሉ፡፡ 5|114|የመርየም ልጅ ዒሳ አለ፡- «ጌታችን አላህ ሆይ! ለእኛ ለመጀመሪያዎቻችንና ለመጨረሻዎቻችን ባዕል (መደሰቻ) የምትኾንን ከአንተም ተአምር የኾነችን ማእድ ከሰማይ በእኛ ላይ አውርድ፡፡ ስጠንም፡፡ አንተ ከሰጪዎች ሁሉ በላጭ ነህና፡፡» 5|115|አላህ፡- «እኔ (ማእድዋን) በናንተ ላይ አውራጅዋ ነኝ፡፡ በኋላም ከእናንተ የሚክድ ሰው እኔ ከዓለማት አንድንም የማልቀጣውን ቅጣት እቀጣዋለሁ» አለ፡፡ 5|116|አላህም፡- «የመርየም ልጅ ዒሳ ሆይ! አንተ ለሰዎቹ፡- እኔንና እናቴን ከአላህ ሌላ ሁለት አምላኮች አድርጋችሁ ያዙ ብላሃልን» በሚለው ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «ጥራት ይገባህ፤ ለእኔ ተገቢዬ ያልኾነን ነገር ማለት ለኔ አይገባኝም፡፡ ብዬው እንደ ኾነም በእርግጥ ዐውቀኸዋል፡፡ በነፍሴ ውስጥ ያለውን ሁሉ ታውቃለህ፡፡ ግን አንተ ዘንድ ያለውን አላውቅም፡፡ አንተ ሩቆችን ሁሉ በጣም ዐዋቂ አንተ ብቻ ነህና» ይላል፡፡ 5|117|«በእርሱ ያዘዝከኝን ቃል ጌታዬንና ጌታችሁን አላህን ተገዙ ማለትን እንጂ ለነርሱ ሌላ አላልኩም፡፡ በውስጣቸውም እስካለሁ ድረስ በነርሱ ላይ ተጣባበቂ ነበርኩ፡፡ በተሞላኸኝም ጊዜ (ባነሳኸኝ ጊዜ) አንተ በነሱ ላይ ተጠባባቂ ነበርክ፡፡ አንተም በነገሩ ሁሉ ላይ ዐዋቂ ነህ፡፡» 5|118|«ብትቀጣቸው እነርሱ ባሮችህ ናቸው፡፡ ለነርሱ ብትምርም አንተ አሸናፊው ጥበበኛው ነህ» (ይላል)፡፡ 5|119|አላህ ይላል፡- «ይህ እውነተኞችን እውነታቸው የሚጠቅምበት ቀን ነው፡፡ ለእነርሱ በሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው በውስጣቸው ሁልጊዜ ዘውታሪዎች ሲኾኑ የሚኖሩባቸው ገነቶች አሉዋቸው፡፡ አላህ ከእነሱ ወደደ፤ እነርሱም ከእርሱ ወደዱ፤ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡» 5|120|የሰማያትና የምድር በውስጣቸውም ያለው ሁሉ ንግሥና የአላህ ብቻ ነው፡፡ እሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 6|1|ምስጋና ለዚያ ሰማያትንና ምድርን ለፈጠረው ጨለማዎችንና ብርሃንንም ላደረገው ለአላህ የተገባ ነው፡፡ ከዚያም እነዚያ የካዱት (ጣዖታትን በጌታቸው) ያስተካክላሉ፡፡ 6|2|እርሱ ያ ከጭቃ የፈጠራችሁ ከዚያም (የሞት) ጊዜን የወሰነ ነው፡፡ እርሱም ዘንድ (ለትንሣኤ) የተወሰነ ጊዜ አልለ፡፡ ከዚያም እናንተ (በመቀስቀሳችሁ) ትጠራጠራላችሁ፡፡ 6|3|እርሱም ያ በሰማያትና በምድር (ሊግገዙት የሚገባው) አላህ ነው፡፡ ምስጢራችሁን ግልጻችሁንም ያውቃል፡፡ የምትሠሩትንም ሁሉ ያውቃል፡፡ 6|4|ከጌታቸውም አንቀጾች አንዲትም አንቀጽ አትመጣቸውም ከርሷ የሚሸሹ ቢኾኑ እንጅ፡፡ 6|5|በእውነቱም (ቁርኣን) በመጣላቸው ጊዜ በእርግጥ አስተባበሉ፡፡ በእርሱም ይሳለቁበት የነበሩት ነገር ዜናዎች (ቅጣት) በእርግጥ ይመጣባቸዋል፡፡ 6|6|ከበፊታቸው ከክፍለ ዘመናት ሕዝቦች ብዙዎችን ማጥፋታችንን አላዩምን ለእናንተ ያላስመቸነውን (ለእነርሱ) በምድር ውስጥ አስመቸናቸው፡፡ በእነርሱም ላይ ዝናምን የተከታተለ ሲኾን ላክን፡፡ ወንዞችንም በሥራቸው እንዲፈሱ አደረግን፡፡ በኃጢአቶቻቸውም አጠፋናቸው፡፡ ከኋላቸውም ሌሎችን የክፍለ ዘመን ሰዎች አስገኘን፡፡ 6|7|ባንተም ላይ በወረቀት የተጻፈን መጽሐፍ ባወረድንና በእጆቻቸው በነኩት ኖሮ እነዚያ የካዱት ሰዎች «ይህ ግልጽ ድግምት እንጅ ሌላ አይደለም» ባሉ ነበር፡፡ 6|8|«በእርሱም (በሙሐመድ) ላይ መልአክ አይወረድለትም ኖሮአልን» አሉ፡፡ መልአክን ባወረድንም ኖሮ (ባያምኑ በጥፋታቸው) ነገሩ በተፈረደ ነበር፡፡ ከዚያም አይቆዩም ነበር፡፡ 6|9|(መልክተኛውን) መልአክም ባደረግነው ኖሮ ወንድ (በሰው ምስል) ባደረግነው ነበር፡፡ በእነርሱም ላይ የሚያመሳስሉትን ነገር ባመሳሰልንባቸው ነበር፡፡ 6|10|ካንተ በፊትም በመልክተኞች በእርግጥ ተላግጧል፡፡ በእነዚያም ከእነሱ ባላገጡት ላይ በእርሱ ያላግጡ የነበሩት ነገር (ቅጣት) ወረደባቸው፡፡ 6|11|«በምድር ላይ ኺዱ የአስተባባዮችም መጨረሻ እንዴት እንደነበረ ተመልከቱ» በላቸው፡፡ 6|12|«በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የማን ነው» በላቸው፡፡ (ሌላ መልስ የለምና) «የአላህ ነው» በል፡፡ «በነፍሱ ላይ እዝነትን ጻፈ፡፡ በትንሣኤ ቀን በእርሱ ጥርጥር የሌለበት ሲኾን በእርግጥ ይሰበስባችኋል፡፡ እነዚያ ነፍሶቻቸውን ያከሰሩ ናቸው፤ እነርሱም አያምኑም፡፡ 6|13|በሌሊትና በቀንም ጸጥ ያለው ሁሉ የርሱ ብቻ ነው፡፡ እርሱም ሰሚው ዐዋቂ ነው፡፡» 6|14|«ሰማያትንና ምድርን ፈጣሪ ከኾነው አላህ እርሱ የሚመግብ የማይመገብም ሲኾን ሌላን አምላክ እይዛለሁን» በላቸው፡፡ «እኔ መጀመሪያ ትእዛዝን ከተቀበለ ሰው ልኾን ታዘዝኩ፡፡ ከአጋሪዎችም ፈጽሞ አትኹን (ተብያለሁ)» በላቸው፡፡ 6|15|«እኔ በጌታዬ ባምጽ የታላቁን ቀን ቅጣት እፈራለሁ» በላቸው፡፡ 6|16|በዚያ ቀን ከእርሱ ላይ (ቅጣት) የሚመለስለት ሰው (አላህ) በእርግጥ አዘነለት፡፡ ይህም ግልጽ ማግኘት ነው፡፡ 6|17|አላህም በጉዳት ቢነካህ ለእርሱ (ለጉዳቱ) ከእርሱ በቀር ሌላ አስወጋጅ የለም፡፡ በበጎም ነገር ቢነካህ እርሱ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 6|18|እርሱም ከባሮቹ በላይ ሲኾን አሸናፊ ነው፡፡ እርሱም ጥበበኛው ውስጥ ዐዋቂው ነው፡፡ 6|19|«በምስክርነት ከነገሩ ሁሉ ይበልጥ ታላቅ ማነው» በላቸው፡፡ (ሌላ መልስ የለምና) «አላህ ነው፡፡ በእኔና በእናንተ መካከል መስካሪ ነው፡፡ ይህም ቁርኣን እናንተንና የደረሰውን ሰው ሁሉ በርሱ ላስፈራራበት ወደኔ ተወረደ፡፡ ከአላህ ጋር ሌሎች አማልክት መኖራቸውን እናንተ ትመሰክራላችሁን» በላቸው፡፡ «እኔ አልመሰክርም» በላቸው፡፡ «እርሱ አንድ አምላክ ብቻ ነው፡፡ እኔም ከምታጋሩት ነገር ንጹሕ ነኝ» በላቸው፡፡ 6|20|እነዚያ መጽሐፍን የሰጠናቸው ልጆቻቸውን እንደሚያውቁ (ሙሐመድን) ያውቁታል፡፡ እነዚያ ከእነርሱ ውስጥ ነፍሶቻቸውን ያከሰሩት እነርሱ አያምኑም፡፡ 6|21|በአላህም ላይ ውሸትን ከቀጣጠፈ ወይም በአንቀጾቹ ካስተባበለ ሰው ይበልጥ በደለኛ ማነው እነሆ በደለኞች አይድኑም፡፡ 6|22|ሁላቸውንም የምንሰበስብበትንና ከዚያም ለእነዚያ (ጣዖታትን) ለአጋሩት እነዚያ (ለአላህ) ተጋሪዎች ናቸው ብላችሁ ታስቧቸው የነበራችሁት ተጋሪዎቻችሁ የት ናቸው የምንልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 6|23|ከዚያም መልሳቸው «በጌታችን በአላህ ይኹንብን አጋሪዎች አልነበርንም» ማለት እንጅ ሌላ አትኾንም፡፡ 6|24|በነፍሳቸው ላይ እንዴት እንደ ዋሹና ይቀጣጥፉት የነበሩት ነገር ከእነሱ እንዴት እንደ ተሰወረ ተመልከት፡፡ 6|25|ከእነርሱም ወደ አንተ የሚያዳምጥ ሰው አልለ፡፡ በልቦቻቸውም ላይ እንዳያውቁት ሺፋኖችን በጆሮዎቻቸውም ላይ ድንቁርናን አደረግን፡፡ ተዓምርንም ሁሉ ቢያዩ በርሷ አያምኑም፡፡ በመጡህም ጊዜ የሚከራከሩህ ሲኾኑ እነዚያ የካዱት «ይህ (ቁርኣን) የቀድሞዎቹ ሰዎች ጽሑፍ ተረቶች እንጅ ሌላ አይደለም» ይላሉ፡፡ 6|26|እነርሱም (ሰዎችን) ከእርሱ ይከለክላሉ፡፡ ከእርሱም ይርቃሉ፡፡ ነፍሶቻቸውንም እንጂ ሌላን አያጠፉም፤ ግን አያውቁም፡፡ 6|27|በእሳትም ላይ በተቆሙ ጊዜ ምነው (ወደ ምድረ ዓለም) በተመለስን በጌታችንም አንቀጾች ባላስተባበልን ከምእምናንም በኾንን ዋ ምኞታችን! ባሉ ጊዜ ብታይ ኖሮ (የሚያሰደነግጥን ነገር ባየህ ነበር)፡፡ 6|28|ይልቁንም ከዚህ በፊት ይደብቁት የነበሩት ሁሉ ለእነርሱ ተገለጸ፡፡ (ወደምድረ ዓለም) በተመለሱም ኖሮ ከእርሱ ወደ ተከለከሉት ነገር በተመለሱ ነበር፡፡ እነሱም በእርግጥ ውሸታሞች ናቸው፡፡ 6|29|እርሷም (ሕይወት) «የቅርቢቱ ሕይወታችን እንጅ ሌላ አይደለችም እኛም ተቀስቀቃሾች አይደለንም» አሉ፡፡ 6|30|በጌታቸውም ላይ (ለምርመራ) በተቆሙ ጊዜ ብታይ ኖሮ (አስደንጋጭን ነገር ባየህ ነበር)፡፡ «ይህ እውነት አይደለምን» ይላቸዋል፡፡ «በጌታችን ይኹንብን እውነት ነው» ይላሉ፡፡ «ትክዱት በነበራችሁት ምክንያት ቅጣቱን ቅመሱ» ይላቸዋል፡፡ 6|31|እነዚያ በአላህ መገናኘት ያስተባበሉ በእርግጥ ከሰሩ፡፡ ሰዓቲቱም በድንገት በመጣቻቸው ጊዜ እነሱ ኃጢኣቶቻቸውን በጀርባዎቻቸው ላይ የሚሸከሙ ሲኾኑ «በርሷ (በምድረ ዓለም) ባጓደልነው ነገር ላይ ዋ ቁጪታችን» ይላሉ፡፡ ንቁ! የሚሸከሙት ነገር ከፋ፡፡ 6|32|የቅርቢቱም ሕይወት ጨዋታና ላግጣ እንጅ ሌላ አይደለችም፡፡ የመጨረሻይቱም አገር (ገነት) ለእነዚያ ለሚጠነቀቁት በጣም በላጭ ናት፡፡ አታውቁምን 6|33|እነሆ ያ የሚሉህ ነገር እንደሚያሳዝንህ በእርግጥ እናውቃለን፡፡ እነርሱም (በልቦቻቸው) አያስተባብሉህም፡፡ ግን በዳዮቹ በአላህ አንቀጾች ይክዳሉ፡፡ 6|34|ከበፊትህም መልክተኞች በእርግጥ ተስተባበሉ፡፡ በተስተባበሉበትም ነገርና በተሰቃዩት ላይ እርዳታችን እስከመጣላቸው ድረስ ታገሱ፡፡ የአላህንም ንግግሮች ለዋጭ የለም፡፡ ከመልክተኞቹም ወሬ (የምትረጋጋበት) በእርግጥ መጣልህ፡፡ 6|35|(ኢስላምን) መተዋቸውም ባንተ ላይ ከባድ ቢኾንብህ በምድር ውስጥ ቀዳዳን ወይም በሰማይ ውስጥ መሰላልን ልትፈልግና በተአምር ልትመጣቸው ብትችል (አድርግ)፡፡ አላህም በሻ ኖሮ በቅኑ መንገድ ላይ በሰበሳባቸው ነበር፡፡ ከተሳሳቱትም ሰዎች በፍጹም አትኹን፡፡ 6|36|ጥሪህን የሚቀበሉት እነዚያ የሚሰሙት ብቻ ናቸው፡፡ ሙታንንም አላህ ይቀሰቅሳቸዋል፡፡ ከዚያም ወደርሱ ብቻ ይመለሳሉ፡፡ 6|37|«ከጌታውም በእርሱ ላይ ለምን ተዓምር አልተወረደም» አሉ፡፡ «አላህ ተአምርን በማውረድ ላይ ቻይ ነው» በላቸው፡፡ ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 6|38|ከተንቀሳቃሽም በምድር (የሚኼድ)፤ በሁለት ክንፎቹ የሚበርም በራሪ መሰሎቻችሁ ሕዝቦች እንጅ ሌላ አይደሉም፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ምንንም ነገር አልተውንም ከዚያም ወደ ጌታቸው ይሰበሰባሉ፡፡ 6|39|እነዚያም በአንቀጾቻችን ያስዋሹ ደንቆሮች ድዳዎችም በጨለማዎች ውስጥ ያሉ ናቸው፡፡ አላህ ማጥመሙን የሚሻውን ሰው ያጠመዋል፡፡ መምራቱን የሚሻውንም ሰው በቀጥተኛ መንገድ ላይ ያደርገዋል፡፡ 6|40|የአላህ ቅጣት ቢመጣባችሁ ወይም ሰዓቲቱ (ትንሣኤ) ብትመጣባችሁ ከአላህ ሌላን ትጠራላችሁን እውነተኞች እንደ ኾናችሁ ንገሩኝ በላቸው፡፡ 6|41|አይደለም እርሱን ብቻ ትጠራላችሁ፡፡ ቢሻም ወደርሱ የምትጠሩበትን ነገር ያስወግዳል፡፡ የምታጋሩትንም ነገር ትተዋላችሁ (በላቸው)፡፡ 6|42|ከበፊትህም ወደ ነበሩት ሕዝቦች (መልክተኞችን) በእርግጥ ላክን፡፡ እንዲዋደቁም በድህነትና በበሽታ ያዝናቸው፡፡ 6|43|ታዲያ ቅጣታችን በመጣባቸው ጊዜ አይዋደቁም ኖሯልን ግን ልቦቻቸው ደረቁ፡፡ ይሠሩት የነበሩትንም ነገር ሰይጣን ለነሱ አሳመረላቸው፡፡ 6|44|በርሱም ይገሰጹበት የነበረውን ነገር በተው ጊዜ በእነሱ ላይ የነገርን ሁሉ ደጃፎች ከፈትን (አስመቸናቸው)፡፡ በተሰጡትም ነገር በተደሰቱ ጊዜ በድንገት ያዝናቸው፡፡ ወዲያውኑም እነርሱ ተስፋ ቆራጮች ኾኑ፡፡ 6|45|የእነዚያም የበደሉት ሕዝቦች መጨረሻ ተቆረጠ፡፡ ምስጋናም ለዓለማት ጌታ ለአላህ ይገባው፡፡ 6|46|ንገሩኝ አላህ መስሚያችሁንና ማያዎቻችሁን ቢወስድ በልቦቻችሁም ላይ ቢያትም ከአላህ ሌላ እሱን የሚያመጣላችሁ አምላክ ማነው በላቸው፡፡ አንቀጾችን እንዴት እንደምናብራራ ከዚያም እነሱ እንዴት እንደሚመለሱ ተመልከት፡፡ 6|47|«ንገሩኝ የአላህ ቅጣት በድንገት ወይም በግልጽ ቢመጣባችሁ አመጠኞች ሕዝቦች እንጅ ሌላ ይጠፋልን» በላቸው፡፡ 6|48|መልክተኞችንም አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን እንጅ አንልክም፡፡ ያመኑና መልካምን የሠሩ ሰዎችም በእነርሱ ላይ ፍርሃት የለባቸውም፤ እነሱም አያዝኑም፡፡ 6|49|እነዚያም ባንቀጾቻችን ያስዋሹ ያምጹ በነበሩት ምክንያት ቅጣቱ ያገኛቸዋል፡፡ 6|50|«ለእናንተ የአላህ ግምጃ ቤቶች እኔ ዘንድ ናቸው አልልም፡፡ ሩቅንም አላውቅም፡፡ ለእናንተም እኔ መልአክ ነኝ አልልም፡፡ ወደእኔ የሚወርድልኝን እንጅ ሌላን አልከተልም» በላቸው፡፡ «ዕውርና የሚያይ ይስተካከላሉን አታስተነትኑምን» በላቸው፡፡ 6|51|እነዚያንም ከእርሱ ሌላ ረዳትና አማላጅ የሌላቸው ሲኾኑ ወደ ጌታቸው መስሰብሰብን የሚፈሩትን ይጠነቀቁ ዘንድ በርሱ (በቁርኣን) አስፈራራ፡፡ 6|52|እነዚያን ጌታቸውን ፊቱን (ውዴታውን) የሚሹ ኾነው በጧትና በማታ የሚጠሩትን አታባር፡፡ ታባርራቸውና ከበደለኞችም ትኾን ዘንድ እነሱን መቆጣጠር ባንተ ላይ ምንም የለብህም፡፡ አንተንም መቆጣጠር በነሱ ላይ ምንም የለባቸውም፡፡ 6|53|እንደዚሁም «ከመካከላችን አላህ የለገሰላቸው እነዚህ ናቸውን» ይሉ ዘንድ ከፊላቸውን በከፊሉ ሞከርን፡፡ አላህ አመስጋኞቹን ዐዋቂ አይደለምን 6|54|እነዚያም በተአምራታችን የሚያምኑት (ወደ አንተ) በመጡ ጊዜ «ሰላም በእናንተ ላይ ይኹን፡፡ ጌታችሁ በነፍሱ ላይ እዝነትን ጻፈ፡፡ እነሆ ከእናንተ ውስጥ በስሕተት ክፉን ሥራ የሠራ ሰው ከዚያም ከእርሱ በኋላ የተጸጸተና ሥራውን ያሳመረ እርሱ (አላህ) መሓሪ አዛኝ ነው» በላቸው፡፡ 6|55|እንደዚሁም (እውነቱ እንዲገለጽና) የወንጀለኞችም መንገድ ትብራራ ዘንድ አንቀጾችን እንገልጻለን፡፡ 6|56|«እኔ እነዚያን ከአላህ ሌላ የምትጠሩዋቸውን ከመገዛት ተከልክያለሁ» በላቸው፡፡ «ዝንባሌያችሁን አልከተልም፡፡ ያን ጊዜ በእርግጥ ተሳሳትኩ፡፡ እኔም ከተመሪዎቹ አይደለሁም» በላቸው፡፡ 6|57|«እኔ ከጌታዬ በኾነች ግልጽ ማስረጃ ላይ ነኝ፡፡ በእርሱም አስተባበላችሁ፡፡ በርሱ የምትቻኮሉበት ቅጣት እኔ ዘንድ አይደለም፡፡ ፍርዱ ለአላህ ብቻ ነው፡፡ እውነትን ይፈርዳል፡፡ እርሱም ከፈራጆች ሁሉ በላጭ ነው» በላቸው፡፡ 6|58|«በእርሱ የምትቻኮሉበት ቅጣት እኔ ዘንድ በኾነ ኖሮ በእኔና በእናንተ መካከል ነገሩ (ቅጣታችሁ) በተፈጸመ ነበር፡፡ አላህም በደለኞችን ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 6|59|የሩቅ ነገርም መክፈቻዎች እርሱ ዘንድ ናቸው፡፡ ከእርሱ በቀር ማንም አያውቃቸውም፡፡ በየብስና በባሕር ያለውንም ሁሉ ያውቃል፡፡ ከቅጠልም አንዲትም አትረግፍም የሚያውቃት ቢኾን እንጅ፡፡ ከቅንጣትም በመሬት ጨለማዎች ውስጥ የለም ከእርጥብም ከደረቅም አንድም የለም ግልጽ በኾነው መጽሐፍ ውሰጥ (የተመዘገበ) ቢኾን እንጅ፡፡ 6|60|እርሱም ያ በሌሊት የሚያስተኛችሁ በቀንም የሠራችሁትን ሁሉ የሚያውቅ ከዚያም የተወሰነው ጊዜ ይፈፀም ዘንድ በእርሱ (በቀን) ውስጥ የሚቀሰቅሳችሁ ነው፡፡ ከዚያም መመለሻችሁ ወደ እርሱ ነው፡፡ ከዚያም ትሠሩት የነበራችሁትን ሁሉ ይነግራችኋል፡፡ 6|61|እርሱም ከባሮቹ በላይ ሲኾን ሁሉን አሸነፊ ነው፡፡ በናንተም ላይ ጠባቂዎችን (መላእክት) ይልካል፡፡ አንዳችሁንም ሞት በመጣበት ጊዜ (የሞት) መልእክተኞቻችን እነርሱ (ትእዛዛትን) የማያጓድሉ ሲኾኑ ይገድሉታል፡፡ 6|62|ከዚያም እውነተኛ ወደ ኾነው ጌታቸው ወደ አላህ ይመለሳሉ፡፡ ንቁ! ፍርዱ ለእርሱ ብቻ ነው፡፡ እርሱም ከተቆጣጣሪዎች ሁሉ ይበልጥ ፈጣን ነው፡፡ 6|63|ከየብስና ከባሕር ጨለማዎች በግልጽና በምስጢር የምትጠሩት ስትኾኑ «ከነዚህ ቢያድነን በእርግጥ ከአመስጋኞች እንኾናለን (ስትሉ) የሚያድናችሁ ማነው» በላቸው፡፡ 6|64|አላህ ከሷና ከጭንቅም ሁሉ ያድናችኋል፡፡ ከዚያም እናንተ ታጋራላችሁ በላቸው፡፡ 6|65|«እርሱ (አላህ) ከበላያችሁ ወይም ከእግሮቻችሁ በታች ቅጣትን በእናንተ ላይ ሊልክ ወይም የተለያዩ ሕዝቦች ስትኾኑ ሊያደባልቃችሁና ከፊላችሁን የከፊሉን ጭካኔ ሊያቀምስ ቻይ ነው» በላቸው፡፡ ያውቁ ዘንድ አንቀጾችን እንዴት እንደምናብራራ ተመልከት፡፡ 6|66|በእርሱም (በቁርኣን) እሱ እውነት ሲኾን ሕዝቦችህ አስተባበሉ፡፡ በላቸው፡- «በናንተ ላይ ጠባቂ አይደለሁም፡፡» 6|67|ለትንቢት ሁሉ (የሚደርስበት) መርጊያ አለው፡፡ ወደፊትም ታውቁታላችሁ፡፡ 6|68|እነዚያንም በአንቀጾቻችን የሚገቡትን ባየህ ጊዜ ከእርሱ ሌላ በኾነ ወሬ እስከሚገቡ ድረስ ተዋቸው፡፡ ሰይጣንም (መከልከልህን) ቢያስረሳህ ከትውስታ በኋላ ከበደለኞች ሕዝቦች ጋር አትቀመጥ፡፡ 6|69|በእነዚያም በሚጠነቀቁት ላይ ከሒሳባቸው ምንም የለባቸውም፡፡ ግን ይጠነቀቁ ዘንድ መገሰጽ (አለባቸው)፡፡ 6|70|እነዚያንም ሃይማኖታቸውን ጨዋታና ላግጣ አድርገው የያዙትን ቅርቢቱም ሕይወት ያታለለቻቸውን ተዋቸው፡፡ በእርሱም (በቁርኣን) ነፍስ በሠራችው ሥራ እንዳትጠፋ አስታውስ፡፡ ለእርሷ ከአላህ ሌላ ረዳትና አማላጅ የላትም፡፡ በመበዢያም ሁሉ ብትበዥ ከርሷ አይወሰድም፡፡ እነዚህ እነዚያ በሠሩት ሥራ የተጠፉት ናቸው፡፡ ለነሱ ይክዱ በነበሩት ምክንያት ከፈላ ውሃ መጠጥና አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 6|71|«ከአላህ ሌላ የማይጠቅመንን እና የማይጎዳንን እንገዛለን አላህም ከመራን ጊዜ በኋላ የኋሊት እንመለሳለን እንደዚያ በምድር ላይ የዋለለ ሲኾን ሰይጣናት እንዳሳሳቱት ለእርሱ ወደኛ ና እያሉ ወደ ቅን መንገድ የሚጠሩ ወዳጆች እንዳሉት (እንደማይከተላቸውም) ሰው እንኾናለን» በላቸው፡፡ «የአላህ መንገድ እርሱ ቀጥተኛው መንገድ ነው፡፡ ለዓለማት ጌታ ልንገዛም ታዘዝን» በላቸው፡፡ 6|72|ሶላትንም በደንቡ ስገዱ ፍሩትም፤ (በማለት ታዘዝን)፡፡ እርሱም ያ ወደርሱ ብቻ የምትሰበሰቡበት ነው፡፡ 6|73|እርሱም ያ ሰማያትንና ምድርን በእውነት የፈጠረ ነው፡፡ «ኹን» የሚልበትንና ወዲያውም የሚኾንበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ ቃሉ እውነት ነው፡፡ በቀንዱም በሚነፋ ቀን ንግሥናው የርሱ ብቻ ነው፡፡ ሩቁንና ቅርቡን ዐዋቂ ነው፡፡ እርሱም ጥበበኛው ውስጥ ዐዋቂው ነው፡፡ 6|74|ኢብራሒምም ለአባቱ ለአዘር «ጣዖታትን አማልክት አድርገህ ትይዛለህን እኔ፤ አንተንም ሕዝቦችህንም በግልጽ መሳሳት ውስጥ ኾናችሁ አያችኋለሁ» ባለ ጊዜ (አስታውስ) 6|75|እንደዚሁም ኢብራሂምን (እንዲያውቅና) ከአረጋጋጮቹም ይኾን ዘንድ የሰማያትንና የምድርን መለኮት አሳየነው፡፡ 6|76|ሌሊቱም በእርሱ ላይ ባጨለመ ጊዜ ኮከብን አየ፡፡ «ይህ ጌታዬ ነው» አለ፡፡ በጠለቀም ጊዜ፡- «ጠላቂዎችን አልወድም» አለ፡፡ 6|77|ጨረቃንም ወጪ ኾኖ ባየ ጊዜ፡- «ይህ ጌታዬ ነው» አለ፡፡ በገባም ጊዜ፡- «ጌታዬ (ቅኑን መንገድ) ባይመራኝ በእርግጥ ከተሳሳቱት ሕዝቦች እኾናለሁ» አለ፡፡ 6|78|ፀሐይንም ጮራዋን ዘርግታ ባየ ጊዜ፡- «ይህ ጌታዬ ነው፡፡ ይህ በጣም ትልቅ ነው» አለ፡፡ በገባችም ጊዜ፡- «ወገኖቼ ሆይ! እኔ ከምታጋሩት ሁሉ ንጹሕ ነኝ» አለ፡፡ 6|79|«እኔ ለዚያ ሰማያትንና ምድርን ለፈጠረው (አምላክ) ቀጥተኛ ስኾን ፊቴን አዞርኩ፡፡ እኔም ከአጋሪዎቹ አይደለሁም» (አለ)፡፡ 6|80|ወገኖቹም ተከራከሩት፡፡ «በአላህ (አንድነት) በእርግጥ የመራኝ ሲኾን ትከራከሩኛላችሁን በእርሱም የምታጋሩትን ነገር አልፈራም፡፡ ግን ጌታዬ ነገርን ቢሻ (ያገኘኛል)፡፡ ጌታዬም ነገሩን ሁሉ ዕውቀቱ ሰፋ፡፡ አትገነዘቡምን» አላቸው፡፡ 6|81|«በእናንተ ላይ በእርሱ ማስረጃን ያላወረደበትን እናንተ ማጋራታችሁን የማትፈሩ ስትኾኑ የምታጋሩትን (ጣዖታት) እንዴት እፈራለሁ! የምታውቁም ብትኾኑ ከሁለቱ ክፍሎች በጸጥታ ይበልጥ ተገቢው ማንኛው ነው» (አለ)፡፡ 6|82|እነዚያ ያመኑና እምነታቸውን በበደል ያልቀላቀሉ እነዚያ ለእነርሱ ጸጥታ አላቸው፡፡ እነሱም የተመሩ ናቸው፤ 6|83|ይህችም ማስረጃችን ናት፡፡ ለኢብራሂም በሕዝቦቹ ላይ (አስረጅ እንድትኾን) ሰጠናት፡፡ የምንሻውን ሰው በደረጃዎች ከፍ እናደርጋለን፡፡ ጌታህ ጥበበኛ ዐዋቂ ነውና፡፡ 6|84|ለርሱም ኢስሐቅን (የልጅ ልጁን) ያዕቁብንም ሰጠነው፡፡ ሁሉንም መራን፡፡ ኑሕንም በፊት መራን፡፡ ከዘሮቹም ዳውድን፣ ሱለይማንንም፣ አዩብንም፣ ዩሱፍንም፣ ሙሳንም፣ ሃሩንንም (መራን)፡፡ እንደዚሁም በጎ ሰሪዎችን እንመነዳለን፡፡ 6|85|ዘከሪያንም፣ የሕያንም፣ ዒሳንም፣ ኢልያስንም (መራን)፡፡ ሁሉም ከመልካሞቹ ናቸው፡፡ 6|86|ኢስማዒልንም፣ አልየስዕንም፣ ዩኑስንም፣ ሉጥንም (መራን)፡፡ ሁሉንም በዓለማት ላይ አበለጥናቸውም፡፡ 6|87|ከአባቶቻቸውም፣ ከዘሮቻቸውም፣ ከወንድሞቻቸውም (መራን)፡፡ መረጥናቸውም፤ ወደ ቀጥታውም መንገድ መራናቸው፡፡ 6|88|ይህ የአላህ መምሪያ ነው፡፡ በእርሱ ከባሮቹ የሚሻውን ሰው ይመራል፡፡ ባጋሩም ኖሮ ይሠሩት የነበሩት ከነሱ በታበሰ ነበር፡፡ 6|89|እነዚህ እነዚያ መጻሕፍትንና ጥበብን፣ ነቢይነትንም የሰጠናቸው ናቸው፡፡ እነዚህ (የመካ ከሓዲዎች) በእርሷ ቢክዱም በእርሷ የማይክዱን ሕዝቦች ለእርሷ በእርግጥ አዘጋጅተናል፡፡ 6|90|እነዚህ (ነቢያት)፤ እነዚያ አላህ የመራቸው ናቸው፡፡ በመንገዳቸውም ተከተል፡፡ «በእርሱ (በቁርአን) ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም፡፡ እርሱ ለዓለማት ግሣጼ እንጅ ሌላ አይደለም» በላቸው፡፡ 6|91|«አላህ በሰው ላይ ምንም አላወረደም» ባሉም ጊዜ አላህን ተገቢ ክብሩን አላከበሩትም፡፡ (እንዲህ) በላቸው፡- «ያንን ብርሃንና ለሰዎች መሪ ኾኖ ሙሳ ያመጣውን መጽሐፍ ክፍልፍሎች የምታደርጉት ስትኾኑ ማን አወረደው (የወደዳችኋትን) ትገልጿታላችሁ ብዙውንም ትደብቃላችሁ፡፡ እናንተም አባቶቻችሁም ያላወቃችሁትን ተስተማራችሁ፤» 6|92|«አላህ (አወረደው)» በላቸው፡፡ ከዚያም በውሸታቸው ውስጥ የሚጫወቱ ሲኾኑ ተዋቸው፡፡ ይህም ያወረድነው የኾነ ብሩክ ያንንም በፊቱ የነበረውን (መጽሐፍ) አረጋጋጭ መጽሐፍ ነው፡፡ የከተሞችን እናት (መካን) እና በዙሪያዋ ያሉትንም ሰዎች ልታስጠነቅቅበት (አወረድነው)፡፡ እነዚያም በመጨረሻይቱ ዓለም የሚያምኑት እነርሱ በሶላታቸው ላይ የሚጠባበቁ ሲኾኑ በርሱ ያምናሉ፡፡ 6|93|በአላህም ላይ እብለትን ከቀጣጠፈ ወይም ወደርሱ ምንም ያልተወረደለት ሲኾን «ወደኔ ተወረደልኝ» ካለና፡-«አላህም ያወረደውን ብጤ በእርግጥ አወርዳለሁ» ካለ ሰው ይበልጥ በዳይ ማን ነው በደለኞችንም በሞት መከራዎች ውስጥ በኾኑ ጊዜ መላእክት እጆቻቸውን ዘርጊዎች ኾነው « (ለቅጥጥብ) ነፍሶቻችሁን አውጡ፤ በአላህ ላይ እውነት ያልኾነን ነገር ትናገሩ በነበራችሁትና ከአንቀጾቹም ትኮሩ በነበራችሁት ምክንያት ዛሬ የውርደትን ቅጣት ትመነዳላችሁ» (የሚሏቸው ሲኾኑ) ብታይ ኖሮ (አስደናቂን ነገር ባየህ ነበር)፡፡ 6|94|መጀመሪያም ጊዜ እንደ ፈጠርናችሁ ኾናችሁ የሰጠናችሁን ሁሉ በጀርባዎቻችሁ ኋላ የተዋችሁ ስትኾኑ የሰጠናችሁን ሁሉ በጀርባዎቻችሁ ኋላ የተዋችሁ ስትኾኑ ለየብቻችሁ ኾናችሁ በእርግጥ መጣችሁን እነዚያንም እነሱ በእናንተ ውስጥ (ለአላህ) ተጋሪዎች ናቸው የምትሉዋቸውን አማላጆቻችሁን ከእናንተ ጋር አናይም፡፡ ግንኙነታችሁ በእርግጥ ተቋረጠ፡፡ ከእናንተም ያ (ያማልደናል) የምትሉት ጠፋ (ይባላሉ)፡፡ 6|95|አላህ ቅንጣትንና የፍሬን አጥንት ፈልቃቂ ነው፡፡ ሕያውን ከሙት ያወጣል፤ ሙትንም ከሕያው አውጪ ነው፡፡ እርሱ አላህ ነው፤ ታዲያ (ከእምነት) እንዴት ትመለሳላችሁ (ትርቃላችሁ) 6|96|እርሱም ጎህን (ከሌሊት ጨለማ) ፈልቃቂ ሌሊትንም ማረፊያ ፀሐይንና ጨረቃንም (ለጊዜ) መቁጠሪያ አድራጊ ነው፡፡ ይህ የአሸናፊው የዐዋቂው (አላህ) ችሎታ ነው፡፡ 6|97|እርሱም ያ ከዋክብትን በየብስና በባሕር ጨለማዎች ውስጥ በእርሷ ትመሩ ዘንድ ለእናንተ ያደረገ ነው፡፡ ለሚያውቁ ሕዝቦች አንቀጾችን በእርግጥ ዘረዘርን፡፡ 6|98|እርሱም ያ ከአንዲት ነፍስ ያስገኛችሁ፤ ነው፡፡ (በማሕፀን) መርጊያና (በጀርባ) መቀመጫም (አላችሁ)፡፡ ለሚያወቁ ሕዝቦች አንቀጾችን በእርግጥ ዘረዘርን፡፡ 6|99|እርሱም ያ ከሰማይ ውሃን ያወረደ ነው፡፡ በርሱም የነገሩን ሁሉ በቃይ አወጣን፡፡ የተደራረበንም ቅንጣት ከርሱ የምናወጣ የኾነን ለምለም (አዝመራ) ከርሱ አወጣን፡፡ ከዘንባባም ከእንቡጧ የተቀራረቡ የኾኑ ዘለላዎች አሉ፡፡ ከወይኖችም፣ ከወይራም፣ ከሩማንም (ቅጠላቸው) ተመሳሳይና (ፍሬያቸው) የማይመሳሰል ሲኾኑ አትክልቶችን (አወጣን)፡፡ ባፈራ ጊዜ ወደ ፍሬውና ወደ መብሰሉ ተመልከቱ፡፡ በእነዚህ ተዓምራት ለሚያምኑ ሕዝቦች ምልክቶች አሉ፡፡ 6|100|ለአላህም አጋንንትን የፈጠራቸው ሲኾን (በመታዘዝ) ተጋሪዎች አደረጉ፡፡ ወንዶች ልጆችንና ሴቶች ልጆችንም ያለ ዕውቀት ለእርሱ ቀጠፉ፡፡ (አላህ) ጥራት የተገባው ከሚሉት ነገር የላቀ ነው፡፡ 6|101|(እርሱ) ሰማያትንና ምድርን ያለ ብጤ ፈጣሪ ነው፡፡ ለእርሱ ሚስት የሌለችው ሲኾን እንዴት ለእርሱ ልጅ ይኖረዋል ነገርንም ሁሉ ፈጠረ፡፡ እርሱም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 6|102|ይህ ጌታችሁ አላህ ነው፡፡ ከእርሱ በቀር አምላክ የለም፡፡ ነገርን ሁሉ ፈጣሪ ነው፡፡ ስለዚህ ተገዙት፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ተጠባባቂ ነው፡፡ 6|103|ዓይኖች አያገኙትም፤ (አያዩትም)፡፡ እርሱም ዓይኖችን ያያል፡፡ እርሱም ርኅራኄው ረቂቁ ውስጠ ዐዋቂው ነው፡፡ 6|104|«ከጌታችሁ ዘንድ ብርሃኖች በእርግጥ መጡላችሁ፡፡ የተመለከተም ሰው (ጥቅሙ) ለነፍሱ ብቻ ነው፡፡ የታወረም ሰው (ጉዳቱ) በራሱ ላይ ብቻ ነው፡፡ እኔም በእናንተ ላይ ጠባቂ አይደለሁም» (በላቸው)፡፡ 6|105|እንደዚሁም « (እንዲገመግሙና ያለፉትን መጻሕፍት) አጥንተሃልም» እንዲሉ ለሚያውቁ ሕዝቦችም (ቁርኣንን) እንድናብራራው አንቀጾችን እንገልጻለን፡፡ 6|106|ከጌታህ ወደ አንተ የተወረደውን ተከተል፡፡ ከእርሱ በቀር አምላክ የለም፡፡ አጋሪዎችንም ተዋቸው፡፡ 6|107|አላህም በሻ ኖሮ ባላጋሩ ነበር፡፡ በእነሱም ላይ ጠባቂ አላደረግንህም፡፡ አንተም በእነሱ ላይ ኃላፊ አይደለህም፡፡ 6|108|እነዚያንም ከአላህ ሌላ የሚገዙዋቸውን (ጣዖታትን) አትስደቡ፡፡ ድንበርን በማለፍ ያለዕውቀት አላህን ይሰድባሉና፡፡ እንደዚሁ ለሕዝቦች ሁሉ ሥራቸውን ደግ አስመሰልንላቸው፡፡ ከዚያም መመለሻቸው ወደ ጌታቸው ነው፡፡ ይሠሩት የነበሩትንም ሁሉ ይነግራቸዋል፡፡ 6|109|ተዓምርም ብትመጣላቸው በእርሷ በቁርጥ ሊያምኑ ጥብቅ መሐሎቻቸውን በአላህ ማሉ፡፡ «ተዓምራት ሁሉ አላህ ዘንድ ናት» በላቸው፡፡ እርሷ በመጣች ጊዜም አለማመናቸውን (ወይም ማመናቸውን) ምን አሳወቃችሁ 6|110|በመጀመሪያም ጊዜ በእርሱ እንዳላመኑ ሁሉ ልቦቻቸውንና ዓይኖቻቸውን እናገላብጣለን፡፡ በጥመታቸውም ውስጥ የሚዋልሉ ሲኾኑ እንተዋቸዋለን፡፡ 6|111|እኛም ወደእነርሱ መላእክትን ባወረድን ሙታንም ባነጋገሩዋቸው ነገሩንም ሁሉ ጭፍራ ጭፍራ አድርገን በእነሱ ላይ በሰበሰብን ኖሮ አላህ ካልሻ በስተቀር የሚያምኑ ባልኾኑ ነበር፡፡ ግን አብዛኞቻቸው (ይህንን) ይስታሉ፡፡ 6|112|እንደዚሁም ለነቢያት ሁሉ ከሰውና ከጋኔን የኾኑን ሰይጣናት ጠላት አደረግን፡፡ ከፊላቸው ወደ ከፊሉ ለማታለል ልብስብስን ቃል ይጥላሉ፡፡ ጌታህም በሻ ኖሮ ባልሠሩት ነበር፡፡ ከቅጥፈታቸውም ጋር ተዋቸው፡፡ 6|113|(የሚጥሉትም ሊያታልሉና) የእነዚያም በመጨረሻይቱ ሕይወት የማያምኑት ሰዎች ልቦች ወደእርሱ እንዲያዘነብሉ እንዲወዱትም እነርሱ ይቀጥፉ የነበሩትንም እንዲቀጣጥፉ ነው፡፡ 6|114|እርሱ ያ መጽሐፉን የተብራራ ኾኖ ወደእናንተ ያወረደ ሲኾን «ከአላህ ሌላ ዳኛን እፈልጋለሁን» (በላቸው)፡፡ እነዚያም መጽሐፍን የሰጠናቸው እርሱ ከጌታህ ዘንድ በእውነት የተወረደ መኾኑን ያውቃሉ፡፡ ከተጠራጣሪዎቹም አትኹን፡፡ 6|115|የጌታህም ቃላት እውነተኛና ትክክለኛ ስትኾን ተፈጸመች፡፡ ለቃላቱ ለዋጭ የለም፡፡ እርሱም ሰሚው ዐዋቂው ነው፡፡ 6|116|በምድርም ካሉት ሰዎች አብዛኞቹን ብትከተል ከአላህ መንገድ ያሳስቱሃል፡፡ ጥርጣሬን እንጅ ሌላን አይከተሉም፡፡ እነርሱም የሚዋሹ እንጂ ሌላ አይደሉም፡፡ 6|117|ጌታህ እርሱ ከመንገዱ የሚሳሳቱትን ዐዋቂ ነው፡፡ እርሱም ተመሪዎቹን ዐዋቂ ነው፡፡ 6|118|በአንቀጾቹም አማኞች እንደ ኾናችሁ (ሲታረድ) የአላህ ስም በእርሱ ላይ ከተወሳበት እንስሳ ብሉ፡፡ 6|119|ወደርሱም (መብላት) ከተገደዳችሁበት በስተቀር በእናንተ ላይ እርም የተደረገውን ለእናንተ (አላህ) በእርግጥ የዘረዘረ ሲኾን ከዚያ በእርሱ ላይ የአላህ ስም ከተጠራበት የማትበሉት ለናንተ ምን (ምክንያት) አላችሁ ብዙዎቹም ያለ ዕውቀት በዝንባሌዎቻቸው ያሳስታሉ፡፡ ጌታህ እርሱ ወሰን አላፊዎቹን ዐዋቂ ነው፡፡ 6|120|የኃጢአትንም ግልጹንም ድብቁንም ተውዉ፡፡ እነዚያ ኃጢአትን የሚሠሩ፤ ይሠሩት በነበሩት ነገር በእርግጥ ይቀጣሉ፡፡ 6|121|በእርሱም ላይ የአላህ ስም ካልተጠራበት ነገር አትብሉ፡፡ እርሱም በእርግጥ አመጽ ነው፡፡ ሰይጣናትም ወደ ወዳጆቻቸው (በክትን በመብላት) ይከራከሯችሁ ዘንድ ያሾከሹካሉ፡፡ ብትታዘዙዋቸውም እናንተ በእርግጥ አጋሪዎች ናችሁ፡፡ 6|122|ሙት የነበረና ሕያው ያደረግነው ለእርሱም በሰዎች መካከል በእርሱ የሚኼድበትን ብርሃን ያደረግንለት ሰው በጨለማዎች ውስጥ ከርሷ የማይወጣ ኾኖ እንዳልለ ሰው ብጤ ነውን እንደዚሁ ለከሓዲዎች ይሠሩት የነበሩት ነገር ተጌጠላቸው፡፡ 6|123|እንደዚሁም በየከተማይቱ በውስጧ ያሴሩ ዘንድ የተንኮለኞችዋን ታላላቆች አደረግን፡፡ በነፍሶቻቸውም ላይ እንጅ በሌላ ላይ አያሴሩም፤ ግን አያውቁም፡፡ 6|124|ተዓምርም በመጣቻቸው ጊዜ፡- «የአላህ መልክተኞች የተሰጡትን ብጤ እስክንሰጥ ድረስ በፍጹም አናምንም» አሉ፡፡ አላህ መልክቱን የሚያደርግበትን ስፍራ ዐዋቂ ነው፡፡ እነዚያን ያመጹትን ሰዎች ይዶልቱ በነበሩት ነገር አላህ ዘንድ ውርደትና ብርቱ ቅጣት ያገኛቸዋል፡፡ 6|125|አላህም ሊመራው የሚሻውን ሰው ደረቱን (ልቡን) ለኢስላም ይከፍትለታል፡፡ ሊያጠመውም የሚሻውን ሰው ደረቱን ጠባብ ቸጋራ ወደ ሰማይ ለመውጣት አንደሚታገል ያደርገዋል፡፡ እንደዚሁ አላህ በእነዚያ በማያምኑት ላይ ርክሰትን ያደርጋል፡፡ 6|126|ይህም (ያለህበት) ቀጥተኛ ሲኾን የጌታህ መንገድ ነው፡፡ ለሚያስታውሱ ሕዝቦች አንቀጾችን በእርግጥ ዘርዝረናል፡፡ 6|127|ለእነርሱ በጌታቸው ዘንድ የሰላም አገር አላቸው፡፡ እርሱም (ጌታህ) ይሠሩት በነበሩት ምክንያት ረዳታቸው ነው፡፡ 6|128|ሁሉንም የሚሰበስብባቸውንም ቀን (አስታውስ)፡፡፡ የአጋንንት ጭፍሮች ሆይ! ከሰዎች (ጭፍራን በማጥመም) በእርግጥ አበዛችሁ (ይባላሉ)፡፡ ከሰዎችም የኾኑት ወዳጆቻቸው፡-«ጌታችን ሆይ! ከፊላችን በከፊሉ ተጠቀመ፡፡ ያንንም ለእኛ የወሰንክልንን ጊዜያችንን ደረስን» ይላሉ፡፡ እሳት አላህ የሻው ጊዜ ሲቀር በውስጧ ዘውታሪዎች ስትኾኑ መኖሪያችሁ ናት ይላቸዋል፡፡ ጌታህ ጥበበኛ ዐዋቂ ነውና፡፡ 6|129|እንደዚሁም የበደለኞችን ከፊል በከፊሉ ላይ ይሠሩት በነበሩት ጥፋት ምክንያት እንሾማለን፡፡ 6|130|የጋኔንና የሰዎች ጭፍሮች ሆይ!፡- «አንቀጾቼን በእናንተ ላይ የሚተርኩ የዚህንም ቀናችሁን (ቅጣት) ማግኘትን የሚያስፈራሩዋችሁ ከእናንተው የኾኑ መልክተኞች አልመጧችሁምን» (ይባላሉ)፡፡ «በነፍሶቻችን ላይ መሰከርን፤ (መጥተውልናል)» ይላሉ፡፡ የቅርቢቱም ሕይወት አታለለቻቸው፡፡ በነፍሶቻቸውም ላይ እነርሱ ከሓዲዎች የነበሩ መኾናቸውን መሰከሩ፡፡ 6|131|ይህ ጌታህ ከተሞችን ባለቤቶችዋ ዘንጊዎች ኾነው ሳሉ በበደል ምክንያት አጥፊ ባለመኾኑ ነው፡፡ 6|132|ለሁሉም ከሠሩት ሥራ (የተበላለጡ) ደረጃዎች አልሏቸው፡፡ ጌታህም ከሚሠሩት ሁሉ ዘንጊ አይደለም፡፡ 6|133|ጌታህም ተብቃቂ የእዝነት ባለቤት ነው፡፡ ቢሻ ያስወግዳችኋል፤ (ያጠፋችኋል)፡፡ ከሌሎች ሕዝቦችም ዘሮች እንዳስገኛችሁ ከበኋላችሁ የሚሻውን ይተካል፡፡ 6|134|የምትቀጠሩት ሁሉ በእርግጥ መጪ ነው፡፡ እናንተም አምላጮች አይደላችሁም፡፡ 6|135|«ሕዝቦቼ ሆይ! በችሎታችሁ ላይ ሥሩ፤ እኔ (በችሎታዬ ላይ) ሠሪ ነኝና፡፡ ምስጉኒቱም አገር (ገነት) ለእርሱ የምትኾንለት ሰው ማን እንደኾነ ወደ ፊት ታውቃላችሁ፡፡ እነሆ በደለኞች አይድኑም» በላቸው፡፡ 6|136|ለአላህም ከፈጠረው ከአዝመራና ከግመል፣ ከከብት፣ ከፍየልም ድርሻን አደረጉ፡፡ በሐሳባቸውም «ይህ ለአላህ ነው፡፡ ይህም ለተጋሪዎቻችን ነው፡፡» ለተጋሪዎቻቸውም «(ለጣዖታት) የኾነው ነገር ወደ አላህ አይደርስም፡፡ ለአላህም የኾነው እርሱ ወደ ተጋሪዎቻቸው ይደርሳል» አሉ፡፡ የሚፈርዱት ፍርድ ከፋ! 6|137|እንደዚሁም ከአጋሪዎቹ ለብዙዎቹ፤ ተጋሪዎቻቸው ሊያጠፉዋቸው ሃይማኖ ታቸውንም በእነሱ ላይ ሊያቀላቅሉባቸው (ሊያመሳስሉባቸው) ልጆቻቸውን መግደልን አሳመሩላቸው፡፡ አላህም በሻ ኖሮ ባልሠሩት ነበር፡፡ ከቅጥፈታቸውም ጋር ተዋቸው፡፡ 6|138|በሐሳባቸውም ይህች እርም የኾነች ለማዳ እንስሳና አዝመራ ናት፡፡ የምንሻው ሰው እንጂ ሌላ አይበላትም፡፡ (ይህች) ጀርቦችዋ እርም የተደረገች ለማዳ እንስሳም ናት (አትጫንም)፡፡ ይህች በርሷ ላይ የአላህን ስም (ስትታረድ) የማይጠሩባትም እንስሳ ናት አሉ፡፡ በእርሱ ላይ ለመቅጠፍ (ነገሩን ወደ አላህ አስጠጉ)፡፡ ይቀጥፉት በነበሩት ነገር በእርግጥ ይቀጣቸዋል፡፡ 6|139|«በነዚህም እንስሶች ሆዶች ውስጥ ያለው ለወንዶቻችን በተለይ የተፈቀደ ነው፡፡ በሚስቶቻችንም ላይ እርም የተደረገ ነው፡፡ ሙትም ቢኾን (ሙት ኾኖ ቢወለድ) እነርሱ (ወንዶቹም ሴቶቹም) በርሱ ተጋሪዎች ናቸው» አሉ፡፡ በመቅጠፋቸው አላህ በእርግጥ ይቀጣቸዋል፡፡ እርሱ ጥበበኛ ዐዋቂ ነውና፡፡ 6|140|እነዚያ ያለ ዕውቀት በሞኝነት ልጆቻቸውን የገደሉና አላህም የሰጣቸውን (ሲሳይ) በአላህ ላይ በመቅጠፍ እርም ያደረጉ በእርግጥ ከሰሩ፡፡ በእርግጥ ተሳሳቱ፡፡ ተመሪዎችም አልነበሩም፡፡ 6|141|እርሱም ያ ዳስ የሚደረግላቸውንና ዳስ የማይደረግላቸውን አትክልቶች የፈጠረ ነው፡፡ ዘምባባንም (የተምርን ዛፍ) አዝመራንም ፍሬዎቹ የተለያዩ ሲኾኑ ወይራንና ሩማንንም (ቅጠላቸው) ተመሳሳይና (ጣዕማቸው) የማይመሳሰል ሲኾኑ (ፈጠረ)፡፡ ባፈራ ጊዜ ከፍሬው ብሉ፡፡ በአጨዳውም ቀን ተገቢውን (ዘካ) ስጡ፡፡ አታባክኑም፡፡ እርሱ አባካኞችን አይወድምና፡፡ 6|142|ከለማዳ እንስሳዎችም የሚጫኑትንና የማይጫኑትን (ፈጠረ)፡፡ አላህ ከሰጣችሁ ሲሳይ ብሉ፡፡ የሰይጣንንም እርምጃዎች አትከተሉ፡፡ እርሱ ለእናንተ ግልጽ ጠላት ነውና፡፡ 6|143|ስምንትን ዓይነቶች ከበግ ሁለትን (ወንድና ሴትን) ከፍየልም ሁለትን (ፈጠረ)፡፡«ከሁለቱም ክፍሎች አላህ ወንዶቹን እርም አደረገን ወይስ ሴቶቹን ወይስ በርሱ ላይ የሁለቱ ሴቶች ማሕፀኖች ያጠቃለሉትን እውነተኞች እንደሆናችሁ በዕውቀት (በአስረጅ) ንገሩኝ» በላቸው፡፡ 6|144|ከግመልም ሁለትን ከከብትም ሁለትን (ፈጠረ)፡፡«አላህ (ከሁለቱ) ወንዶቹን እርም አደረገን ወይስ ሴቶቹን ወይስ የሁለቱ ሴቶች ማሕፀኖች በእርሱ ላይ ያጠቃለሉትን በእውነቱ አላህ በዚህ ባዘዛችሁ ጊዜ የተጣዳችሁ ነበራችሁን ሰዎችንም ያለ ዕውቀት ሊያጠም በአላህ ላይ ውሸትንም ከቀጠፈ ሰው ይበልጥ በደለኛ ማን ነው አላህ በደለኞችን ሕዝቦች (ቅኑን መንገድ) አይመራም፡፡» 6|145|(ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው፡- «ወደእኔ በተወረደው ውስጥ በክት ወይም ፈሳሽ ደም ወይም የአሳማ ስጋ እርሱ ርኩስ ነውና ወይም በአመጽ ከአላህ ስም ሌላ በእርሱ ላይ የተወሳበት ካልኾነ በስተቀር በሚመገበው ተመጋቢ ላይ እርም የኾነን ነገር አላገኝም፡፡ አመጸኛና ወሰን ያለፈ ሳይኾንም የተገደደ ሰው (ከተወሱት ቢበላ ኃጢአት የለበትም)፡፡ ጌታህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡» 6|146|በእነዚያም አይሁዳውያን በኾኑት ላይ ባለ ጥፍርን ሁሉ እርም አደረግን፡፡ ከከብት፣ ከፍየልና ከበግም ሞራዎቻቸውን ጀርባዎቻቸው ወይም አንጀቶቻቸው የተሸከሙት ወይም በአጥንት የተቀላቀለው (ስብ) ሲቀር በነርሱ ላይ እርም አደረግን፡፡ ይህንን በአመጻቸው ምክንያት ቀጣናቸው፡፡ እኛ እውነተኞች ነን፡፡ 6|147|ቢያስተባብሉህም፡- «ጌታችሁ የሰፊ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ ብርቱ ቅጣቱም ከአመጸኞች ሕዝቦች ላይ አይመለስም» በላቸው፡፡ 6|148|እነዚያ ያጋሩት «አላህ በሻ ኖሮ እኛም አባቶቻቸንም ባላገራን ነበር፡፡ አንዳችንም ነገር እርም ባላደረግን ነበር ይላሉ፡፡ እንደዚሁ (እነዚህን እንደዋሹ) እነዚያ ከበፊታቸው የነበሩት ብርቱ ቅጣታችንን እስከቀመሱ ድረስ አስተባባሉ፡፡ ለእኛ ታዘልቁልን ዘንድ (ማጋራታችሁን ለመውደዱ) እናንተ ዘንድ ዕውቀት አለን ጥርጣሬን እንጅ ሌላ አትከተሉም፡፡ እናንተ ዋሾዎች እንጂ ሌላ አይደላችሁም» በላቸው፡፡ 6|149|«የተሟላው ማስረጃ የአላህ ነው፡፡ በሻም ኖሮ ሁላችሁንም ባቀናችሁ ነበር» በላቸው፡፡ 6|150|«እነዚያን አላህ ይህን እርም ማድረጉን የሚመሰክሩትን ምስክሮቻችሁን አምጡ» በላቸው፡፡ ቢመሰክሩም ከእነርሱ ጋር አትመስክር፡፡ የነዚያንም በአንቀጾቻችን ያስተባበሉትን የነዚያንም እነርሱ በጌታቸው (ሌላን) የሚያስተካክሉ ሲኾኑ በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑትን ሰዎች ዝንባሌዎች አትከተል፡፡ 6|151|«ኑ፤ ጌታችሁ በእናንተ ላይ እርም ያደርገውን ነገር (በእርሱም ያዘዛችሁን) ላንብብላችሁ» በላቸው፡፡ «በእርሱ (በአላህ) ምንንም ነገር አታጋሩ፡፡ ለወላጆችም በጎን ሥራ (ሥሩ)፡፡ ልጆቻችሁንም ከድህንት (ፍራቻ) አትግደሉ፡፡ እኛ እናንተንም እነርሱንም እንመግባችኋለንና፡፡ መጥፎ ሥራዎችንም ከእርሷ የተገለጸውንም የተደበቀውንም ሁሉ አትቅረቡ፡፡ ያችንም አላህ እርም ያደረጋትን ነፍስ በሕግ ቢኾን እንጅ አትግደሉ፡፡ ይህን ታውቁ ዘንድ (አላህ) በእርሱ አዘዛችሁ፡፡» 6|152|«የየቲምንም ገንዘብ ብርታቱን (አካለ መጠን) እስኪደርስ ድረስ በዚያች እርሷ መልካም በኾነች ኹኔታ እንጅ አትቅረቡ፡፡ ስፍርንና ሚዛንንም በትክክሉ ሙሉ፡፡ ነፍስን ችሎታዋን እንጂ አናስገድድም፡፡ በተናገራችሁም ጊዜ በዘመዶቻችሁ ላይ ቢኾንም እንኳ (እውነትን በመናገር) አስተካክሉ፡፡ በአላህም ቃል ኪዳን ሙሉ፡፡ እነሆ ትገሰጹ ዘንድ በርሱ አዘዛችሁ፡፡» 6|153|«ይህም ቀጥተኛ ሲኾን መንገዴ ነው፤ ተከተሉትም፡፡ (የጥመት) መንገዶችንም አትከተሉ፡፡ ከ(ቀጥተኛው) መንገዱ እናንተን ይለያዩዋችኋልና፡፡እነሆ ትጠነቀቁ ዘንድ በርሱ አዘዛችሁ፡፡» 6|154|ከዚያም ለሙሳ በዚያ መልካም በሠራው ላይ (ጸጋችንን) ለማሟላት ነገርንም ሁሉ ለመዘርዘር መጽሐፉን (ለእስራኤል ልጆች) መሪና እዝነት ይኾን ዘንድ ሰጠነው፡፡ እነርሱ በጌታቸው መገናኘት ሊያምኑ ይከጀላልና፡፡ 6|155|ይህም ያወረድነው የኾነ የተባረከ መጽሐፍ ነው፡፡ ተከተሉትም፡፡ ይታዘንላችሁም ዘንድ (ከክህደት) ተጠንቀቁ፡፡ 6|156|«(ያወረድነውም) መጽሐፍ የተወረደው ከፊታችን በሁለቱ ጭፍሮች ላይ ብቻ ነው፡፡ እኛም ከንባባቸው ዘንጊዎች ነበርን» እንዳትሉ ነው፡፡ 6|157|ወይም «እኛ መጽሐፍ በእኛ ላይ በተወረደ ኖሮ ከእነሱ ይበልጥ የተመራን እንኾን ነበር» እንዳትሉ ነው፡፡ ስለዚህ ከጌታችሁ ግልጽ ማስረጃ፣ መምሪያም፣ እዝነትም በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ በአላህም አንቀጾች ካስተባበለና ከእርሷም ከዞረ ሰው ይበልጥ በዳይ ማን ነው እነዚያን አንቀጾቻችንን የሚተውትን ይተውት በነበሩት ምክንያት ብርቱን ቅጣት በእርግጥ እንቀጣቸዋለን፡፡ 6|158|መላእክት ልትመጣላቸው ወይም ጌታህ (ቅጣቱ) ሊመጣ ወይም ከጌታህ ምልክቶች ከፊሉ ሊመጣ እንጂ ይጠባበቃሉን ከጌታህ ምልክቶች ከፊሉ በሚመጣ ቀን ከዚህ በፊት አማኝ ያልኾነችን ነፍስ እምነትዋ ወይም በእምነትዋ (ጊዜ) በጎ ያልሠራችን (ነፍስ ጸጸትዋ) አይጠቅማትም፡፡ ተጠባበቁ እኛ ተጠባባቂዎች ነንና በላቸው፡፡ 6|159|እነዚያ ሃይማኖታቸውን የለያዩ አሕዛብም የኾኑ በምንም ከእነሱ አይደለህም፡፡ ነገራቸው ወደ አላህ ብቻ ነው፡፡ ከዚያም ይሠሩት የነበሩትን ሁሉ ይነገራቸዋል፡፡ 6|160|በመልካም ሥራ የመጣ ሰው ለእርሱ ዐሥር ብጤዎችዋ አሉት፡፡ በክፉ ሥራም የመጣ ሰው ብጤዋን እንጅ አይመነዳም፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 6|161|«እኔ ጌታዬ ወደ ቀጥተኛው መንገድ ትክክለኛን ሃይማኖት ወደ እውነት አዘንባይ ሲኾን የአብርሃምን መንገድ መራኝ፡፡ እርሱም ከአጋሪዎቹ አልነበረም» በል፡፡ 6|162|«ስግደቴ፣ መገዛቴም፣ ሕይወቴም፣ ሞቴም ለዓለማት ጌታ ለአላህ ነው» በል፡፡ 6|163|«ለእርሱ ተጋሪ የለውም፡፡ በዚህም (በማጥራት) ታዘዝኩ፡፡ እኔም የሙስሊሞች መጀመሪያ ነኝ» (በል)፡፡ 6|164|በላቸው «እርሱ (አላህ) የሁሉ ጌታ ሲኾን ከአላህ በቀር ሌላን ጌታ እፈልጋለሁን ነፍስም ሁሉ በራሷ ላይ እንጅ (ክፉን) አትሠራም፡፡ ተሸካሚም (ነፍስ) የሌላይቱን ሸክም (ኃጢአት) አትሸከምም፡፡ ከዚያም መመለሻችሁ ወደ ጌታችሁ ነው፡፡ ወዲያውም በእርሱ ትለያዩበት የነበራችሁትን ሁሉ ይነገራችኋል፡፡» 6|165|እርሱም ያ በምድር ምትኮች ያደረጋችሁ በሰጣችሁም ጸጋ ሊፈትናችሁ ከፊላችሁን ከከፊሉ በላይ በደረጃዎች ከፍ ያደረገ ነው፡፡ ጌታህ ቅጣቱ ፈጣን ነው፡፡ እርሱም እጅግ መሓሪ ሩኅሩኅ ነው፡፡ 7|1|አ.ለ.መ.ሰ (አሊፍ፤ ላም ፤ሚም፤ ሷድ)፡፡ 7|2|(ይህ) ወደ አንተ የተወረደ መጽሐፍ ነው፡፡ በደረትህም ውስጥ ከእርሱ ጭንቀት አይኑር፡፡ (የተወረደውም) በእርሱ ልታስፈራራበትና ለምእምናን መገሠጫ እንዲኾን ነው፡፡ 7|3|ከጌታችሁ ወደእናንተ የተወረደውን ተከተሉ፡፡ ከአላህም ሌላ ረዳቶችን አትከተሉ፡፡ ጥቂትን ብቻ ትገሰጻላችሁ፡፡ 7|4|ከከተማም ልናጠፋት የሻነው ወዲያውም ብርቱ ቅጣታችን ሌሊት ወይም ቀን እነርሱ በቀትር አርፈው ሳሉ የመጣባቸው ብዙ ናቸው፡፡ 7|5|ቅጣታችንም በመጣባቸው ጊዜ «ጸሎታቸው እኛ በደለኞች ነበርን» ከማለት በቀር ሌላ አልነበረም፡፡ 7|6|እነዚያንም ወደነሱ የተላከባቸውን (ሕዝቦች) በእርግጥ መልክተኞቹንም እንጠይቃለን፡፡ 7|7|በእነርሱም ላይ (የነበሩበትን ሁሉ) ከዕውቀት ጋር በእርግጥ እንተርክላቸዋለን፡፡ የራቅንም አልነበርንም፡፡ 7|8|ትክክለኛውም ሚዛን የዚያን ቀን ነው፡፡ ሚዛኖቻቸው የከበዱላቸው ሰዎችም እነዚያ እነርሱ የፈለጉትን ያገኙ ናቸው፡፡ 7|9|ሚዛኖቻቸው የቀለሉባቸው ሰዎችም እነዚያ እነርሱ ተአምራቶቻችንን ይክዱ በነበሩት ምክንያት ነፍሶቻቸውን ያከሰሩ ናቸው፡፡ 7|10|በምድርም ላይ በእርግጥ አስመቸናችሁ፡፡ በእርሷም ላይ ለናንተ መኖሪያዎችን አደረግንላችሁ፤ ምስጋናችሁ በጣም ጥቂት ነው፡፡ 7|11|በእርግጥም ፈጠርናችሁ፡፡ ከዚያም ቀረጽናችሁ፡፡ ከዚያም ለመላእክቶች «ለአዳም ስገዱ» አልን፡፡ ወዲያውም ሰገዱ፡፡ ኢብሊስ (ዲያብሎስ) ሲቀር ከሰጋጆቹ አልኾነም፡፡ 7|12|(አላህ) «ባዘዝኩህ ጊዜ ከመስገድ ምን ከለከለህ» አለው፡፡ «እኔ ከርሱ የበለጥኩ ነኝ፡፡ ከእሳት ፈጠርከኝ፡፡ እርሱን ግን ከጭቃ ፈጠርከው» አለ፡፡ 7|13|ከእርሷ ውረድ፤ በእርሷ ውስጥ ልትኮራ አይገባህምና፡፡ ውጣም አንተ ከወራዶቹ ነህና አለው፡፡ 7|14|«እስከሚቀሰቀሱበት ቀን ድረስ አቆየኝ» አለ፡፡ 7|15|፡-አንተ ከሚቆዩት ነህ አለው፡፡ 7|16|«ስለአጠመምከኝም ለእነርሱ በቀጥተኛው መንገድ ላይ በእርግጥ እቀመጥባቸዋለሁ» አለ፡፡ 7|17|«ከዚያም ከስተፊቶቻቸው ከኋላቸውም ከቀኞቻቸውም ከግራዎቻቸውም በእርግጥ እመጣባቸዋለሁ፡፡ አብዛኞቻቸውንም አመስጋኞች ኾነው አታገኛቸውም» (አለ)፡፡ 7|18|«የተጠላህ ብራሪ ስትኾን ከእርሷ ውጣ፡፡ ከእነርሱ የተከተለህ ከእናንተ ከመላችሁም ገሀነምን በእርግጥ እሞላታለሁ» አለው፡፡ 7|19|«አዳም ሆይ! አንተም ሚስትህም በገነት ተቀመጡ፡፡ ከሻችሁትም ስፍራ ብሉ፡፡ ግን ይህችን ዛፍ አትቅረቡ፡፡ (ራሳቸውን) ከሚበድሉት ትኾናላችሁና» (አላቸው)፡፡ 7|20|ሰይጣንም ከሐፍረተ ገላቸው የተሸሸገውን ለእነርሱ ሊገልጽባቸው በድብቅ ንግግር ጎተጎታቸው፡፡ «ጌታችሁም መልኣኮች እንዳትኾኑ ወይም ከዘላለም ነዋሪዎች እንዳትኾኑ እንጂ ከዚህች ዛፍ አልከለከላችሁም» አላቸው፡፡ 7|21|«እኔ ለእናንተ በእርግጥ ከሚመክሩዋችሁ ነኝ» ሲልም አማለላቸው፡፡ 7|22|በማታለልም አዋረዳቸው፡፡ ከዛፊቱም በቀመሱ ጊዜ ኀፍረተ ገላቸው ለሁለቱም ተገለጠችላቸው፡፡ ከገነት ቅጠልም በላያቸው ላይ ይደርቱ ጀመር፡፡ ጌታቸውም «ከዚህ ዛፍ አልከለከልኋችሁምን ሰይጣንም ለእናንተ ግልጽ ጠላት ነው አላልኳችሁምን» ሲል ጠራቸው፡፡ 7|23|«ጌታችን ሆይ! ነፍሶቻችንን በደልን፡፡ ለእኛ ባትምር ባታዝንልንም በእርግጥ ከከሳሪዎቹ እንኾናለን» አሉ፡፡ 7|24|(አላህ) « ከፊላችሁ ለከፊሉ ጠላት ሲኾን ውረዱ፡፡ ለእናንተም በምድር ላይ እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ መርጊያና መጠቀሚያ አላችሁ» አላቸው፡፡ 7|25|«በእርሷ ላይ ትኖራላችሁ፡፡ በእርሷም ላይ ትሞታላችሁ፡፡ ከእርሷም ውስጥ ትወጣላችሁ» አላቸው፡፡ 7|26|የአዳም ልጆች ሆይ! ኀፍረተ ገላችሁን የሚሸሽግን ልብስ ጌጥንም በእርግጥ በናንተ ላይ አወረድን፡፡ አላህን የመፍራትም ልብስ ይህ የተሻለ ነው፡፡ ይህ ከአላህ ታምራቶች ነው፡፡ ይገሠጹ ዘንድ (አወረደላቸው)፡፡ 7|27|የአዳም ልጆች ሆይ! ሰይጣን አባትና እናታችሁን ኀፍረተ ገላቸውን ሊያሳያቸው ልብሶቻቸውን ከነሱ የገፈፋቸው ሲኾን ከገነት እንዳወጣቸው ሁሉ እናንተን አይሞክራችሁ፡፡ እነሆ እርሱ ከነሰራዊቱ ከማታዩዋቸው ስፍራ ያዩዋችኋልና፡፡ እኛ ሰይጣናትን ለእነዚያ ለማያምኑት ወዳጆች አድርገናል፡፡ 7|28|መጥፎንም ሥራ በሠሩ ጊዜ በእርሷ ላይ አባቶቻችንን አገኘን አላህም በእርሷ አዞናል ይላሉ፡፡ «አላህ በመጥፎ ነገር አያዝም፡፡ በአላህ ላይ የማታውቁትን ትናገራላችሁን» በላቸው፡፡ 7|29|ጌታዬ በማስተካከል አዘዘ፡፡ በየመስጊዱም ዘንድ ፊቶቻችሁን (እርሱን ለመገዛት) አስተካክሉ፡፡ ሃይማኖትንም ለእርሱ ፍጹም አድርጋችሁ ተገዙት፡፡ እንደጀመራችሁ ትመለሳላችሁ» በላቸው፡፡ 7|30|ከፊሉን ወደ ቅን መንገድ መራ፡፡ ከፊሎቹም በእነሱ ላይ ጥመት ተረጋግጦባቸዋል፡፡ እነርሱ ሰይጣናትን ከአላህ ሌላ ረዳቶች አድርገው ይዘዋልና፡፡ እነርሱም (ቅኑን መንገድ) የተመራን ነን ብለው ያስባሉ፡፡ 7|31|የአዳም ልጆች ሆይ! (ኀፍረተ ገላችሁን የሚሸፍኑትን) ጌጦቻችሁን በመስገጃው ሁሉ ዘንድ ያዙ፡፡ ብሉም፤ ጠጡም፤ አታባክኑም፡፡ እርሱ አባካኞችን አይወድምና፡፡ 7|32|«የአላህን ጌጥ ያችን ለባሮቹ የፈጠራትን ከሲሳይም ጥሩዎቹን እርም ያደረገ ማን ነው» በላቸው፡፡ «እርሷ በትንሣኤ ቀን ለእነዚያ ላመኑት ብቻ ስትኾን በቅርቢቱ ሕይወት ተገቢያቸው ናት» በላቸው፡፡ እንደዚሁ ለሚያውቁ ሕዝቦች አንቀጾችን እናብራራለን፡፡ 7|33|«ጌታዬ እርም ያደረገው መጥፎ ሥራዎችን፣ ከርሷ የተገለጸውንና የተደበቀውን ኃጢኣትንም፣ ያላግባብ መበደልንም፣ በርሱም ማስረጃ ያላወረደበትን (ጣዖት) በአላህ ማጋራታችሁን፣ በአላህም ላይ የማታውቁትን መናገራችሁን ብቻ ነው» በላቸው፡፡ 7|34|ለሕዝብም ሁሉ የተወሰነ ጊዜ አላቸው፡፡ ጊዜያቸውም በመጣ ወቅት አንዲትን ሰዓት አይቆዩም፡፡ (ከጊዜያቱ) አይቀደሙምም፡፡ 7|35|የአዳም ልጆች ሆይ! ከእናንተ ውስጥ በናንተ ላይ አንቀጾቼን የሚያነቡ መልከተኞች ቢመጧችሁ ከእናንተ ክሕደትን የተጠነቀቁና መልካምንም የሠሩ በነሱ ላይ ፍርሃት የለባቸውም፡፡ እነሱም አያዝኑም፡፡ 7|36|እነዚያም በአንቀጾቻችን ያስተባበሉ ከእርሷም የኮሩ እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነሱ በርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 7|37|በአላህ ላይ ውሸትን ከቀጠፈ ወይም በአንቀጾቹ ከአስዋሸ ሰው ይበልጥ በዳይ ማን ነው እነዚያ (ከተጻፈላቸው) ከመጽሐፉ ውስጥ ሲኾን ዕድላቸው ያገኛቸዋል፡፡ (የሞት) መልክተኞቻችንም የሚገድሏቸው ኾነው በመጡባቸው ጊዜ «ከአላህ ሌላ ትገዟቸው የነበራችሁት የት አሉ» ይሏቸዋል፡፡ «ከእኛ ተሰወሩን» ይላሉ፡፡ እነርሱም ከሃዲያን እንደነበሩ በነፍሶቻቸው ላይ ይመሰክራሉ፡፡ 7|38|«ከጋኔንም ከሰውም ከእናንተ በፊት በእርግጥ ካለፉት ሕዝቦች ጋር ኾናችሁ እሳት ውስጥ ግቡ» ይላቸዋል፡፡ አንዲቱ ሕዝብ ወደ እሳት በገባች ቁጥር (ያሳሳተቻትን) ብጤዋን ትረግማለች፡፡ መላውም በውስጧ ተሰብስበው በተገናኙም ጊዜ የኋለኛይቱ ለመጀመሪያይቱ (ተከታዮች ለአስከታዮች) «ጌታችን ሆይ! እነዚህ አሳሳቱን፡፡ ከእሳትም ስቃይ እጥፍን ስጣቸው» ትላለች፡፡ (አላህም)፡- ለሁሉም እጥፍ አለው ግን አታውቁም ይላቸዋል፡፡ 7|39|«መጀመሪያይቱም ለኋለኛይቱ ለእናንተ በእኛ ላይ ምንም ብልጫ አልነበራችሁም» ትላለች፡፡ «ትሠሩትም በነበራችሁት ቅጣቱን ቅመሱ» (ይላቸዋል)፡፡ 7|40|እነዚያ አንቀጾቻችንን ያስተባበሉ ከእርሷም የኮሩ ለእነርሱ የሰማይ ደጃፎች አይከፈቱላቸውም፡፡ ግመል በመርፌ ቀዳዳ እስከሚገባም ድረስ ገነትን አይገቡም፡፡ እንደዚሁም አጋሪዎችን እንቀጣለን፡፡ 7|41|ለእነርሱ ከገሀነም እሳት (በሥራቸው) ምንጣፍ ከበላያቸውም (የእሳት) መሸፈኛዎች አሏቸው፡፡ እንደዚሁም በደለኞችን እንቀጣለን፡፡ 7|42|እነዚያም ያመኑና መልካሞችን የሠሩ ነፍስን ችሎታዋን እንጂ አናስገድድምና፤ እነዚያ የገነት ሰዎች ናቸው፡፡ እነርሱ በርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 7|43|በደረቶቻቸው ውስጥ ያለውንም ጥላቻ እናስወግዳለን፡፡ ወንዞች በሥሮቻቸው ይፈሳሉ፡፡ «ለዚያም ወደዚህ (ላደረሰን ሥራ) ለመራን አላህ ምስጋና ይገባው፡፡ አላህ ባልመራንም ኖሮ አንመራም ነበር፡፡ የጌታችን መልክተኞች በእውነት ላይ ሲኾኑ በእርግጥ መጥተውልናል» ይላሉ፡፡ ይህች ገነት ትሠሩት በነበራችሁት ተሰጣችኋት በማለት ይጠራሉ፡፡ 7|44|የገነትም ሰዎች የእሳትን ሰዎች «ጌታችን ቃል የገባልንን እውነት ኾኖ አገኘን፡፡ ጌታችሁ የዛተባችሁንስ እውነት ኾኖ አገኛችሁትን» ሲሉ ይጣራሉ፡፡ «አዎን አገኘን» ይላሉ፡፡ በመካከላቸውም «የአላህ ርግማን በበደለኞች ላይ ይኹን» ሲል ለፋፊ ይለፍፋል፡፡ 7|45|(በደለኞች) እነዚያ ከአላህ መንገድ የሚከለክሉ፣ (የአላህም መንገድ) እንድትጣመምም የሚፈልጉዋት፣ እነርሱም በመጨረሻዋ ዓለም ከሓዲዎች የኾኑ ናቸው፡፡ 7|46|በመካከላቸውም ግርዶሽ አልለ፡፡ በአዕራፍም ላይ ሁሉንም በምልክታቸው የሚያውቁ ሰዎች አልሉ፡፡ የገነትንም ሰዎች ሰላም ለናንተ ይኹን በማለት ይጣራሉ፡፡ እነርሱም (የአዕራፍ ሰዎች) የሚከጅሉ ሲኾኑ ገና አልገቧትም፡፡ 7|47|ዓይኖቻቸውም ወደ እሳት ሰዎች አቅጣጫ በተዞሩ ጊዜ፡- «ጌታችን ሆይ! ከበደለኞች ጋር አታድርገን» ይላሉ፡፡ 7|48|የአዕራፍም ሰዎች በምልክታቸው የሚያውቁዋቸውን (ታላላቅ) ሰዎች ይጣራሉ፡፡ «ስብስባችሁና በብዛታችሁ የምትኮሩ መኾናችሁም ከእናንተ ምንም አልጠቀማችሁ» ይሏቸዋል፡፡ 7|49|እነዚያ አላህ በችሮታው አያገኛቸውም ብላችሁ የማላችሁት (ደካሞች) እነዚህ ናቸውን «ገነትን ግቡ ፍርሃት የለባችሁም እናንተም አታዝኑም» (ተባሉ ይሏቸዋል)፡፡ 7|50|የእሳትም ሰዎች የገነትን ሰዎች «በእኛ ላይ ከውሃ አፍስሱብን ወይም አላህ ከሰጣችሁ ሲሳይ (ጣሉልን)» ብለው ጠሩዋቸዋል፡፡ እነርሱም «አላህ በከሓዲዎች ላይ እርም አድርጓቸዋል» ይሏቸዋል፡፡ 7|51|እነዚያ ሃይማኖታቸውን መሳለቂያና መጫወቻ አድርገው የያዙ የቅርቢቱም ሕይወት ያታለለቻቸው ይህንን ቀናቸውን መገናኘትን እንደረሱ በተአምራታችንም ይክዱ እንደነበሩ ዛሬ እንረሳቸዋልን፡፡ 7|52|ከዕውቀት ጋርም የዘረዘርነው የኾነን መጽሐፍ ለሚያምኑ ሕዝቦች መምሪያና እዝነት ሲኾን በእርግጥ አመጣንላቸው፡፡ 7|53|(የዛቻውን) ፍጻሜውን እንጂ ሌላ አይጠባበቁም፡፡ ፍጻሜው በሚመጣበት ቀን እነዚያ ከመምጣቱ በፊት የረሱት ሰዎች «የጌታችን መልክተኞች በእርግጥ በውነት መጥተዋል፡፡ ለእኛ ያማልዱም ዘንድ አማላጆች አልሉን ወይስ ከዚያ እንሠራው ከነበርነው ሌላን ሥራ እንሠራ ዘንድ (ወደ ምድረ ዓለም) እንመለሳለን» ይላሉ፡፡ ነፍሶቻቸውን በእርግጥ አከሰሩ፡፡ ይቀጥፉት የነበሩትም ከእነርሱ ጠፋቸው፡፡ 7|54|ጌታችሁ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ አላህ ነው፡፡ ከዚያም (ስልጣኑ) በዐርሹ ላይ ተደላደለ፡፡ (አላህ) ሌሊትን በቀን ፈጥኖ የሚፈልገው ሲኾን ይሸፍናል፡፡ ፀሐይንና ጨረቃንም ከዋክብትንም በትእዛዙ የተገሩ ሲኾኑ (ፈጠራቸው)፡፡ ንቁ! መፍጠርና ማዘዝ የእርሱ ብቻ ነው፡፡ የዓለማት ጌታ አላህ (ክብሩ) ላቀ፡፡ 7|55|ጌታችሁን ተዋርዳችሁ በድብቅም ለምኑት፡፡ እርሱ ወሰን አላፊዎችን አይወድምና፡፡ 7|56|በምድርም ውስጥ ከተበጀች በኋላ አታበላሹ፡፡ ፈርታችሁና ከጅላችሁም ተገዙት፡፡ የአላህ ችሮታ ከበጎ አድራጊዎች ቅርብ ነውና፡፡ 7|57|እርሱም ያ ነፋሶችን ከችሮታው (ከዝናም) በፊት አብሳሪዎች አድርጎ የሚልክ ነው፡፡ ከባዳዎችንም ደመናዎች በተሸከሙ ጊዜ ሙት ወደ ኾነ አገር እንነዳዋለን፡፡ በእርሱም ውሃን እናወርዳለን፡፡ ከፍሬዎችም ሁሉ በእርሱ እናወጣለን፡፡ እንደዚሁ ትገነዘቡ ዘንድ ሙታንን (ከመቃብር) እናወጣለን፡፡ 7|58|መልካሙም አገር በጌታው ፈቃድ በቃዩ (ያማረ ኾኖ) ይወጣል፡፡ ያም መጥፎ የኾነው (በቃዩ) ደካማ ኾኖ እንጂ አይወጣም፡፡ እንደዚሁ ለሚያመሰግኑ ሕዝቦች ታምራትን እናብራራለን፡፡ 7|59|ኑሕን ወደ ወገኖቹ በእርግጥ ላክነው፡፡ አላቸውም፡- «ወገኖቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ለእናንተ ከርሱ ሌላ ምንም አምላክ የላችሁም፡፡ እኔ በእናንተ ላይ የከባድ ቀንን ቅጣት እፈራላችኋለሁ፡፡» 7|60|ከሕዝቦቹ (የካዱት) መሪዎቹ፡- «እኛ በግልጽ መሳሳት ውስጥ ኾነህ በእርግጥ እናይሃለን» አሉት፡፡ 7|61|አላቸው «ወገኖቼ ሆይ! ምንም መሳሳት የለብኝም፡፡ ግን እኔ ከዓለማት ጌታ መልእክተኛ ነኝ፡፡» 7|62|«የጌታዬን መልክቶች አደርስላችኋለሁ፡፡ ለእናንተም እመክራችኋለሁ፡፡ ከአላህም በኩል የማታውቁትን ዐውቃለሁ፡፡» 7|63|«አላህን ልትፈሩና ይታዘንላችሁም ዘንድ ከእናንተው (ጎሳ) በኾነ ሰው ላይ እንዲያስጠነቅቃችሁ ከጌታችሁ ግሳጼ ቢመጣላችሁ ትደነቃላችሁን» (አላቸው)፡፡ 7|64|ወዲያውም አስተባበሉት፡፡ እርሱንና እነዚያንም ከእርሱ ጋር ያሉትን (አማኞች) በታንኳዋ ውስጥ አዳንናቸው፡፡ እነዚያንም በአንቀጾቻችን ያስተባበሉትን አሰጠምን፡፡ እነርሱ (ልበ) ዕውራን ሕዝቦች ነበሩና፡፡ 7|65|ወደ ዓድም ወንድማቸውን ሁድን ላክን፡፡ «ወገኖቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ከእርሱ ሌላ ምንም አምላክ የላችሁም፡፡ (የአላህን ቅጣት) አትፈሩምን» አላቸው፡፡ 7|66|ከሕዝቦቹ እነዚያ የካዱት መሪዎች «እኛ በሞኝነት ላይ ኾነህ በእርግጥ እናይሃለን፡፡ እኛም ከውሸተኞቹ ነህ ብለን እንጠረጥርሃለን» አሉት፡፡ 7|67|(እርሱም) አላቸው «ወገኖቼ ሆይ! እኔ ሞኝነት የለብኝም፡፡ ግን እኔ ከዓለማት ጌታ የተላክሁ ነኝ፡፡» 7|68|«የጌታዬን መልክቶች አደርስላችኋለሁ፡፡ እኔም ለእናንተ ታማኝ መካሪ ነኝ፡፡» 7|69|«ከጌታችሁ የኾነ ግሣጼ ከእናንተው ውስጥ ባንድ ሰው ላይ ያስጠነቀቃችሁ ዘንድ ቢመጣባችሁ ትደነቃላችሁን ከኑሕም ሕዝቦች በኋላ ምትኮች ባደረጋችሁና በፍጠረትም ግዙፍነትን በጨመረላችሁ ጊዜ አስታውሱ፡፡ የሻችሁትንም ታገኙ ዘንድ የአላህን ጸጋዎች አስታውሱ፡፡» 7|70|«አላህን ብቻውን እንድንገዛ አባቶቻችንም ይገዙት የነበረውን (አማልክት) እንድንተው መጣህብን ከውነተኞች ከኾንክ የምታስፈራብንን (ቅጣት) አምጣብን» አሉ፡፡ 7|71|«ከጌታችሁ የኾነ ቅጣትና ቁጣ በእናንተ ላይ በእውነት ተረጋገጠ፡፡ እናንተና አባቶቻችሁም (አማልክት ብላችሁ) በጠራችኋቸው ስሞች አላህ በእርሷ ምንም ማስረጃ ያላወረደባት ስትኾን ትከራከሩኛላችሁን ተጠባባቁም እኔ ከእናንተ ጋር ከተጠባባቂዎቹ ነኝና» አለ፡፡ 7|72|እርሱንና እነዚያንም አብረውት የነበሩትን ከእኛ በኾነው ችሮታ (ከቅጣት) አዳንናቸው፡፡ የእነዚያንም በተአምራታችን ያስተባበሉትንና አማኞች ያልነበሩትን መሠረት ቆረጥን፡፡ 7|73|ወደ ሰሙድም ወንድማቸውን ሷሊህን ላክን፡፡ አላቸው «ወገኖቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ከእርሱ ሌላ ለእናንተ ምንም አምላክ የላችሁም፡፡ (እውነተኛ ለመኾኔ) ከጌታችሁ የኾነች ምልክት በእርግጥ መጥታላችኋለች፡፡ ይህች ለእናንተ ተዓምር ስትኾን የአላህ ግመል ናትና ተዋት፡፡ በአላህ ምድር ውስጥ ትብላ፤ (ትጠጣም)፡፡ በክፉ አትንኳትም፡፡ አሳማሚ ቅጣት ይይዛችኋልና፡፡» 7|74|«ከዓድም በኋላ ምትኮች ባደረጋችሁና በምድሪቱም ላይ ባስቀመጣችሁ ጊዜ አስታውሱ፡፡ ከሜዳዎቿ (ሸክላ) ሕንጻዎችን ትገነባላችሁ፡፡ ከተራራዎችም ቤቶችን ትጠርባላችሁ፡፡ ስለዚህ የአላህን ጸጋዎች አስታውሱ፡፡ በምድርም ውስጥ አጥፊዎች ኾናችሁ አታበላሹ፡፡» 7|75|ከወገኖቹ እነዚያ የኮሩት መሪዎች ለእነዚያ ለተሸነፉት ከነሱ ላመኑት፡- «ሷሊህ ከጌታው መላኩን ታውቃላችሁን» አሏቸው፡፡ « (አዎን)፡- እኛ እርሱ በተላከበት ነገር አማኞች ነን» አሉ፡፡ 7|76|እነዚያ የኮሩት፡- «እኛ በዚያ እናንተ በርሱ ባመናችሁበት ከሓዲዎች ነን» አሉ፡፡ 7|77|ወዲያውም ግመሊቱን ወጓት፡፡ ከጌታቸውም ትዕዛዝ ወጡ፡፡ አሉም፡- «ሷሊህ ሆይ! ከመልክተኞቹ እንደኾንክ የምታስፈራራብንን (ቅጣት) አምጣብን፡፡» 7|78|ወዲያውም የምድር መንቀጥቀጥ (ጩኸትም) ያዘቻቸው፡፡ በቤቶቻቸውም ውስጥ ተንከፍርረው አነጉ፡፡ 7|79|(ሷሊህ) ከእነርሱም ዞረ፡፡ (እንዲህም) አለ «ወገኖቼ ሆይ! የጌታዬን መልክት በእርግጥ አደረስኩላችሁ፡፡ ለእናንተም መከርኳችሁ፡፡ ግን መካሪዎችን አትወዱም፡፡» 7|80|ሉጥንም ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «አስቀያሚን ሥራ ትሠራላችሁን በእርሷ ከዓለማት አንድም አልቀደማችሁም፡፡» 7|81|«እናንተ ከሴቶች ሌላ ወንዶችን በመከጀል በእርግጥ ትመጡባቸዋላችሁ፡፡ በእውነቱ እናንተ ወሰንን አላፊዎች ሕዝቦች ናችሁ፡፡» 7|82|የሕዝቦቹም መልስ « (ሎጥንና ተከታዮቹን) ከከተማችሁ አውጧቸው፡፡ እነሱ የሚጥራሩ ሰዎች ናቸውና» ማለት እንጂ ሌላ አልነበረም፡፡ 7|83|እርሱንና ቤተሰቦቹንም አዳንናቸው ሚስቱ ብቻ ስትቀር፡፡ እርሷ (ለጥፋት) ከቀሩት ኾነች፡፡ 7|84|በእነሱም ላይ (የእሳት) ዝናብን አዘነብንባቸው፡፡ የኃጢአተኞችም መጨረሻ እንዴት እንደነበረ ተመልከት፡፡ 7|85|ወደ መድየንም (ምድያን) ወንድማቸውን ሹዓይብን (ላክን)፤ አላቸው፡- «ወገኖቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ከእርሱ በቀር ምንም አምላክ የላችሁም፡፡ ከጌታችሁ ዘንድ ግልጽ ማስረጃ በእርግጥ መጥታላችኋለች፡፡ ስፍርንና ሚዛንን ሙሉ፡፡ ሰዎችንም አንዳቾቻቸውን (ገንዘቦቻቸውን) አታጉድሉባቸው፡፡ በምድርም ውስጥ ከተበጀች በኋላ አታበላሹ፡፡ ይህ ምእምናን እንደኾናችሁ ለእናንተ የተሻለ ነው፡፡» 7|86|« (ሰዎችን) የምታስፈራሩና ከአላህም መንገድ በእርሱ ያመኑትን የምታግዱ መጥመሟንም የምትፈልጉዋት ኾናችሁ በየመንገዱ አትቀመጡ፡፡ ጥቂቶችም በነበራችሁና ባበዛችሁ ጊዜ አስታውሱ፡፡ የአጥፊዎችም መጨረሻ እንዴት እንደነበረ ተመልከቱ፡፡» 7|87|«ከእናንተም በዚያ እኔ በእርሱ በተላክሁበት ያመኑ ጭፍሮችና ያላመኑ ጭፍሮችም ቢኖሩ በመካከላችን አላህ እስከሚፈርድ ታገሱ፡፡ እርሱም ከፈራጆች ሁሉ በላጭ ነው፡፡» 7|88|ከሕዝቦቹ እነዚያ የኮሩት መሪዎች፡- «ሹዓይብ ሆይ! አንተንና እነዚያን ከአንተጋር ያመኑትን ከከተማችን በእርግጥ እናስወጣችኋለን፡፡ ወይም ወደ ሃይማኖታችን መመለስ አለባችሁ አሉ፡፡ የጠላንም ብንኾን» አላቸው፡፡ 7|89|«አላህ ከእርሷ ከአዳነን በኋላ ወደ ሃይማኖታችሁ ብንመለስ በአላህ ላይ በእርግጥ ውሸትን ቀጠፍን፡፡ አላህ ጌታችን ካልሻም በስተቀር ለእኛ ወደእርሷ ልንመለስ አይገባንም፡፡ ጌታችን ዕውቀቱ ሁሉን ነገር ሰፋ፡፡ በአላህ ላይ ተጠጋን፡፡ ጌታችን ሆይ! በኛና በወገኖቻችን መካከል በውነት ፍረድ፡፡ አንተም ከፈራጆቹ ሁሉ በላጭ ነህ» (አለ) 7|90|ከወገኖቹም እነዚያ የካዱት መሪዎች «ሹዓይብን ብትከተሉ እናንተ ያን ጊዜ ከሳሪዎች ናችሁ» አሉ፡፡ 7|91|ወዲያውም የምድር መንቀጥቀጥ (ጩኸትም) ያዘቻቸው፡፡ በከተማቸውም ውስጥ ተንከፍርረው አነጉ፡፡ 7|92|እነዚያ ሹዓይብን ያሰተባበሉት በእርሷ እንዳልነበሩባት ኾኑ፡፡ እነዚ ሹዓይብን ያስተባበሉት እነርሱ ከሳሪዎች ኾኑ፡፡ 7|93|ከእነርሱም (ትቷቸው) ዞረ፡- «ወገኖቼ ሆይ! የጌታዬን መልክቶች በእርግጥ አደረስኩላችሁ፡፡ ለእናንተም መከርኩ፡፡ ታዲያ በከሓዲዎች ሰዎች ላይ እንዴት አዝናለሁ» አለም፡፡ 7|94|በከተማ አንድንም ነቢይ አልላክንም ሰዎችዋን ይዋደቁ ዘንድ በድህነትና በጉዳት የያዝናቸው ብንኾን እንጂ፡፡ 7|95|ከዚያም እስከበዙና «አባቶቻችንን ድህነትና በሺታ በእርግጥ ነክቷቸዋል፡፡ (ይኽም የጊዜ ልማድ ነው)» እስካሉ ድረስ በመጥፎው ስፍራ በጎውን ለወጥን፡፡ ወዲያውም እነርሱ የማያውቁ ኾነው በድንገት ያዝናቸው፡፡ 7|96|የከተማዋም ሰዎች ባመኑና በተጠነቀቁ ኖሮ በእነሱ ላይ ከሰማይም ከምድርም በረከቶችን በከፈትንላቸው ነበር፡፡ ግን አስተባበሉ፡፡ ይሠሩት በነበሩትም ኃጢኣት ያዝናቸው፡፡ 7|97|የከተማዋ ሰዎችም እነሱ የተኙ ኾነው ቅጣታችን ሌሊት ሊመጣባቸው አይፈሩምን 7|98|የከተማዋ ሰዎችም እነሱ የሚጫወቱ ኾነው ሳሉ ቅጣታችን ቀን በረፋድ ሊመጣባቸው አይፈሩምን 7|99|የአላህንም ማዘናጋት አይፈሩምን የአላህንም ማዘናጋት ከከሳሪዎች ሕዝቦች በስተቀር የሚተማመን የለም፡፡ 7|100|ለእነዚያ ምድርን ከባለቤቶችዋ (ጥፋት) በኋላ ለሚወርሱት ብንሻ ኖሮ በኃጢኣቶቻቸው የምንቀጣቸው መኾናችን አልተገለጸላቸውምን በልቦቻቸውም ላይ እናትማለን፡፡ ስለዚህ እነርሱ አይሰሙም፡፡ 7|101|እነዚህ ከተሞች (ከኑሕ እስከ ሹዓይብ ሰዎች የተነገሩት) ከወሬዎቻቸው ባንተ ላይ እንተርካለን፡፡ መልክተኞቻቸውም በግልጽ ተዓምራት በእርግጥ መጥተዋቸዋል፡፡ ከመምጣታቸው በፊት ባስተባበሉትም ነገር የሚያምኑ አልኾኑም፡፡ እንደዚሁ አላህ በከሓዲያን ልቦች ላይ ያትማል፡፡ 7|102|ለብዙዎቻቸውም በቃል ኪዳናቸው መሙላትን አላገኘንም፡፡ አብዛኞቻቸውንም በእርግጥ አመጸኞች ኾነው አገኘናቸው፡፡ 7|103|ከዚያም ከበኋላቸው ሙሳን ወደ ፈርዖንና ወደ መማክርቶቹ በተዓምራታችን ላክነው፡፡ በእርሷም ካዱ፡፡ ያጥፊዎችም መጨረሻ እንዴት እንደነበረ ተመልከት፡፡ 7|104|ሙሳም አለ፡- «ፈርዖን ሆይ! እኔ ከዓለማት ጌታ የተላክሁ መልክተኛ ነኝ፡፡» 7|105|«»በአላህ ላይ ከእውነት በቀር አለመናገር ተገቢዬ ነው፡፡ ከጌታችሁ በተዓምር በእርግጥ መጣኋችሁ፡፡ የእስራኤልንም ልጆች ከእኔ ጋር ልቀቅ፡፡ 7|106|(ፈርዖንም «በተዓምር የመጣህ እንደኾንክ ከውነተኞቹ ከኾንክ እርሷን አምጣት» አለው፡፡ 7|107|በትሩንም ጣለ፡፡ እርስዋም ወዲያውኑ ግልጽ እባብ ኾነች፡፡ 7|108|እጁንም አወጣ፡፡ እርሷም ወዲያውኑ ለተመልካቾች ነጭ ኾነች፡፡ 7|109|ከፈርዖን ሰዎች መማክርቶቹ፡- «ይህ በእርግጥ ዐዋቂ ድግምተኛ ነው» አሉ፡፡ 7|110|«ከምድራችሁ ሊያወጣችሁ ይሻል» (አሉ)፡፡ «ታዲያ ምን ታዛላችሁ» (አለ) 7|111|(እነርሱም) አሉ «እርሱንና ወንድሙን አቆይ፡፡ ወደ ከተሞቹም ሁሉ ሰብሳቢዎችን (ዘበኞች) ላክ፡፡» 7|112|«ዐዋቂ ድግምተኛ የኾነን ሁሉ ያመጡልሃልና፡፡» 7|113|ድግምተኞቹም ወደ ፈርዖን መጡ፡፡ «እኛ አሸናፊዎች ብንኾን ለእኛ በእርግጥ ዋጋ አለን» አሉ፡፡ 7|114|«አዎን እናንተም በእርግጥ ከባለሟሎቹ ትኾናላችሁ» አላቸው፡፡ 7|115|«ሙሳ ሆይ (በትርህን) ወይም (በፊት) ትጥላለህ ወይም እኛ ጣዮች እንኾናለን» አሉት፡፡ 7|116|«ጣሉ» አላቸው፡፡ (ገመዶቻቸውን) በጣሉም ጊዜ የሰዎቹን ዓይኖች ደገሙባቸው፡፡ አስፈራሩዋቸውም፡፡ ትልቅ ድግምትንም አመጡ፡፡ 7|117|ወደ ሙሳም፡- «በትርህን ጣል» ስንል ላክን፡፡ (ጣላትም) ወዲያውኑም የሚቀጣጥፉትን (ማታለያ) ትውጣለች፡፡ 7|118|እውነቱም ተገለጸ፡፡ ይሠሩት የነበሩትም (ድግምት) ተበላሸ፡፡ 7|119|እዚያ ዘንድ ተሸነፉም፡፡ ወራዶችም ኾነው ተመለሱ፡፡ 7|120|ድግምተኞቹም ሰጋጆች ኾነው ወደቁ፡፡ 7|121|አሉ፡- «በዓለማት ጌታ አመንን፡፡» 7|122|«በሙሳና በሃሩን ጌታ፡፡» 7|123|ፈርዖን አለ፡- «እኔ ለእናንተ ሳልፈቅድላችሁ በፊት በእርሱ አመናችሁን ይህ በከተማይቱ ውስጥ ሰዎቿን ከእርሷ ለማውጣት በእርግጥ የተስማማችሁበት ተንኮል ነው፡፡ ወደፊትም (የሚደርስባችሁን) ታውቃላችሁ፡፡» 7|124|«እጆቻችሁንና እግሮቻችሁን በማፈራረቅ በእርግጥ እቆራርጣለሁ፡፡ ከዚያም ሁላችሁንም በእርግጥ እሰቅላችኋለሁ፡፡» 7|125|አሉ፡- «እኛ ወደ ጌታችን ተመላሾች ነን፡፡» 7|126|«የጌታችንም ተዓምራቶች በመጡልን ጊዜ ከማመናችን በቀር ከእኛ አትጠላም፡፡ ጌታችን ሆይ! በእኛ ላይ ትዕግስትን አፍስስ፡፡ ሙስሊሞች ኾነን ግደለን፡፡» 7|127|ከፈርዖንም ሰዎች ታላላቆቹ (ለፈርዖን) «ሙሳንና ሰዎቹን በምድር ላይ እንዲያበላሹና (ሙሳም) አንተንና አማልክቶችህን እንዲተው ትተዋቸዋለህን» አሉ፡፡ «ወንዶች ልጆቻቸውን እንገድላለን፡፡ ሴቶቻቸውንም እናስቀራለን፡፡ እኛም ከበላያቸው ነን፡፡ አሸናፊዎች (ነን)» አለ፡፡ 7|128|ሙሳ ለሰዎቹ፡- «ለአላህ ተገዙ ታገሱም፡፡ ምድር ለአላህ ናትና፡፡ ከባሮቹ ለሚሻው ያወርሳታል፡፡ ምሰጉንዋም ፍጻሜ ለጥንቁቆቹ ናት» አላቸው፡፡ 7|129|«ከመምጣትህም በፊት ከመጣኽልንም በኋላ ተሰቃየን» አሉት፡፡ «ጌታችሁ ጠላቶቻችሁን ሊያጠፋ እንዴት እንደምትሠሩም ይመለከት ዘንድ በምድር ላይ ሊተካችሁ ይሻል» አላቸው፡፡ 7|130|የፈርዖንንም ቤተሰቦች እንዲገሰጹ በድርቅ ዓመታትና ከፍሬዎችም በመቀነስ በእርግጥ ያዝናቸው፡፡ 7|131|ደጊቱም ነገር (ምቾት) በመጣችላቸው ጊዜ «ይህች ለእኛ (ተገቢ) ናት» ይላሉ፡፡ ክፉትም ብታገኛቸው በሙሳና አብረውት ባሉት ገደቢስነት ያመካኛሉ፡፡ ንቁ! ገደቢስነታቸው አላህ ዘንድ ብቻ ነው፡፡ ግን አብዛኛዎቻቸው አያውቁም፡፡ 7|132|(ለሙሳም) «በማንኛይቱም ተዓምር በእርሷ ልትደግምብን ብትመጣብን እኛ ለአንተ የምናምንልህ አይደለንም» አሉ፡፡ 7|133|ወዲያም የወሃን ማጥለቅለቅ አንበጣንም ነቀዝንም እንቁራሪቶችንም ደምንም የተለያዩ ተዓምራት ሲኾኑ በነሱ ላይ ላክን ኮሩም ተንኮለኞችም ሕዝቦች ነበሩ፡፡ 7|134|በእነርሱም ላይ ቅጣቱ በወደቀባቸው ጊዜ «ሙሳ ሆይ! ጌታህን ላንተ ቃል ኪዳን በገባልህ ነገር ለእኛ ለምንልን፡፡ ከእኛ ቅጣቱን ብታነሳልን ለአንተ በእርግጥ እናምንልሃለን፡፡ የእስራኤልንም ልጆች ከአንተ ጋር በእርግጥ እንለቃለን፤» አሉ፡፡ 7|135|እነርሱም ደራሾቹ እኾኑበት ጊዜ ድረስ ቅጣትን ከእነሱ ላይ ባነሳን ጊዜ ወዲያውኑ እነርሱ ቃላቸውን ያፈርሳሉ፡፡ 7|136|እነርሱ በተዓምራታችን ስለአስተባበሉም ከእርሷ ዘንጊዎች ስለኾኑም፤ ከእነሱ ተበቀልን፡፡ በባሕርም ውስጥ አሰጠምናቸው፡፡ 7|137|እነዚያንም ደካሞች የነበሩትን ሕዝቦች ያችን በውስጧ በረከት ያደረግንባትን ምድር ምሥራቆችዋንም ምዕራቦቿንም አወረስናቸው፡፡ የጌታህም መልካሚቱ ቃል በእስራኤል ልጆች ላይ በመታገሳቸው ተፈጸመች፡፡ ፈርዖንና ሰዎቹም ይሠሩት የነበረውን (ሕንጻ) ዳስ ያደርጉትም የነበረውን አፈረስን፡፡ 7|138|የእስራኤልንም ልጆች ባሕሩን አሻገርናቸው፡፡ ለእነርሱ በኾኑ ጣዖታት (መገዛት) ላይ በሚዘወትሩ ሕዝቦች ላይ አለፉም፡፡ «ሙሳ ሆይ፡- ለእነርሱ (ለሰዎቹ) አማልክት እንዷላቸው ለእኛም አምላክን አድርግልን» አሉት፡፡ «እናንተ የምትሳሳቱ ሕዝቦች ናችሁ፤» አላቸው፡፡ 7|139|«እነዚህ እነርሱ በውስጡ ያሉበት ነገር ጠፊ ነው፡፡ ይሰሩት የነበሩትም ብልሹ ነው» (አላቸው)፤ 7|140|«ከአላህ ሌላ እርሱ ከዓለማት ያበለጣችሁ ሲኾን (የምትገዙት) አምላክን እፈልግላችኋለሁን» አለ፡፡ 7|141|ከፈርዖንም ቤተሰቦች ብርቱን ቅጣት የሚያቀምሱዋችሁ ወንዶች ልጆቻችሁን የሚገድሉ ሴቶቻችሁንም የሚተዉ ሲኾኑ ባዳናችሁ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ በዚህም ውስጥ ከጌታችሁ ዘንድ የኾነ ከባድ ፈተና አለበት፡፡ 7|142|ሙሳንም ሰላሳን ሌሊት (ሊጾምና ልናነጋግረው) ቀጠርነው፡፡ በዐስርም (ሌሊት) ሞላናት፡፡ የጌታውም ቀጠሮ አርባ ሌሊት ሲኾን ተፈጸመ፡፡ ሙሳም ለወንድሙ ሃሩን «በሕዝቦቼ ላይ ተተካኝ፡፡ አሳምርም የአጥፊዎችንም መንገድ አትከተል» አለው፡፡ 7|143|ሙሳም ለቀጠሯችን በመጣና ጌታውም ባነጋገረው ጊዜ፡- «ጌታዬ ሆይ! (ነፍስህን) አሳየኝ ወደ አንተ እመለከታለሁና» አለ፡፡ (አላህም)፡- «በፍጹም አታየኝም ግን ወደ ተራራው ተመልከት፡፡ በስፍራውም ቢረጋ በእርግጥ ታየኛለህ» አለው፡፡ ጌታው ለተራራው በተገለጸ ጊዜ እንኩትኩት አደረገው፡፡ ሙሳም ጮሆ ወደቀ፡፡ በአንሰራራም ጊዜ «ጥራት ይገባህ፡፡ ወዳንተ ተመለስኩ፡፡ እኔም (በወቅቱ) የምእምናን መጀመሪያ ነኝ» አለ፡፡ 7|144|(አላህም) አለው፡- «ሙሳ ሆይ! እኔ በመልክቶቼና በማናገሬ በሰዎች ላይ መረጥኩህ፡፡ የሰጡህንም ያዝ፡፡ ከአመስጋኞቹም ኹን፡፡» 7|145|ለእርሱም በሰሌዳዎቹ ላይ ከነገሩ ሁሉ ግሳጼንና ለነገሩም ሁሉ ማብራራትን ጻፍንለት፡፡ (አልንም) በብርታትም ያዛት፡፡ ሕዝቦችህንም በመልካሟ እንዲይዙ እዘዛቸው፡፡ የአመጸኞቹን አገር በእርግጥ አሳያችኋለሁ፡፡ 7|146|እነዚያን ያለአግባብ በምድር ላይ የሚኮሩትን ከአንቀጾቼ በእርግጥ አዞራቸዋለሁ፡፡ ተዓምርንም ሁሉ ቢያዩ በርሷ አያምኑም፡፡ ቅንንም መንገድ ቢያዩ መንገድ አድርገው አይዙትም፡፡ ግን የጥመትን መንገድ ቢያዩ መንገድ አድርገው ይይዙታል፡፡ ይህ እነርሱ በአንቀጾቻችን ስለአስተባበሉና ከእርሷም ዘንጊዎች ስለኾኑ ነው፡፡ 7|147|እነዚያም በአንቀጾቻችንና መጨረሻይቱን ዓለም በመገናኘት ያስተባበሉት ሥራዎቻቸው ተበላሹ፡፡ ይሠሩት የነበረውን እንጂ ይመነዳሉን 7|148|የሙሳም ሕዝቦች ከእርሱ (መኼድ) በኋላ ከጌጦቻቸው ወይፈንን አካልን ለርሱ ማግሳት ያለውን (አምላክ አድርገው) ያዙ፡፡ እርሱ የማያናግራቸው መንገድንም የማይመራቸው መኾኑን አይመለከቱምን (አምላክ አድርገው) ያዙት፡፡ በዳዮችም ኾኑ፡፡ 7|149|በተጸጸቱና እነሱም በእርግጥ የተሳሳቱ መኾናቸውን ባዩ ጊዜ፡- «ጌታችን ባያዝንልንና ባይምረን በእርግጥ ከከሳሪዎቹ እንኾናለን» አሉ፡፡ 7|150|ሙሳም እየተቆጣና እያዘነ ወደ ሕዝቦቹ በተመለሰ ጊዜ «ከእኔ በኋላ በእኔ ላይ የተካችሁት ነገር ከፋ! የጌታችሁን ትእዛዝ ተቻኮላችሁን» አላቸው፡፡ ሰሌዳዎቹንም ጣላቸው፡፡ የወንድሙንም ራስ (ጸጉር) ወደርሱ የሚጎትተው ሲኾን ያዘ፡፡ (ወንድሙም)፡- «የናቴ ልጅ ሆይ! ሕዝቦቹ ናቁኝ፡፡ ሊገድሉኝም ተቃራቡ፡፡ ስለዚህ በእኔ ጠላቶችን አታስደስትብኝ፡፡ ከአመጸኞች ሕዝቦችም ጋር አታድርገኝ» አለው፡፡ 7|151|(ሙሳም)፡- «ጌታዬ ሆይ! ለእኔም ለወንድሜም ማር፡፡ በእዝነትህም ውስጥ አግባን፡፡ አንተም ከአዛኞች ሁሉ ይበልጥ አዛኝ ነህ» አለ፡፡ 7|152|እነዚያ ወይፈኑን (አምላክ አድርገው) የያዙ ከጌታቸው ዘንድ ቁጣ፤ በቅርቢቱም ሕይወት ውርደት በእርግጥ ያገኛቸዋል፡፡ እንዲሁም ቀጣፊዎችን እንቀጣለን፡፡ 7|153|እነዚያም ኃጢአቶችን የሠሩ ከዚያም ከእርሷ በኋላ የተጸጸቱ ያመኑም ጌታህ ከእርሷ በኋላ በእርግጥ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 7|154|ከሙሳም ቁጣው በበረደ ጊዜ ሰሌዳዎቹን በግልባጫቸው ውስጥ ለእነዚያ እነርሱ ጌታቸውን የሚፈሩ ለኾኑት መምሪያና እዝነት ያለባቸው ሲኾኑ ያዘ፡፡ 7|155|ሙሳም ከሕዝቦቹ ውስጥ ለቀጠሮዋችን ሰባን ሰዎች መረጠ፡፡ ብርቱ የምድር እንቅጥቃጤ በያዘቻቸውም ጊዜ ሙሳ አለ «ጌታዬ ሆይ! በሻህ ኖሮ ከአሁን በፊት በአጠፋሃቸው ነበር፡፡ እኔንም (ባጠፋኸኝ ነበር)፡፡ ከእኛ ቂሎቹ በሠሩት ነገር ታጠፋናለህን እርሷ (ፈተናይቱ) ያንተ ፈተና እንጂ ሌላ አይደለችም፡፡ በእርሷ የምትሻውን ታሳስታለህ፡፡ የምትሻውንም ታቀናለህ፡፡ አንተ ረዳታችን ነህና ለእኛ ምሕረት አድርግልን፡፡ እዘንልንም፡፡ አንተም ከመሓሪዎች ሁሉ በላጭ ነህ፡፡» 7|156|«ለእኛም በዚች በቅርቢቱ ዓለም መልካሟን በመጨረሻይቱም (መልካሟን) ጻፍልን፡፡ እኛ ወደ አንተ ተመለስን፡፡» (ሲል ሙሳ ጸለየ፤ አላህም) አለ፡- «ቅጣቴ በእርሱ የምሻውን ሰው እቀጣበታለሁ፡፡ ችሮታየም ነገሩን ሁሉ ሰፋች፡፡ ለእነዚያም ለሚጠነቀቁ፣ ዘካንም ለሚሰጡ፣ ለእነዚያም እነሱ በአንቀጾቻችን ለሚያምኑ በእርግጥ» እጽፋታለሁ፡፡ 7|157|ለእነዚያ ያንን እነሱ ዘንድ በተውራትና በኢንጂል ተጽፎ የሚያገኙትን የማይጽፍና የማያነብ ነቢይ የኾነውን መልክተኛ የሚከተሉ ለኾኑት (በእርግጥ እጽፍለታለሁ)፡፡ በበጎ ሥራ ያዛቸዋል፡፡ ከክፉም ነገር ይከለክላቸዋል፡፡ መልካም ነገሮችንም ለነርሱ ይፈቅድላቸዋል፡፡ መጥፎ ነገሮችንም በእነርሱ ላይ እርም ያደርግባቸዋል፡፡ ከእነሱም ላይ ሸክማቸውንና እነዚያንም በእነርሱ ላይ የነበሩትን እንዛዝላዎች (ከባድ ሕግጋቶች) ያነሳላቸዋል፡፡ እነዚያም በእርሱ ያመኑ ያከበሩትም የረዱትም ያንንም ከእርሱ ጋር የተወረደውን ብርሃን የተከተሉ እነዚያ እነሱ የሚያድኑ ናቸው፡፡ 7|158|(ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው፡- «እናንተ ሰዎች ሆይ! እኔ ወደናንተ ወደሁላችሁም የአላህ መልክተኛ ነኝ፡፡ (እርሱም) ያ የሰማያትና የምድር ንግሥና ለእርሱ ብቻ የኾነ ነው፡፡ እርሱ እንጂ ሌላ አምላክ የለም፡፡ ሕያው ያደርጋል፡፡ ይገድላልም፡፡ በአላህ በዚያም በአላህና በቃላቶቹ በሚያምነው የማይጽፍ የማያነብ ነቢይ በኾነው መልክተኛው እመኑ፡፡ ቅንንም መንገድ ትመሩ ዘንድ ተከተሉት፡፡» 7|159|ከሙሳም ሕዝቦች በእውነት የሚመሩት በእርሱም (ፍርድን) የሚያስተካክሉ ጭፍሮች አሉ፡፡ 7|160|ዐሥራ ሁለት ነገዶች ሕዝቦች አድርገንም ከፋፈልናቸው፡፡ ወደ ሙሳም ወገኖቹ መጠጣትን በፈለጉበት ጊዜ «ድንጋዩን በበትርህ ምታው» ስንል ላክን፡፡ (መታውም) ከእርሱ ዐሥራ ሁለት ምንጮችም ፈለቁ፡፡ ሰዎቹ ሁሉ መጠጫቸውን በእርግጥ ዐወቁ፡፡ በእነሱም ላይ ደመናን አጠለልን፡፡ በእነሱም ላይ መናንና ድርጭትን አወረድን፡፡ «ከሰጠናችሁም መልካም ሲሳይ ብሉ» (አልን፤ ጸጋችንን በመካዳቸው) አልበደሉንምም፡፡ ግን ነፍሶቻቸውን የሚበድሉ ነበሩ፡፡ 7|161|ለእነርሱም በተባሉ ጊዜ (አስታውስ) «በዚህች ከተማ ተቀመጡ፡፡ ከእርሷም በሻችሁት ስፍራ ብሉ፡፡ (የምንፈልገው) የኃጢኣታችንን መርገፍ ነው በሉም፡፡ የከተማይቱንም በር አጎንብሳችሁ ግቡ፡፡ ኃጢኣቶቻችሁን ለእናንተ እንምራለንና፡፡ በጎ ለሠሩት በእርግጥ እንጨምራለን፡፡» 7|162|ከእነሱም ውስጥ እነዚያ (ራሳቸውን) የበደሉት ሰዎች ከዚያ ለእነርሱ ከተባለው ሌላ የኾነን ቃል ለወጡ፡፡ በእነርሱም ላይ ይበድሉ በነበሩት በደል መዐትን ከሰማይ ላክንባቸው፡፡ 7|163|ከዚያችም በባህሩ ዳርቻ ከነበረችው ከተማ በቅዳሜ (ቀን) ወሰን ባለፉ ጊዜ በሰንበታቸው ቀን ዐሳዎቻቸው የተከማቹ ኾነው በሚመጡላቸው ጊዜ (የኾነውን) ጠይቃቸው፡፡ ሰንበትንም በማያከብሩበት (በሌላው) ቀን አይመጡላቸውም፡፡ እንደዚሁ ያምጹበት በነበሩት ምክንያት እንሞክራቸዋለን፡፡ 7|164|ከእነሱም (ከፊሎቹ) ሕዝቦች «አላህ አጥፊያቸው ወይም በብርቱ ቅጣት ቀጪአቸው የኾኑትን ሕዝቦች ለምን ትገስፃጻላችሁ» ባሉ ጊዜ (ገሳጮቹ) «ወደ ጌታችሁ በቂ ምክንያት እንዲኾንና እነርሱም ቢከለከሉ ብለን ነው» አሉ፡፡ 7|165|በእርሱም የተገሰጹበትን ነገር በተዉ ጊዜ እነዚያን ከክፉ የሚከለከሉትን አዳንን፤ እነዚያንም የበደሉትን ያምጹ በነበሩት ምክንያት በብርቱ ቅጣት ያዝናቸው፡፡ 7|166|ከእርሱም ከተከለከሉት ነገር በኮሩ ጊዜ ለእነሱ «ወረዶች ዝንጀሮች ኹኑ አልን፤» (ኾኑም)፡፡ 7|167|ጌታህም እስከ ትንሣኤ ቀን ክፉ ቅጣትን የሚያቀምሳቸውን ሰው በነሱ ላይ በእርግጥ የሚልክ መኾኑን ባስታወቀ ጊዜ (አስታውሳቸው)፡፡ ጌታህ በእርግጥ ቅጣተ ፈጣን ነው፡፡ እርሱም በእርግጥ እጅግ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 7|168|(የእስራኤልን ልጆች) በምድር ላይ የተለያዩ ሕዝቦች አድርገንም ከፋፈልናቸው፡፡ ከእነሱ መልካሞች አሉ፡፡ ከእነሱም ከዚያ ሌላ አልሉ፡፡ ይመለሱ ዘንድም በተድላዎችም በመከራዎችም ሞከርናቸው፡፡ 7|169|ከኋላቸውም፡- መጽሐፉን የወረሱ መጥፎ ምትኮች ተተኩ፡፡ የዚህን የቅርቡን ጠፊ ጥቅም ይይዛሉ፡፡ ብጤውም ጥቅም ቢመጣላቸው የሚይዙት ሲኾኑ « (በሠራነው)፡- ለኛ ምሕረት ይደረግልናል» ይላሉ፡፡ በአላህ ላይ ከእውነት በቀር እንዳይናገሩ በእነርሱ ላይ የመጽሐፉ ቃል ኪዳን አልተያዘባቸውምን በእርሱ ውስጥ ያለውንም አላነበቡምን የመጨረሻይቱም አገር ለእነዚያ ጌታቸውን ለሚፈሩት በላጭ ናት፡፡ አታውቁምን 7|170|እነዚያም መጽሐፉን ጠብቀው የሚይዙ ሶላትንም በደንቡ የሰገዱ እኛ የመልካም ሠሪዎችን ዋጋ አናጠፋም፡፡ 7|171|የጡርን ተራራ ነቅለን ከበላያቸው እንደ ጥላ ኾኖ በአነሳነውና እርሱም በነሱ ላይ ወዳቂ መኾኑን ባረጋገጡ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «የሰጠናችሁን በብርታት ያዙ፡፡ ትጠነቀቁም ዘንድ በውስጡ ያለውን ተገንዘቡ» (አልን)፡፡ 7|172|ጌታህም ከአደም ልጆች ከጀርቦቻቸው ዘሮቻቸውን ባወጣና «ጌታችሁ አይደለሁምን» ሲል በነፍሶቻቸው ላይ ባስመሰከራቸው ጊዜ (የኾነውን አስታውስ)፡፡ «ጌታችን ነህ መሰከርን» አሉ፡፡ «በትንሣኤ ቀን ከዚህ (ኪዳን) ዘንጊዎች ነበርን እንዳትሉ፡፡» 7|173|ወይም «(ጣዖታትን) ያጋሩት ከእኛ በፊት የነበሩት አባቶቻችን ብቻ ናቸው፡፡ እኛም ከእነሱ በኋላ የኾን ዘሮች ነበርን፡፡ አጥፊዎቹ በሠሩት ታጠፋናለህን» እንዳትሉ (አስመሰከርናችሁ)፡፡ 7|174|እንደዚሁም (እንዲያስቡ) እንዲመለሱም አንቀጾችን እናብራራለን፡፡ 7|175|የዚያንም ተዓምራታችንን የሰጠነውንና ከእርሷ የወጣውን ሰይጣንም ያስከተለውን ከጠማሞቹም የኾነውን ሰው ወሬ በእነርሱ ላይ አንብብላቸው፡፡ 7|176|በሻንም ኖሮ በእርሷ ከፍ ባደረግነው ነበር፡፡ እርሱ ግን ወደ ምድር ተዘነበለ፡፡ ፍላጎቱንም ተከተለ፡፡ ብጤውም ብታባርረው ምላሱን አውጥቶ የሚያለከልክ ወይም ብትተወው ምላሱን አውጥቶ የሚያለከልክ እንደ ኾነ ውሻ ነው፡፡ ይህ የእነዚያ በአንቀጾቻችን ያስተባበሉት ሕዝቦች ምሳሌ ነው፡፡ ያስተነትኑም ዘንድ ታሪኮችን ተርክላቸው፡፡ 7|177|የእነዚያ በአንቀጾቻችን ያስተባበሉትና ነፍሶቻቸውን ይበድሉ የነበሩት ሰዎች ምሳሌ ከፋ! 7|178|አላህ የሚያቀናው ሰው ቅን እርሱ ነው፡፡ የሚያጠመውም ሰው እነዚያ ከሳሪዎቹ እነሱ ናቸው፡፡ 7|179|ከጋኔንም ከሰዎችም ብዙዎችን ለገሀነም በእርግጥ ፈጠርን፡፡ ለእነርሱ በርሳቸው የማያውቁባቸው ልቦች አሏቸው፡፡ ለእነሱም በሳቸው የማያዩባቸው ዓይኖች አሉዋቸው፡፡ ለእነሱም በሳቸው የማይሰሙባቸው ጆሮዎች አሉዋቸው፡፡ እነዚያ እንደ እንስሳዎች ናቸው፡፡ ይልቁንም እነርሱ በጣም የተሳሳቱ ናቸው፡፡ እነዚያ ዘንጊዎቹ እነርሱ ናቸው፤ 7|180|ለአላህም መልካም ስሞች አሉት፡፡ (ስትጸልዩ) በእርሷም ጥሩት፡፡ እነዚያንም ስሞቹን የሚያጣምሙትን ተውዋቸው፡፡ ይሠሩት የነበሩትን ነገር በእርግጥ ይምመነዳሉ፡፡ 7|181|ከፈጠርናቸውም ሰዎች በእውነት የሚመሩ በእርሱም (ፍርድን) የሚያስተካክሉ ሕዝቦች አልሉ፡፡ 7|182|እነዚያንም በአንቀጾቻችን ያስተባበሉትን ከማያውቁት ስፍራ ቀስ በቀስ (ምቾትን በመጨመር) እናዘነጋቸዋለን፡፡ 7|183|ለእነርሱም ጊዜ እሰጣቸዋለሁ ጥበቤ ብርቱ ነውና፡፡ 7|184|በነቢያቸው (በሙሐመድ) ምንም ዕብደት የሌለበት መኾኑን አያስተውሉምን እርሱ ግልጽ አስጠንቃቂ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ 7|185|በሰማያትና በምድር ግዛት ውስጥ ከማንኛው ነገር አላህ በፈጠረውም ሁሉ የሞት ጊዜያቸውም በእርግጥ መቅረቡ የሚፈራ መኾኑን አያስተውሉምን ከእርሱም (ከቁርኣን) ወዲያ በየትኛው ንግግር ያምናሉ፡፡ 7|186|አላህ የሚያጠመው ሰው ለእርሱ ምንም አቅኝ የለውም፡፡ በጥምመታቸውም ውስጥ እየዋለሉ ይተዋቸዋል፡፡ 7|187|ከሰዓቲቱ መቼ እንደምትረጋ (እንደምትመጣ) ይጠይቁሃል፡፡ «ዕውቀቷ በጌታዬ ዘንድ ነው፡፡ በጊዜዋ እርሱ እንጂ ሌላ አይገልጣትም፡፡ በሰማያትና በምድርም ከበደች፡፡ በድንገት ቢኾን እንጂ አትመጣችሁም» በላቸው፡፡ ከእርሷ አጥብቀህ እንደ ተረዳህ አድርገው ይጠይቁሃል፡፡ «ዕውቀቷ አላህ ዘንድ ብቻ ነው፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም» በላቸው፡፡ 7|188|«አላህ የሻውን በስተቀር ለእራሴ ጥቅምንም ጉዳትንም ማምጣት አልችልም፡፡ ሩቅንም (ምስጢር) የማውቅ በነበርኩ ኖሮ ከመልካም ነገር ባበዛሁና ክፉም ነገር ባልነካኝ ነበር፡፡ እኔ ለሚያምኑ ሕዝቦች አስፈራሪና አብሳሪ እንጂ ሌላ አይደለሁም» በላቸው፡፡ 7|189|እርሱ ያ ከአንዲት ነፍስ (ከአደም) የፈጠራችሁ ከእርሷም መቀናጆዋን ወደርሷ ይረካ ዘንድ ያደረገ ነው፡፡ በተገናኛትም ጊዜ ቀላልን እርግዝና አረገዘች፡፡ እርሱንም (ፅንሱን) ይዛው ኼደች፡፡ በከበደችም ጊዜ «ደግን ልጅ ብትሰጠን በእርግጥ ከአመስጋኞቹ እንኾናለን፤» ሲሉ ጌታቸውን አላህን ለመኑ፡፡ 7|190|መልካም ልጅ በሰጣቸውም ጊዜ በሰጣቸው ልጅ (ስም) ለእርሱ ተጋሪዎችን አደረጉለት፡፡ አላህም ከሚያጋሩት ሁሉ ላቀ፡፡ 7|191|ምንንም የማይፈጥሩትንና እነርሱም የሚፈጠሩትን (በአላህ) ያጋራሉን 7|192|ለእነርሱም መርዳትን የማይችሉትን ነፍሶቻቸውንም የማይረዱትን (ያጋራሉን) 7|193|(ጣዖቶቹን) ወደ ቅን መንገድ ብትጠሩዋቸውም አይከተሉዋችሁም፡፡ ብትጠሩዋቸው ወይም እናንተ ዝምተኞችም ብትኾኑ በእናንተ ላይ እኩል ነው፡፡ 7|194|እነዚያ ከአላህ ሌላ የምትገ³ቸው ብጤዎቻችሁ ተገዢዎች ናቸው፡፡ እውነተኞችም እንደኾናችሁ ጥሩዋቸውና ለእናንተ ይመልሱላችሁ፤ (መመለስ ግን አይችሉም)፡፡ 7|195|ለእነርሱ በእርሳቸው የሚኼዱባቸው እግሮች አሉዋቸውን ወይስ ለእነሱ በርሳቸው የሚጨብጡባቸው እጆች አሉዋቸውን ወይስ ለእነሱ በእርሳቸው የሚያዩባቸው ዓይኖች አሉዋቸውን ወይስ ለእነሱ በእርሳቸው የሚሰሙባቸው ጆሮዎች አሉዋቸውን «ያጋራችኋቸውን ጥሩ ከዚያም ተተናኮሉኝ፡፡ ጊዜም አትስጡኝ፤ (አልፈራችሁም)» በላቸው፡፡ 7|196|«የእኔ ረዳቴ ያ መጽሐፉን (ቁርኣንን) ያወረደልኝ አላህ ነውና፤ እርሱም መልካም ሠሪዎችን ይረዳል» (በላቸው)፡፡ 7|197|እነዚያም ከእርሱ በቀር የምትገ³ቸው ሊረÇችሁ አይችሉም፡፡ ነፍሶቻቸውንም አይረዱም፡፡ 7|198|«ወደ ቅንም መንገድ (እንዲመሩዋችሁ) ብትጠሩዋቸው አይሰሙም፤» (በላቸው)፡፡ እነርሱንም የማያዩ ሲኾኑ ወደ አንተ ሲመለከቱ ታያቸዋለህ፡፡ 7|199|ገርን ጠባይ ያዝ፡፡ በመልካምም እዘዝ፡፡ ባለጌዎቹንም ተዋቸው፡፡ 7|200|ከሰይጣንም (በኩል) ጉትጎታ ቢያገኝህ በአላህ ተጠበቅ፡፡ እርሱ ሰሚው ዐዋቂው ነውና፡፡ 7|201|እነዚያ የተጠነቀቁት ከሰይጣን የኾነ ዘዋሪ በነካቸው ጊዜ (ጌታቸውን) ይገነዘባሉ፡፡ ወዲያውም እነሱ ተመልካቾች ይኾናሉ፡፡ 7|202|ወንድሞቻቸውም ጥመትን ይጨምሩላቸዋል፤ ከዚያም (እነርሱ) አይገቱም፡፡ 7|203|በተዓምርም ባልመጣሃቸው ጊዜ (በራስህ) «ለምን አትፈጥራትም» ይላሉ፡፡ ከጌታዬ ወደኔ የተወረደውን ብቻ እከተላለሁ፡፡ ይህ (ቁርኣን) ከጌታችሁ ሲኾን ለሚያምኑ ሕዝቦች መረጃዎችና መምሪያ እዝነትም ነው በላቸው፡፡ 7|204|ቁርኣንም በተነበበ ጊዜ እርሱን አዳምጡ፡፡ ጸጥም በሉ፡፡ ይታዘንላችኋልና፡፡ 7|205|ጌታህንም በምስጢር ተዋድቀህና ፈርተህ ከጩኸት በታችም በኾነ ቃል በጧትም በማታም አውሳው፡፡ ከዘንጊዎቹም አትኹን፡፡ 7|206|እነዚያ እጌታህ ዘንድ ያሉት (መላእክት) እርሱን ከመገዛት አይኮሩም፡፡ ያወድሱታልም፡፡ ለእርሱም ብቻ ይሰግዳሉ፡፡ 8|1|ከጦር ዘረፋ ገንዘቦች ይጠይቁሃል፡፡ «የዘረፋ ገንዘቦች የአላህና የመልክተኛው ናቸው፡፡» ስለዚህ አላህን ፍሩ፡፡ በመካከላችሁ ያለችውንም ኹኔታ አሳምሩ፡፡ አማኞችም እንደኾናችሁ አላህንና መልክተኛውን ታዘዙ በላቸው፡፡ 8|2|ፍጹም ምእምናን እነዚያ አላህ በተወሳ ጊዜ ልቦቻቸው የሚፈሩት፣ በነሱም ላይ አንቀጾቻችን በተነበቡ ጊዜ እምነትን የሚጨምሩላቸው፣ በጌታቸውም ላይ ብቻ የሚመኩት ናቸው፡፡ 8|3|እነዚያ ሶላትን ደንቡን አሟልተው የሚሰግዱ ከሰጠናቸውም ሲሳይ የሚለግሱ ናቸው፡፡ 8|4|እነዚያ በእውነት አማኞች እነሱ ብቻ ናቸው፡፡ ለእነሱ በጌታቸው ዘንድ ደረጃዎች ምህረትና የከበረ ሲሳይም አላቸው፡፡ 8|5|(ይህ በዘረፋ ክፍያ የከፊሉ ሰው መጥላት) ከምእምናን ከፊሉ የጠሉ ሲኾኑ ጌታህ ከቤትህ በእውነት ላይ ኾነህ እንዳወጣህ ነው፡፡ 8|6|እነርሱ እያዩ ወደሞት እንደሚነዱ ኾነው በእውነቱ ነገር (በመጋደል ግዴታነት) ከተገለጸላቸው በኋላ ይከራከሩሃል፡፡ 8|7|አላህም ከሁለቱ ጭፍሮች አንደኛዋን እርሷ ለናንተ ናት ሲል ተስፋ በሰጣችሁ ጊዜ፣ የሀይል ባለቤት ያልኾነችውም (ነጋዴይቱ) ለናንተ ልትኾን በወደዳችሁ ጊዜ፣ አላህም በተስፋ ቃላቱ እውነትን ማረጋገጡን ሊገልጽና የከሓዲዎችንም መጨረሻ ሊቆርጥ በሻ ጊዜ (የኾነውን አስታውስ)፡፡ 8|8|(ይህንንም ያደረገው) አጋሪዎቹ ቢጠሉም እውነቱን ሊያረጋግጥ ክህደትንም ሊያጠፋ ነው፡፡ 8|9|ከጌታችሁ ርዳታን በፈለጋችሁ ጊዜ «እኔ በሺህ መላእክት ተከታታዮች ሲኾኑ እረዳችኋለሁ» ሲል ለናንተ የተቀበላችሁን (አስታውሱ)፡፡ 8|10|አላህም (ይኽንን ርዳታ) ለብስራትና ልቦቻችሁ በርሱ ሊረኩበት እንጂ ለሌላ አላደረገውም፡፡ ድልም መንሳት ከአላህ ዘንድ እንጂ ከሌላ አይደለም፡፡ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና፡፡ 8|11|ከእርሱ በኾነው ጸጥታ (በጦር ግንባር) በእንቅልፍ በሸፈናችሁና ውሃውንም በእርሱ ሊያጠራችሁ፣ የሰይጣንንም ጉትጎታ ከእናንተ ሊያስወግድላችሁ፣ ልቦቻችሁንም (በትዕግስት) ሊያጠነክርላችሁ፣ በእርሱም ጫማዎችን (በአሸዋው ላይ) ሊያደላድልላችሁ በእናንተ ላይ ከሰማይ ባወረደላችሁ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ 8|12|ጌታህ ወደ መላእክቱ «»እኔ (በእርዳታዬ) ከእናንተ ጋር ነኝና እነዚያን ያመኑትን አጽናኑ፡፡ በእነዚያ በካዱት ልቦች ውስጥ ፍርሃትን በእርግጥ እጥላለሁ፡፡ ከአንገቶችም በላይ (ራሶችን) ምቱ፡፡ ከእነሱም የቅርንጫፎችን መለያልይ ሁሉ ምቱ፡፡ ሲል ያወረደውን (አስታውስ)፡፡ 8|13|ይህ እነርሱ አላህንና መልክተኛውን ስለተቃወሙ ነው፡፡ አላህንና መልክተኛውንም የሚቃወም ሁሉ አላህ ቅጣቱ ብርቱ ነው፡፡ 8|14|ይህ (ቅጣታችሁ ነው) ቅመሱትም፡፡ ለከሓዲዎችም የእሳት ቅጣት በእርግጥ አለባቸው፡፡ 8|15|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እነዚያን የካዱትን ሰዎች (ለጦር) ሲጓዙ ባገኛችኋቸው ጊዜ ጀርባዎችን አታዙሩላቸው፡፡ 8|16|ያን ጊዜም ለግድያ ለመዘዋወር ወይም ወደ ሠራዊት ለመቀላቀል ሳይኾን ጀርባውን የሚያዞርላቸው ሰው ከአላህ በኾነ ቁጣ በእርግጥ ተመለሰ፡፡ መኖሪያውም ገሀነም ናት፡፡ መመለሻይቱም ከፋች፡፡ 8|17|አልገደላችኋቸውም ግን አላህ ገደላቸው፡፡ (ጭብጥን ዐፈር) በወረወርክም ጊዜ አንተ አልወረወርክም፡፡ ግን አላህ ወረወረ (ወደ ዓይኖቻቸው አደረሰው)፡፡ ለአማኞችም ከርሱ የኾነን መልካም ጸጋ ለመስጠት (ይህን አደረገ)፡፡ አላህ ሰሚ ዐዋቂ ነውና፡፡ 8|18|ይህ (ዕውነት ነው)፡፡ አላህም የከሓዲዎችን ተንኮል አድካሚ ነው፡፡ 8|19|ፍትሕን (ፍርድን) ብትጠይቁ ፍትሑ በእርግጥ መጥቶላችኋል፡፡ (ክህደትንና መዋጋትን) ብትከለከሉም እርሱ ለእናንተ የተሻለ ነው፡፡ (ወደ መጋደል) ብትመለሱም እንመለሳለን፡፡ ሰራዊታችሁም ብትበዛም እንኳ ከናንተ ምንም አትጠቅማችሁም፡፡ አላህም ከምእምናን ጋር ነው፡፡ 8|20|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህንና መልክተኛውን ታዘዙ፡፡ እናንተም የምትሰሙ ስትኾኑ ከርሱ አትሽሹ፡፡ 8|21|እንደነዚያም እነሱ የማይሰሙ ሲኾኑ ሰማን እንዳሉት አትሁኑ፡፡ 8|22|ከተንቀሳቃሾች ሁሉ አላህ ዘንድ መጥፎ ተንኮለኞች እነዚያ የማያውቁት፣ ደንቆሮዎቹ፣ ዲዳዎቹ ናቸው፡፡ 8|23|በውስጣቸውም ደግ መኖሩን አላህ ባወቀ ኖሮ (የመረዳትን መስማት) ባሰማቸው ነበር፡፡ (ደግ የሌለባቸው መኾኑን ሲያውቅ) ባሰማቸውም ኖሮ እነሱ እውነትን የተው ኾነው በሸሹ ነበር፡፡ 8|24|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! (መልክተኛው) ሕያው ወደሚያደርጋችሁ እምነት በጠራችሁ ጊዜ ለአላህና ለመልክተኛው ታዘዙ፡፡ አላህም በሰውየውና በልቡ መካከል የሚጋርድ መኾኑን ወደርሱም የምትሰበሰቡ መኾናችሁን እወቁ፡፡ 8|25|ከናንተም ውስጥ እነዚያን የበደሉትን ብቻ ለይታ የማትነካን ፈተና ተጠንቀቁ፡፡ አላህም ቅጣቱ ብርቱ መኾኑን እወቁ፡፡ 8|26|እናንተም በምድር ላይ የተናቃችሁ ጥቂቶች ኾናችሁ ሳላችሁ ሰዎች ሊነጥቁዋችሁ የምትፈሩ ስትኾኑ ያስጠጋችሁን በእርዳታውም ያበረታችሁን ከመልካሞች ሲሳዮችም ታመሰግኑ ዘንድ የሰጣችሁን አስታውሱ፡፡ 8|27|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህንና መልክተኛውን አትክዱ፡፡ አደራዎቻችሁንም እናንተ እያወቃችሁ አትክዱ፡፡ 8|28|ገንዘቦቻችሁና ልጆቻችሁም ፈተና ብቻ መኾናቸውንና አላህም እሱ ዘንድ ታላቅ ምንዳ ያለው መኾኑን እወቁ፡፡ 8|29|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ብትፈሩ የእውነት መለያን ብርሃን ያደርግላችኋል፡፡ ክፉ ሥራዎቻችሁንም ከእናንተ ላይ ያብስላችኋል፡፡ ለእናንተም ይምራችኋል፡፡ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 8|30|እነዚያም የካዱት ሊያስሩህ ወይም ሊገድሉህ ወይም (ከመካ) ሊያወጡህ ባንተ ላይ በመከሩብህ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ይመክራሉም አላህም ተንኮላቸውን ይመልስባቸዋል፡፡ አላህም ከመካሪዎቹ ሁሉ በላይ ነው፡፡ 8|31|አንቀጾቻችንም በነሱ ላይ በተነበቡ ጊዜ «በእርግጥ ሰምተናል፤ በሻን ኖሮ የዚህን ብጤ ባልን ነበር፤ ይህ የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ጽሑፍ ተረቶች እንጂ ሌላ አይደለም» ይላሉ፡፡ 8|32|«ጌታችን ሆይ! ይህ እርሱ ካንተ ዘንድ (የተወረደ) እውነት እንደ ኾነ በኛ ላይ ከሰማይ ድንጋዮችን አዝንብብን ወይም አሳማሚ ቅጣትን አምጣብን» ባሉም ጊዜ (አስታውስ) 8|33|አላህም አንተ በውስጣቸው እያለህ (ድንጋይ በማዝነብና ባሳማሚ ቅጣት) የሚቀጣቸው አይደለም፡፡ አላህም እነሱ ምህረትን የሚለምኑ ሲኾኑ የሚቀጣቸው አይደለም፡፡ 8|34|እነሱ ከተከበረው መስጊድ የሚከለክሉ ሲኾኑም አላህ (በሰይፍ) የማይቀጣቸው ለነሱ ምን አልላቸው (የቤቱ) ጠባቂዎችም አልነበሩም፡፡ ጠባቂዎቹ (ክሕደትን) ተጠንቃቂዎቹ እንጂ ሌሎቹ አይደሉም፡፡ ግን አብዛኛዎቻቸው አያውቁም፡፡ 8|35|በቤቱ ዘንድም (በካዕባ) ስግደታቸው ማፏጨትና ማጨብጨብ እንጂ ሌላ አልነበረም፡፡ ትክዱት በነበራችሁትም ነገር ቅጣትን ቅመሱ (ይባላሉ)፡፡ 8|36|እነዚያ የካዱት ከአላህ መንገድ ሊከለክሉ ገንዘቦቻቸውን ያወጣሉ፡፡ በእርግጥም ያወጡዋታል፡፡ ከዚያም በእነሱ ላይ ጸጸት ትኾንባቸዋለች፡፡ ከዚያም ይሸነፋሉ፡፡ እነዚያም የካዱት ወደ ገሀነም ይሰበሰባሉ፡፡ 8|37|አላህ መጥፎውን ከመልካሙ ሊለይ መጥፎውንም ከፊሉን በከፊሉ ላይ ሊያደርግና ባንድ ላይ ሊያነባብረው በገሀነም ውስጥም ሊያደርገው (ይሰበሰባሉ)፡፡ እነዚያ እነሱ ከሳሪዎቹ ናቸው፡፡ 8|38|ለነዚያ ለካዱት በላቸው፡- ቢከለከሉ ለእነሱ በእርግጥ ያለፈውን (ሥራ) ምሕረት ይደረግላቸዋል፡፡ (ወደ መጋደል) ቢመለሱም (እናጠፋቸዋለን)፡፡ የቀድሞዎቹ ሕዝቦች ልማድ በእርግጥ አልፋለችና፡፡ 8|39|ሁከትም እስከማትገኝ ሃይማኖትም ሁሉ ለአላህ ብቻ እስከሚኾን ድረስ ተጋደሏቸው፡፡ ቢከለከሉም አላህ የሚሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 8|40|(ከእምነት) ቢዞሩም አላህ ረዳታችሁ መኾኑን ዕወቁ፡፡ (እርሱ) ምን ያምር ጠባቂ! ምን ያምርም ረዳት! 8|41|ከማንኛውም ነገር በጦር (ከከሓዲዎች) የዘረፋችሁትም አንድ አምስተኛው ለአላህና ለመልክተኛው፣ (ለነቢዩ) የዝምድና ባለቤቶችም፣ ለየቲሞችም፣ ለምስኪኖችም፣ ለመንገደኛም የተገባ መኾኑን ዕውቁ፣ በአላህና በዚያም እውነትና ውሸት በተለየበት ቀን ሁለቱ ጭፍሮች በተገናኙበት (በበድር) ቀን በባሪያችን ላይ ባወረድነው የምታምኑ እንደኾናችሁ (ይህንን ዕወቁ)፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 8|42|እናንተ በቅርቢቱ ዳርቻ ኾናችሁ እነርሱም በሩቂቱ ዳርቻ ኾነው የነጋዴዎቹም ጭፍራ ከናንተ በታች ሲኾኑ በሰፈራችሁ ጊዜ (ያደረግንላችሁን አስታውሱ)፡፡ በተቃጠራችሁም ኖሮ በቀጠሮው በተለያያችሁ ነበር፡፡ ግን አላህ ሊሠራው የሚገባውን ነገር ሊፈጽም የሚጠፋ ሰው ከአስረጅ በኋላ እንዲጠፋ ሕያው የሚኾንም ሰው ከአስረጅ በኋላ ሕያው እንዲኾን (ያለቀጠሮ አጋጠማችሁ)፡፡ አላህም በእርግጥ ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 8|43|አላህ በሕልምህ እነሱን ጥቂት አድርጎ ባሳየህ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ እነሱን ብዙ አድርጎ ባሳየህም ኖሮ በፈራችሁና በነገሩ በተጨቃጨቃችሁ ነበር፡፡ ግን አላህ አዳናችሁ፡፡ እርሱ በደረቶች ውስጥ ያለን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 8|44|አላህም ሊሠራው የሚገባን ነገር ይፈጽም ዘንድ በተጋጠማችሁ ጊዜ እነርሱን በዓይኖቻችሁ ጥቂት አድርጎ ያሳያችሁንና በዓይኖቻቸውም ላይ ያሳነሳችሁን (አስታውሱ)፡፡ ነገሮቹም ሁሉ ወደ አላህ ብቻ ይመለሳሉ፡፡ 8|45|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ሰራዊትን በገጠማችሁ ጊዜ እርጉ፤ (መክቱ)፡፡ አላህንም በብዙ አውሱ፤ በእርግጥ ትድናላችሁና፡፡ 8|46|አላህንና መልክተኛውንም ታዘዙ፡፡ አትጨቃጨቁም፡፡ ትፈራላችሁና ኃይላችሁም ትኼዳለችና፡፡ ታገሱም፤ አላህ ከትዕግስተኞች ጋር ነውና፡፡ 8|47|እንደነዚያ ለትዕቢትና ለሰዎች ይዩልኝ ሲሉ ከአላህም መንገድ ለማገድ ከአገራቸው እንደወጡት አትኹኑ፡፡ አላህም በሚሠሩት ሁሉ (በዕውቀቱ) ከባቢ ነው፡፡ 8|48|ሰይጣንም ሥራዎቻቸውን ለእነርሱ ባሳመረላቸውና «ዛሬ ለእናንተ ከሰዎች አሸናፊ የላችሁም እኔም ለእናንተ ረዳት ነኝ» ባለ ጊዜም (አስታውስ)፡፡ ሁለቱ ጭፍሮችም በተያዩ ጊዜ፤ ወደኋላው አፈገፈገ፡፡ «እኔ ከናንተ ንጹህ ነኝ፡፡ እኔ እናንተ የማታዩትን አያለሁ፡፡ እኔ አላህን እፈራለሁ፡፡ አላህም ቅጣተ ብርቱ ነው» አላቸውም፡፡ 8|49|መናፍቃንና እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ያለባቸው «እነዚህን (ሙስሊሞች) ሃይማኖታቸው አታለላቸው» ባሉ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ በአላህም ላይ የሚጠጋ (ያሸንፋል)፤ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና፡፡ 8|50|እነዚያንም የካዱትን መላእክት ፊቶቻቸውንና ጀርባዎቻቸውን እየመቱ «የቃጠሎንም ስቃይ ቅመሱ» (እያሉ) በሚገድሏቸው ጊዜ ብታይ ኖሮ (አስደንጋጭን ነገር ታይ ነበር)፡፡ 8|51|ይህ እጆቻችሁ ባስቀደሙት ምክንያት አላህም ለባሮቹ በዳይ ባለመኾኑ ነው (ይባላሉ)፡፡ 8|52|(የነዚያ ልማድ) እንደ ፈርዖን ቤተሰብና እንደነዚያም ከእነሱ በፊት እንደ ነበሩት ልማድ ነው፡፡ በአላህ አንቀጾች ካዱ፤ አላህም በኃጢኣቶቻቸው ያዛቸው፤ አላህ ኀይለኛ ቅጣተ ብርቱ ነውና፡፡ 8|53|ይህ (ቅጣት) አላህ በሕዝቦች ላይ የለገሰውን ጸጋ በነፍሶቻቸው ያለውን ነገር እስከሚለውጡ ድረስ የማይለውጥ በመኾኑ ምክንያት ነው፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 8|54|እንደ ፈርዖን ቤተሰቦችና እንደእነዚያም ከእነሱ በፊት እንደ ነበሩት ልማድ (እስከሚለውጡ ድረስ አይለውጥባቸውም)፡፡ በጌታቸው ተአምራት አስተባበሉና በኃጢኣቶቻቸው አጠፋናቸው፡፡ የፈርዖንንም ቤተሰቦች አሰጠምናቸው፡፡ ሁሉም በዳዮች ነበሩም፡፡ 8|55|ከሚንቀሳቀሱ እንስሳዎች ሁሉ አላህ ዘንድ ይበልጥ ክፉዎቹ እነዚያ ዘወትር የካዱት ናቸው፡፡ ስለዚህ እነሱ አያምኑም፡፡ 8|56|እነዚያ ከነሱ ቃል ኪዳን የያዝክባቸው ከዚያም በየጊዜው ቃል ኪዳናቸውን የሚያፈርሱ ናቸው፡፡ እነሱም አይጠነቀቁም፡፡ 8|57|በጦርም ላይ ብታገኛቸው በእነርሱ ቅጣት ምክንያት (ሌሎቹ ከሓዲዎች) ይገሰጹ ዘንድ ከኋላቸው ያሉትን በትንባቸው፡፡ 8|58|ከሕዝቦችም ክዳትን ብትፈራ (የኪዳኑን መፍረስ በማወቅ) በመተካከል ላይ ኾናችሁ ኪዳናቸውን ወደነሱ ጣልላቸው፡፡ አላህ ከዳተኞችን አይወድምና፡፡ 8|59|እነዚያም የካዱት ከአላህ ቅጣት ያመለጡ መኾናቸውን አያስቡ፡፡ እነሱ አያቅቱምና፡፡ 8|60|ለእነሱም ከማንኛውም ኃይልና ከታጀቡ ፈረሶችም የቻላችሁትን ሁሉ በእርሱ የአላህን ጠላትና ጠላታችሁን ሌሎችንም ከእነርሱ በቀር ያሉትን የማታውቋቸውን አላህ የሚያውቃቸውን (መናፍቃን) የምታሸብሩበት ስትኾኑ አዘጋጁላቸው፡፡ ከማንኛውም ነገር በአላህ መንገድ የምትለግሱትም ምንዳው ወደናንተ በሙሉ ይሰጣል፡፡ እናንተም አትበደሉም፡፡ 8|61|ወደ ዕርቅም ቢያዘነብሉ ወደ እርሷ አዘንብል፡፡ በአላህም ላይ ተጠጋ፡፡ እነሆ እርሱ ሰሚ ዐዋቂ ነውና፡፡ 8|62|ሊያታልሉህም ቢፈልጉ አላህ በቂህ ነው፡፡ እርሱ ያ በእርዳታውና በምእምናን ያበረታህ ነው፡፡ 8|63|በልቦቻቸውም መካከል ያስማማ ነው፡፡ በምድር ያለውን ሁሉ (ሀብት) በለገስክ ኖሮ በልቦቻቸው መካከል ባላስማማህ ነበር፡፡ ግን አላህ በመካከላቸው አስማማ፡፡ እርሱ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና፡፡ 8|64|አንተ ነቢዩ ሆይ! አላህ በቂህ ነው፡፡ ለተከተሉህም ምእምናን (አላህ በቂያቸው ነው)፡፡ 8|65|አንተ ነቢዩ ሆይ! ምእምናንን በመዋጋት ላይ አደፋፍራቸው፡፡ ከእናንተ ውስጥ ሃያ ታጋሾች ኖሩ ሁለት መቶን ያሸንፋሉ፡፡ ከእናንተም መቶ ቢኖሩ ከእነዚያ ከካዱት እነሱ የማያውቁ ሕዝቦች ስለኾኑ ሺህን ያሸንፋሉ፤ 8|66|አሁን አላህ ከእናንተ ላይ አቀለለላችሁ፡፡ በእናንተ ውስጥም ድክመት መኖሩን ዐወቀ፡፡ ስለዚህ ከእናንተ መቶ ታጋሾች ቢኖሩ ሁለት መቶን ያሸንፋሉ፡፡ ከእናንተም ሺህ ቢኖሩ በአላህ ፈቃድ ሁለት ሺህን ያሸንፋሉ፡፡ አላህም ከታጋሾቹ ጋር ነው፡፡ 8|67|ለነቢይ በምድር ላይ እስቲያደክም ድረስ ለእርሱ ምርኮኞች ሊኖሩት አይገባም፡፡ የቅርቢቱን ዓለም ጠፊ ጥቅም ትፈልጋላችሁ፡፡ አላህም መጨረሻይቱን ይሻል፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 8|68|ከአላህ ያለፈ ፍርድ ባልነበረ ኖሮ በወሰዳችሁት (ቤዛ) ከባድ ቅጣት በነካችሁ ነበር፡፡ 8|69|(ከጠላት) ከዘረፋችሁትም (ሀብት) የተፈቀደ መልካም ሲኾን ብሉ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 8|70|አንተ ነቢዩ ሆይ! ከምርኮኞች በእጆቻችሁ ላሉት በላቸው፡- «አላህ በልቦቻችሁ ውስጥ በጎን ነገር (እምነትን) ቢያውቅ ከእናንተ ከተወሰደባችሁ የተሻለን ይሰጣችኋል፡፡ ለእናንተም ይምራችኋል፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡» 8|71|ሊከዱህም ቢፈልጉ ከዚህ በፊት አላህን በእርግጥ ከድተዋል፡፡ ከነሱም አስመችቶሃል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 8|72|እነዚያ ያመኑና የተሰደዱ፡፡ በአላህም መንገድ ላይ በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸው የታገሉ፡፡ እነዚያም (ስደተኞቹን) ያስጠጉና የረዱ፡፡ እነዚያ ከፊሎቻቸው ለከፊሉ ረዳቶች ናቸው፡፡ እነዚያም ያመኑና ያልተሰደዱ እስከሚሰደዱ ድረስ ከነሱ ምንም ዝምድና የላችሁም፡፡ በሃይማኖትም እርዳታን ቢፈልጉባችሁ በእናንተና በነሱ መካከል ቃል ኪዳን ባላችሁ ሕዝቦች ላይ ካልኾነ በስተቀር በናንተ ላይ መርዳት አለባችሁ፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 8|73|እነዚያም የካዱት ከፊሎቻቸው ለከፊሉ ረዳቶች ናቸው፡፡ (ከምእምናን መረዳዳትን ከከሓዲያን መቆራረጥን) ባትሠሩት በምድር ላይ ሁከትና ታላቅ ጥፋት ይኾናል፡፡ 8|74|እነዚያም ያመኑና የተሰደዱ በአላህም መንገድ ላይ የታገሉ፣ እነዚያም ያስጠጉና የረዱ እነዚያ እነሱ በእውነት አማኞች ናቸው፡፡ ለእነሱም ምሕረትና የከበረ ሲሳይ አላቸው፡፡ 8|75|እነዚያም በኋላ ያመኑና የተሰደዱ፣ ከእናንተም ጋር ኾነው የታገሉ እነዚያ ከናንተው ናቸው፡፡ የዝምድናዎች ባለቤቶችም በአላህ መጽሐፍ ከፊሎቻቸው በከፊሉ (መውረስ) የተገቡ ናቸው፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 9|1|(ይህች) ከአላህና ከመልክተኛው ወደእነዚያ ቃል ኪዳን ወደ ተጋባችኋቸው አጋሪዎች የምትደርስ ንጽሕና ናት፡፡ 9|2|በምድር ላይም አራት ወሮችን (ጸጥተኞች ስትኾኑ) ኺዱ፡፡ እናንተም ከአላህ (ቅጣት) የማታመልጡ መኾናችሁንና አላህም ከሓዲዎችን አዋራጅ መኾኑን ዕወቁ፤ (በሏቸው)፡፡ 9|3|(ይህ) ከአላህና ከመልክተኛው በታላቁ ሐጅ ቀን የወጣ አላህ ከአጋሪዎቹ ንጹሕ ነው መልክተኛውም (እንደዚሁ)፡፡ (ከክህደት) ብትጸጸቱም እርሱ ለእናንተ በላጭ ነው፡፡ (ከእምነት) ብትሸሹም እናንተ አላህን የማታቅቱት መኾናችሁን ዕወቁ በማለት ወደ ሰዎች የሚደርስ ማስታወቂያ ነው፡፡ እነዚያን የካዱትንም በአሳማሚ ቅጣት አብስራቸው፡፡ 9|4|ከአጋሪዎቹ እነዚያ ቃል ኪዳን የተጋባችኋቸውና ከዚያም ምንም ያላጎደሉባችሁ በናንተ ላይም አንድንም ያልረዱባችሁ ሲቀሩ፤ (እነዚህን) ቃል ኪዳናቸውን እስከጊዜያታቸው (መጨረሻ) ሙሉላቸው፡፡ አላህ ጥንቁቆችን ይወዳልና፡፡ 9|5|የተከበሩትም ወሮች ባለቁ ጊዜ አጋሪዎቹን በአገኛችሁባቸው ስፍራ ግደሉዋቸው፡፡ ያዙዋቸውም፣ ክበቡዋቸውም፣ ለእነሱም (መጠባበቅ) በየመንገዱ ተቀመጡ፡፡ ቢጸጸቱም፣ ሶላትንም በደንቡ ቢሰግዱ፣ ግዴታ ምጽዋትንም ቢሰጡ መንገዳቸውን ልቀቁላቸው፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 9|6|ከአጋሪዎችም አንዱ ጥገኝነትን ቢጠይቅ የአላህን ቃል ይሰማ ዘንድ አስጠጋው፡፡ ከዚያም ወደ መጠበቂያው ስፍራ አድርሰው፡፡ ይህ እነሱ የማያውቁ ሕዝቦች በመኾናቸው ነው፡፡ 9|7|ለአጋሪዎቹ አላህ ዘንድና እመልክተኛው ዘንድ ቃል ኪዳን እንዴት ይኖራቸዋል እነዚያ በተከበረው መስጊድ ዘንድ ቃል ኪዳን የተጋባችኋቸው ብቻ ሲቀሩ፡፡ (እነዚህ) በቃል ኪዳናቸው ለእናንተ ቀጥ እስካሉላችሁ ድረስ ለነርሱም ቀጥ በሉላቸው፡፡ አላህ ጥንቁቆችን ይወዳልና፡፡ 9|8|በእናንተ ላይ ቢያይሉም በእናንተ ውስጥ ዝምድናንና ቃል ኪዳንን የማይጠብቁ ሲኾኑ እንዴት (ቃል ኪዳን ይኖራቸዋል)፡፡ በአፎቻቸው ያስወድዷችኋል፡፡ ልቦቻቸውም እንቢ ይላሉ፡፡ አብዛኞቻቸውም አመጸኞች ናቸው፡፡ 9|9|በአላህ አንቀጾች ጥቂትን ዋጋ ገዙ፡፡ ከመንገዱም አገዱ፡፡ እነርሱ ይሠሩት የነበሩት ሥራ ከፋ! 9|10|በምእምን ነገር ዝምድናንም ኪዳንንም አይጠብቁም፤ እነዚያም እነሱ ወሰን አላፊዎች ናቸው፡፡ 9|11|ቢጸጸቱም፣ ሶላትንም ቢሰግዱ፣ ዘካንም ቢሰጡ የሃይማኖት ወንድሞቻችሁ ናቸው፡፡ ለሚያውቁ ሕዝቦችም አንቀጾችን እናብራራለን፡፡ 9|12|ከቃል ኪዳናቸው በኋላ መሓላዎቻቸውን ቢያፈርሱ፣ ሃይማኖታችሁንም ቢያነውሩ፣ የክህደት መሪዎችን (ከክህደት) ይከለከሉ ዘንድ ተዋጉዋቸው፡፡ እነርሱ ቃል ኪዳን የላቸውምና፡፡ 9|13|መሓላዎቻቸውን ያፈረሱትን መልክተኛውንም ለማውጣት ያሰቡትን ሕዝቦች እነሱ ለመጀመሪያ ጊዜ የጀመሩዋችሁ ሲኾኑ ለምን አትዋጉዋቸውም ትፈሩዋቸዋላችሁን ምእምናን እንደ ኾናችሁም አላህ ይበልጥ ልትፈሩት የተገባው ነው፡፡ 9|14|ተጋደሉዋቸው፡፡ አላህ በእጆቻችሁ ያሰቃያቸዋል፡፡ ያዋርዳቸዋልም፡፡ በእነሱም ላይ ይረዳችኋል፡፡ የምእምናን ሕዝቦችንም ልቦች ያሽራል፡፡ 9|15|የልቦቻችሁንም ቁጭት ያስወግዳል፡፡ አላህም ከሚሻው ሰው ላይ ጸጸትን ይቀበላል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 9|16|እነዚያን ከእናንተ ውስጥ የታገሉትንና ከአላህም ከመልክተኛውም ከምእመናንም ሌላ ምስጢረኛ ወዳጅ ያልያዙትን አላህ ሳይገልጽ ልትተው ታስባላችሁን አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 9|17|ለከሓዲዎች በነፍሶቻቸው ላይ በክህደት የሚመሰክሩ ሲኾኑ የአላህን መስጊዶች ሊሠሩ አይገባቸውም፡፡ እነዚያ ሥራዎቻቸው ተበላሹ፡፡ እነሱም በእሳት ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 9|18|የአላህን መስጊዶች የሚሠራው በአላህና በመጨረሻው ቀን ያመነ፣ ሶላትንም በደንቡ የሰገደ፣ ግዴታ ምጽዋትንም የሰጠ ከአላህም ሌላ (ማንንም) ያልፈራ ሰው ብቻ ነው፡፡ እነዚያም ከተመሩት ጭምር መኾናቸው ተረጋገጠ፡፡ 9|19|ካዕባን ጎብኝዎችን ማጠጣትንና የተከበረውን መስጊድ መሥራትን በአላህና በመጨረሻው ቀን እንዳመነና በአላህ መንገድ እንደታገለ ሰው (እምነትና ትግል) አደረጋችሁን አላህ ዘንድ አይተካከሉም፡፡ አላህም በዳዮች ሕዝቦችን አይመራም፡፡ 9|20|እነዚያ ያመኑት፣ ከአገራቸውም የተሰደዱት፣ በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸውም በአላህ መንገድ ላይ የታገሉት አላህ ዘንድ በደረጃ በጣም የላቁ ናቸው፡፡ እነዚያም እነሱ ፍላጎታቸውን ያገኙ ናቸው፡፡ 9|21|ጌታቸው ከርሱ በኾነው እዝነትና ውዴታ በገነቶችም ለነሱ በውስጥዋ የማያቋርጥ መጠቀሚያ ያለባት ስትኾን ያበስራቸዋል፡፡ 9|22|በውስጧ ዘላለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ (ያበስራቸዋል)፡፡ አላህ እርሱ ዘንድ ታላቅ ምንዳ አለና፡፡ 9|23|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አባቶቻችሁና ወንድሞቻችሁ ክህደትን ከእምነት አብልጠው ቢወዱ ወዳጆች አድርጋችሁ አትያዙዋቸው፡፡ ከእናንተም ውስጥ ወዳጅ የሚያደርጋቸው እነዚያ እነሱ በዳዮች ናቸው፤ 9|24|«አባቶቻችሁና ወንዶች ልጆቻችሁ፣ ወንድሞቻችሁም፣ ሚስቶቻችሁም፣ ዘመዶቻችሁም፣ የሰበሰባችኋቸው ሀብቶችም፣ መክሰሩዋን የምትፈሩዋት ንግድም፣ የምትወዷቸው መኖሪያዎችም እናንተ ዘንድ ከአላህና ከመልክተኛው በርሱ መንገድም ከመታገል ይበልጥ የተወደዱ እንደኾኑ አላህ ትእዛዙን እስከሚያመጣ ድረስ ተጠባበቁ» በላቸው፡፡ አላህም አመጸኞች ሕዝቦችን አይመራም፡፡ 9|25|አላህም በብዙ ስፍራዎች በእርግጥ ረዳችሁ፤ የሑነይንም ቀን ብዛታችሁ በአስደነቀቻችሁና ከእናንተም ምንም ባልጠቀመቻችሁ ጊዜ ምድርም ከስፋቷ ጋር በጠበበቻችሁና ከዚያም ተሸናፊዎች ኾናችሁ በዞራችሁ ጊዜ (ረዳችሁ)፡፡ 9|26|ከዚያም አላህ እርጋታውን በመልክተኛውና በምእምናኖቹ ላይ አወረደ፡፡ ያላያችኋቸውንም ሰራዊት አወረደ፡፡ እነዚያን የካዱትንም በመገደልና በመማረክ አሰቃየ፡፡ ይህም የከሓዲያን ፍዳ ነው፡፡ 9|27|ከዚያም ከዚህ በኋላ አላህ በሚሻው ሰው ላይ ጸጸትን ይቀበላል፡፡ አላህም እጅግ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 9|28|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አጋሪዎች እርኩሶች ብቻ ናቸው፡፡ ከዚህም ዓመታቸው በኋላ የተከበረውን መስጊድ አይቅረቡ፡፡ ድኽነትንም ብትፈሩ አላህ ቢሻ ከችሮታው በእርግጥ ያከብራችኋል፡፡ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡ 9|29|ከእነዚያ መጽሐፍን ከተሰጡት ሰዎች እነዚያን በአላህና በመጨረሻው ቀን የማያምኑትን፣ አላህና መልክተኛው እርም ያደረጉትንም እርም የማያደርጉትንና እውነተኛውንም ሃይማኖት የማይቀበሉትን እነርሱ የተዋረዱ ኾነው ግብርን በእጆቻቸው እስከሚሰጡ ድረስ ተዋጉዋቸው፡፡ 9|30|አይሁድ ዑዘይር የአላህ ልጅ ነው አለች፡፡ ክርስቲያኖችም አልመሲሕ የአላህ ልጅ ነው አሉ፡፡ ይህ በአፎቻቸው (የሚናገሩት) ቃላቸው ነው፡፡ የእነዚያን ከነሱ በፊት የካዱትን ሰዎች ቃል ያመሳስላሉ፡፡ አላህ ያጥፋቸው፡፡ (ከእውነት) እንዴት ይመለሳሉ! 9|31|ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ የሌለውን አንድን አምላክ ሊገዙ እንጂ ያልታዘዙ ሲኾኑ ሊቃውንቶቻቸውንና መነኮሳታቸውን፣ የመርየምን ልጅ አልመሲሕንም ከአላህ ሌላ አማልክት አድርገው ያዙ፡፡ ከሚያጋሩት ሁሉ የጠራ ነው፡፡ 9|32|የአላህን ብርሃን በአፎቻቸው ለማጥፋት ይፈልጋሉ፡፡ አላህም ከሓዲዎች ቢጠሉም እንኳ ብርሃኑን መሙላትን እንጅ ሌላን አይሻም፡፡ 9|33|እርሱ ያ አጋሪዎቹ ቢጠሉም መልክተኛውን (ሙሐመድን) በቅን መንገድና በእውነተኛ ሃይማኖት ላይ ከሃይማኖት ሁሉ በላይ ይፋ ያደርገው ዘንድ የላከው ነው፡፡ 9|34|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከሊቃውንትና ከመነኮሳት ብዙዎቹ የሰዎችን ገንዘቦች በውሸት በእርግጥ ይበላሉ፡፡ ከአላህም መንገድ ያግዳሉ፡፡ እነዚያንም ወርቅንና ብርን የሚያደልቡትን በአላህም መንገድ ላይ የማያወጧትን በአሳማሚ ቅጣት አብስራቸው፡፡ 9|35|በርሷ ላይ በገሀነም እሳት ውስጥ በሚጋልባትና ግንባሮቻቸውም፣ ጎኖቻቸውም፣ ጀርባዎቻቸውም በርሷ በሚተኮሱ ቀን (አሳማሚ በኾነ ቅጣት አብስራቸው)፡፡ ይህ ለነፍሶቻችሁ ያደለባችሁት ነው፡፡ ታደልቡት የነበራችሁትንም ቅመሱ (ይባላሉ)፡፡ 9|36|የወሮች ቁጥር አላህ ዘንድ በአላህ መጽሐፍ ውስጥ ሰማያትንና ምድርን በፈጠረበት ቀን ዐሥራ ሁለት ወር ነው፡፡ ከእነሱ አራቱ የተከበሩ ናቸው፡፡ ይህ ቀጥተኛው ሃይማኖት ነው፡፡ በእነርሱ ውስጥም ነፍሶቻችሁን አትበድሉ፡፡ አጋሪዎችንም በአንድ ላይ ኾነው እንደሚዋጉዋችሁ በአንድ ላይ ኾናችሁ ተጋደሉዋቸው፡፡ አላህም ከሚፈሩት ጋር መኾኑን ዕወቁ፡፡ 9|37|የአንዱን ወር ክብር ወደ ሌላው ማዘግየት በክህደት ላይ (ክህደትን) መጨመር ብቻ ነው፡፡ በእርሱ እነዚያ የካዱት ሰዎች ይሳሳቱበታል፡፡ በአንድ ዓመት የተፈቀደ ያደርጉታል፡፡ በሌላው ዓመትም ያወግዙታል፡፡ (ይህ) አላህ ያከበራቸውን ወሮች ቁጥር ሊያስተካክሉ፣ አላህም እርም ያደረገውን የተፈቀደ ሊያደርጉ ነው፡፡ የሥራዎቻቸው መጥፎው ለነርሱ ተዋበላቸው፡፡ አላህም ከሓዲያን ሕዝቦችን አይመራም፡፡ 9|38|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በአላህ መንገድ (ለመታገል) ውጡ በተባላችሁ ጊዜ ወደ ምድር የምትወዘፉት ለእናንተ ምን አላችሁ የቅርቢቱን ሕይወት ከመጨረሻይቱ ይበልጥ ወደዳችሁን የቅርቢቱም ሕይወት ጥቅም በመጨረሻይቱ (አንጻር) ጥቂት እንጂ አይደለም፡፡ 9|39|ለዘመቻ ባትወጡ (አላህ) አሳማሚን ቅጣት ይቀጣችኋል፡፡ ከእናንተ ሌላ የኾኑንም ሕዝቦች ይለውጣል፡፡ በምንም አትጎዱትምም፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 9|40|(ነቢዩን) ባትረዱት እነዚያ የካዱት ሕዝቦች የሁለት (ሰዎች) ሁለተኛ ኾኖ (ከመካ) ባወጡት ጊዜ አላህ በእርግጥ ረድቶታል፡፡ ሁለቱም በዋሻው ሳሉ ለጓደኛው አትዘን አላህ ከእኛ ጋር ነውና ባለ ጊዜ አላህም መረጋጋትን በእርሱ ላይ አወረደ፡፡ ባላያችኋቸውም ሰራዊት አበረታው፡፡ የእነዚያንም የካዱትን ሰዎች ቃል ዝቅተኛ አደረገ፡፡ የአላህም ቃል ለእርሷ ከፍተኛ ናት፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 9|41|ቀላሎችም ከባዶችም ኾናችሁ ዝመቱ፡፡ በአላህም መንገድ በገንዘቦቻችሁ በነፍሶቻችሁም ታገሉ፡፡ ይህ የምታውቁ ብትኾኑ ለናንተ በጣም የተሻለ ነው፡፡ 9|42|(የጠራህባቸው ነገር) ቅርብ ጥቅምና መካከለኛ ጉዞ በኾነ ኖሮ በተከተሉህ ነበር፡፡ ግን በነሱ ላይ መንገዲቱ ራቀችባቸው፡፡ «በቻልንም ኖሮ ከእናንተ ጋር በወጣን ነበር» ሲሉ በአላህ ይምላሉ፡፡ ነፍሶቻቸውን ያጠፋሉ፡፡ አላህም እነሱ ውሸታሞች መኾናቸውን በእርግጥ ያውቃል፡፡ 9|43|አላህ ከአንተ ይቅር አለ፡፡ እነዚያ እውነተኛዎቹ ላንተ እስከሚገለጹልህና ውሸታሞቹንም እስከምታውቅ ድረስ ለነርሱ (እንዲቀሩ) ለምን ፈቀድክላቸው 9|44|እነዚያ በአላህና በመጨረሻው ቀን የሚያምኑት በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸው ከመታገላቸው (ለመቅረት) ፈቃድን አይጠይቁህም፡፡ አላህም የሚፈሩትን ዐዋቂ ነው፡፡ 9|45|ፈቃድን የሚጠይቁህ እነዚያ በአላህና በመጨረሻው ቀን የማያምኑት ልቦቻቸውም የተጠራጠሩት ብቻ ናቸው፡፡ እነሱም በጥርጣሬያቸው ውስጥ ይዋልላሉ፡፡ 9|46|መውጣትንም ባሰቡ ኖሮ ለርሱ ዝግጅትን ባሰናዱ ነበር፡፡ ግን አላህ (ለመውጣት) እንቅስቃሴያቸውን ጠላ (አልሻውም)፡፡ አሰነፋቸውም፡፡ ከተቀማጮቹም ጋር ተቀመጡ ተባሉ፡፡ 9|47|ከእናንተ ጋር በወጡ ኖሮ ጥፋትን እንጂ አይጨምሩላችሁም ነበር፡፡ ሁከትንም የሚፈልጉላችሁ ሲኾኑ በመካከላችሁ (በማሳበቅ) ይቻኮሉ ነበር፡፡ በናንተም ውስጥ ለነሱ አዳማጮች አሏቸው፡፡ አላህም በዳዮችን ዐዋቂ ነው፡፡ 9|48|እነርሱ ጠይዎች ሲኾኑ እውነቱ እስከመጣና የአላህም ትዕዛዝ እስከተገለጸ ድረስ ከዚህ በፊት ሁከትን በእርግጥ ፈለጉ፡፡ ነገሮችንም ሁሉ አገላበጡልህ፡፡ 9|49|ከነሱም ውስጥ «ለእኔ ፍቀድልኝ አትሞክረኝም» የሚል ሰው አልለ፡፡ ንቁ! በመከራ ውስጥ ወደቁ፡፡ ገሀነምም ከሓዲዎችን በእርግጥ ከባቢ ናት፡፡ 9|50|መልካም ነገር ብታገኝህ ታስከፋቸዋለች፡፡ መከራም ብታገኝህ «ከዚህ በፊት በእርግጥ ጥንቃቄያችንን ይዘናል» ይላሉ፡፡ እነርሱም ተደሳቾች ኾነው ይሸሻሉ፡፡ 9|51|«አላህ ለኛ የጻፈልን (ጥቅም) እንጂ ሌላ አይነካንም፡፡ እርሱ ረዳታችን ነው፡፡ በአላህ ላይም ምእመናን ይመኩ» በላቸው፡፡ 9|52|«በእኛ ላይ ከሁለቱ መልካሞች አንደኛዋን እንጂ ሌላን ትጠባበቃላችሁን እኛም አላህ ከእርሱ በኾነው ቅጣት ወይም በእጆቻችን የሚያጠፋችሁ መኾኑን በናንተ ላይ እንጠባበቃለን፡፡ ተጠባበቁም እኛ ከእናንተ ጋር ተጠባባቂዎች ነንና» በላቸው፡፡ 9|53|«ወዳችሁም ኾነ ጠልታችሁ ለግሱ፡፡ ከእናንተ ተቀባይ የላችሁም፡፡ እናንተ አመጸኞች ሕዝቦች ናችሁና» በላቸው፡፡ 9|54|ልግስናዎቻቸውን ከነሱ ተቀባይ የሚያገኙ ከመኾን እነሱ በአላህና በመልክተኛው የካዱ፣ ሶላትንም እነሱ ታካቾች ኾነው በስተቀር የማይሰግዱ፣ እነሱም ጠይዎች ኾነው በስተቀር የማይሰጡ መኾናቸው እንጂ ሌላ አልከለከላቸውም፡፡ 9|55|ገንዘቦቻቸውና ልጆቻቸውም አይድነቁህ፡፡ አላህ የሚሻው በቅርቢቱ ሕይወት በነርሱ (በገንዘቦቻቸውና በልጆቻቸው) ሊቀጣቸው ነፍሶቻቸውም እነሱ ከሓዲዎች ኾነው ሊወጡ ብቻ ነው፡፡ 9|56|እነሱም በእርግጥ ከእናንተ ለመኾናቸው በአላህ ይምላሉ፡፡ እነርሱም ከናንተ አይደሉም፡፡ ግን እነሱ (አጋሪዎችን ያገኘ እንዳያገኛቸው) የሚፈሩ ሕዝቦች ናቸው፡፡ 9|57|መጠጊያን ወይም ዋሻዎችን ወይም መግቢያን (ቀዳዳ) ባገኙ ኖሮ እነርሱ እየገሰገሱ ወደርሱ በሸሹ ነበር፡፡ 9|58|ከነሱም ውስጥ በምጽዋቶች የሚዘልፉህ ሰዎች አሉ፡፡ ከርሷም (የሚሹትን) ቢስሰጡ ይደሰታሉ፡፡ ከርሷም ባይስሰጡ እነሱ ያን ጊዜ ይጠላሉ፡፡ 9|59|እነሱም አላህና መልክተኛው የሰጣቸውን በወደዱ፣ «አላህም በቂያችን ነው፤ አላህ ከችሮታው በእርግጥ ይሰጠናል፣ መልክተኛውም (ይሰጠናል)፣ እኛ ወደ አላህ ከጃዮች ነን» ባሉ ኖሮ (ለነሱ በተሻላቸው ነበር)፡፡ 9|60|ግዴታ ምጽዋቶች (የሚከፈሉት) ለድኾች፣ ለምስኪኖችም፣ በርሷም ላይ ለሚሠሩ ሠራተኞች፣ ልቦቻቸውም (በእስልምና) ለሚለማመዱት፣ ጫንቃዎችንም (በባርነት ተገዢዎችን) ነጻ በማውጣት፣ በባለ ዕዳዎችም፣ በአላህ መንገድም በሚሠሩ፣ በመንገደኛም ብቻ ነው፡፡ ከአላህ የተደነገገች ግዴታ ናት፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 9|61|ከእነሱም (ከመናፍቃን) እነዚያ ነቢዩን የሚያሰቃዩ «እርሱም ጆሮ ነው» (ወሬ ሰሚ ነው) የሚሉ አልሉ በላቸው፡፡ ለእናንተ የበጎ (ወሬ) ሰሚ ነው፡፡ በአላህ ያምናል፣ ምእምናንንም ያምናቸዋል፣ ከእናንተም ውስጥ ለነዚያ ላመኑት እዝነት ነው፡፡ እነዚያም የአላህን መልክተኛ የሚያሰቃዩ ለነሱ አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 9|62|አላህንና መልክተኛውን ሊያስወድዱ ተገቢያቸው ሲኾን እናንተን ያስወደዷችሁ ዘንድ በአላህ ይምሉላችኋል፡፡ ምእምናኖች ቢኾኑ (አላህንና መልክተኛውን ያስወድዱ)፡፡ 9|63|አላህንና መልክተኛውን የሚከራከር ሰው ለእርሱ የገሀነም እሳት በውስጧ ዘውታሪ ሲኾን የተገባቺው መኾኑን አያውቁምን ይህ ታላቅ ውርደት ነው፡፡ 9|64|መናፍቃን በልቦቻቸው ውስጥ ያለውን ነገር የምትነግራቸው ሱራ በእነርሱ ላይ መውረዷን ይፈራሉ፡፡ «አላግጡ አላህ የምትፈሩትን ሁሉ ገላጭ ነው» በላቸው፡፡ 9|65|በእርግጥ ብትጠይቃቸው «እኛ የምንዘባርቅና የምንጫወት ብቻ ነበርን» ይላሉ፡፡ «በአላህና በአንቀጾቹ፣ በመልክተኛውም ታላግጡ ነበራችሁን» በላቸው፡፡ 9|66|አታመካኙ፤ ከእምነታችሁ በኋላ በእርግጥ ካዳችሁ፡፡ ከእናንተ አንዷን ጭፍራ ብንምር (ሌላዋን) ጭፍራ እነሱ ኃጢአተኞች በመኾናቸው እንቀጣለን፡፡ 9|67|መናፍቃንና መናፍቃት ከፊሎቻቸው ከከፊሉ ናቸው፡፡ በመጥፎ ነገር ያዛሉ ከደግም ነገር ይከለክላሉ፡፡ እጆቻቸውንም (ከልግስና) ይሰበስባሉ፡፡ አላህን ረሱ፡፡፤ ስለዚህ (እርሱ) ዋቸው፡፡ መናፍቃን አመጸኞቹ እነሱ ናቸው፡፡ 9|68|መናፍቃንንና መናፍቃትን፣ ከሓዲዎችንም አላህ የገሀነምን እሳት በውስጧ ዘውታሪዎች ሲኾኑ ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ እርሷ በቂያቸው ናት፡፡ አላህም ረግሟቸዋል፡፡ ለእነርሱም ዘውታሪ ቅጣት አላቸው፡፡ 9|69|እንደነዚያ ከናንተ በፊት እንደ ነበሩት ናችሁ፡፡ ከእናንተ ይበልጥ በኃይል የበረቱ በገንዘቦችም በልጆችም ይበልጥ የበዙ ነበሩ፡፡ በዕድላቸውም ተጠቀሙ፡፡ እነዚያም ከእናንተ በፊት የነበሩት በዕድላቸው እንደተጠቀሙ በዕድላችሁ ተጠቀማችሁ፡፡ እንደነዚያም እንደዘባረቁት ዘባረቃችሁ፡፡ እነዚያ ሥራዎቻቸው በቅርቢቱም በመጨረሻይቱም ዓለም ተበላሹ፡፡ እነዚያም ከሳሪዎቹ እነሱ ናቸው፡፡ 9|70|የእነዚያ ከእናንተ በፊት የነበሩት የኑሕ ሕዝቦች፣ የዓድና የሰሙድም፣ የኢብራሂምም ሕዝቦች የመድየን ባለቤቶችና የተገልባጮቹም ከተሞች ወሬ አልመጣላቸውምን መልክተኞቻቸው በተዓምራት መጧቸው፡፡ አላህም የሚበድላቸው አልነበረም፡፡ ግን ነፍሶቻቸውን የሚበድሉ ነበሩ፡፡ 9|71|ምእምንና ምእምናትም ከፊሎቻቸው ለከፊሉ ረዳቶች ናቸው፡፡ በደግ ነገር ያዛሉ፤ ከክፉም ይከለክላሉ፡፡ ሶላትንም ይሰግዳሉ፡፡ ዘካንም ይሰጣሉ፡፡ አላህንና መልክተኛውንም ይታዘዛሉ፡፡ እነዚያን አላህ በእርግጥ ያዝንላቸዋል፡፡ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና፡፡ 9|72|አላህ ምእምናንንና ምእምናትን ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ በመኖሪያ ገነቶችም ውስጥ መልካም መኖሪያ ቤቶችን ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ ከአላህም የኾነው ውዴታ ከሁሉ የበለጠ ነው፡፡ ይህ እርሱ ታላቅ እድል ነው፡፡ 9|73|አንተ ነቢዩ ሆይ! ከሓዲዎችንና መናፍቃንን ታገል፡፡ በእነሱም ላይ ጨክን፡፡ መኖሪያቸውም ገሀነም ናት፡፡ መመለሻይቱም ከፋች፡፡ 9|74|ምንም ያላሉ ለመኾናቸው በአላህ ይምላሉ፡፡ የክህደትንም ቃል በእርግጥ አሉ፡፡ ከእስልምናቸውም በኋላ ካዱ፡፡ ያላገኙትንም ነገር አሰቡ፡፡ አላህም ከችሮታው መልክተኛውም (እንደዚሁ) ያከበራቸው መኾኑን እንጂ ሌላን አልጠሉም፡፡ ቢጸጸቱም ለእነሱ የተሻለ ይኾናል፡፡ ቢሸሹም አላህ በቅርቢቱና በመጨረሻይቱ ዓለም አሳማሚን ቅጣት ይቀጣቸዋል፡፡ ለእነሱም በምድር ውስጥ ምንም ወዳጅና ረዳት የላቸውም፡፡ 9|75|ከእነሱም «አላህን ከችሮታው ቢሰጠን በእርግጥ እንመጸውታለን ከመልካሞቹም በእርግጥ እንኾናለን» ሲል ቃል የተጋባ አልለ፡፡ 9|76|ከችሮታውም በሰጣቸው ጊዜ በእርሱ ሰሰቱ፡፡ እነሱ (ኪዳናቸውን) የተዉ ኾነውም ዞሩ፡፡ 9|77|አላህንም ቃል የገቡለትን በማፍረሳቸውና ይዋሹትም በነበሩት ምክንያት እስከሚገናኙት ቀን ድረስ ንፍቅናን አስከተላቸው፡፡ 9|78|አላህ ምስጢራቸውንና ውይይታቸውን የሚያውቅ መኾኑን አላህም ሩቆችን ሁሉ በጣም ዐዋቂ መኾኑን አያውቁምን 9|79|እነዚያ ከምእምናን በምጽዋቶች ፈቃደኛ የኾኑትን፣ እነዚያንም የችሎታቸውን ያክል እንጅ የማያገኙትን ሰዎች የሚያነውሩ፣ ከእነሱም የሚስቁ አላህ ከነሱ ይሳለቅባቸዋል፤ (ይቀጣቸዋል)፡፡ ለእነሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 9|80|ለእነርሱ ምሕረትን ለምንላቸው፤ ወይም ለእነሱ ምሕረትን አትለምንላቸው (እኩል ነው)፡፡ ለእነሱ ሰባ ጊዜ ምሕረትን ብትለምንላቸው አላህ ለነሱ በፍጹም አይምርም፡፡ ይህ እነርሱ አላህና መልክተኛውን በመካዳቸው ነው፡፡ አላህም አመጸኞች ሕዝቦችን አያቀናም፡፡ 9|81|እነዚያ ከዘመቻ የቀሩት ከአላህ መልክተኛ በኋላ በመቀመጣቸው ተደሰቱ፡፡ በአላህም መንገድ በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸው መታገልን ጠሉ፡፡ «በሐሩር አትኺዱ» አሉም፡፡ «የገሀነም እሳት ተኳሳነቱ በጣም የበረታ ነው» በላቸው፡፡ የሚያውቁ ቢኾኑ ኖሮ (አይቀሩም ነበር)፡፡ 9|82|ጥቂትንም ይሳቁ፡፡ ይሠሩት በነበሩት ዋጋ ብዙን ያለቅሳሉ፡፡ 9|83|ከእነሱም ወደ ኾነችው ጭፍራ አላህ ቢመልስህ (ከአንተ ጋር) ለመውጣትም ቢያስፈቅዱህ፡-«ከኔ ጋር በፍጹም አትወጡም፡፡ ከእኔም ጋር ጠላትን አትዋጉም፡፡ እናንተ በመጀመሪያ ጊዜ መቀመጥን ወዳችኋልና፡፡ ከተቀማጮቹ ጋርም ተቀመጡ» በላቸው፡፡ 9|84|ከእነሱም በአንድም በሞተ ሰው ላይ ፈጽሞ አትስገድ፡፡ በመቃብሩም ላይ አትቁም፡፡ እነሱ አላህንና መልክተኛውን ክደዋልና፡፡ እነሱም አመጸኞች ኾነው ሞተዋልና፡፡ 9|85|ገንዘቦቻቸውና ልጆቻቸውም አይድነቁህ፡፡ አላህ የሚሻው በቅርቢቱ ዓለም በነሱ ሊቀጣቸውና ከሓዲዎችም ኾነው ነፍሶቻቸው እንዲወጡ ብቻ ነው፡፡ 9|86|በአላህ እመኑ፡፡ ከመልክተኛውም ጋር ኾናችሁ ታገሉ፤ በማለት ምዕራፍ በተወረደች ጊዜ ከነሱ የሰፊ ሀብት ባለቤቶች የኾኑት (ለመቅረት) ፈቃድ ይጠይቁሃል፡፡ «ከተቀማጮቹ ጋርም እንኹን ተወን» ይሉሃል፡፡ 9|87|በቤት ከሚቀሩት ጋር መኾናቸውን ወደዱ፡፡ በልቦቻቸውም ላይ (ዝገት) ታተመባቸው፡፡ ስለዚህ እነሱ አያውቁም፡፡ 9|88|ግን መልክተኛው እነዚያም ከርሱ ጋር ያመኑት በገንዘቦቻቸውም በነፍሶቻቸውም ታገሉ፡፡ እነዚያም መልካሞች ሁሉ ለነሱ ናቸው፡፡ እነዚያም እነሱ ምኞታቸውን ያገኙ ናቸው፡፡ 9|89|ለእነሱም ገነቶችን በሥራቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ አላህ አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ይህ ታላቅ ማግኘት ነው፡፡ 9|90|ከአዕራቦችም ይቅርታ ፈላጊዎቹ ለእነሱ እንዲፈቀድላቸው መጡ፡፡ እነዚያ አላህንና መልክተኛውን የዋሹትም ተቀመጡ፡፡ ከነሱ እነዚያን የካዱትን አሳማሚ ቅጣት በእርግጥ ይነካቸዋል፡፡ 9|91|በደካሞች ላይ በበሽተኞችም ላይ በነዚያም የሚያወጡት ገንዘብ በማያገኙት ላይ ለአላህና ለመልክተኛው ፍጹም ታዛዦች ከኾኑ (ባይወጡም) ኃጢኣት የለባቸውም፡፡ በበጎ አድራጊዎች ላይ (የወቀሳ) መንገድ ምንም የለባቸውም፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 9|92|በእነዚያም ልትጭናቸው በመጡህ ጊዜ «በርሱ ላይ የምጭናችሁ (አጋሰስ) አላገኝም፤» ያልካቸው ስትኾን የሚያወጡት ገንዘብ ባለማግኘታቸው ለማዘናቸው ዓይኖቻቸው እንባን እያፈሰሱ በዞሩት ላይ (የወቀሳ መንገድ የለባቸውም)፡፡ 9|93|(የወቀሳ) መንገዱ በእነዚያ እነሱ ባለጸጋዎች ኾነው ሳሉ ለመቅረት ፈቃድ በሚጠይቁህ ሰዎች ላይ ብቻ ነው፡፡ ከቀሪዎቹ ጋር መኾናቸውን ወደዱ፡፡ አላህም በልቦቻቸው ላይ አተመባቸው፤ ስለዚህ እነሱ አያውቁም፡፡ 9|94|ወደእነሱ በተመለሳችሁ ጊዜ ምክንያታቸውን ያቀርቡላችኋል፡፡ አታመካኙ፤ እናንተን ፈጽሞ አናምንም፡፡ አላህ ከወሬዎቻችሁ በእርግጥ ነግሮናልና፡፡ አላህም ሥራችሁን በእርግጥ ያያል፡፡ መልክተኛውም (እንደዚሁ)፤ ከዚያም ሩቅንና ቅርብን ሁሉ ዐዋቂ ወደ ኾነው (አላህ) ትመለሳላችሁ ወዲያውም ትሠሩት የነበራችሁትን ሁሉ ይነግራችኋል በላቸው፡፡ 9|95|ወደእነሱ በተመለሳችሁ ጊዜ እንድትተውዋቸው ለእናንተ በእርግጥ በአላህ ይምላሉ፡፡ እነሱንም ተዋቸው፡፡ እነሱ እርኩሶች ናቸውና፡፡ ይሠሩትም በነበሩት ዋጋ መኖሪያቸው ገሀነም ነው፡፡ 9|96|ከእነሱ ትወዱላቸው ዘንድ ለናንተ ይምሉላችኋል፡፡ ከእነሱ ብትወዱም አላህ አመጸኞች ሕዝቦችን አይወድም፡፡ 9|97|አዕራቦች በክህደትና በንፍቅና በጣም የበረቱ፤ አላህም በመልክተኛው ላይ ያወረደውን ሕግጋት ባለማወቅ የተገቡ ናቸው፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 9|98|ከአዕራቦችም (በአላህ መንገድ) የሚወጣውን (ገንዘብ) ዕዳ አድርጎ የሚይዝ በእናንተም ላይ የጊዜን መገለባበጥ የሚጠባበቅ ሰው አልለ፡፡ በእነሱ ላይ ጥፋቱ ይዙርባቸው፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 9|99|ከአዕራቦችም በአላህና በመጨረሻው ቀን የሚያምን የሚሰጣቸውንም (ምጽዋቶች) አላህ ዘንድ መቃረቢያዎችና ወደ መልክተኛው ጸሎቶች መዳረሻ አድርጎ የሚይዝ ሰው አልለ፡፡ ንቁ! እርሷ ለእነሱ በእርግጥ አቃራቢ ናት፡፡ አላህ በችሮታው ውስጥ (በገነቱ) በእርግጥ ያስገባቸዋል፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 9|100|ከስደተኞቹና ከረዳቶቹም ሲኾኑ የመጀመሪያዎቹ ቀዳሚዎች እነዚያም በበጎ ሥራ የተከተሏቸው አላህ ከእነሱ ወዷል ከእርሱም ወደዋል፡፡ በሥሮቻቸውም ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘለዓለም ነዋሪዎች ሲኾኑ ለእነርሱ አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ 9|101|በዙሪያችሁም ካሉት ከዐረብ ዘላኖች መናፍቃን አልሉ፡፡ ከመዲና ሰዎችም በንፍቅና ላይ በማመጽ የዘወተሩ አልሉ፡፡ አታውቃቸውም፡፡ እኛ እናውቃቸዋለን፡፡ ሁለት ጊዜ እንቀጣቸዋለን፡፡ ከዚያም ወደታላቅ ቅጣት ይመለሳሉ፡፡ 9|102|ሌሎችም በኃጢአቶቻቸው የተናዘዙ መልካም ሥራንና ሌላን መጥፎ ሥራ የቀላቀሉ አልሉ፡፡ አላህ ከእነሱ ጸጸታቸውን ሊቀበል ይከጀላል፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 9|103|ከገንዘቦቻቸው ስትኾን በእርሷ የምታጠራቸውና የምታፋፋቸው የኾነችን ምጽዋት ያዝ፡፡ ለነሱም ጸልይላቸው፡፡ ጸሎትህ ለእነሱ እርጋታ ነውና አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 9|104|አላህ እርሱ ከባሮቹ ንስሓን የሚቀበል ምጽዋቶችንም የሚወስድ መኾኑን አላህም እርሱ ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ መኾኑን አያውቁም 9|105|በላቸውም ሥሩ አላህ ሠራችሁን በእርግጥ ያያልና፡፡ መልክተኛውና ምእምናንም (እንደዚሁ ያያሉ)፡፡ ሩቁንና ቅርቡን ሁሉ ዐዋቂ ወደ ኾነውም (አላህ) በእርግጥ ትመለሳላችሁ፡፡ ትሠሩትም የነበራችሁትን ሁሉ ይነግራችኋል፡፡ 9|106|ሌሎችም ለአላህ ትዕዛዝ የተቆዩ ሕዝቦች አልሉ፡፡ ወይ ይቀጣቸዋል ወይም ከነሱ ላይ ጸጸትን ይቀበላል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 9|107|እነዚያም (ምእምናንን) ለመጉዳት፣ ክህደትንም ለማበርታት፣ በምእምናንም መካከል ለመለያየት፣ ከአሁን በፊት አላህንና መልክተኛውን የተዋጋውንም ሰው ለመጠባበቅ መስጊድን የሠሩት (ከነሱ ናቸው)፡፡ መልካምን ሥራ እንጂ ሌላ አልሻንም ሲሉም በእርግጥ ይምላሉ፡፡ አላህም እነሱ በእርግጥ ውሸታሞች መኾናቸውን ይመሰክራል፡፡ 9|108|በእርሱ ውስጥ በፍጹም አትስገድ፡፡ ከመጀመሪያ ቀን ይዞ በአላህ ፍራቻ ላይ የተመሠረተው (የቁባ) መስጊድ በውስጡ ልትሰግድበት ይልቅ የተገባው ነው፡፡ በእሱ ውስጥ መጥራራትን የሚወዱ ወንዶች አልሉ፡፡ አላህም ተጥራሪዎችን ይወዳል፡፡ 9|109|አላህን በመፍራትና ውዴታውን በመፈለግ ላይ ግንቡን የመሠረተው ሰው ይበልጣልን ወይስ ጎርፍ በሸረሸረው ለመናድ በተቃረበ ገደል አፋፍ ላይ ግንቡን የመሠረተውና በርሱ (ይዞት) በገሀነም እሳት ውስጥ የወደቀ (ይበልጣል)፡፡ አላህም በደለኞች ሕዝቦችን አይመራም፡፡ 9|110|ያ የካቡት ግንባቸው ልቦቻቸው (በሞት) ካልተቆራረጡ በቀር በልቦቻቸው ውስጥ የመጠራጠር ምክንያት ከመኾን አይወገድም፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 9|111|አላህ ከምእምናን ነፍሶቻቸውንና ገንዘቦቻቸውን ገነት ለእነሱ ብቻ ያላቸው በመኾን ገዛቸው፡፡ በአላህ መንገድ ላይ ይጋደላሉ፡፡ ይገድላሉም፤ ይገደላሉም፡፡ በተውራት በኢንጅልና በቁርኣንም (የተነገረውን) ተስፋ በእርሱ ላይ አረጋገጠ፡፡ ከአላህም የበለጠ በኪዳኑ የሚሞላ ማነው በዚያም በእርሱ በተሻሻጣችሁበት ሽያጫችሁ ተደሰቱ፡፡ ይህም እርሱ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ 9|112|(እነርሱ) ተጸጻቺዎች፣ ተገዢዎች፣ አመስጋኞች፣ ጿሚዎች፣ አጎንባሾች፣ በግንባር ተደፊዎች፣ በበጎ ሥራ አዛዦች ከክፉም ከልካዮች፣ የአላህንም ሕግጋት ጠባቂዎች ናቸው ምእምናንንም አብስር፡፡ 9|113|ለነቢዩና ለነዚያ ላመኑት ለአጋሪዎቹ የዝምድና ባለቤቶች ቢኾኑም እንኳ እነሱ (ከሓዲዎቹ) የእሳት ጓዶች መኾናቸው ከተገለጸላቸው በኋላ ምሕረትን ሊለምኑ የሚገባ አልነበረም፡፡ 9|114|የኢብራሂምም ለአባቱ ምሕረትን መለመን ለእርሱ ገብቶለት ለነበረችው ቃል (ለመሙላት) እንጂ ለሌላ አልነበረም፡፡ እርሱም የአላህ ጠላት መኾኑ ለእርሱ በተገለጸለት ጊዜ ከርሱ ራቀ፤ (ተወው)፡፡ ኢብራሂም በእርግጥ በጣም ርኅሩኅ ታጋሽ ነውና፡፡ 9|115|አላህም ሕዝቦችን ከአቀናቸው በኋላ የሚጠነቀቁትን (ሥራ) ለእነሱ እስከሚገልጸላቸው (እስከሚተውትም) ድረስ ጥፋተኛ የሚያደርግ አይደለም፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 9|116|አላህ የሰማያትና የምድር ንግስና የርሱ ብቻ ነው፡፡ ሕያው ያደርጋል፤ ይገድላልም፡፡ ለእናንተም ከርሱ በቀር ጠባቂም ረዳትም የላችሁም፡፡ 9|117|በነቢዩ በነዚያም በችግሪቱ ጊዜያት (በተቡክ ዘመቻ) ከእነሱ የከፊሎቹ ልቦች (ለመቅረት) ሊዘነበሉ ከተቃረቡ በኋላ በተከተሉት ስደተኞችና ረዳቶች ላይ አላህ በእርግጥ ጸጸታቸውን ተቀበለ፡፡ ከዚያም ከእነሱ ንስሓ መግባታቸውን ተቀበለ፡፡ እርሱ ለእነሱ ርኅሩኅ አዛኝ ነውና፡፡ 9|118|በእነዚያም በሦስቱ ሰዎች ላይ ምድር ከስፋትዋ ጋር በእነሱ ላይ እስከ ጠበበች፣ ነፍሶቻቸውም በርሳቸው ላይ እስከተጠበቡ፣ ከአላህም ወደርሱ ቢኾን እንጂ ሌላ መጠጊያ አለመኖሩን እስከ አረጋገጡ ድረስ በተቆዩት ላይ (አላህ ጸጸትን ተቀበለ)፡፡ ከዚያም ይጸጸቱ ዘንድ ወደ ጸጸት መራቸው፡፡ አላህ እርሱ ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ነውና፡፡ 9|119|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ፤ ከእውነተኞቹም ጋር ኹኑ፡፡ 9|120|ለመዲና ሰዎችና ከአዕራብም በዙሪያቸው ላሉት ሰዎች ከአላህ መልክተኛ ወደኋላ ሊቀሩ ነፍሶቻቸውንም ከነፍሱ አብልጠው ሊወዱ አይገባቸውም ነበር፡፡ ይህ (ከመቅረት መከልከል) ለእነርሱ መልካም ሥራ የሚጻፍላቸው ቢኾን እንጅ፡፡ በአላህ መንገድ ላይ ጥምም፣ ድካምም፣ ረኃብም፣ የማይነካቸው ከሐዲዎችንም የሚያስቆጭን ስፍራ የማይረግጡ፣ ከጠላትም የሚጎዳን ነገር (መግደልን መማረክን መዝረፍን) የማያገኙ በመኾናቸው ነው፡፡ አላህ የመልካም ሠሪዎችን ምንዳ አያጠፋምና፡፡ 9|121|ትንሽንም ትልቅንም ልግስና አይለግሱም ወንዝንም አያቋርጡም አላህ ይሠሩት ከነበረው የበለጠን ምንዳ ይመነዳቸው ዘንድ ለእነሱ የሚጻፍላቸው ቢሆን እንጅ፡፡ 9|122|ምእምናንም (ከነቢዩ ጋር ካልኾነ) በሙሉ ሊወጡ አይገባም፡፡ ከእነሱ ውስጥ ከየክፍሉ አንዲት ጭፍራ ለምን አትወጣም፡፡ (ሌሎቹ) ሃይማኖትን እንዲማሩና ወገኖቻቸው ወደነርሱ በተመለሱ ጊዜ እንዲጠነቀቁ ይገስጹዋቸው ዘንድ (ለምን አይቀሩም)፡፡ 9|123|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እነዚያን በአቅራቢያችሁ ያሉትን ከሓዲዎች ተዋጉ፡፡ ከእናንተም ብርታትን ያግኙ፡፡ አላህም ከሚጠነቀቁት ጋር መኾኑን ዕወቁ፡፡ 9|124|ሱራም (ምዕራፍ) በተወረደች ጊዜ ከእነሱ (ከመናፍቃን) ውስጥ ማንኛችሁ ነው ይህች (ምዕራፍ) እምነትን የጨመረችለት የሚል ሰው አልለ፡፡ እነዚያ ያመኑትማ የሚደሰቱ ሲኾኑ እምነትን ጨመረችላቸው፡፡ 9|125|እነዚያም በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ያለባቸውማ በርክሰታቸው ላይ ርክሰትን ጨመረችላቸው፡፡ እነርሱም ከሓዲዎች ኾነው ሞቱ፡፡ 9|126|በየዓመቱ አንድ ወይም ሁለት ጊዜ እነርሱ የሚሞከሩ መኾናቸውን አያዩምን ከዚያም አይጸጸቱምን እነሱም አይገሰጹምን 9|127|(እነሱን የምታነሳ) ምዕራፍም በተወረደች ጊዜ አንድ ሰው ያያችኋልን እያሉ ከፊሎቻቸው ወደ ከፊሉ ይመለከታሉ፡፡ ከዚያም (ተደብቀው) ይኼዳሉ፡፡ እነርሱ የማያውቁ ሕዝቦች በመኾናቸው አላህ ልቦቻቸውን አዞረ፡፡ 9|128|ከጎሳችሁ የሆነ ችግራችሁ በእርሱ ላይ ጽኑ የሆነ፣ በእናንተ (እምነት) ላይ የሚጓጓ፣ በምእምናን (ላይ) ርኅሩኅ አዛኝ የኾነ መልክተኛ በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ 9|129|ቢያፈገፍጉም አላህ በቂዬ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ በእርሱ ላይ ተጠጋሁ እርሱም የታላቁ ዐርሽ ጌታ ነው በላቸው፡፡ 10|1|አ.ለ.ረ (አሊፍ ላም ራ) ይህቺ (ሱራ) ጥበብ ከተመላው መጽሐፍ (ከቁርኣን) አንቀጾች ናት፡፡ 10|2|«ሰዎችን አስፈራራ፡፡ እነዚያንም ያመኑትን ለእነሱ ከጌታቸው ዘንድ መልካም ምንዳ ያላቸው መኾኑን አብስር» በማለት ከነርሱው ወደ ኾነ አንድ ሰው ራእይን ማውረዳችን ለሰዎች ድንቅ ኾነባቸውን ከሓዲዎቹ፡- «ይህ በእርግጥ ግልጽ ድግምተኛ ነው» አሉ፡፡ 10|3|ጌታችሁ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ አላህ ነው፡፡ ከዚያም ነገሩን ሁሉ የሚያስተናብር ሲኾን በዐርሹ ላይ (ስልጣኑ) ተደላደለ፡፡ ከእርሱ ፈቃድ በኋላ ቢኾን እንጂ አንድም አማላጅ የለም፡፡ እነሆ! አላህ ጌታችሁ ነውና ተገዙት፤ አትገሰጹምን 10|4|ሁላችሁም ኾናችሁ መመለሻችሁ ወደ እርሱ ነው፡፡ (ይህም) የተረጋገጠ የአላህ ቃል ኪዳን ነው፤ እርሱ መፍጠርን ይጀምራል፡፡ ከዚያም እነዚያን ያመኑትንና መልካም የሠሩትን በትክክል ይመነዳ ዘንድ ይመልሰዋል፡፡ እነዚያ የካዱትም ይክዱት በነበሩት ነገር ለነርሱ ከፈላ ውሃ የኾነ መጠጥና አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 10|5|እርሱ ያ ፀሐይን አንጻባራቂ ጨረቃንም አብሪ ያደረገ ነው፡፡ የዓመታትን ቁጥርና ሒሳብን ታውቁ ዘንድም ለእርሱ መስፈሪያዎችን የለካ ነው፡፡ አላህ ይህንን በእውነት እንጂ (በከንቱ) አልፈጠረውም፡፡ ለሚያውቁ ሕዝቦች አንቀጾችን ያብራራል፡፡ 10|6|ሌሊትና ቀን በመተካካታቸው አላህም በሰማያትና በምድር ውስጥ በፈጠረው ሁሉ ለሚጠነቀቁ ሕዝቦች ምልክቶች አሉ፡፡ 10|7|እነዚያ መገናኘታችንን የማይፈሩ ቅርቢቱንም ሕይወት የወደዱ በእሷም የረኩ እነዚያም እነሱ ከአንቀጾቻችን ዘንጊዎች የኾኑ፡፡ 10|8|እነዚያ ይሠሩት በነበሩት ምክንያት መኖሪያቸው በእሳት ውስጥ ነው፡፡ 10|9|እነዚያ ያመኑና መልካም ሥራዎችን የሠሩ ጌታቸው በእምነታቸው ምክንያት (የገነትን መንገድ) ይመራቸዋል፡፡ ከሥራቸው ወንዞች ይፈስሳሉ፡፡ በመጠቀሚያ ገነቶች ውስጥ ይኖራሉ፡፡ 10|10|በእርሷም ውስጥ ጸሎታቸው ጌታችን ሆይ! ጥራት ይገባህ (ማለት) ነው፡፡ በእርሷ ውስጥ መከባበሪያቸውም ሰላም መባባል ነው፤ የመጨረሻ ጸሎታቸውም ምስጋና ለዓለማት ጌታ ይሁን (ማለት) ነው፡፡ 10|11|አላህ ለሰዎች ደግን ነገር ለማግኘት እንደ መቻኮላቸው (አጥፋን ሲሉት) ክፉን ነገር ቢያስቸኩል ኖሮ ጊዜያቸው ወደነሱ በተፈጸመ ነበር፡፡ እነዚያንም መገናኘታችንን የማይፈሩትን በጥመታቸው ውስጥ የሚዋልሉ ሲኾኑ እንተዋቸዋለን፡፡ 10|12|ሰውንም ጉዳት ባገኘው ጊዜ በጎኑ ላይ ተጋድሞ ወይም ተቀምጦ ወይም ቆሞ ይለምነናል፡፡ ጉዳቱንም ከእሱ ላይ በገለጥንለት ጊዜ ወደ አገኘው ጉዳት እንዳልጠራን ሆኖ ያልፋል፡፡ እንደዚሁ ለድንበር አላፊዎች ይሠሩት የነበሩት ሥራ ተሸለመላቸው፡፡ 10|13|ከእናንተ በፊት የነበሩትንም የክፍለ ዘመናት ሰዎች መልክተኞቻቸው በማስረጃዎች የመጧቸው ሲኾኑ በበደሉና የማያምኑም በኾኑ ጊዜ በእርግጥ አጠፋናቸው፡፡ እንደዚሁ ተንኮለኞችን ሕዝቦች እንቀጣለን፡፡ 10|14|ከዚያም እንዴት እንደምትሠሩ ልንመለከት ከእነሱ በኋላ በምድር ላይ ምትኮች አደረግናችሁ፡፡ 10|15|አንቀጾቻችንም ግልጽ ኾነው በእነርሱ ላይ በተነበቡላቸው ጊዜ እነዚያ መገናኘታችንን የማይፈሩት ከዚህ ሌላ የሆነን ቁርኣን አምጣልን ወይም ለውጠው ይላሉ፡፡ እኔ ከራሴ በኩል ልለውጠው አይገባኝም፡፡ ወደእኔ የሚወርደውን እንጂ አልከተልም፡፡ እኔ ከጌታዬ ባምጽ የታላቁን ቀን ቅጣት እፈራለሁ በላቸው፡፡ 10|16|አላህ በሻ ኖሮ በእናንተ ላይ ባለነበብኩትም (አላህ) እርሱን ባላሳወቃችሁም ነበር፡፡ በእናንተም ውስጥ ከእርሱ በፊት (ምንም ሳልል) ብዙን ዕድሜ በእርግጥ ኖሬአለሁ፤ አታውቁምን 10|17|በአላህም ላይ እብለትን ከቀጣጠፈ ወይም በአንቀጾቹ ከአስተባበለ ይበልጥ በዳይ ማን ነው እነሆ አመጸኞች አይድኑም፡፡ 10|18|ከአላህም ሌላ የማይጎዳቸውን የማይጠቅማቸውንም ይግገዛሉ፡፡ «እነዚህም አላህ ዘንድ አማላጆቻችን ናቸው» ይላሉ፡፡ «አላህን በሰማያትና በምድር ውስጥ የማያውቀው ነገር ኖሮ ትነግሩታላችሁን» በላቸው፡፡ ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ፤ ላቀም፡፡ 10|19|ሰዎችም አንድ ሕዝብ እንጂ ሌላ አልነበሩም፡፡ ተለያዩም፡፡ ከጌታህ ያለፈች ቃልም ባልነበረች ኖሮ በእርሱ በሚለያዩበት ነገር በመካከላቸው በእርግጥ (በቶሎ) በተፈረደ ነበር፡፡ 10|20|በእርሱ ላይም ከጌታው የሆነች ተዓምር ለምን አትወረድለትም ይላሉ፡፡ «ሩቅ ነገርም ሁሉ የአላህ ብቻ ነው፡፡ ተጠባበቁም፤ እኔ ከናንተ ጋር ከሚጠባበቁት ነኝና» በላቸው፡፡ 10|21|ሰዎችንም ካገኛቸው ጉዳት በኋላ እዝነትን (ዝናብና ምቾትን) ባቀመስናቸው ጊዜ ወዲያውኑ ለእነሱ በተዓምራቶቻችን (በማላገጥ) ተንኮል ይኖራቸዋል፡፡ አላህ ቅጣተ ፈጣን ነው፡፡ «መልክተኞቻችን የምትመክሩትን ነገር በእርግጥ ይጽፋሉ» በላቸው፡፡ 10|22|እርሱ (አላህ) ያ በየብስና በባሕር የሚያስኬዳችሁ ነው፡፡ በመርከቦችም ውስጥ በሆናችሁና በእነርሱም በመልካም ነፋስ በርሷ የተደሰቱ ኾነው (መርከቦቹ) በተንሻለሉ ጊዜ ኀይለኛ ነፋስ ትመጣባታለች፡፡ ከየስፍራውም ማዕበል ይመጣባቸዋል፡፡ እነሱም (ለጥፋት) የተከበቡ መሆናቸውን ያረጋግጣሉ፡፡ (ያን ጊዜ) አላህን ከዚህች (ጭንቀት) ብታድነን በእርግጥ ከአመስጋኞቹ እንሆናለን ሲሉ ሃይማኖትን ለርሱ ብቻ ያጠሩ ሆነው ይለምኑታል፡፡ 10|23|በአዳናቸውም ጊዜ እነሱ ወዲያውኑ ያለ አግባብ በምድር ላይ ወሰን ያልፋሉ፡፡ እናንተ ሰዎች ሆይ! ወሰን ማለፋችሁ (ጥፋቱ) በነፍሶቻችሁ ላይ ብቻ ነው፡፡ (እርሱም) የቅርቢቱ ሕይወት መጠቀሚያ ነው፡፡ ከዚያም መመለሻችሁ ወደኛ ነው፡፡ ትሠሩት የነበራችሁትንም ሁሉ እንነግራችኋለን፡፡ 10|24|የቅርቢቱ ሕይወት ምሳሌ ከሰማይ እንዳወረድነው ውሃ፣ በእርሱም ሰውና እንስሳዎች ከሚበሉት የምድር በቃይ ተቀላቅሎበት (እንደ ፋፋ) ምድርም ውበትዋን በያዘችና ባጌጠች ጊዜ ባለቤቶችዋም በርሷ ላይ እነርሱ ቻዮች መኾናቸውን ባሰቡ ጊዜ ትእዛዛችን ሌሊት ወይም ቀን መጥቶባት ትላንት እንዳልነበረች የታጨደች እንዳደረግናት ብጤ ነው፡፡ እንደዚሁም ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች አንቀጾችን እናብራራለን፡፡ 10|25|አላህም ወደ ሰላም አገር ይጠራል፡፡ የሚሻውንም ሰው ወደ ቀጥተኛው መንገድ ይመራል፡፡ 10|26|ለእነዚያ መልካም ለሠሩት መልካም ነገርና ጭማሪም አላቸው፡፡ ፊቶቻቸውንም ጥቁረትና ውርደት አይሸፍናቸውም፡፡ እነዚያ የገነት ሰዎች ናቸው፡፡ እነርሱ በውስጧ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 10|27|ለእነዚያም ኃጢአቶችን ለሠሩት የኃጢኣቲቱ ቅጣት በብጤዋ አለቻቸው፡፡ ውርደትም ትሸፍናቸዋለች፡፡ ለእነሱ ከአላህ (ቅጣት) ጠባቂ የላቸውም፡፡ ፊቶቻቸው ከጨለመ ሌሊት ቁራጮች እንደ ተሸፈኑ ይኾናሉ፡፡ እነዚያ የእሳት ሰዎች ናቸው፡፡ እነርሱ በውስጧ ዘለዓለም ነዋሪዎች ናቸው፡፡ 10|28|ሁሉንም የምንሰበስባቸውን ከዚያም ለእነዚያ ለአጋሩት እናንተም ተጋሪዎችሁም ስፍራችሁን ያዙ የምንልበትን ተጋሪዎቻቸውም እኛን ትገዙ አልነበራችሁም የሚሉዋቸው ሲኾኑ በመካከላቸው የምንለይበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 10|29|«(ጣዖታቶቹ ለእኛ) ከመገዛታችሁ በእርግጥ ዘንጊዎች ለመኾናችንም በእኛና በእናንተ መካከል የአላህ መስካሪነት በቃ» (ይሏቸዋል)፡፡ 10|30|በዚያ ቀን ነፍስ ሁሉ ያሳለፈችውን ሥራ ታውቃለች፡፡ (አጋሪዎች) ወደ አላህም እውነተኛ ወደ ሆነው ጌታቸው ይመለሳሉ፡፡ ከእነሱም ይቀጣጥፉት የነበሩት ነገር ይጠፋቸዋል፡፡ 10|31|«ከሰማይና ከምድር ሲሳይን የሚሰጣችሁ ማን ነው መስሚያዎችንና ማያዎችንስ የፈጠረ ማን ነው ከሙትም ሕያውን የሚያወጣ ከሕያውም ሙትን የሚያወጣስ ማን ነው ነገሩን ሁሉ የሚያስተናብርስ ማን ነው» በላቸው፡፡ «በእርግጥም አላህ ነው» ይሉሃል፡፡ «ታዲያ (ለምን ታጋራላችሁ) አትፈሩትምን» በላቸው፡፡ 10|32|እርሱ እውነተኛ ጌታችሁ አላህ ነው፡፡ ከእውነትም በኋላ ጥመት እንጂ ሌላ ምን አለ (ከውነት) እንዴት ትዞራላችሁ 10|33|እንደዚሁ የጌታህ ቃል በእነዚያ ባመጹት ላይ እነርሱ የማያምኑ መሆናቸው ተረጋገጠች፡፡ 10|34|«ከምታጋሩዋቸው (ጣዖታት) ውስጥ መፍጠርን የሚጀምር ከዚም የሚመልሰው አለን» በላቸው፡፡ «አላህ መፍጠርን ይጀምራል፤ ከዚያም ይመልሰዋል፡፡ ታዲያ (ከእምነት) እንዴት ትዞራላችሁ» በላቸው፡፡ 10|35|«ከምታጋሩዋቸው፤ ወደ እውነት የሚመራ አለን» በላቸው፡፡ «አላህ ወደ እውነቱ ይመራል፡፡ ወደ እውነት የሚመራው ሊከተሉት የተገባው ነውን ወይስ ካልተመራ በስተቀር የማይመራው ለእናንተም ምን (አስረጅ) አላችሁ እንዴት (በውሸት) ትፈርዳላችሁ» በላቸው፡፡ 10|36|አብዛኞቻቸውም ጥርጣሬን እንጂ አይከተሉም፡፡ ጥርጣሬ ከእውነት ምንም አያብቃቃም፡፡ አላህ የሚሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 10|37|ይህም ቁርኣን ከአላህ ሌላ (ከሆነ ፍጡር) የተቀጠፈ ሊሆን አይገባውም፡፡ ግን ያንን ከእርሱ በፊት ያለውን (መጽሐፍ) የሚያረጋግጥና በመጽሐፉ ውስጥ ያለውን የሚዘረዝር በእርሱ ጥርጣሬ የሌለበት ሲሆን ከዓለማት ጌታ (የተወረደ) ነው፡፡ 10|38|በእውነትም «(ሙሐመድ) ቀጣጠፈው» ይላሉን «ይህ ከሆነ መሰሉን (አንዲት) ሱራ አምጡ፡፡ ከአላህም ሌላ የቻላችሁትን ሁሉ (ረዳት) ጥሩ፡፡ እውነተኞች እንደሆናችሁ (ተጋግዛችሁ አምጡ)» በላቸው፡፡ 10|39|ይልቁንም (ከቁርኣን) እውቀቱን ባላደረሱት ፍቹም ገና ባልመጣቸው ነገር አስተባበሉ፡፡ እንደዚሁ እነዚያ ከእነሱ በፊት የነበሩት አስተባብለዋል፡፡ የበዳዮችም መጨረሻ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከት፡፡ 10|40|ከእነርሱም ውስጥ (ወደፊት) በርሱ የሚያምኑ አልሉ፡፡ ከእነርሱም በእርሱ የማያምኑ አልሉ፡፡ ጌታህም አጥፊዎቹን በጣም ዐዋቂ ነው፡፡ 10|41|«ቢያስተባብሉህም ለእኔ ሥራዬ አለኝ፡፡ ለእናንተም ሠራችሁ አላችሁ፡፡ እናንተ ከምሠራው ነገር ንጹሕ ናችሁ፡፡ እኔም ከምትሠሩት ነገር ንጹሕ ነኝ» በላቸው፡፡ 10|42|ከእነሱም ወደ አንተ የሚያዳምጡ (እና የማያምኑ) አልሉ፡፡ አንተ ደንቆሮዎችን የማያውቁ ቢኾኑም ታሰማለህን 10|43|ከእነሱም ወደ አንተ የሚመለከቱ አልሉ፡፡ አንተ (ልበ) ዕውራንን የማያዩ ቢኾኑም ትመራለህን 10|44|አላህ ሰዎችን ምንም አይበድልም፡፡ ግን ሰዎች ነፍሶቻቸውን ይበድላሉ፡፡ 10|45|(ከሓዲዎችን) ከቀን አንዲትን ሰዓት እንጂ እንዳልቆዩ መስለው በመካከላቸው የሚተዋወቁ ሲሆኑ በምንሰበስባቸው ቀን (አስታውስ)፡፡ እነዚያ በአላህ መገናኘት ያስተባበሉት በእርግጥ ከሰሩ የተመሩም አልነበሩም፡፡ 10|46|የዚያንም የምናስፈራራቸውን ከፊሉን (በሕይወትህ) ብናሳይህ (መልካም ነው)፡፡ ወይም (ሳናሳይህ) ብንገድልህ መመለሻቸው ወደ እኛ ነው፡፡ ከዚያም አላህ በሚሠሩት ስራ ላይ ዐዋቂ ነው፡፡ 10|47|ለሕዝቦችም ሁሉ መልክተኛ አላቸው፡፡ መልክተኛውም በመጣ ጊዜ (ሲያስተባብሉ) በመካከላቸው በትክክል ይፈረዳል፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 10|48|«እውነተኞችም ከሆናችሁ ይህ (የቅጣቱ) ቀጠሮ መቼ ነው» ይላሉ፡፡ 10|49|«ለራሴ ጉዳትንም ጥቅምንም አላህ ከሻው በስተቀር አልችልም፡፡ ለሕዝቦች ሁሉ የተወሰነ ጊዜ አልላቸው፡፡ ጊዜያቸው በመጣ ወቅት አንዲትን ሰዓት አይቆዩም፤ አይቀደሙምም» በላቸው፡፡ 10|50|«ቅጣቱ በሌሊት ወይም በቀን ቢመጣባችሁ፤ አጋሪዎቹ ከርሱ የሚቻኮሉበት ነገር ምንድን ነው ንገሩኝ» በላቸው፡፡ 10|51|«ከዚያም (ቅጣቱ) በወደቀ ጊዜ በእርሱ አመናችሁበትን በእርግጥ በእርሱ የምትቻኮሉ የነበራችሁ ስትሆኑ አሁን» (ይባላሉ)፡፡ 10|52|ከዚያም ለእነዚያ ለበደሉት፡- «ዘውታሪን ቅጣት ቅመሱ ትሠሩት የነበረችሁትን ዋጋ እንጂ አትመነዱም» ይባላሉ፡፡ 10|53|እርሱም «እውነት ነውን» (ሲሉ) ይጠይቁሃል፡፡ «አዎን፤ በጌታዬ እምላለሁ፤ እርሱ እውነት ነው፡፡ እናንተም አምላጮች አይደላችሁም፤» በላቸው፡፡ 10|54|ለበደለችም ነፍስ ሁሉ በምድር ላይ ያለው ሁሉ ቢኖራት ኖሮ በእርግጥ በተበዠችበት ነበር፡፡ ቅጣቱንም ባዩ ጊዜ ጸጸትን ይገልጻሉ፡፡ በመካከላቸውም በትክክል ይፈረዳል፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 10|55|ንቁ! በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ ንቁ! የአላህ ተስፋ ቃል እርግጥ ነው፡፡ ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 10|56|እርሱ ሕያው ያደርጋል፤ ይገድላልም ወደ እርሱም ትመለሳላችሁ፡፡ 10|57|እናንተ ሰዎች ሆይ! ከጌታችሁ ግሳጼ በደረቶች ውስጥም ላለው (የመጠራጠር በሽታ) መድኃኒት ለምእምናንም ብርሃንና እዝነት በእርግጥ መጣችላችሁ፡፡ 10|58|«በአላህ ችሮታና በእዝነቱ (ይደሰቱ)፡፡ በዚህም ምክንያት ይደሰቱ፡፡ እርሱ ከሚሰበስቡት ሀብት በላጭ ነው» በላቸው፡፡ 10|59|«አላህ ከሲሳይ ለእናንተ ያወረደውን ከእርሱም እርምና የተፈቀደ ያደረጋችሁትን አያችሁን» በላቸው፡፡ «አላህ (ይህንን) ለእናንተ ፈቀደላችሁን ወይስ በአላህ ላይ ትቀጣጥፋላችሁ» በላቸው፡፡ 10|60|የእነዚያም በአላህ ላይ ውሸትን የሚቀጣጥፉ (ሰዎች) በትንሣኤ ቀን (በአላህ) ጥርጣሬያቸው ምንድን ነው (አይቀጡም ይመስላቸዋልን) አላህ በሰዎች ላይ (ቅጣትን ባለማቻኮል) የልግስና ባለቤት ነው፡፡ ግን አብዛኛዎቹ አያመሰግኑም፡፡ 10|61|(ሙሐመድ ሆይ!) በማንኛውም ነገር ላይ አትሆንም፣ ከርሱም ከቁርኣን አታነብም፣ ማንኛውንም ሥራ (አንተም ሰዎቹም) አትሠሩም በገባችሁበት ጊዜ በናንተ ላይ ተጠባባቂዎች ብንሆን እንጂ፡፡ በምድርም ሆነ በሰማይ የብናኝ ክብደት ያክል ከጌታህ (ዕውቀት) አይርቅም፡፡ ከዚያም ያነሰ የተለቀም የለም፤ በግልጹ መጽሐፍ ውስጥ የተጻፈ ቢሆን እንጂ፡፡ 10|62|ንቁ! የአላህ ወዳጆች በእነሱ ላይ ፍርሃት የለባቸውም፤ እነሱም አያዝኑም፡፡ 10|63|(እነሱም) እነዚያ ያመኑትና ይፈሩት የነበሩ ናቸው፡፡ 10|64|ለእነሱ በቅርቢቱ ሕይወትም በመጨረሻይቱም ብስራት አላቸው፤ የአላህ ቃላት መለወጥ የላትም፤ ይህ እርሱ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ 10|65|ንግግራቸውም አያሳዝንህ፡፡ ኀይል ሁሉ በሙሉ የአላህ ብቻ ነውና፡፡ እርሱ ሰሚው ዐዋቂው ነው፡፡ 10|66|ንቁ! በሰማያት ያሉትና በምድርም ያሉት ሁሉ በእርግጥ የአላህ ናቸው፤ እነዚያ ከአላህ ሌላ ተጋሪዎችን የሚጠሩ ምንን ይከተላሉ ጥርጣሬን እንጂ ሌላ አይከተሉም፡፡ እነርሱም የሚዋሹ እንጂ አይደሉም፡፡ 10|67|እርሱ ያ ሌሊትን በውስጡ ልታርፉበት (ጨለማ)፤ ቀንንም (ልትሠሩበት) ብርሃን ያደረገላችሁ ነው፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚሰሙ ሕዝቦች በእርግጥ ታምራቶች አሉ፡፡ 10|68|«አላህ ልጅን ያዘ (ወለደ)» አሉ፡፡ (ከሚሉት) ጥራት ተገባው፡፡ እርሱ ተብቃቂ ነው፡፡ በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የርሱ ነው፡፡ እናንተ ዘንድ በዚህ (በምትሉት) ምንም አስረጅ የላችሁም፡፡ በአላህ ላይ የማታውቁትን ትናገራላችሁን 10|69|«እነዚያ በአላህ ላይ ውሸትን የሚቀጣጥፉ ፈጽሞ አይድኑም፤» በላቸው፡፡ 10|70|(እነሱ) በቅርቢቱ ዓለም መጠቀም አላቸው፡፡ ከዚያም መመለሻቸው ወደእኛ ነው፡፡ ከዚያም ይክዱ በነበሩት ምክንያት ብርቱን ቅጣት እናቀምሳቸዋለን፡፡ 10|71|የኑሕንም ወሬ በእነሱ ላይ አንብብላቸው፡፡ ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «ሕዝቦቼ ሆይ! በእናንተ ውስጥ ብዙ ጊዜ መቆየቴ በአላህም ተዓምራት ማስታወሴ በእናንተ ላይ የከበደ ቢሆን፤ በአላህ ላይ ተጠግቻለሁ፡፡ ነገራችሁንም ከምታጋሩዋቸው (ጣዖታት) ጋር ሆናችሁ ቁረጡ፡፡ ከዚያም ነገራችሁ በእናንተ ላይ ድብቅ አይሁን (ግለጹት)፡፡ ከዚያም (የሻችሁትን) ወደእኔ አድርሱ፡፡ ጊዜም አትስጡኝ (ከምንም አልቆጥራችሁም)፡፡» 10|72|«ብትሸሹም (አትጎዱኝም)፡፡ ከምንዳ ምንንም አልለምናችሁምና፡፡ ምንዳዬ በአላህ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ ከሙስሊሞች እንድሆንም ታዝዣለሁ፡፡» 10|73|አስተባበሉትም፡፡ እርሱንና ከእርሱ ጋር የነበሩትንም በታንኳይቱ ውስጥ አዳንናቸው፡፡ (ለጠፉት) ምትኮችም አደረግናቸው፡፡ እነዚያንም በአንቀጾቻችን ያስተባበሉትን አሰጠምን፡፡ የተስፈራሩትም ሕዝቦች መጨረሻ እንዴት እንደነበረ ተመልከት፡፡ 10|74|ከዚያም ከእርሱ በኋላ መልክተኞችን ወደየሕዝቦቻቸው ላክን፡፡ በግልጽ ማስረጃዎችም መጧቸው፡፡ (ከመላካቸው) በፊት በእርሱ ባስተባበሉበትም ነገር፤ የሚያምኑ አልሆኑም፡፡ እንደዚሁ በወሰን አላፊዎች ልቦች ላይ እናትማለን፡፡ 10|75|ከዚያም ከእነሱ ኋላ ሙሳንና ሃሩንን ወደ ፈርዖንና ወደ መማክርቱ በተዓምራታችን ላክን፡፡ ኮሩም ትዕቢተኞች ሕዝቦችም ነበሩ፡፡ 10|76|ከእኛም ዘንድ እውነቱ በመጣላቸው ጊዜ «ይህ በእርግጥ ግልጽ ድግምት ነው» አሉ፡፡ 10|77|ሙሳ አለ፡- «እውነቱን በመጣላችሁ ጊዜ ድግምተኞች የማይድኑ ሲኾኑ (እርሱ ድግምት ነው) ትላላችሁን ይህ ድግምት ነውን» 10|78|(እነርሱም) አሉ፡- «አባቶቻችንን በእርሱ ላይ ካገኘንበት ሃይማኖት ልታዞረን ለእናንተም በምድር ውስጥ ኩራት (ሹመት) ልትኖራችሁ መጣህብን እኛም ለእናንተ አማኞች አይደለንም፡፡» 10|79|ፈርዖንም፡- «ዐዋቂ ድግምተኛን ሁሉ አምጡልኝ» አለ፡፡ 10|80|ድግምተኞቹም በመጡ ጊዜ ሙሳ ለእነርሱ፡- «እናንተ የምትጥሉትን ነገር ጣሉ» አላቸው፡፡ 10|81|(ገመዶቻቸውን) በጣሉም ጊዜ ሙሳ አለ፡- «ያ በርሱ የመጣችሁበት ነገር ድግምት ነው፡፡ አላህ በእርግጥ ያፈርሰዋል፡፡ አላህ የአጥፊዎችን ሥራ ፈጽሞ አያበጅምና፡፡» 10|82|አላህም ከሓዲዎች ቢጠሉም እውነትን በቃላቱ ያረጋግጣል፡፡ 10|83|ለሙሳም ከፈርዖንና ከሹማምንቶቻቸው ማሰቃየትን ከመፍራት ጋር ከወገኖቹ የኾኑ ጥቂቶች ትውልዶች እንጂ አላመኑለትም፡፡ ፈርዖንም በምድር ላይ በእርግጥ የኮራ ነበር፡፡ እርሱም በእርግጥ ወሰን ካለፉት ነበር፡፡ 10|84|ሙሳም አለ፡- «ሕዝቦቼ ሆይ! በአላህ አምናችሁ እንደ ሆነ በርሱ ላይ ተጠጉ፡፡ ታዛዦች እንደ ሆናችሁ (በአላህ ላይ ትመካላችሁ)፡፡» 10|85|አሉም፡- «በአላህ ላይ ተጠጋን፡፡ ጌታችን ሆይ! ለበደለኞች ሕዝቦች መፈተኛ አታድርገን፡፡» 10|86|በእዝነትህም ከከሓዲዎች ሕዝቦች አድነን፡፡ 10|87|ወደ ሙሳና ወደ ወንድሙ፡- «ለሕዝቦቻችሁ በምስር ቤቶችን ሥሩ፡፡ ቤቶቻችሁንም መስገጃ አድርጉ፡፡ ሶላትንም በደንቡ ስገዱ፡፡ (ለሙሳ) ምእምናኖቹንም አብስር» ስንል ላክን፡፡ 10|88|ሙሳም አለ፡- «ጌታችን ሆይ! አንተ ለፈርዖንና ለሹሞቹ በቅርቢቱ ሕይወት ጌጥን ብዙ ገንዘቦችንም በእርግጥ ሰጠህ፡፡ ጌታችን ሆይ! ከመንገድህ ያሳስቱ ዘንድ (ሰጠሃቸው)፡፡ ጌታችን ሆይ! ገንዘቦቻቸውን አጥፋ፡፡ በልቦቻቸውም ላይ አትም፡፡ አሳማሚን ቅጣት እስከሚያዩ አያምኑምና፡፡» 10|89|(አላህም) «ጸሎታችሁ በእርግጥ ተሰምታለች፡፡ ቀጥም በሉ፡፡ የእነዚያንም የማያውቁትን ሰዎች መንገድ አትከተሉ» አላቸው፡፡ 10|90|የእስራኤልንም ልጆች ባሕሩን አሳለፍናቸው፡፡ ፈርዖንና ሰራዊቱም ወሰን ለማለፍና ለመበደል ተከተሏቸው፡፡ መስጠምም ባገኘው ጊዜ፡- «አመንኩ፡፡ እነሆ ከዚያ የእስራኤል ልጆች በርሱ ከአመኑበት በስተቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ እኔም ከታዛዦቹ ነኝ» አለ፡፡ 10|91|ከአሁን በፊት በእርግጥ ያመጽክ ከአጥፊዎችም የነበርክ ስትሆን አሁን (አመንኩ ትላለህ) 10|92|ዛሬማ ከኋላህ ላሉት ተዓምር ትሆን ዘንድ በድን ሆነህ (ከባሕሩ) እናወጣሃለን (ተባለ)፡፡ ከሰዎችም ብዙዎቹ ከተዓምራታችን በእርግጥ ዘንጊዎች ናቸው፡፡ 10|93|የእስራኤልንም ልጆች ምስጉንን ስፍራ በእርግጥ አሰፈርናቸው፡፡ ከመልካም ሲሳዮችም ሰጠናቸው፡፡ ዕውቀትም (ቁርኣን) እስከመጣቸው ድረስ አልተለያዩም፡፡ ጌታህ በርሱ ይለያዩበት በነበሩት ነገር በትንሣኤ ቀን በመካከላቸው ይፈርዳል፡፡ 10|94|ወደ አንተም ካወረድነው በመጠራጠር ውስጥ ብትሆን እነዚያን ከአንተ በፊት መጽሐፉን የሚያነቡትን ጠይቅ፡፡ እውነቱ ከጌታህ ዘንድ በእርግጥ መጥቶልሃል፡፡ ከተጠራጣሪዎቹም አትሁን፡፡ 10|95|ከእነዚያም የአላህን አንቀጾች ከአስተባበሉት አትሁን፡፡ ከከሳሪዎቹ ትሆናለህና፡፡ 10|96|እነዚያ በእነርሱ ላይ የጌታህ ቃል የተረጋገጠባቸው አያምኑም፡፡ 10|97|ተዓምር ሁሉ ብትመጣላቸውም አሳማሚን ቅጣት እስከሚያዩ ድረስ (አያምኑም)፡፡ 10|98|(ከዩኑስ በፊት ካለፉት ከተሞች) ያመነችና እምነትዋ የጠቀማት ከተማ ለምን አልኖረችም ግን የዩኑስ ሕዝቦች ባመኑ ጊዜ በቅርቢቱ ሕይወት የውርደትን ቅጣት ከእነሱ ላይ አነሳንላቸው፡፡ እስከ ጊዜም ድረስ አጣቀምናቸው፡፡ 10|99|ጌታህም በሻ ኖሮ በምድር ያሉት ሰዎች ሁሉም የተሰበሰቡ ሆነው ባመኑ ነበር፡፡ ታዲያ አንተ ሰዎችን አማኞች እንዲኾኑ ታስገድዳለህን 10|100|ለማንኛዋም ነፍስ በአላህ ፈቃድ ቢሆን እንጂ ልታምን (ችሎታ) የላትም፡፡ (አላህ ለከፊሎቹ እምነትን ይሻል)፡፡ በእነዚያም በማያውቁት ላይ ርክሰትን ያደርጋል፡፡ 10|101|«በሰማያትና በምድር ያለውን (ተዓምር) ተመልከቱ» በላቸው፡፡ ተዓምራቶችና አስፈራሪዎችም ለማያምኑ ሕዝቦች አይጠቅሙም፡፡ 10|102|የእነዚያን ከእነሱ በፊት ያለፉትን ሕዝቦች ቀኖች ብጤ እንጂ ሌላን ይጠባበቃሉን «ተጠባበቁ፤ እኔ ከናንተ ጋር ከሚጠባበቁት ነኝ» በላቸው፡፡ 10|103|ከዚያም መልክተኞቻችንን እነዚያንም ያመኑትን እናድናለን፡፡ እንደዚሁም ምእምናንን (ከጭንቅ ሁሉ) እናድናለን፡፡ (ይህ) በእኛ ላይ ተረጋገጠ፡፡ 10|104|«እናንተ ሰዎች ሆይ! ከእኔ ሃይማኖት በመጠራጠር ውስጥ ብትሆኑ እነዚያን ከአላህ ሌላ የምትገዟቸውን አልገዛም፡፡ ግን ያንን የሚገድላችሁን አላህን እገዛለሁ፡፡ ከምእምናን እንድሆንም ታዝዣለሁ» በላቸው፡፡ 10|105|ፊትህንም (ወደ ቀጥታ) ያዘነበልክ ስትሆን ለሃይማኖት ቀጥ አድርግ፡፡ ከአጋሪዎቹም አትሁን፡፡ 10|106|«ከአላህም በቀር የማይጠቅምንና የማይጎዳን አትገዛ፡፡ ብትሠራም አንተ ያንጊዜ ከበደለኞቹ ትሆናለህ» (ተብያለሁ በላቸው)፡፡ 10|107|አላህም ጉዳትን ቢያደርስብህ ከእርሱ ሌላ ለእርሱ ገላጭ የለውም፡፡ በጎንም ነገር ቢሻልህ ለችሮታው መላሽ የለም፡፡ ከባሮቹ የሚሻውን በእርሱ ይለይበታል፡፡ እርሱም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 10|108|«እናንተ ሰዎች ሆይ! እውነቱ ከጌታችሁ በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ (በእርሱ) የተመራም ሰው የሚመራው ለራሱ ነው፡፡ የተሳሳተም ሰው የሚሳሳተው (ጉዳቱ) በራሱ ላይ ነው፡፡ እኔም በእናንተ ላይ ተጠባበቂ አይደለሁም» በላቸው፡፡ 10|109|ወዳንተም የሚወረደውን ነገር ተከተል፡፡ አላህም (በነሱ ላይ) እስከሚፈርድ ድረስ ታገስ፡፡ እርሱም ከፈራጆቹ ሁሉ በላጭ ነው፡፡ 11|1|አ.ለ.ረ (አሊፍ ላም ራ፤ ይህ ቁርኣን) አንቀጾቹ በጥንካሬ የተሰካኩ ከዚያም የተዘረዘሩ የሆነ መጽሐፍ ነው፡፡ ጥበበኛ ውስጠ ዐዋቂ ከሆነው ዘንድ (የተወረደ) ነው፡፡ 11|2|(እንዲህ በላቸው)፡- «አላህን እንጂ ሌላን አትገዙ፡፡ እኔ ለእናንተ ከርሱ (የተላክሁ) አስፈራሪና አብሳሪ ነኝ፡፡» 11|3|ጌታችሁንም ምሕረትን ለምኑት፡፡ ከዚያም ወደእርሱ ተመለሱ፡፡ እስከተወሰነ ጊዜ ድረስ መልካምን መጥቀም ይጠቅማችኋልና፡፡ የትሩፋትንም ባለቤት ሁሉ ችሮታውን (ምንዳውን) ይሰጠዋል፡፡ ብትሸሹም እኔ በእናንተ ላይ የታላቁን ቀን ቅጣት እፈራላችኋለሁ፡፡ 11|4|መመለሻችሁ ወደ አላህ ብቻ ነው፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 11|5|ንቁ! እነሱ ከእርሱ (ከአላህ) ይደበቁ ዘንድ ደረቶቻቸውን ያጥፋሉ፡፡ ንቁ! ልብሶቻቸውን በሚከናነቡ ጊዜ የሚደብቁትን የሚገልጹትንም ሁሉ ያውቃል፡፡ እርሱ በደረቶች ውስጥ ያለውን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 11|6|በምድርም ላይ ምንም ተንቀሳቃሽ የለችም ምግቧ በአላህ ላይ ያለ ቢኾን እንጂ፡፡ ማረፊያዋንም መርጊያዋንም ያውቃል፡፡ ሁሉም ግልጽ በሆነው መጽሐፍ ውስጥ ነው፡፡ 11|7|እርሱም ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ ነው፡፡ ዐርሹም በውሃ ላይ ነበር፡፡ የትኛችሁ ሥራው ያማረ መሆኑን ይፈትናችሁ ዘንድ (ፈጠራቸው)፡፡ «እናንተ ከሞት በኋላ በእርግጥ ተቀስቃሾች ናችሁ» ብትልም እነዚያ የካዱት ይህ ግልጽ ድግምት እንጂ ሌላ አይደለም ይላሉ፡፡ 11|8|ቅጣቱንም ወደ ተቆጠሩ (ጥቂት) ጊዜያቶች ከእነርሱ ብናቆይላቸው «(ከመውረድ) የሚከለክለው ምንድን ነው» ይላሉ፡፡ ንቁ! በሚመጣባቸው ቀን ከእነሱ ላይ ተመላሽ አይደለም፡፡ በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩትም (ቅጣት) በእነርሱ ላይ ይወርድባቸዋል፡፡ 11|9|ሰውንም ከእኛ ችሮታን ብናቀምሰው ከዚያም ከርሱ ብንወስዳት እርሱ በእርግጥ ተስፋ ቆራጭ ክህደተ ብርቱ ነው፡፡ 11|10|ካገኘችውም ችግር በኋላ ጸጋዎችን ብናቀምሰው «ችግሮች ከኔ ላይ በእርግጥ ተወገዱ» ይላል (አያመሰግንም)፡፡ እርሱ ተደሳች ጉረኛ ነውና፡፡ 11|11|ግን እነዚያ የታገሱ መልካም ሥራዎችንም የሠሩ እነዚያ ለእነሱ ምሕረትና ታላቅ ምንዳ አልላቸው፡፡ 11|12|በእርሱ ላይ የገንዘብ ድልብ ለምን አልተወረደም ወይም ከርሱ ጋር መልአክ ለምን አልመጣም ማለታቸውንም በመፍራት ወደ አንተ ከሚወርደው ከፊሉን ልትተው በእርሱም ልብህ ጠባብ ሊኾን ይፈራልሃል፡፡ አንተ አስፈራሪ ብቻ ነህ፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ተጠባባቂ ነው፡፡ 11|13|ይልቁንም «(ቁርኣንን) ቀጣጠፈው» ይላሉን፡- «እውነተኞች እንደሆናችሁ ብጤው የሆኑን ዐስር የተቀጣጠፉ ሱራዎች አምጡ፡፡ ከአላህም ሌላ የቻላችሁትን (ረዳት) ጥሩ» በላቸው፡፡ 11|14|ለእናንተም (ጥሪውን) ባይቀበሏችሁ የተወረደው በአላህ እውቀት ብቻ መሆኑንና ከእርሱ ሌላ አምላክ አለመኖሩን ዕወቁ፡፡ ታዲያ እናንተ የምትሰልሙ ናችሁን (ስለሙ በላቸው)፡፡ 11|15|ቅርቢቱን ሕይወትና ጌጧን የሚሹ የሆኑትን ሰዎች ሥራዎቻቸውን (ምንዳዋን) በእርሷ ውስጥ ወደነሱ እንሞላላቸዋለን፡፡ እነሱም በርሷ ውስጥ ምንም አይጎድልባቸውም፤ 11|16|እነዚያ እነርሱ በመጨረሻይቱ ዓለም ለእነርሱ ከእሳት በቀር የሌላቸው ናቸው፡፡ የሠሩትም ሥራ በርሷ ውስጥ ተበላሸ፡፡ (በቅርቢቱ ዓለም) ይሠሩት የነበሩትም በጎ ሥራ ብልሹ ነው፡፡ 11|17|ከጌታው ከአስረጅ ጋር የኾነ ሰው፤ ከእርሱም (ከአላህ) የኾነ መስካሪ የሚከተለው፣ ከእርሱ በፊትም የሙሳ መጽሐፍ መሪና እዝነት ሲኾን (የመሰከረለት) የቅርቢቱን ሕይወት እንደሚሻው ሰው ነውን እነዚያ በእርሱ (በቁርኣን) ያምናሉ፡፡ ከአሕዛቦቹም በእርሱ የሚክድ ሰው እሳት መመለሻው ናት፡፡ ከእርሱም በመጠራጠር ውስጥ አትሁን፡፡ እርሱ ከጌታህ የሆነ እውነት ነው፡፡ ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያምኑም፡፡ 11|18|በአላህ ላይ እብለትን ከሚቀጣጥፍም ይበልጥ በዳይ ማነው እነዚያ በጌታቸው ላይ ይቀርባሉ፡፡ መስካሪዎቹም «እነዚህ በጌታቸው ላይ የዋሹት ናቸው» ይላሉ፡፡ ንቁ! የአላህ ርግማን በበዳዮች ላይ ይሁን፡፡ 11|19|(እነሱም) እነዚያ ከአላህ መንገድ የሚከለክሉ መጥመሟንም የሚፈልጓት ናቸው፡፡ እነሱም መጨረሻይቱን ዓለም እነሱ ከሓዲዎች ናቸው፡፤ 11|20|እነዚያ በምድር ውስጥ (ከአላህ) የሚያመልጡ አልነበሩም፡፡ ከአላህም ሌላ ለእነርሱ ረዳቶች አልነበሯቸውም፡፡ ለእነሱ ቅጣቱ ይደራረብላቸዋል፡፡ (እውነትን) መስማትን የሚችሉ አልነበሩም የሚያዩም አልነበሩም፡፡ 11|21|እነዚያ እነርሱ ነፍሶቻቸውን ያከሰሩ ከእነሱም ይቀጣጥፉት የነበሩት ነገር የጠፋቸው ናቸው፡፡ 11|22|እነርሱ በመጨረሻይቱ ዓለም በጣም ከሳሪዎቹ እነሱ መሆናቸው ጥርጥር የለውም፡፡ 11|23|እነዚያ ያመኑትና በጎ ሥራዎችን የሠሩት ወደ ጌታቸውም የተዋረዱት እነዚያ የገነት ሰዎች ናቸው፡፡ እነሱ በውስጧ ዘላለም ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 11|24|የሁለቱ ክፍሎች ምሳሌ እንደ ዕውርና እንደ ደንቆሮ እንደሚያይና እንደሚሰማም ብጤ ነው፡፡ በምሳሌ ይተካከላሉን አትገሰጹምን 11|25|ኑሕንም ወደ ሕዝቦቹ በእርግጥ ላክን፡፡ (አላቸውም)፡- «እኔ ለእናንተ ግልጽ አስፈራሪ (አስጠንቃቂ) ነኝ፡፡» 11|26|«አላህን እንጂ ሌላን አትገዙ፡፡ እኔ በእናንተ ላይ የአሳማሚን ቀን ቅጣት እፈራላችኋለሁና፡፡» 11|27|ከሕዝቦቹም እነዚያ የካዱት መሪዎቹ ብጤያችን ሰው ሆነህ እንጂ አናይህም፡፡ እነዚያም እነሱ ሐሳበ ጥሬዎች የሆኑት ወራዶቻችን እንጂ ሌላ ተከትሎህ አናይህም፡፡ ለእናንተም በእኛ ላይ ምንም ብልጫን አናይም፡፡ ከቶውንም ውሸታሞች መሆናችሁን እንጠረጥራችኋለን አሉ፡፡ 11|28|«ሕዝቦቼ ሆይ! ንገሩኝ ከጌታዬ በግልጽ ማስረጃ ላይ ብሆን ከእርሱም ዘንድ የሆነን ችሮታ (ነብይነት) ቢሰጠኝና በእናንተ ላይ ብትደበቅባችሁ እናንተ ለርቯ ጠይዎች ስትሆኑ እርቯን (በመቀበል) እናስገድዳችኋለን» አላቸው፡፡ 11|29|«ሕዝቦቼም ሆይ! በርሱ (በተላክሁበት ማድረስ) ላይ ገንዘብን አልጠይቃችሁም፡፡ ምንዳዬ በአላህ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ እኔም እነዚያን ያመኑትን አባራሪ አይደለሁም፡፡ እነርሱ ጌታቸውን የሚገናኙ ናቸውና፡፡ ግን እኔም የምትሳሳቱ ሕዝቦች ሆናችሁ አያችኋለሁ፡፡» 11|30|«ሕዝቦቼም ሆይ ባባርራቸው ከአላህ (ቅጣት) የሚያድነኝ ማን ነው አትገሰጹምን» 11|31|«ለእናንተም እኔ ዘንድ የአላህ ግምጃ ቤቶች አልሉ ሩቅንም ዐውቃለሁ አልላችሁም፡፡ እኔም መልአክ ነኝ አልላችሁም፡፡ ለእነዚያም ዓይኖቻችሁ ለሚያዋርዷቸው አላህ ደግ ነገርን (እምነትን) አይሰጣቸውም አልልም፡፡ አላህ በነፍሶቻቸው ውስጥ ያለውን ነገር አዋቂ ነው፡፡ እኔ ያን ጊዜ ከበደለኞች እሆናለሁና» (አላቸው)፡፡ 11|32|«ኑህ ሆይ! በእርግጥ ተከራከርከን፡፡ እኛን መከራከርህንም አበዛኸው፡፡ ከእውነተኞቹም እንደሆንክ የምታስፈራራብንን ቅጣት አምጣው» አሉ፡ 11|33|«እርሱን የሚያመጣባችሁ የሻ እንደ ሆነ አላህ ብቻ ነው፡፡ እናንተም የምታቅቱ አይደላችሁም» አላቸው፡፡ 11|34|«ለእናንተም ልመክራችሁ ብሻ አላህ ሊያጠማችሁ ሽቶ እንደ ኾነ ምክሬ አይጠቅማችሁም፡፡ እርሱ ጌታችሁ ነው፡፡ ወደ እርሱም ትመለሳላችሁ» (አላቸው)፡፡ 11|35|«ይልቁንም ቀጠፈው ይላሉን ብቀጥፈው ኃጢኣቴ (ቅጣቱ) በኔ ላይ ነው፡፡ እኔም ከምታጠፉት (ጥፋት) ንጹሕ ነኝ» በላቸው፡፡ 11|36|ወደ ኑሕም እነሆ «ከሕዝቦችህ በእርግጥ ካመኑት በስተቀር (ወደፊት) አያምኑም፡፡ ይሠሩትም በነበሩት (ክህደት) አትዘን ማለት ተወረደ፡፡» 11|37|(አላህም) «በጥበቃችንና በትእዛዛችንም ሆነህ መርከቢቱን ሥራ፡፡ በእነዚያም በበደሉት ሰዎች ነገር አታናግረኝ እነሱ በእርግጥ ሰማጮች ናቸውና» (አለው)፡፡ 11|38|ከወገኖቹም መሪዎቹ በእርሱ አጠገብ ባለፉ ቁጥር ከእርሱ እየተሳለቁ መርከቢቱን ይሠራል፡፡ «ከእኛ ብትሳለቁ እኛም እንደተሳለቃችሁብን ከናንተ እንሳለቅባችኋለን» አላቸው፡፡ 11|39|«የሚያዋርደው ቅጣት የሚመጣበትን በእርሱም ላይ ዘውታሪ ቅጣት የሚሰፍርበት ሰው (ማን እንደ ሆነ) ወደፊት ታውቃላችሁ» (አላቸው)፡፡ 11|40|ትእዛዛችንም በመጣና እቶኑም በገነፈለ ጊዜ «በእርሷ ውስጥ ከየዓይነቱ ሁሉ ሁለት ሁለት (ወንድና ሴት) ፤ ቤተሰቦችህንም ቃል ያለፈበት ብቻ ሲቀር ያመነንም ሰው ሁሉ ጫን» አልነው፡፡ ከእርሱም ጋር ጥቂቶች እንጂ አላመኑም፡፡ 11|41|«መሄዷም መቆሟም በአላህ ስም ነው እያላችሁም በውስጧ ተሳፈሩ፡፡ ጌታ መሓሪ አዛኝ ነውና» አላቸው፡፡ 11|42|እርሷም እንደ ተራራዎች በሆነ ማዕበል ውስጥ በእነርሱ (ይዛቸው) የምትንሻለል ስትሆን (በአላህ ስም ተቀመጡባት)፡፡ ኑሕም ልጁን ከመርከቢቱ የራቀ ሆኖ ሳለ «ልጄ ሆይ! ከኛ ጋር ተሳፈር ከከሓዲዎቹም አትሁን» ሲል ጠራው፡፡ 11|43|(ልጁም) «ከውሃው ወደሚጠብቀኝ ተራራ እጠጋለሁ» አለ፡፡ (አባቱም)፡- «ዛሬ ከአላህ ትዕዛዝ ምንም ጠባቂ የለም (እርሱ) ያዘነለት ካልሆነ በቀር» አለው፡፡ ማዕበሉም በመካከላቸው ጋረደ፡፡ ከሰጣሚዎቹም ሆነ፡፡ 11|44|ተባለም፡- «ምድር ሆይ! ውሃሽን ዋጪ፡፡ ሰማይም ሆይ (ዝናብሽን) ያዢ፡፡ ውሃውም ሰረገ፡፡ ቅጣቱም ተፈጸም፡፡ ጁዲይ በሚባልም ተራራ ላይ (መርከቢቱ) ተደላደለች፡፡ ለከሓዲዎችም ሰዎች ጥፋት ተገባቸው (ጠፉ)» ተባለ፡፡ 11|45|ኑሕም ጌታውን ጠራ፡፡ አለም «ጌታዬ ሆይ! ልጄ ከቤተሰቤ ነው፡፡ ኪዳንህም እውነት ነው፡፡ አንተም ከፈራጆች ሁሉ ይበልጥ ዐዋቂ ነህ፡፡» 11|46|(አላህም) «ኑሕ ሆይ! እርሱ ከቤተሰብህ አይደለም፤ እርሱ መልካም ያልሆነ ሥራ ነው፤ በርሱ ዕውቀት የሌለህንም ነገር አትጠይቀኝ፤ እኔ ከሚሳሳቱት ሰዎች እንዳትሆን እገስጽሀለሁ» አለ፡፡ 11|47|«ጌታዬ ሆይ! በእርሱ ለእኔ ዕውቀት የሌለኝን ነገር የምጠይቅህ ከመሆን እኔ ባንተ እጠበቃለሁ፡፡ ለእኔም ባትምረኝና ባታዝንልኝ ከከሳሪዎቹ እሆናለሁ» አለ፡፡ 11|48|«ኑሕ ሆይ! ከእኛ በሆነ ሰላም ባንተ ላይና አንተም ጋር ባሉት ሕዝቦች (ትውልድ) ላይ በሆኑ በረከቶችም የተጎናጸፍክ ሆነህ ውረድ፡፡ (ከእነሱው ዘሮች የሆኑ) ሕዝቦችም በቅርቢቱ ዓለም በእርግጥ እናስመቻቸዋለን፡፡ ከዚያም ከኛ የሆነ አሳማሚ ቅጣት ይነካቸዋል» ተባለ፡፡ 11|49|ይህቺ ከሩቁ ወሬዎች ናት፡፡ ወደ አንተ እናወርዳታለን፡፡ አንተም ሕዝቦችህም ከዚህ በፊት የምታውቋት አልነበራችሁም፡፡ ታገስም፤ ምስጉን የሆነችው ፍጻሜ ለሚጠነቀቁት ናትና፡፡ 11|50|ወደ ዓድም ወንድማቸውን ሁድን (ላክን)፡፡ አላቸው፡- «ወገኖቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ከእርሱ ሌላ ምንም አምላክ የላችሁም፡፡ እናንተም ቀጣፊዎች እንጂ ሌላ አይደላችሁም፡፡ 11|51|«ሕዝቦቼ ሆይ! በእርሱ (በማድረሴ) ላይ ምንዳን አልጠይቃችሁም፡፡ ምንዳዬ በዚህ በፈጠረኝ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ አታውቁምን 11|52|«ሕዝቦቼም ሆይ! ጌታችሁን ምሕረትን ለምኑት፡፡ ከዚያም ወደርሱ ተጸጸቱ፡፡ ዝናብን በእናንተ ላይ ተከታታይ አድርጎ ይልክላችኋልና፡፡ ወደ ኃይላችሁም ኃይልን ይጨምርላችኋል፡፡ አመጸኞችም ሆናችሁ አትሽሹ፡፡» 11|53|አሉ፡- «ሁድ ሆይ! በአስረጅ አልመጣህልንም፡፡ እኛም ላንተ ንግግር ብለን አማልክቶቻችንን የምንተው አይደለንም፡፡ እኛም ለአንተ አማኞች አይደለንም፡፡ 11|54|«ከፊሎቹ አማልክቶቻችን በክፉ ነገር (በዕብደት) ለክፈውሃል እንጂ ሌላን አንልም» (አሉ)፡፡ «እኔ አላህን አስመሰክራለሁ፡፡ ከምታጋሩትም እኔ ንጹሕ መሆኔን መስክሩ» አላቸው፡፡ 11|55|ከእርሱ ሌላ (አማልክትን ከምታጋሩት ንጹህ ነኝ)፡፡ ሁላችሁም ሆናችሁ ተንኮልን ሥሩብኝ፤ ከዚያም አታቆዩኝ፡፡ 11|56|«እኔ በጌታዬና በጌታችሁ በአላህ ላይ ተጠጋሁ፡፡ በምድር ላይ ምንም ተንቀሳቃሽ የለችም እርሱ አናትዋን የያዛት ብትሆን እንጂ፡፡ ጌታዬ (ቃሉም ሥራውም) በቀጥተኛው መንገድ ላይ ነው» (አላቸው)፡፡ 11|57|«ብትዞሩም በእርሱ ወደእናንተ የተላክሁበትን ነገር በእርግጥ አድርሼላችኋለሁ፡፡ ጌታዬ ከእናንተ ሌላ ሕዝብም ይተካል ምንም አትጎዱትምም፡፡ ጌታዬ በነገሩ ሁሉ ላይ ተጠባባቂ ነውና» (አላቸው)፡፡ 11|58|ትዕዛዛችንም በመጣ ጊዜ ሁድንና እነዚያን ከእሱ ጋር ያመኑትን ከእኛ በሆነው ችሮታ አዳን፡፡ ከብርቱ ቅጣትም አዳናቸው፡፡ 11|59|ይህች (ነገድ) ዓድ ናት፡፡ በጌታቸው ታምራት ካዱ፡፡ መልክተኞቹንም አመጹ፤ የኃያል ሞገደኛን ሁሉ ትዕዛዝም ተከተሉ፡፡ 11|60|በዚህች በቅርቢቱ ዓለምም እርግማን እንዲከተላቸው ተደረጉ፡፡ በትንሣኤም ቀን (እንደዚሁ)፡፡ ንቁ! ዓዶች ጌታቸውን ካዱ፡፡ ንቁ! የሁድ ሕዝቦች ለሆኑት ዓዶች (ከእዝነት) መራቅ ይገባቸው፡፡ 11|61|ወደ ሰሙዶችም ወንድማቸውን ሷሊህን (ላክን)፡፡ «ሕዝቦቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ከእርሱ ሌላ ለእናንተ አምላክ የላችሁም፡፡ እርሱ ከምድር ፈጠራችሁ፡፡ በውስጧ እንድታለሟትም አደረጋችሁ፡፡ ምሕረቱንም ለምኑት፡፡ ከዚህም ወደእርሱ ተመለሱ፡፡ ጌታዬ ቅርብ (ለለመነው) ተቀባይ ነውና» አላቸው፡፡ 11|62|«ሷሊህ ሆይ! ከዚህ በፊት በእኛ ውስጥ (መሪ ልትሆን) በእርግጥ የምትከጅል ነበርክ፡፡ አባቶቻችን የሚገዙትን ከመገዛት ትከለክለናለህን እኛም ወደርሱ ከምትጠራን ነገር በእርግጥ አወላዋይ በሆነ መጠራጠር ውስጥ ነን» አሉ፡፡ 11|63|«ሕዝቦቼ ሆይ! ንገሩኝ ከጌታዬ በሆነ ማስረጃ ላይ ብሆን ከእርሱም የሆነን ችሮታ (ነቢይነት) ቢሰጠኝና ባልታዘዘው ከአላህ (ቅጣት) የሚያድነኝ ማነው ከማሳሳትም በስተቀር ምንም አትጨምሩልኝም» አላቸው፡፡ 11|64|ሕዝቦቼም ሆይ! ይህቺ ለእናንተ ተዓምር ስትሆን የአላህ ግመል ናት፡፡ ተውዋትም፡፡ በአላህ ምድር ውስጥ ትብላ፡፡ በክፉም አትንኳት፡፡ ቅርብ የሆነ ቅጣት ይይዛችኋልና» (አላቸው)፡፡ 11|65|ወግተው ገደሏትም፡፡ (ሷሊህ) «በአገራችሁም ሶስትን ቀናት (ብቻ) ተጠቀሙ፡፡ ይህ የማይዋሽ ቀጠሮ ነው» አላቸው፡፡ 11|66|ትዕዛዛችንም በመጣ ጊዜ ሷሊህንና እነዚያን ከሱ ጋር ያመኑትን ከእኛ በሆነው እዝነት አዳን፡፡ ከዚያም ቀን ውርደት (አዳንናቸው)፡፡ ጌታህ እርሱ ብርቱው አሸናፊው ነውና፡፡ 11|67|እነዚያንም የበደሉትን ጩኸት ያዛቸው፡፡ በቤቶቻቸውም ውስጥ የተንበረከኩ ሆነው ሞተው አነጉ፡፡ 11|68|በእሷ ውስጥ እንዳልኖሩባት ሆኑ፡፡ ንቁ! ሰሙዶች ጌታቸውን በእርግጥ ካዱ፡፡ ንቁ! ለሰሙዶች (ከአላህ እዝነት) መራቅ ተገባቸው፡፡ 11|69|መልክተኞቻችንም ኢብራሂምን በ(ልጅ) ብስራት በእርግጥ መጡት፡፡ ሰላም አሉት፡፡ ሰላም አላቸው፡፡ ጥቂትም ሳይቆይ ወዲያውኑ የተጠበሰን የወይፈን ስጋ አመጣ፡፡ 11|70|እጆቻቸውም ወደ እርሱ የማይደርሱ መኾነቸውን ባየ ጊዜ ሸሻቸው፡፡ ከነሱም ፍርሃት ተሰማው፡፡ «አትፍራ እኛ ወደ ሉጥ ሕዝቦች ተልከናልና» አሉት፡፡ 11|71|ሚስቱም የቆመች ስትኾን (አትፍራ አሉት) ሳቀችም፡፡ በኢስሐቅም አበሰርናት፡፡ ከኢስሐቅም በኋላ (በልጁ) በያዕቁብ (አበሰርናት)፡፡ 11|72|(እርሷም) ዋልኝ! እኔ አሮጊት ይህም ባሌ ሽማግሌ ሆኖ ሳለ እወልዳለሁን ይህ በእርግጥ አስደናቂ ነገር ነው አለች፡፡ 11|73|«ከአላህ ትዕዛዝ ትደነቂያለሽን የአላህ ችሮታና በረከቶቹ በእናንተ በኢብራሂም ቤተሰቦች ላይ ይሁን እርሱ ምስጉን ለጋስ ነውና» አሉ፡፡ 11|74|ከኢብራሂም ፍራቻው በሌደለትና ብስራት በመጣችለትም ጊዜ በሉጥ ሕዝቦች (ነገር) ይከራከረን ጀመር፡፡ 11|75|ኢብራሂም በእርግጥ ታጋሽ አልቃሻ መላሳ ነውና፡፡ 11|76|«ኢብራሂም ሆይ! ከዚህ (ክርክር) ተው፡፡ እነሆ የጌታህ ትዕዛዝ በእርግጥ መጥቷል፡፡ እነሱም የማይመለስ ቅጣት የሚመጣባቸው ናቸው» (አሉት)፡፡ 11|77|መልክተኞቻችንም ሉጥን በመጡት ጊዜ በነሱ (ምክንያት) አዘነ፡፡ ልቡም በነሱ ተጨነቀ፡፡ «ይህ ብርቱ ቀን ነውም» አለ፡፡ 11|78|ሕዝቦቹም ወደርሱ እየተጣደፉ መጡት፡፡ ከዚህም በፊት መጥፎ ሥራዎችን ይሠሩ ነበር፡፡ «ሕዝቦቼ ሆይ! እኝህ ሴቶች ልጆቼ ናቸው፡፡ እነሱ ለእናንተ ይልቅ በጣም የጸዱ ናቸው፤ (አግቧቸው)፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ በእንግዶቼም አታሳፍሩኝ፡፡ ከእናንተ ውስጥ ቅን ሰው የለምን» አላቸው፡፡ 11|79|«ከሴቶች ልጆችህ ለእኛ ምንም ጉዳይ የለንም፡፡ አንተም የምንሻውን በእርግጥ ታውቃለህ» አሉት፡፡ 11|80|«በእናንተ ላይ ለኔ ኀይል በኖረኝ ወይም ወደ ብርቱ ወገን ብጠጋ ኖሮ (የምሠራውን በሠራሁ ነበር)» አላቸው፡፡ 11|81|«ሉጥ ሆይ! እኛ የጌታህ መልክተኞች ነን፡፡ (ሕዝቦችህ) ወደ አንተ (በክፉ) አይደርሱብህም፡፡ ቤተሰብህንም ይዘህ ከሌሊቱ በከፊሉ ውስጥ ሊድ፡፡ ከእናንተም አንድም (ወደኋላው) አይገላመጥ፡፡ ሚስትህ ብቻ ስትቀር፡፡ እነሆ እርሷን (እነሱን) የሚያገኛቸው ስቃይ ያገኛታልና፡፡ ቀጠሯቸው እንጋቱ ላይ ነው፡፡ ንጋቱ ቅርብ አይደለምን» አሉት፡፡ 11|82|82|ትዕዛዛችንም በመጣ ጊዜ (ከተማይቱን) ላይዋን ከታችዋ አደረግን (ገለበጥናት)፡፡ ተከታታይም የሆነን የሸክላ ድንጋይ በርሷ ላይ አዘነብን፡፡ 11|83|ከጌታህ ዘንድ ምልክት የተደረገባት ስትሆን (አዘነብናት)፡፡ እርሷም ከበደለኞቹ ሩቅ አይደለችም፡፡ 11|84|ወደ መድየንም ወንድማቸውን ሹዐይብን (ላክን)፡፡ አላቸው «ሕዝቦቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ከእርሱ ሌላ ለናንተ አምላክ የላችሁም፡፡ ስፍርንና ሚዛንንም አታጉድሉ፤ እኔ በጸጋ ላይ ሆናችሁ አያችኋለሁ፡፡ እኔም በእናንተ ላይ የከባቢን ቀን ቅጣት እፈራለሁ፡፡ 11|85|«ሕዝቦቼም ሆይ! ስፍርንና ሚዛንን በትክክል ሙሉ፡፡ ሰዎችንም ምንም ነገራቸውን አታጉድሉባቸው፡፡ በምድርም ውስጥ አጥፊዎች ሆናችሁ አታበላሹ፡፡ 11|86|አላህ ያስቀረላችሁ ለእናንተ የተሻለ ነው፡፡ ምእመናን እንደሆናችሁ (አላህ በሰጣችሁ ውደዱ)፡፡ እኔም (መካሪ እንጅ) በናንተ ላይ ተጠባባቂ አይደለሁም፡፡» 11|87|«ሹዐይብ ሆይ! ስግደትህ አባቶቻችን የሚገዙትን ጣዖታት እንድንተው ወይም በገንዘቦቻችን የምንሻውን መሥራትን (እንድንተው) ታዝሃለችን አንተ በእርግጥ ታጋሹ ቅኑ አንተ ነህና» አሉት፡፡ 11|88|«ሕዝቦቼ ሆይ! ንገሩኝ፤ ከጌታዬ በሆነ አስረጅ ላይ ብሆንና ከእርሱም የሆነን መልካም ሲሳይ ቢሰጠኝ (በቅጥፈት ልቀላቅለው ይገባልን) ከእርሱ ወደ ከለከልኳችሁም ነገር ልለያችሁ አልሻም፡፡ በተቻለኝ ያክል ማበጀትን እንጂ አልሻም (ለደግ ሥራ) መገጠሜም በአላህ እንጂ በሌላ አይደለም፡፡ በእርሱ ላይ ተመካሁ፡፡ ወደእርሱም እመለሳለሁ፤» አላቸው፡፡ 11|89|«ወገኖቼም ሆይ! እኔን መከራከራችሁ የኑሕን ሕዝቦች ወይም የሁድን ሕዝቦች ወይም የሷሊሕን ሕዝቦች ያገኛቸው (ቅጣት) ብጤ እንዲያገኛችሁ አይገፋፋችሁ፡፡ የሉጥም ሕዝቦች ከእናንተ ሩቅ አይደሉም፡፡ 11|90|«ጌታችሁንም ምሕረትን ለምኑት፡፡ ከዚያም ወደርሱ ተመለሱ፡፡ ጌታዬ አዛኝ ወዳድ ነውና (አላቸው)፡፡ 11|91|«ሹዐይብ ሆይ! ከምትለው ነገር ብዙውን አናውቀውም፡፡ እኛም አንተን በእኛ ውስጥ ደካማ ሆነህ እናይሃለን፡፡ ጎሳዎችህም ባልኖሩ ኖሮ በወገርንህ ነበር፤ አንተም በእኛ ላይ የተከበርክ አይደለህም» አሉት፡፡ 11|92|«ሕዝቦቼ ሆይ! ጎሳዎቼ በእናንተ ላይ ከአላህ ይልቅ የከበሩ ናቸውን (አላህን) ከኋላችሁ ወደ ጀርባ አድርጋችሁም ያዛችሁት፡፡ ጌታዬ በምትሠሩት ሁሉ ከባቢ ነው» አላቸው፡፡ 11|93|«ሕዝቦቼም ሆይ! በችሎታችሁ ልክ ሥሩ፡፡ እኔ ሠሪ ነኝና፡፡ የሚያዋርደው ቅጣት የሚመጣበትና እርሱ ውሸታም የሆነው ማን እንደኾነ ወደ ፊት ታውቃላችሁ፡፡ ጠብቁም እኔ ከናንተ ጋር ተጠባባቂ ነኝና»(አላቸው)፡፡ 11|94|ትዕዛዛችንም በመጣ ጊዜ ሹዐይብንና እነዚያን ከርሱ ጋር ያመኑትን ከእኛ በሆነው ችሮታ አዳን፡፡ እነዚያን የበደሉትንም (የጂብሪል) ጩኸት ያዘቻቸው፡፡ በቤቶቻቸውም ውስጥ ተንከፍርረው አደሩ፡፡ 11|95|በእርሷ ውስጥ እንዳልነበሩ ሆኑ፡፡ ንቁ! ሰሙድ (ከአላህ እዝነት) እንደ ራቀች መድየንም ትራቅ፡፡ 11|96|ሙሳንም በተዓምራታችንና በግልጽ ብርሃን በእርግጥ ላክነው፡፡ 11|97|ወደ ፈርዖንና ወደ ሰዎቹ (ላክነው)፡፡ የፈርዖንንም ነገር (ሕዝቦቹ) ተከተሉ፡፡ የፈርዖን ነገርም ቀጥተኛ አልነበረም፡፡ 11|98|በትንሣኤ ቀን ሕዝቦቹን ይቀድማል፡፡ ወደ እሳትም ያወርዳቸዋል፡፡ የሚገቡትም አገባብ ምንኛ ከፋ! 11|99|በዚችም (በቅርቢቱ ዓለም) እርግማንን አስከተልናቸው፡፡ በትንሣኤም ቀን (እንደዚሁ)፡፡ የተሰጡት ስጦታ ምንኛ ከፋ! 11|100|ይህ (የተነገረው) ከከተሞቹ ወሬዎች ነው፡፡ ባንተ ላይ እንተርከዋለን፡፡ ከእርሷ ፋናው የቀረና ሙሉ በሙሉ የተደመሰሰ አለ፡፡ 11|101|እኛም አልበደልናቸውም፡፡ ግን ነፍሶቻቸውን በደሉ፡፡ የአላህም ትእዛዝ በመጣ ጊዜ እነዚያ ከአላህ ሌላ የሚገዙዋቸው አማልክቶቻቸው በምንም አላዳኗቸውም፡፡ ከማክሰርም በቀር ምንም አልጨመሩላቸውም፡፡ 11|102|የጌታህም ቅጣት የከተሞችን ሰዎች እነሱ በዳዮች ሲሆኑ በቀጣቸው ጊዜ እንደዚህ ነው፡፡ ቅጣቱ በእርግጥ አሳማሚ ብርቱ ነው፡፡ 11|103|በዚህ ውስጥ የመጨረሻውን ቀን ቅጣት ለሚፈሩ ሁሉ መገሰጫ አለ፡፡ ይህ (የትንሣኤ ቀን) ሰዎች በርሱ የሚሰበሰቡበት ቀን ነው፡፡ ይህም የሚጣዱት ቀን ነው፡፡ 11|104|(ይህንን ቀን) ለተቆጠረም ጊዜ እንጂ አናቆየውም፡፡ 11|105|በሚመጣ ቀን ማንኛዋም ነፍስ በእርሱ ፈቃድ ቢሆን እንጂ አትናገርም፡፡ ከነሱም መናጢና ዕድለኛም አልለ፡፡ 11|106|እነዚያ መናጢ የሆኑትማ፡ በእሳት ውስጥ ናቸው፡፡ ለእነርሱ በእርሷ ውስጥ ማናፋትና መንሰቅሰቅ አላቸው፡፡ 11|107|ጌታህ ከሻው (ጭማሬ) ሌላ ሰማያትና ምድር እስከ ዘወተሩ ድረስ በውስጧ ዘውተሪዎች ሲኾኑ (በእሳት ይኖራሉ)፡፡ ጌታህ የሚሻውን ሠሪ ነውና፡፡ 11|108|እነዚያም ዕድለኞቹማ ጌታህ ከሻው (ጭማሬ) ሌላ ሰማያትና ምድር እስከ ዘወተሩ ድረስ በውስጧ ዘውታሪዎች ኾነው በገነት ውስጥ ይኖራሉ፡፡ የማይቋረጥ ስጦታን ተሰጡ፡፡ 11|109|እነዚህ (ከሓዲዎች) ከሚገዙት ጣዖት በመጠራጠር ውስጥ አትሁን፤ አባቶቻቸው ከዚህ በፊት እንደሚግገዙት እንጂ አይግገዙም፡፡ እኛም (እነዚህን) ፈንታቸውን የማይጓደል ሲሆን የምንሞላላቸው ነን፡፡ 11|110|ለሙሳም መጽሐፍን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ በእርሱም ተለያዩበት፡፡ ከጌታህም ያለፈች ቃል ባልነበረች ኖሮ በመካከላቸው (አሁን) ይፈረድ ነበር፡፡ እነሱም ከእርሱ (ከቁርኣን) አወላዋይ በሆነ መጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ 11|111|ሁሉንም ጌታህ ሥራዎቻቸውን (ምንዳቸውን) በእርግጥ ይሞላላቸዋል፡፡ እርሱ በሚሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነውና፡፡ 11|112|እንደ ታዘዝከውም ቀጥ በል፡፡ ከአንተ ጋር ያመኑትም (ቀጥ ይበሉ)፡፡ ወሰንንም አትለፉ፤ እርሱ የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነውና፡፡ 11|113|ወደእነዚያም ወደ በደሉት አትጠጉ፡፡ እሳት ትነካችኋለችና፡፡ ከአላህም ሌላ ጠባቂዎች የሏችሁም፡፡ ከዚያም አትረድዱም፡፡ 11|114|ሶላትንም በቀን ጫፎች ከሌሊትም ክፍሎች ፈጽም፡፡ መልካም ሥራዎች ኀጢአቶችን ያስወገድዳሉና፡፡ ይህ ለተገሳጮች ግሳጼ ነው፡፡ 11|115|ታገስም፤ አላህ የበጎ ሠሪዎችን ምንዳ አያጠፋምና፡፡ 11|116|ከእናንተም በፊት ከነበሩት ከክፍለ ዘመናት ሰዎች ውስጥ በምድር ላይ ከማበላሸት የሚከለክሉ የመልካም ቀሪ ሥራዎች ባለቤቶች ለምን አልነበሩም ግን ከእነሱ ያዳንናቸው ጥቂቶቹ (ከለከሉና ዳኑ)፡፡ እነዚያም የበደሉት ሰዎች (አልከለከሉም)፡፡ በእርሱ የተቀማጠሉበትን ተድላ ተከተሉ፡፡ አመጸኞችም ነበሩ፡፡ 11|117|ጌታህም ከተሞችን ባለቤቶቻቸው መልካም ሠሪዎች ሆነው ሳሉ በመበደል የሚያጠፋቸው አልነበረም፡፡ 11|118|ጌታህም በሻ ኖሮ ሰዎችን ሁሉ አንድ ሕዝብ ባደረጋቸው ነበር፡፡ የተለያዩም ከመሆን አይወገዱም፡፡ 11|119|ጌታህ ያዘነለት ብቻ ሲቀር፤ (ከመለያየት አይወገዱም)፡፡ ለዚሁም ፈጠራቸው፡፡ የጌታህም ቃል ገሀነምን ከአጋንንትና ከሰዎች ከሁሉም በእርግጥ እሞላታለሁ በማለት ተፈጸመች፡፡ 11|120|ከመልክተኞቹም ዜናዎች (ተፈላጊውን) ሁሉንም ልብህን በርሱ የምናረካበትን እንተርክልሃለን፡፡ በዚህችም (ሱራ) እውነቱ ነገር ለምእምናን ግሳጼና ማስታወሻ መጥቶልሃል፡፡ 11|121|ለእነዚያም ለማያምኑት ባላችሁበት ሁኔታ ላይ ሥሩ፤ እኛ ሠሪዎች ነንና በላቸው፡፡ 11|122|ተጠባበቁም እኛ ተጠባባቂዎች ነንና (በላቸው)፡፡ 11|123|በሰማያትና በምድርም ያለው ምስጢር ሁሉ የአላህ ነው፡፡ ነገሩ ሁሉም ወደርሱ ይመለሳል፡፡ ስለዚህ ተገዛው፡፡ በእርሱም ላይ ተጠጋ፡፡ ጌታህም ከሚሠሩት ሁሉ ዘንጊ አይደለም፡፡ 12|1|አ.ለ.ረ (አሊፍ ላም ራ) እነዚህ የገላጩ መጽሐፍ አንቀጾች ናቸው፡፡ 12|2|እኛ (ፍቹን) ታውቁ ዘንድ ዐረብኛ ቁርኣን ሲሆን በእርግጥ አወረድነው፡፡ 12|3|እኛ ይህንን ቁርኣን ወደ አንተ በማውረዳችን በጣም መልካም ዜናዎችን በአንተ ላይ እንተርክልሃለን፡፡ እነሆ ከእርሱ በፊት (ካለፉት ሕዝቦች ታሪክ) በእርግጥ ከዘንጊዎቹ ነበርክ፡፡ 12|4|ዩሱፍ ለአባቱ፡- «አባቴ ሆይ! እኔ ዐስራ አንድ ከዋክብትን ፀሐይንና ጨረቃንም (በሕልሜ) አየሁ፡፡ ለእኔ ሰጋጆች ሆነው አየኋቸው» ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 12|5|(አባቱም) አለ «ልጄ ሆይ! ሕልምህን ለወንድሞችህ አታውራ፡፡ ላንተ ተንኮልን ይሰሩብሃልና፡፡ ሰይጣን ለሰው ግልጽ ጠላት ነውና፡፡» 12|6|«እንደዚሁም (እንዳየኸው) ጌታህ ይመርጥሃል፡፡ ከንግግሮችም ፍች ያስተምርሃል፡፡ ጸጋውንም ከአሁን በፊት በሁለቱ አባቶችህ በኢብራሂምና በኢስሐቅ ላይ እንዳሟላት በአንተ ላይና በያዕቆብ ዘሮችም ላይ ይሞላታል፡፡ ጌታህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡» 12|7|በዩሱፍና በወንድሞቹ (ታሪኮች) ውስጥ ለጠያቂዎች ሁሉ በእርግጥ አስደናቂ ምልክቶች ነበሩ፡፡ 12|8|(ወንድሞቹ) ባሉ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «እኛ ጭፍሮች ስንሆን ዩሱፍና ወንድሙ (ብንያም) ወደ አባታችን ከእኛ ይበልጥ የተወደዱ ናቸው፡፡ አባታችን በግልጽ ስህተት ውስጥ ነው፡፡ 12|9|«ዩሱፍን ግደሉ፡፡ ወይም በ(ሩቅ) ምድር ላይ ጣሉት፡፡ ያባታችሁ ፊት ለእናንተ የግል ይኾናልና፡፡ ከእርሱም በኋላ መልካም ሕዝቦች ትሆናላችሁና» (ተባባሉ)፡፡ 12|10|ከእነሱ አንድ ተናጋሪ «ዩሱፍን አትግደሉ ግን በጉድጓድ አዘቅት ጨለማ ውስጥ ጣሉት፤ ከተጓዢዎች አንዱ ያነሳዋልና፡፡ ሠሪዎች ብትኾኑ (በዚሁ ተብቃቁ) አላቸው፡፡ 12|11|(እነሱም) አሉ «አባታችን ሆይ! በዩሱፍ ላይ ለምን አታምነንም እኛም ለእርሱ በእርግጥ አዛኞች ነን፡፡» 12|12|«ነገ ከእኛ ጋር ላከውና ይደሰት፤ ይጫወትም፡፡ እኛም ለእርሱ ጠባቂዎች ነን፡፡» 12|13|«እኔ እርሱን (ዩሱፍን) ይዛችሁ መሌዳችሁ በእርግጥ ያሳዝነኛል፡፡ እናንተም ከእርሱ ዘንጊዎች ስትሆኑ ተኩላ ይበላዋል ብዬ እፈራለሁ» አላቸው፡፡ 12|14|«እኛ ጭፍራዎች ሆነን ሳለን ተኩላ ቢበላውማ እኛ ያን ጊዜ በእርግጥ ከሳሪዎች ነን» አሉት፡፡ 12|15|እርሱንም ይዘውት በሌዱና በጉድጓዱ ጨለማ አዘቅት ውስጥ እንዲያደርጉት በቆረጡ ጊዜ (ሐሳባቸውን ፈጸሙበት)፡፡ ወደእርሱም እነሱ የማያውቁ ሲሆኑ ይህንን ሥራቸውን በእርግጥ ትነግራቸዋለህ ስንል ላክንበት፡፡ 12|16|አባታቸውንም በምሽት እያለቀሱ መጡት፡፡ 12|17|«አባታችን ሆይ! እኛ (ለሩጫና ለውርወራ) ልንሽቀዳደም ሌድን፡፡ ዩሱፍንም ዕቃችን ዘንድ ተውነው፡፡ ወዲያውም ተኩላ በላው፡፡ አንተም እውነተኞች ብንሆንም የምታምነን አይደለህም» አሉ፡፡ 12|18|በቀሚሱም ላይ የውሸትን ደም አመጡ፡፡ (አባታቸው) «አይደለም፤ ነፍሶቻችሁ (ውሸት) ነገርን ለእናንተ ሸለሙላችሁ፡፡ ስለዚህ መልካም ትዕግስት (ማድረግ አለብኝ) በምትሉትም ነገር ላይ መታገዣው አላህ ብቻ ነው» አለ፡፡ 12|19|መንገደኞችም መጡ፡፡ ውሃ ቀጂያቸውንም ላኩ፡፡ አኮሊውንም (ወደ ጉድጓዱ) ሰደደ «የምስራች! ይህ ወጣት ልጅ ነው» አለ፡፡ ሸቀጥ አድርገውም ደበቁት፡፡ አላህም የሚሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 12|20|በርካሽ ዋጋም በሚቆጠሩ ዲርሃሞች ሸጡት፡፡ በእርሱም ከቸልተኞቹ ነበሩ፡፡ 12|21|ያም ከምስር የገዛው ሰው ለሚስቱ «መኖሪያውን አክብሪ፡፡ ሊጠቅመን ወይም ልጅ አድርገን ልንይዘው ይከጀላልና» አላት፡፡ እንደዚሁም ለዩሱፍ (ገዥ ልናደርገውና) የሕልሞችንም ፍች ልናስተምረው በምድር ላይ አስመቸነው፡፡ አላህም በነገሩ ላይ አሸናፊ ነው፤ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 12|22|ጥንካሬውንም በደረሰ ጊዜ ጥበብንና ዕውቀትን ሰጠነው፡፡ እንደዚሁም መልካም ሠሪዎችን ሁሉ እንመነዳለን፡፡ 12|23|ያቺም እርሱ በቤቷ የነበረባት ሴት ከነፍሱ አባበለችው፡፡ ደጃፎቹንም ዘጋች፤ «ላንተ ተዘጋጅቼልሃለሁና ቶሎ ናም» አለችው፡፡ «በአላህ እጠበቃለሁ እርሱ (የገዛኝ) ጌታዬ ኑሮዬን ያሳመረልኝ ነውና፤ (አልከዳውም)፡፡ እነሆ! በደለኞች አይድኑም» አላት፡፡ 12|24|በእርሱም በእርግጥ አሰበች፡፡ በእርሷም አሰበ፤ የጌታውን ማስረጃ ባላየ ኖሮ (የተፈጥሮ ፍላጎቱን ባረካ ነበር፤)፡፡ እንደዚሁ መጥፎ ነገርንና ኀጢአትን ከእርሱ ላይ ልንመልስለት (አስረጃችንን አሳየነው)፡፡ እርሱ ከተመረጡት ባሮቻችን ነውና፡፡ 12|25|በሩንም ተሽቀዳደሙ ቀሚሱንም ከበስተኋላው ቀደደችው፡፡ ጌታዋንም (ባለቤቷን) እበሩ አጠገብ አገኙት፡፡ (ቀደም ብላ) «በባለቤትህ መጥፎን ያሰበ ሰው ቅጣቱ መታሰር ወይም አሳማሚ ስቃይ እንጂ ሌላ አይደለም» አለችው፡፡ 12|26|(ዩሱፍም) «እርሷ ከነፍሴ አባበለችኝ» አለ፡፡ ከቤተሰቦቿም መስካሪ (እንዲህ ሲል) መሰከረ፡፡ «ቀሚሱ ከበስተፊት ተቀድዶ እንደሆነ እውነት ተናገረች፡፡ እርሱም ከውሸታሞቹ ነው፡፡ 12|27|«ቀሚሱም ከበስተኋላ ተቀድዶ እንደሆነ ዋሸች፡፡ እርሱም ከእውነተኞቹ ነው፡፡» 12|28|ቀሚሱንም ከበስተኋላ ተቀድዶ ባየ ጊዜ «እርሱ (የተናገርሺው) ከተንኮላችሁ ነው (ሴቶች) ተንኮላችሁ በእርግጥ ብርቱ ነውና» አላት፡፡ 12|29|«ዩሱፍ ሆይ! ከዚህ (ወሬ) ተከልከል፡፡ ለኃጢአትሽም ማርታን ለምኚ፡፡ አንቺ ከስህተተኞቹ ሆነሻልና» (አለ)፡፡ 12|30|በከተማው ያሉ ሴቶችም «የዐዚዝ ሚስት ብላቴናዋን ከነፍሱ ታባብለዋለች፡፡ በእውነቱ ፍቅሩ ልቧን መቷታል፡፡ እኛ በግልጽ ስህተት ውስጥ ሆና በእርግጥ እናያታለን» አሉ፡፡ 12|31|ሀሜታቸውንም በሰማች ጊዜ ወደነሱ ላከችባቸው፡፡ ምግብንም ለእነርሱ አዘጋጀችላቸው፡፡ ከእነሱ ለያንዳንዳቸውም ቢላዋን ሰጠች፡፡ በእነሱም ላይ «ውጣ» አለችው፡፡ ባዩትም ጊዜ አደነቁት፡፡ እጆቻቸውንም ቆረጡ፡፡ አላህም ጥራት ይገባው፡፡ ይህ ሰው አይደለም፡፡ ይህ ያማረ መልአክ እንጅ ሌላ አይደለም አሉ፡፡ 12|32|«ታዲያ ይህ ያ በርሱ (ፍቅር) የዘለፋችሁኝ ነው፡፡ በእርግጥም ከነፍሱ አባበልኩት፡፡ እምቢ አለም፡፡ የማዘውንም ነገር ባይሠራ በእርግጥ ይታሰራል፡፡ ከወራዶቹም ይሆናል» አለች፡፡ 12|33|«ጌታዬ ሆይ! ወደርሱ ከሚጠሩኝ ነገር (ከዝሙት) ይልቅ መታሰር ለእኔ የተወደደ ነው፡፡ ተንኮላቸውንም ከእኔ ላይ ባትመልስልኝ ወደነሱ እዘነበላለሁ፡፡ ከስህተተኞቹም እሆናለሁ» አለ፡፡ 12|34|ጌታውም ጸሎቱን ተቀበለው፡፡ ተንኮላቸውንም ከእርሱ መለሰለት፡፡ እነሆ! እርሱ ሰሚው ዐዋቂው ነውና፡፡ 12|35|ከዚያም ማስረጃዎቹን ካዩ በኋላ እስከጊዜ ድረስ እንዲያስሩት ለነሱ ታያቸው፡፡ 12|36|ከእሱም ጋር ሁለት ጎበዞች እስር ቤቱ ገቡ፡፡ አንደኛቸው «እኔ በህልሜ የወይን ጠጅን ስጠምቅ አየሁ» አለ፡፡ ሌላውም፡- «እኔ በራሴ ላይ እንጀራን ተሸክሜ ከእሱ በራሪ (አሞራ) ስትበላ አየሁ፡፡ ፍቹን ንገረን፡፡ እኛ ከአሳማሪዎች ሆነህ እናይሃለንና» አሉት፡፡ 12|37|(ዩሱፍም) አለ፡- «ማንኛውም የምትስሰጡት ምግብ ለናንተ ከመምጣቱ በፊት ፍቹን የምነግራችሁ ቢሆን እንጂ አይመጣላችሁም፡፡ ይኸ ጌታዬ ካሳወቀኝ ነገር ነው፤ እኔ በአላህ የማያምኑን እነርሱም መጨረሻይቱን ዓለም እነርሱ ከሓዲዎች የሆኑትን ሕዝቦች ሃይማኖት ትቻለሁ፡፡ 12|38|«የአባቶቼንም የኢብራሂምንና የኢስሐቅን፣ የያዕቆብንም ሃይማኖት ተከትያለሁ፡፡ ለእኛ በአላህ ምንንም ማጋራት አይገባንም ያ (አለማጋራት) በእኛ ላይና በሰዎቹ ላይ የአላህ ችሮታ ነው፡፡ ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያመሰግኑም፡፡ 12|39|«የእስር ቤት ጓደኞቼ ሆይ! የተለያዩ አምላኮች ይሻላሉን ወይስ አሸናፊው አንዱ አላህ 12|40|«ከእርሱ ሌላ እናንተና አባቶቻችሁ (አማልክት ብላችሁ) የጠራችኋቸውን ስሞች እንጅ አትገዝዙም፡፡ አላህ በእርሷ ምንም አስረጅ አላወረደም፡፡ ፍርዱ የአላህ እንጅ የሌላ አይደለም፡፡ እርሱን እንጅ ሌላን እንዳትገዙ አዟል፡፡ ይህ ትክክለኛው ሃይማኖት ነው፡፡ ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 12|41|«የወህኒ ቤት ጓደኞቼ ሆይ! አንደኛችሁማ ጌታውን (ንጉሡን) ጠጅ ያጠጣል፡፡ ሌላውማ ይሰቀላል፡፡ ከራሱም በራሪ (አሞራ) ትበላለች፡፡ ያ ፍቹን የምትጠይቁት ነገር ተፈጸመ፤» (አላቸው)፡፡ 12|42|ለዚያም ከሁለቱ እርሱ የሚድን መሆኑን ለተጠራጠረው እጌታህ ዘንድ አስታውሰኝ አለው፡፡ ጌታውንም ከማስታወስ ሰይጣን አስረሳው፡፡ ለጥቂት ዓመታትም በወህኒ ቤቱ ውስጥ ቆየ፡፡ 12|43|ንጉሡም «እኔ ሰባትን የሰቡ ላሞች ሰባት ከሲታዎች ሲበሏቸው ሰባትንም ለምለም ዘለላዎች ሌሎችንም ደረቆችን (ሲጠመጠሙባቸው በሕልሜ) አያለሁ፡፡ እናንተ ታላላቅ ሰዎች ሆይ! ሕልምን የምትፈቱ እንደሆናችሁ ሕልሜን ፍቱልኝ» አላቸው፡፡ 12|44|«የሕልሞች ቅዠቶች ናቸው፡፡ እኛም የሕልሞችን ፍች ዐዋቂዎች አይደለንም» አሉት፡፡ 12|45|ያም ከሁለቱ የዳነውና ከብዙ ጊዜ በኋላ (ዩሱፍን) ያስታወሰው ሰው «እኔ ፍቹን እነግራችኋለሁና ላኩኝ» አለ፤ (ወደ ዩሱፍ ሌደም)፡፡ 12|46|«አንተ እውነተኛው ዩሱፍ ሆይ! ሰባትን የሰቡ ላሞች ሰባት ከሲታዎች ላሞች ሲበሉዋቸው ሰባትን ለምለም ዘለላዎችም ሌሎችንም ደረቆች (በነሱ ላይ ሲጠመጠሙባቸው ያየን ሰው ሕልም ፍች) ተችልን፡፡ ያውቁ ዘንድ ወደ ሰዎቹ ልመለስ እከጅላለሁና» (አለው)፡፡ 12|47|(እርሱም) አለ፡- «ሰባትን የተከታተሉ ዓመታት ትዘራላችሁ፡፡ ያጨዳችሁትንም ሁሉ ከምትበሉት ጥቂት በስተቀር በዘለላው ውስጥ ተዉት፡፡ 12|48|«ከዚያም ከእነዚያ በኋላ ካደለባችሁት ጥቂት ሲቀር ለእነሱ ያደለባችሁትን ሁሉ የሚበሉ ሰባት የችግር ዓመታት ይመጣሉ፡፡ 12|49|«ከዚያም ከእነዚያ በኋላ ሰዎቹ በርሱ የሚዘነቡበት በርሱም (ወይንን) የሚጨምቁበት ዓመት ይመጣል፡፡» 12|50|ንጉሡም «እርሱን አምጡልኝ» አለ፡፡ መልክተኛውም (ዩሱፍን) በመጣው ጊዜ «ወደጌታህ ተመለስ፡፡ የዚያንም እጆቻቸውን የቆረጡትን ሴቶች ሁኔታ ጠይቀው፡፡ ጌታዬ ተንኮላቸውን ዐዋቂ ነውና» አለው፡፡ 12|51|(ንጉሡም)፡- «ዩሱፍን ከነፍሱ ባባበላችሁት ጊዜ ነገራችሁ ምንድን ነው» አላቸው፡፡ «ለአላህ ጥራት ይገባው፡፡ በእርሱ ላይ ምንም መጥፎን ነገር አላወቅንም» አሉት፡፡ የዐዚዝ ሚስት፡-«አሁን እውነቱ ተገለጸ፡፡ እኔ ከነፍሱ አባበልኩት፡፡ እርሱም ከእውነተኞቹ ነው» አለች፡፡ 12|52|(ዩሱፍ) «ይህ (ጌታዬ) ሩቅ ሆኖ ሳለ ያልከዳሁት መሆኔን አላህም የከዳተኞችን ተንኮል የማያቃና መሆኑን እንዲያውቅ ነው፤» (አለ)፡፡ 12|53|«ነፍሴንም (ከስሕተት) አላጠራም፡፡ ነፍስ ሁሉ ጌታዬ የጠበቃት ካልሆነች በስተቀር በመጥፎ ነገር በእርግጥ አዛዥ ናትና፡፡ ጌታዬ በጣም መሓሪ አዛኝ ነው» (አለ)፡፡ 12|54|ንጉሡም «እርሱን አምጡልኝ ለራሴ ግለኛ አደርገዋለሁና» አለ፡፡ ባናገረውም ጊዜ «አንተ ዛሬ እኛ ዘንድ ባለሟል ታማኝ ነህ» አለው፡፡ 12|55|«በምድር ግምጃ ቤቶች ላይ (ሹም) አድርገኝ፡፡ እኔ ጠባቂ አዋቂ ነኝና» አለ፡፡ 12|56|እንደዚሁም ለዩሱፍ በምድር ላይ ከእርሷ በፈለገው ስፍራ የሚሰፍር ሲሆን አስመቸነው፡፡ በችሮታችን የምንሻውን ሰው እንለያለን፡፡ የበጎ ሠሪዎችንም ዋጋ አናጠፋም፡፡ 12|57|የመጨረሻይቱም ዓለም ምንዳ ለእነዚያ ላመኑትና ይጠነቀቁ ለነበሩት የበለጠ ነው፡፡ 12|58|የዩሱፍ ወንድሞችም መጡ፡፡ በእርሱም ላይ ገቡ፡፡ እነሱም እርሱን የሳቱት ሲሆኑ ዐወቃቸው፡፡ 12|59|(ጉዳያቸውን ፈጽሞ) ስንቃቸውንም ባዘጋጀላቸው ጊዜ አለ፡- «ከአባታችሁ በኩል የሆነውን ወንድማችሁን አምጡልኝ፡፡ እኔ ከአስተናጋጆች ሁሉ በላጭ ስሆን፤ ስፍርን የምሞላ መሆኔን አታዩምን 12|60|እርሱንም ባታመጡልኝ እኔ ዘንድ ለእናንተ ስፍር የላችሁም፤ አትቀርቡኝምም፡፡» 12|61|«ስለእርሱ አባቱን በጥብቅ እንጠይቃለን፡፡ እኛም (ይህንን) በእርግጥ ሠሪዎች ነን» አሉት፡፡ 12|62|ለአሽከሮቹም «ሸቀጣቸውን ወደ ቤተሰቦቻቸው በተመለሱ ጊዜ ያውቋት ዘንድ በየጓዞቻቸው ውስጥ አድርጉላቸው፡፡ ሊመለሱ ይከጀላልና» አላቸው፡፡ 12|63|ወደ አባታቸውም በተመሰሉ ጊዜ፡- «አባታችን ሆይ! (ወንድማችንን እስከምንወስድ) ስፍር ከእኛ ተከልክሏል፡፡ ስለዚህ ወንድማችንን ከእኛ ጋር ላከው፡፡ ይሰፍርልናልና እኛም ለርሱ ጠባቂዎች ነን» አሉ፡፡ 12|64|«ከአሁን በፊት በወንድሙ ላይ እንዳመንኳችሁ እንጂ በእርሱ ላይ አምናችኋለሁን አላህም በጠባቂነት (ከሁሉ) የበለጠ ነው፡፡ እርሱም ከአዛኞች ሁሉ ይበልጥ አዛኝ ነው፤» አላቸው፡፡ 12|65|ዕቃቸውንም በከፈቱ ጊዜ ሸቀጣቸው ወደእነርሱ ተመልሳ አገኙ፡፡ ፡-«አባታችን ሆይ! ምን እንፈልጋለን ይህቺ ሸቀጣችን ናት፡፡ ወደኛ ተመልሳልናለች፤ (እንረዳባታለን)፡፡ ለቤተሰቦቻችንም እንሸምታለን፡፡ ወንድማችንንም እንጠብቃለን፡፡ የግመልንም ጭነት እንጨምራለን፡፡ ይህ (በንጉሡ ላይ) ቀላል ስፍር ነው» አሉ፡፡ 12|66|«ካልተከበባችሁ በስተቀር እርሱን በእርግጥ የምታመጡልኝ ለመሆናችሁ ከአላህ የሆነን ቃል ኪዳን መተማመኛ እስከምትሰጡኝ ድረስ ከእናንተ ጋር ፈጽሞ አልልከውም» አላቸው፡፡ መተማመኛቸውንም በሰጡት ጊዜ «አላህ በምንለው ሁሉ ላይ ምስክር ነው» አላቸው፡፡ 12|67|አለም «ልጆቼ ሆይ! በአንድ በር አትግቡ፡፡ ግን በተለዩ በሮች ግቡ፡፡ ከአላህም (ፍርድ) በምንም አልጠቅማችሁም፤ (አልመልስላችሁም)፡፡ ፍርዱ የአላህ እንጅ የሌላ አይደለም፡፡ በእርሱ ላይ ተመካሁ፡፡ ተመኪዎችም ሁሉ በእርሱ ብቻ ይመኩ፡፡» 12|68|አባታቸውም ካዘዛቸው ስፍራ በገቡ ጊዜ ከአላህ (ፍርድ) ምንም ነገር ከነርሱ የሚከለክልላቸው አልነበረም፡፡ ግን በያዕቆብም ነፍስ ውስጥ የነበረች ጉዳይ ናት፡፡ ፈጸማት፡፡ እርሱም ስላሳወቅነው የዕውቀት ባለቤት ነው፤ ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 12|69|በዩሱፍ ላይ በገቡ ጊዜም ወንድሙን ወደርሱ አስጠጋው፡፡ «እነሆ እኔ ወንድምህ ነኝ፡፡ ይሠሩት በነበሩትም ሁሉ አትቆላጭ» አለው፡፡ 12|70|ዕቃቸውንም ባዘጋጀላቸው ጊዜ፤ ዋንጫይቱን በወንድሙ ዕቃ ውስጥ አደረገ፡፡ ከዚያም «እናንተ ባለ ግመሎች ሆይ! እናንተ በእርግጥ ሌቦች ናችሁ ሲል ጠሪ ተጣራ፡፡» 12|71|ወደነሱ ዞረውም «ምንድን ጠፋችሁ» አሉ፡፡ 12|72|«የንጉሡ መስፈሪያ ጠፍቶናል፡፡ እርሱንም ላመጣ ሰው የግመል ጭነት አለው፡፡ እኔም በእርሱ ተያዥ ነኝ» አለ፡፡ 12|73|«በአላህ እንምላለን በምድር ላይ ለማጥፋት እንዳልመጣን በእርግጥ ዐውቃችኋል፡፡ ሌቦችም አልነበርንም» አሉ፡፡ 12|74|«ውሸታሞች ብትሆኑ ቅጣቱ ምንድን ነው» አሏቸው፡፡ 12|75|«ቅጣቱ (በያዕቆብ ሕግ) ዕቃው በጓዙ ውስጥ የተገኘበት ሰው (ራሱ መወሰድ) ነው፡፡ እርሱም ቅጣቱ ነው፡፡ እንደዚሁ በደለኞችን እንቀጣለን» አሉ፡፡ 12|76|(ምርመራውን) ከወንድሙም ዕቃ በፊት በዕቃዎቻቸው ጀመረ፡፡ ከዚያም (ዋንጫይቱን) ከወንድሙ ዕቃ ውስጥ አወጣት፡፡ እንደዚሁ ለዩሱፍ ብልሃትን አስተማርነው፡፡ አላህ ባልሻ ኖሮ በንጉሡ ሕግ ወንድሙን ሊይዝ አይገባውም ነበር፡፡ የምንሻውን ሰው በደረጃዎች ከፍ እናደርጋለን፡፡ ከዕውቀት ባለቤቶች ሁሉ በላይም ዐዋቂ አልለ፡፡ 12|77|«ቢሰርቅ ከአሁን በፊት የርሱው ወንድም በእርግጥ ሰርቋል» አሉ፡፡ ዩሱፍም (ይህችን ንግግር) በነፍሱ ውስጥ ደበቃት፡፡ ለእነሱም አልገለጣትም፡፡ (በልቡ) «እናንተ ሥራችሁ የከፋ ነው፡፡ አላህም የምትሉትን ሁሉ ይበልጥ ዐዋቂ ነው» አለ፡፡ 12|78|አንተ የተከበርከው ሆይ! «ለእርሱ በእርግጥ ታላቅ ሽማግሌ አባት አለው፡፡ ስለዚህ በእርሱ ስፍራ አንደኛችንን ያዝ፡፡ እኛ ከመልካም ሠሪዎች ሆነህ እናይሃለንና» አሉት፡፡ 12|79|«ዕቃችንን እርሱ ዘንድ ያገኘንበትን ሰው እንጂ ሌላን ከመያዝ በአላህ እንጠብቃለን፡፡ እኛ ያን ጊዜ በእርግጥ በዳዮች ነን» አለ፡፡ 12|80|ከርሱም ተስፋን በቆረጡ ጊዜ የሚመካከሩ ሆነው ገለል አሉ፡፡ ታላቃቸው አለ «አባታቸሁ በናንተ ላይ ከአላህ የሆነን መታመኛ ኪዳን በእርግጥ የያዘባችሁ መሆኑን ከዚህም በፊት በዩሱፍ ላይ ግፍ የሠራችሁትን አታውቁምን ስለዚህ አባቴ ለእኔ እስከሚፈቅድልኝ ወይም አላህ ለኔ እስከሚፈርድልኝ ድረስ የምስርን ምድር አልለይም፡፡ እርሱም ከፈራጆች ሁሉ በላጭ ነው፡፡ 12|81|«ወደ አባታችሁ ተመለሱ በሉትም፡- አባታችን ሆይ! ልጅህ ሰረቀ፡፡ ባወቅነውም ነገር እንጂ አልመሰከርንም፡፡ ሩቁንም ነገር (ምስጢሩን) ዐዋቂዎች አልነበርንም፡፡ 12|82|«ያችንም በውስጧ የነበርንባትን ከተማ ያችንም በውስጧ የመጣነውን ባለ ግመል ጓድ ጠይቅ፡፡ እኛም በእርግጥ እውነተኞች ነን፡፡» 12|83|(ያዕቆብ) «አይደለም ነፍሶቻችሁ አንዳች ነገርን ለእናንተ ሸለሙላችሁ፡፡ (ሠራችሁትም)፡፡ መልካምም ትእግስት (ማድረግ) አለብኝ፡፡ እነርሱን (ሦስቱንም) የተሰበሰቡ ሆነው አላህ ሊያመጣልኝ ይከጀላል፡፡ እነሆ እርሱ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና» አላቸው፡፡ 12|84|ከእነሱም ዘወር አለናኣ«በዩሱፍ ላይ ዋ ሐዘኔ!» አለ፡፡ ዓይኖቹም ከሐዘን (ለቅሶ) የተነሳ ነጡ፡፡ እርሱም በትካዜ የተመላ ነው፡፡ 12|85|(እነርሱም) «በአላህ እንምላለን፡፡ ለጥፋት የቀረብክ እስከምትሆን ወይም ከጠፊዎቹ እስከምትሆን ድረስ ዩሱፍን ከማውሳት አትወገድም» አሉ፡፡ 12|86|«ጭንቀቴንና ሐዘኔንና የማሰሙተው ወደ አላህ ብቻ ነው፡፡ ከአላህም በኩል የማታውቁትን ነገር ዐውቃለሁ» አላቸው፡፡ 12|87|«ልጆቼ ሆይ! ሊዱ፤ ከዩሱፍና ከወንድሙም (ወሬ) ተመራመሩ፡፡ ከአላህም እዝነት ተስፋ አትቁረጡ፡፡ እነሆ ከአላህ እዝነት ከሓዲዎች ሕዝቦች እንጂ ተስፋ አይቆርጥም» (አለ)፡፡ 12|88|በእርሱም ላይ በገቡ ጊዜ «አንተ የተከበርከው ሆይ! እኛንም ቤተሰቦቻችንንም ጉዳት ደረሰብን፡፡ ርካሽ ሸቀጥም ይዘን መጥተናል፡፡ ስፍርንም ለኛ ሙላልን፡፡ በኛም ላይ መጽውት አላህ መጽዋቾችን ይመነዳልና» አሉት፡፡ 12|89|«እናንተ የማታውቁ በነበራችሁ ጊዜ በዩሱፍና በወንድሙ ላይ የሰራችሁትን ግፍ ዐወቃችሁን» አላቸው፡፡ 12|90|«አንተ በእርግጥ አንተ ዩሱፍ ነህን» አሉት፡፡ «እኔ ዩሱፍ ነኝ፡፡ ይህም ወንድሜ ነው፡፡ አላህ በኛ ላይ በእርግጥ ለገሰልን፡፡ እነሆ! የሚጠነቀቅና የሚታገስ ሰው (አላህ ይክሰዋል)፡፡ አላህ የበጎ አድራጊዎችን ዋጋ አያጠፋምና» አለ፡፡ 12|91|«በአላህ እንምላለን፡፡ አላህ በኛ ላይ በእርግጥ አበለጠህ፡፡ እኛም በእርግጥ አጥፊዎች ነበርን» አሉ፡፡ 12|92|«ዛሬ በናንተ ላይ ወቀሳ የለባችሁም፡፡ አላህ ለእናንተ ይምራል፡፡ እርሱም ከአዛኞች ሁሉ ይበልጥ አዛኝ ነው» አላቸው፡፤ 12|93|«ይህንን ቀሚሴን ይዛችሁ ሊዱ፡፡ በአባቴ ፊትም ጣሉት የሚያይ ሆኖ ይመጣልና፡፡ ቤተሰቦቻችሁንም ሰብስባችሁ አምጡልኝ» (አላቸው)፡፡ 12|94|ግመል ጫኞቹም (ምስርን) በተለዩ ጊዜ አባታቸው «እኔ የዩሱፍን ሽታ በእርግጥ አገኛለሁ፡፡ ባታቄሉኝ ኖሮ (ታምኑኝ ነበር)» አለ፡፡ 12|95|«በአላህ እንምላለን፡፡ አንተ በእርግጥ በቀድሞው ስህተትህ ውስጥ ነህ» አሉት፡፡ 12|96|አብሳሪውም በመጣ ጊዜ (ቀሚሱን) በፊቱ ላይ ጣለው፡፡ ወዲውም የሚያይ ኾነ፡፡ «እኔ ለእናንተ፡- ከአላህ በኩል የማታውቁትን ዐውቃለሁ አላልኳችሁምን» አላቸው፡፡ 12|97|«አባታችን ሆይ! ለኀጢአቶቻችን ምሕረትን ለምንልን እኛ ጥፋተኞች ነበርንና» አሉ፡፡ 12|98|«ወደፊት ለእናንተ ጌታዬን ምሕረትን እለምንላችኋለሁ፡፡ እነሆ! እርሱ መሓሪው አዛኙ ነውና» አላቸው፡፤ 12|99|በዩሱፍ ላይም በገቡ ጊዜ ወላጆቹን ወደርሱ አስጠጋቸው፡፡ «በአላህም ፈቃድ ጥብቆች ስትኾኑ ምስርን ግቡ» አላቸው፡፡ 12|100|ወላጆቹንም በዙፋኑ ላይ አወጣቸው፡፡ ለእርሱም ሰጋጆች ኾነው ወረዱለት፡፡ «አባቴም ሆይ! ይህ ፊት ያየኋት ሕልሜ ፍች ነው፡፡ ጌታ በእርግጥ እውነት አደረጋት፡፡ ከወህኒ ቤትም ባወጣኝና ሰይጣንም በእኔና በወንድሞቼ መካከል ከአበላሸ በኋላ እናንተን ከገጠር ባመጣችሁ ጊዜ በእርግጥ ለኔ መልካም ዋለልኝ፡፡ ጌታዬ ለሚሻው ነገር እዝነቱ ረቂቅ ነው፡፡ እነሆ እሱ ዐዋቂው ጥበበኛው ነው» አለ፡፡ 12|101|«ጌታዬ ሆይ! ከንግሥና በእርግጥ ሰጠኸኝ፡፡ ከሕልሞችም ፍች አስተማርከኝ፡፡ የሰማያትና የምድር ፈጣሪ ሆይ! አንተ በቅርቢቱና በመጨረሻይቱ ዓለም ረዳቴ ነህ፡፡ ሙስሊም ሆኘ ግደለኝ፡፡ በመልካሞቹም አስጠጋኝ» (አለ)፡፡ 12|102|(ሙሐመድ ሆይ) ይህ ወዳንተ የምናወርደው ሲኾን፤ ከሩቅ ወሬዎች ነው፡፡ አንተም እነርሱ (በዩሱፍ) የሚመክሩ ኾነው ነገራቸውን በቆረጡ ጊዜ እነሱ ዘንድ አልነበርክም፡፡ 12|103|አብዛኛዎቹም ሰዎች (ለማመናቸው) ብትጓጓም የሚያምኑ አይደሉም፡፡ 12|104|በእርሱም (በቁርአን) ላይ ምንም ዋጋ አትጠይቃቸውም፡፡ እርሱ ለዓለማት ግሳጼ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ 12|105|በሰማያትና በምድርም ካለችው ምልክት ብዙይቱ እነሱ ከርሷ ዘንጊዎች ኾነው በርሷ ላይ ያልፋሉ፡፡ 12|106|አብዛኞቻቸውም፤ እነሱ አጋሪዎች ኾነው እንጂ በአላህ አያምኑም፡፡ 12|107|ከአላህ ቅጣት ሸፋኝ አደጋ የምትመጣባቸው ወይም ሰዓቲቱ እነሱ የማያውቁ ሲኾኑ በድንገት የምትመጣባቸው መኾኑዋን አይፈሩምን 12|108|«ይህች መንገዴ ናት፡፡ ወደ አላህ እጠራለሁ፡፡ እኔም የተከተለኝም ሰው በግልጽ ማስረጃ ላይ ነን፡፡ ጥራትም ለአላህ ይገባው፡፡ እኔም ከአጋሪዎቹ አይደለሁም» በል፡፡ 12|109|ካንተ በፊትም ከከተሞች ሰዎች ወደነርሱ ራእይ የምናወርድላቸው የኾኑን ወንዶችን እንጂ አልላክንም፡፡ በምድር ላይ አይኼዱምና የእነዚያን ከእነሱ በፊት የነበሩትን ሰዎች መጨረሻ አይመለከቱምን የመጨረሻይቱም አገር ለእነዚያ ለተጠነቀቁት በእርግጥ የተሻለች ናት፤ አታውቁምን 12|110|መልክተኞቹም ተስፋ በቆረጡና እነርሱ በእርግጥ የተዋሹ መኾናቸውን በተጠራጠሩ ጊዜ እርዳታችን መጣላቸው፡፡ (እኛ) የምንሻውም ሰው እንዲድን ተደረገ፡፡ ቅጣታችንም ከአጋሪዎቹ ሕዝቦች ላይ አይመለስም፡፡ 12|111|በታሪካቸው ውስጥ ለአእምሮ ባለ ቤቶች በእርግጥ መገሰጫ ነበረ፡፡ (ይህ ቁርኣን) የሚቀጣጠፍ ወሬ አይደለም፡፡ ግን ያንን በስተፊቱ ያለውን አረጋጋጭ ለነገርም ሁሉ ገላጭ ለሚያምኑ ሕዝቦችም መሪና ችሮታ ነው፡፡ 13|1|አ.ለ.መ.ረ (አሊፍ ላም ሚም ራ) ይህች (አናቅጽ) ከመጽሐፉ አንቀጾች ናት፡፡ ያም ከጌታህ ወዳንተ የተወረደው እውነት ነው፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያምኑም፡፡ 13|2|አላህ ያ ሰማያትን የምታዩዋት አዕማድ ሳትኖር ያነሳት ከዚያም በዐርሹ (ዙፋኑ) ላይ (ስልጣኑ) የተደላደለ ፀሐይንና ጨረቃንም የገራ ነው፡፡ ሁሉም ለተወሰነ ጊዜ ይሮጣሉ፡፡ ነገሩን ሁሉ ያስተናብራል፡፡ በጌታችሁ መገናኘት ታረጋግጡ ዘንድ ተዓምራቶችን ይዘረዝራል፡፡ 13|3|እርሱም ያ ምድርን የዘረጋ በሷም ተራራዎችንና ወንዞችን ያደረገ በውስጧም ከፍሬዎች ሁሉ ሁለት ሁለት ዓይነቶችን ያደረገ ነው፡፡ ሌሊትን በቀን ይሸፍናል፡፡ በዚህም ውስጥ ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች ምልክቶች አሉ፡፡ 13|4|በምድርም የተጎራበቱ ቁርጥራጮች አልሉ፡፡ ከወይኖችም አትክልቶች አዝርዕቶችም መንታዎችና መንታዎች ያልኾኑ ዘንባባዎችም አልሉ፡፡ በአንድ ውሃ ይጠጣሉ፤ (በጣዕምም ይለያያሉ)፡፡ ከፊሉዋንም በከፊሉ ላይ በሚበላው ሰብል እናበልጣለን፡፡ በዚህም ውስጥ ለሚያውቁ ሕዝቦች ተዓምራት አለበት፡፡ 13|5|ብትደነቅም ዐፈር በኾንን ጊዜ እና አዲስ ፍጥረት እንኾናለን ማለታቸው (ታላቅ) ድንቅ ነው፡፡ እነዚህ እነዚያ በጌታቸው የካዱት ናቸው፡፡ እነዚህም እንዛዝላዎች በአንገቶቻቸው ላይ ያሉባቸው ናቸው፡፡ እነዚሀም የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነሱ በውስጧ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 13|6|ከእነሱ በፊት የመሰሎቻቸው ቅጣቶች በእርግጥ ያለፉ ሲኾኑ ከመልካሙ በፊት በመጥፎው ያስቸኩሉሃል፡፡ ጌታህም ለሰዎች ከመበደላቸው ጋር በእርግጥ የምህረት ባለቤት ነው፡፡ ጌታህም በእርግጥ ቅጣተ ብርቱ ነው፡፡ 13|7|እነዚያም የካዱት በእርሱ ላይ ከጌታው ተዓምር ለምን አልተወረደለትም ይላሉ፡፡ አንተ አስፈራሪ ብቻ ነህ፡፡ ለሕዝብም ሁሉ መሪ አላቸው፡፡ 13|8|አላህ ሴት ሁሉ የምታረግዘውን ያውቃል፡፡ ማሕጸኖችም የሚያጎድሉትን የሚጨምሩትንም (ያውቃል)፡፡ ነገሩም ሁሉ እርሱ ዘንድ በልክ የተወሰነ ነው፡፤ 13|9|ሩቁንና ቅርቡን ዐዋቂ ታላቅ የላቀ ነው፡፡ 13|10|ከእናንተ ውስጥ ቃሉን ዝቅ ያደረገ ሰው በእርሱ የጮኸም ሰው እርሱ በሌሊት ተደባቂም በቀን (ተገልጾ) ኺያጅም የኾነ ሰው (እርሱ ዘንድ) እኩል ነው፡፡ 13|11|ለእርሱ (ለሰው) ከስተፊቱም ከኋላውም በአላህ ትዕዛዝ (ከክፉ) የሚጠብቁት ተተካኪዎች (መላእክት) አሉት፡፡ አላህ በሕዝቦች ዘንድ ያለውን ጸጋ በነፍሶቻቸው ያለውን (ኹኔታ) እስከሚለውጡ ድረስ አይለውጥም፡፡ አላህም በሰዎች ላይ ክፉን በሻ ጊዜ ለእርሱ መመለስ የለውም፡፡ ለእነርሱም ከእርሱ ሌላ ምንም ተከላካይ የላቸውም፡፡ 13|12|እርሱ ያ የምትፈሩና የምትከጅሉም ስትሆኑ ብልጭታን የሚያሳያችሁ ከባዶች ደመናዎችንም የሚያስገኝ ነው፡፡ 13|13|ነጎድጓድም አላህን በማመስገን ያጠራል፡፡ መላእክትም እርሱን ለመፍራት (ያጠሩታል)፡፡ መብረቆችንም ይልካል፡፡ እነርሱም (ከሓዲዎች) በአላህ የሚከራከሩ ሲሆኑ በእርሷ የሚሻውን ሰው ይመታል፡፡ እርሱም ኀይለ ብርቱ ነው፡፡ 13|14|ለእርሱ (ለአላህ) የእውነት መጥሪያ አለው፡፡ እነዚያም ከእርሱ ሌላ የሚገዙዋቸው (ጣዖታት) ወደ አፉ ይደርስ ዘንድ ወደ ውሃ መዳፎቹን (በሩቅ ሆኖ) እንደሚዘረጋ (ሰው መልስ) እንጂ ለነርሱ በምንም አይመልሱላቸውም፡፡ እርሱም ወደ አፉ ደራሽ አይደለም፡፡ የከሓዲዎችም ጥሪ በከንቱ እንጂ አይደለም፡፡ 13|15|በሰማያትና በምድርም ያሉት ሁሉ በውድም ሆነ በግድ ለአላህ ይሰግዳሉ፡ ጥላዎቻቸውም በጧቶችና በሠርኮች ይሰግዳሉ፡፡ 13|16|«የሰማያትና የምድር ጌታ ማን ነው» በላቸው፡፡ «አላህ ነው» በል፡፡ «ለነፍሶቻቸው ጥቅምንም ጉዳትንም የማይችሉን ረዳቶች ከርሱ ሌላ ያዛችሁን» በላቸው፡፡ «ዕውርና የሚያይ ይስተካከላሉን ወይስ ጨለማዎችና ብርሃን ይስተካከላሉን ወይስ ለአላህ እንደርሱ አፈጣጠር የፈጠሩን ተጋሪዎች አደረጉለትና ፍጥረቱ በእነሱ ላይ ተመሳሰለባቸውን» በል፤ «አላህ ሁለመናውን ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱም አንዱ አሸናፊው ነው» በል፡፡ 13|17|ከሰማይ ውሃን አወረደ፡፡ ሸለቆዎቹም በመጠናቸው ፈሰሱ፡፡ ጎርፉም አሰፋፊውን ኮረፋት ተሸከመ፡፡ ለጌጥ ወይም ለዕቃ ፍላጎት በእርሱ ላይ እሳት የሚያነዱበትም (ማዕድን) ብጤው የኾነ ኮረፋት አልለው፡፡ እንደዚሁ አላህ ለእውነትና ለውሸት ምሳሌን ያደርጋል፡፡ ኮረፋቱማ ግብስብስ ኾኖ ይጠፋል፡፡ ለሰዎች የሚጠቅመውማ በምድር ላይ ይቆያል፡፡ እንደዚሁ አላህ ምሳሌዎችን ይገልፃል፡፡ 13|18|ለእነዚያ ለጌታቸው ለታዘዙት መልካም ነገር (ገነት) አልላቸው፡፡ እነዚያም ለእርሱ ያልታዘዙት ለእነሱ በምድር ያለው ሁሉ ከእርሱም ጋር ብጤው ቢኖራቸው ኖሮ በእርሱ በተበዡበት ነበር፡፡ እነዚያ ለእነሱ ክፉ ምርመራ አለባቸው፡፡ መኖሪያቸውም ገሀነም ናት፡፡ ፍራሻቸውም ከፋች! 13|19|ከጌታህ ወዳንተ የተወረደው እውነት መኾኑን የሚያውቅ ሰው እንደዚያ እርሱ ዕውር እንደኾነው ሰው ነውን የሚገሠጹት የአእምሮ ባለቤቶች ብቻ ናቸው፡፡ 13|20|እነዚያ በአላህ ቃል ኪዳን የሚሞሉ የጠበቀውንም ኪዳን የማያፈርሱ ናቸው፡፡ 13|21|እነዚያም አላህ እንዲቀጠል በእርሱ ያዘዘውን ነገር የሚቀጥሉ ጌታቸውንም የሚያከብሩ መጥፎንም ቁጥጥር የሚፈሩ ናቸው፡፡ 13|22|እነዚያም የጌታቸውን ውዴታ ለመፈለግ የታገሱ፣ ሶላትንም አዘውትረው የሰገዱ፣ እኛ ከሰጠናቸው ሲሳይም በምስጢርም ኾነ በግልጽ የመጸወቱ፣ ክፉውንም ነገር በበጎ የሚገፈትሩ ናቸው፡፡ እነዚያ ለእነሱ መጨረሻይቱ ምስጉን አገር አለቻቸው፡፡ 13|23|(እርሷም) የመኖሪያ ገነቶች ናት፡፡ ይገቡባታል፡፡ ከአባቶቻቸውም፣ ከሚስቶቻቸውም፣ ከዝርያቸውም መልካም የሠራ ሰው (ይገባታል)፡፡ መላእክትም በእነርሱ ላይ ከየደጃፉ ሁሉ ይገባሉ፡፡ 13|24|«ሰላም ለእናንተ ይኹን፡፡ (ይህ ምንዳ) በመታገሳችሁ ነው፡፡ የመጨረሻይቱም አገር ምን ታምር!» (ይሏቸዋል)፡፡ 13|25|እነዚያም የአላህን ቃል ኪዳን ከጠበቀ በኋላ የሚያፈርሱ አላህም እንዲቀጠል በእርሱ ያዘዘውን ነገር የሚቆርጡ በምድርም ላይ የሚያበላሹ እነዚያ ለነሱ እርግማን አለባቸው፡፡ ለእነሱም መጥፎ አገር (ገሀነም) አላቸው፡፡ 13|26|አላህ ለሚሻው ሰው ሲሳይን ያሰፋል፤ ያጠባልም፡፡ (ከሓዲዎች) በቅርቢቱም ሕይወት ተደሰቱ፡፡ የቅርቢቱም ሕይወት በመጨረሻይቱ አንጻር (ትንሽ) መጠቀሚያ እንጂ ምንም አይደለችም፡፡ 13|27|እነዚያም የካዱት «በእርሱ ላይ ከጌታው ተዓምር ለምን አልተወረደም» ይላሉ፡፡ «አላህ የሚሻውን ያጠምማል፡፡ የተመለሰውንም ሰው ወደርሱ ይመራል» በላቸው፡፡ 13|28|(እነሱም) እነዚያ ያመኑ ልቦቻቸውም አላህን በማውሳት የሚረኩ ናቸው፡፡ ንቁ! አላህን በማውሳት ልቦች ይረካሉ፡፡ 13|29|እነዚያ ያመኑትና መልካም ሥራዎችን የሠሩት ለእነሱ ደግ ኑሮ መልካም መመለሻም አላቸው፡፡ 13|30|እንደዚሁ ከበፊትዋ ብዙ ሕዝቦች በእርግጥ ያለፉ ወደኾነችው ሕዝብ እነርሱ በአልረሕማን የሚክዱ ሲኾኑ ያንን ወደ አንተ ያወረድነውን ቁርኣን በእነርሱ ላይ ታነብላቸው ዘንድ ላክንህ፡፡ «እርሱ (አልረሕማን) ጌታዬ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ በርሱ ላይ ተጠጋሁ፡፡ መመለሻየም ወደርሱ ብቻ ነው» በላቸው፡፡ 13|31|ቁርኣንም በእርሱ ተራራዎች በተነዱበት ወይም በእርሱ ምድር በተቆራረጠችበት ወይም በእርሱ ሙታን እንዲናገሩ በተደረጉበት ኖሮ (የመካ ከሓዲዎች ባላመኑ ነበር)፡፡ በእውነቱ ነገሩ ሁሉ የአላህ ነው፡፡ እነዚያ ያመኑት ሰዎች እነሆ አላህ በሻ ኖሮ ሰዎችን በመላ በእርግጥ ይመራቸው እንደነበረ አያውቁምን እነዚያም የካዱት በሥራቸው ምክንያት (አጥፊ) ዐደጋ የምታገኛቸው ከመኾን ወይም የአላህ ቀጠሮ እስኪመጣ በአገራቸው አቅራቢያ (አንተ) የምትሰፍርባቸው ከመኾን አይወገዱም፡፡ አላህ ቀጠሮውን አያፈርስምና፡፡ 13|32|ከአንተ በፊት በነበሩትም መልክተኞች በእርግጥ ተላግጦባቸዋል፡፡ ለእነዚያም ለካዱት ጊዜን ሰጠኋቸው፡፡ ከዚያም (በቅጣት) ያዝኩዋቸው፡፡ ቅጣቴም እንዴት ነበር! 13|33|እርሱ በነፍስ ሁሉ ላይ በሠራቸው ሥራ ተጠባባቂ የኾነው (አላህ እንደዚህ እንዳልኾነው ጣዖት ብጤ ነውን) ለአላህም ተጋሪዎችን አደረጉ፡፡ ጥሯቸው «አላህን በምድር ውስጥ የማያውቀው ኖሮ ትነግሩታላችሁን ወይስ ከቃል በግልጽ (ፍቺ በሌለው ከንቱ ቃል ተጋሪዎች በማለት ትጠሩዋቸዋላችሁን)» በላቸው፡፡ በእውነቱ ለእነዚያ ለካዱት ተንኮላቸው ተሸለመላቸው፡፡ ከእውነቱ መንገድም ታገዱ፡፡ አላህም ያጠመመው ሰው ለእርሱ ምንም አቅኚ የለውም፡፡ 13|34|ለእነሱ በቅርቢቱ ሕይወት ቅጣት አላቸው፡፡ የመጨረሻይቱም (ዓለም) ቅጣት በጣም የበረታ ነው፡፡ ለእነሱም ከአላህ (ቅጣት) ምንም ጠባቂ የላቸውም፡፡ 13|35|ያች ጥንቁቆቹ ተስፋ የተሰጧት ገነት ምጣኔዋ (እንደሚነገራችሁ ነው)፡፡ ከሥርዋ ወንዞች ይፈስሳሉ፡፡ ምግቧ (ሁልጊዜ) የማይቋረጥ፤ ነው፡፡ ጥላዋም (እንደዚሁ)፡፡ ይህች የእነዚያ የተጠነቀቁት መጨረሻ ናት፡፡ የከሃዲዎችም መጨረሻ እሳት ናት፡፡ 13|36|እነዚያም መጽሐፉን የሰጠናቸው ወዳንተ በተወረደው ይደሰታሉ፡፡ ከአሕዛብም ከፊሉን የሚክዱ ሰዎች አልሉ፡፡ «እኔ የታዘዝኩት አላህን ብቻ እንድገዛ በእርሱም እንደዳላጋራ ነው፡፡ ወደእርሱ እጠራለሁ፤ መመለሻዬም ወደእርሱ ነው» በላቸው፡፡ 13|37|እንደዚሁ በዐረብኛ የተነገረ ፍትሕ ሲኾን አወረድነው፡፡ ዕውቀቱ ከመጣልህም በኋላ ዝንባሌዎቻቸውን ብትከተል ከአላህ ቅጣት ምንም ረዳትም ጠባቂም የለህም፡፡ 13|38|ከአንተ በፊትም መልክተኞችን በእርግጥ ልከናል፡፡ ለእነርሱም ሚስቶችንና ልጆችን አድርገናል፡፡ ለማንኛውም መልክተኛ በአላህ ፈቃድ እንጂ ተዓምር ሊያመጣ አይገባውም፡፡ ለጊዜው ሁሉ ጽሑፍ አለው፡፡ 13|39|አላህ የሚሻውን ያብሳል፤ ያጸድቃልም፡፡ የመጽሐፉ መሠረትም እርሱ ዘንድ ነው፡፡ 13|40|የዚያንም ያስፈራራናቸውን ከፊሉን ብናሳይህ (መልካም ነው)፡፡ ወይም ብንገድልህ (ወቀሳ የለብህም)፡፡ በአንተ ላይ ያለብህ ማድረስ ብቻ ነው፡፡ ምርመራውም በኛ ላይ ነው፡፤ 13|41|እኛ ምድርን ከጫፎችዋ የምናጎድላት ኾነን የምንመጣባት መኾናችንን አላዩምን አላህም ይፈርዳል፡፡ ለፍርዱም ገልባጭ የለውም፡፡ እርሱም ምርመራው ፈጣን ነው፡፡ 13|42|እነዚያም ከእነሱ በፊት የነበሩት በእርግጥ መከሩ፡፡ አዘንግቶም የመያዙ ዘዴ በሙሉ የአላህ ነው፡፡ ነፍስ ሁሉ የምትሠራውን ያውቃል፡፡ ከሓዲዎችም የመጨረሻይቱ አገር ለማን እንደምትኾን ወደፊት ያውቃሉ፡፡ 13|43|እነዚያም የካዱት ሰዎች «መልክተኛ አይደለህም» ይላሉ፡፡ «በእኔና በእናንተ መካከል መስካሪ በአላህና እርሱ ዘንድ የመጽሐፉ ዕውቀት ባለው ሰው በቃ» በላቸው፡፡ 14|1|አ.ለ.ረ (አሊፍ ላም ራ፤ ይህ ቁርአን) ሰዎችን በጌታቸው ፈቃድ ከጨለማዎች ወደ ብርሃን አሸናፊ ምስጉን ወደ ኾነው፡፡ ጌታ መንገድ ታወጣ ዘንድ ወዳንተ ያወረድነው መጽሐፍ ነው፡፡ 14|2|አላህ ያ በሰማያት ያለው በምድርም ያለው ሁሉ የርሱ ብቻ የኾነ ነው፤ ለከሓዲዎችም ከብርቱ ቅጣት ወዮላቸው፡፡ 14|3|እነዚያ የቅርቢቱን ሕይወት ከመጨረሻይቱ ሕይወት ይበልጥ የሚወዱ ከአላህም መንገድ የሚያግዱ መጥመሟንም የሚፈልጉዋት ናቸው፡፡ እነዚያ በሩቅ ስሕተት ውስጥ ናቸው፡፡ 14|4|ከመልክተኛ ማንኛውንም ለእነርሱ ያብራራላቸው ዘንድ በወገኖቹ ቋንቋ እንጂ በሌላ አልላክንም፡፡ አላህም የሚሻውን ያጠማል፡፡ የሚሻውንም ያቀናል፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 14|5|ሙሳንም ወገኖችህን ከጨለማዎች ወደ ብርሃን አውጣ አላህንም ቀኖች አስገንዝባቸው በማለት በተዓምራታችን በእርግጥ ላክነው፡፡ በዚህ ውስጥ በብዙ ታጋሽና በብዙ አመስጋኝ ለኾኑት ሁሉ በእርግጥ ተዓምራቶች አሉ፡፡ 14|6|ሙሳም ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፤ ከፈርዖን ቤተሰቦች መጥፎን ቅጣት የሚያቀምሱዋችሁ ወንዶች ልጆቻችሁንም የሚያርዱ ሴቶቻችሁንም የሚተዉ ሲኾኑ በአዳንናችሁ ጊዜ በእናንተ ላይ (የዋለላችሁን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ፡፡ በዚህም ከጌታችሁ የኾነ ታላቅ ፈተና አለበት፡፡ 14|7|ጌታችሁም «ብታመሰግኑ በእርግጥ እጨምርላችኋለሁ ብትክዱም (እቀጣችኋለሁ) ቅጣቴ በእርግጥ ብርቱ ነውና» በማለት ባስታወቀ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ 14|8|ሙሳም አለ «እናንተም በምድር ያለውም ሁሉ በመላ ብትክዱ አላህ በእርግጥ ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡» 14|9|የእነዚያ ከናንተ በፊት የነበሩት የኑሕ ሕዝቦች የዓድም የሰሙድም የእነዚያም ከእነሱ በኋለ የነበሩት ከአላህ በስተቀር ሌላ የማያውቃቸው (ሕዝቦች) ወሬ አልመጣላችሁምን መልክተኞቻቸው በማስረጃዎች መጧቸው፡፡ እጆቻቸውንም (በቁጭት ሊነክሱ) ወደ አፎቻቸው መለሱ፡፡ አሉም «እኛ እናንተ በርሱ በተላካችሁበት ነገር ካድን እኛም ወደርሱ ከምትጠሩን ነገር አወላዋይ በኾነ ጥርጣሬ ውስጥ ነን፡፡» 14|10|መልክተኞቻቸው «ከኀጢአቶቻችሁ እንዲምራችሁ ወደ ተወሰነ ጊዜም (ያለ ቅጣት) እንዲያቆያችሁ የሚጠራችሁ ሲኾን ሰማያትንና ምድርን ፈጣሪ በኾነው አላህ (በመኖሩ) ጥርጣሬ አለን» አሏቸው፡፡ (ሕዝቦቹም) «እናንተ ብጤያችን ሰው እንጂ አይደላችሁም አባቶቻችን ይገዙት ከነበሩት ልትከለክሉን ትሻላችሁ፡፡ ግልጽንም አስረጅ (ካመጣችሁት ሌላ) አምጡልን» አሉ፡፡ 14|11|መልክተኞቻቸው ለእነርሱ አሉ «እኛ ብጤያችሁ ሰው እንጂ ሌላ አይደለንም ግን አላህ ከባሮቹ በሚሻው ሰው ላይ ይለግሳል፡፡ ለእኛም በአላህ ፈቃድ እንጂ ማስረጃን ልናመጣላችሁ አይገባንም፡፡ በአላህም ላይ ምእምናኖች ይጠጉ፡፡ 14|12|«መንገዳችንንም በእርግጥ የመራን ሲኾን በአላህ ላይ የማንመካ ለእኛ ምን አለን በማሰቃየታችሁም ላይ በእርግጥ እንታገሳለን፡፡ በአላህም ላይ ተመኪዎች ሁሉ ይመኩ፡፡» 14|13|እነዚያም የካዱት ለመልክተኞቻቸው «ከምድራችን በእርግጥ እናወጣችኋለን፤ ወይም ወደ ሃይማኖታችን በእርግጥ ትመለሳላችሁ» አሉ፡፡ ወደእነርሱም ጌታቸው እንዲህ ሲል ላከ «ከሓዲዎችን በእርግጥ እናጠፋለን፡፡ 14|14|«ከእነሱም በኋላ ምድሪቱን በእርግጥ እናስቀምጣችኋለን፡፡ ይኸ በፊቴ መቆሙን ለሚፈራ ዛቻዬንም ለሚፈራ ሰው ነው፡፡» 14|15|እርዳታንም (ከአላህ) ፈለጉ፤ (ተረዱም)፡፡ ጨካኝ ሞገደኛ የኾነም ሁሉ አፈረ፡፡ 14|16|ከስተፊቱ ገሀነም አለበት፡፡ እዥ ከኾነም ውሃ ይጋታል፡፡ 14|17|ይጎነጨዋል፤ ሊውጠውም አይቀርብም፡፡ ሞትም ከየስፍራው ሁሉ ይመጣበታል፤ እርሱም የሚሞት አይደለም፡፡ ከስተፊቱም ከባድ ቅጣት አለ፡፡ 14|18|የእነዚያ በጌታቸው የካዱት ሰዎች ምሳሌ (መልካም) ሥራዎቻቸው በነፋሻ ቀን ነፋስ በርሱ እንደ በረታችበት አመድ ነው፡፡ በሠሩት ሥራ በምንም ላይ (ሊጠቀሙ) አይችሉም፡፡ ይህ እርሱ ሩቅ ጥፋት ነው፡፡ 14|19|አላህ ሰማያትንና ምድርን በእውነት የፈጠረ መኾኑን አታይምን ቢሻ ያጠፋችኋል፡፡ አዲስ ፍጡርንም ያመጣል፡፡ 14|20|ይህም በአላህ ላይ አስቸጋሪ አይደለም፡፡ 14|21|የተሰበሰቡም ኾነው ለአላህ ይገለጻሉ፡፡ (ሐሳበ) ደካማዎቹም (ተከታዮች) ለእነዚያ ለኮሩት «እኛ ለእናንተ ተከታዮች ነበርን፤ እናንተ ከአላህ ቅጣት ከኛ ላይ አንዳችን ነገር ተከላካዮች ናችሁን» ይላሉ፡፡ (አስከታዮቹም) «አላህ ባቀናን ኖሮ በእርግጥ በመራናችሁ ነበር» ይሏቸዋል፡፡ «ብንበሳጭ ወይም ብንታገስም በእኛ ላይ እኩል ነው፡፡ ለእኛ ምንም መጠጊያ የለንም» ይላሉ፡፡ 14|22|ነገሩም በተፈጸመ ጊዜ ሰይጣን ይላቸዋል «አላህ እውነተኛውን ቃል ኪዳን ገባላችሁ፡፡ ቃል ኪዳንም ገባሁላችሁ፤ አፈረስኩባችሁም፡፡ ለእኔም በእናንተ ላይ ምንም ስልጣን አልበረኝም፡፡ ግን ጠራኋችሁ፡፡ ለእኔም ታዘዛችሁ፡፡ ስለዚህ አትውቀሱኝ፤ ነፍሶቻችሁንም ውቀሱ፡፡ እኔ የምረዳችሁ አይደለሁም፡፡ እናንተም የምትረዱኝ አይደላችሁም፡፡ እኔ ከአሁን በፊት ለአላህ ተጋሪ በአደረጋችሁት ነገር ካድኩ፡፡ በዳዮቹ ለእነርሱ በእርግጥ አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡» 14|23|እነዚያም ያመኑና መልካም ሥራዎችን የሠሩ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ በጌታቸው ፈቃድ እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡ በውስጣቸው መከባበሪያቸው ሰላም (ለእናንተ ይኹን መባባል) ነው፡፡ 14|24|አላህ መልካምን ቃል ሥርዋ (በምድር ውስጥ) የተደላደለች ቅርንጫፍዋም ወደ ሰማይ (የረዘመች) እንደሆነች መልካም ዛፍ አድርጎ ምሳሌን እንዴት እንደገለጸ አላየኽምን 14|25|ምግቧን (ፍሬዋን) በጌታዋ ፈቃድ በየጊዜው ትሰጣለች፡፡ አላህም ለሰዎች ይገሰጹ ዘንድ ምሳሌዎችን ይገልጻል፡፡ 14|26|የመጥፎም ቃል ምሳሌ ከምድር በላይ የተጎለሰሰች ለእርሷ ምንም መደላደል የሌላት እንደኾነች መጥፎ ዛፍ ነው፡፡ 14|27|አላህ እነዚያን ያመኑትን በቅርቢቱም ሕይወት በመጨረሻይቱም (በመቃብር) በተረጋገጠው ቃል ላይ ያረጋቸዋል፡፡ ከሓዲዎችንም አላህ ያሳስታቸዋል፡፡ አላህም የሚሻውን ይሠራል፡፡ 14|28|ወደእነዚያ የአላህን ጸጋ በክህደት ወደ ለወጡት ሕዝቦቻቸውንም በጥፋት አገር ወዳሰፈሩት (ወደ ቁረይሾች) አላየህምን 14|29|(አገሪቱም) የሚገቧት ስትኾን ገሀነም ናት፡፡ ምን ትከፋም መርጊያ! 14|30|ለአላህም ከመንገዱ ያሳስቱ ዘንድ ባላንጣዎችን አደረጉለት፡፡ «(ጥቂትን) ተጠቀሙ መመለሻችሁም ወደ እሳት ነው» በላቸው፡፡ 14|31|ለእነዚያ ላመኑት ባሮቼ በእርሱ ውስጥ ሽያጭና ወዳጂነት የሌለበት ቀን ከመምጣቱ በፊት ሶላትን በደንቡ ይሰግዳሉ፡፡ ከሰጠናቸውም ሲሳይ በምስጢርም በግልጽም ይለግሳሉ፡፡ (ስገዱ ለግሱም) በላቸው፡፡ 14|32|አላህ ያ ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ ከሰማይም ውሃን ያወረደ በእርሱም ከፍሬዎች ሲሳይን ለእናንተ ያወጣ መርከቦችንም በፈቃዱ በባሕር ላይ ይንሻለሉ ዘንድ ለናንተ የገራ ወንዞችንም ለናንተ የገራ ነው፡፡ 14|33|ፀሐይንና ጨረቃንም ዘወትር ኼያጆች ሲኾኑ ለእናንተ የገራ ሌሊትንና ቀንንም ለእናንተ የገራላችሁ ነው፡፡ 14|34|ከለመናችሁትም ሁሉ የሰጣችሁ ነው፡፡ የአላህንም ጻጋ ብትቆጥሩ አትዘልቋትም፡፡ ሰው በጣም በደለኛ ከሓዲ ነው፡፡ 14|35|ኢብራሂምም ባለ ጊዜ (አስታውስ) «ጌታዬ ሆይ! ይህንን አገር (መካን) ጸጥተኛ አድርገው፡፡ እኔንም ልጆቼንም ጣዖታትን ከመገዛት አርቀን፡፡ 14|36|«ጌታዬ ሆይ! እነርሱ (ጣዖታት) ከሰዎች ብዙዎችን አሳስተዋልና፡፡ የተከተለኝም ሰው እርሱ ከኔ ነው፡፡ ትእዛዜንም የጣሰ ሰው አንተ መሓሪ አዛኝ ነህ፡፡ 14|37|«ጌታችን ሆይ! እኔ አዝመራ በሌለው ሸለቆ ውስጥ በተከበረው ቤት (በካዕባ) አጠገብ ከዘሮቼ አስቀመጥኩ፡፡ ጌታችን ሆይ! ሶላትን ያቋቁሙ ዘንድ (አስቀመጥኳቸው)፡፡ ከሰዎችም ልቦችን ወደእነሱ የሚናፍቁ አድርግ፡፡ ያመሰግኑህም ዘንድ ከፍሬዎች ስጣቸው፡፡ 14|38|«ጌታችን ሆይ! አንተ የምንደብቀውንም የምንገልጸውንም ሁሉ በእርግጥ ታውቃለህ፡፡ በአላህም ላይ በምድርም በሰማይም ምንም ነገር አይደበቅም፡፡ 14|39|«ለእዚያ ከሽምግልና በኋላ ኢስማዒልን ኢስሐቅንም ለእኔ ለሰጠኝ አላህ ምሰጋና ይገባው፡፡ ጌታዬ ልመናን በእርግጥ ሰሚ ነውና፡፡ 14|40|«ጌታዬ ሆይ! ሰላትን አዘውትሬ የምሰግድ አድርገኝ፡፡ ከዘሮቼም (አድርግ)፡፡ ጌታችን ሆይ! ጸሎቴንም ተቀበለኝ፤ 14|41|«ጌታችን ሆይ! ለእኔም ለወላቼም ለምእመናንም ሁሉ ምርመራ በሚደረግበት ቀን ማር፡፡» 14|42|አላህንም በደለኞች ከሚሠሩት ግፍ ዘንጊ አድርገህ አታስብ፡፡ የሚያቆያቸው ዓይኖች በእርሱ እስከሚፈጡበት ቀን ድረስ ብቻ ነው፡፡ 14|43|(ወደ ጠሪው መልአክ) ቸኳዮች ራሶቻቸውን አንጋጣጮች ኾነው (ዓይኖቻቸው ይፈጣሉ)፡፡ ዓይኖቻቸው ወደነርሱ አይመለሱም፡፡ ልቦቻቸውም ባዶዎች ናቸው፡፡ 14|44|ሰዎችንም ቅጣቱ የሚመጣባቸውን ቀን አስፈራራቸው፡፡ እነዚያም የበደሉት «ጌታችን ሆይ! ወደ ቅርበ ጊዜ ድረስ አቆየን፡፡ ጥሪህን እንቀበላለንና መልክተኞቹንም እንከተላለንና» ይላሉ፡፡ «ከአሁን በፊት (በምድረ ዓለም) ለእናንተ ምንም መወገድ የላችሁም በማለት የማላችሁ አልነበራችሁምን» (ይባላሉ)፡፡ 14|45|«በእነዚያም ነፍሶቻቸውን በበደሉት ሰዎች መኖሪያ ውስጥ ተቀመጣችሁ፡፡ በእነሱም እንዴት እንደሠራንባቸው ለእናንተ ተገለጸላችሁ፡፡ ለእናንተም ምሳሌዎችን ገለጽንላችሁ፡፡» 14|46|(በነቢዩ ላይ) ሴራቸውንም በእርግጥ አሴሩ፡፡ ሴራቸውም (ቅጣቱ) አላህ ዘንድ ነው፡፡ ሴራቸውም ኮረብታዎች (ሕግጋቶች) በእርሱ የሚወገዱበት አልነበረም፡፡ 14|47|አላህንም መልክተኞቹን (የገባላቸውን) ቃል ኪዳኑን አፍራሽ አድርገህ አታስብ፡፡ አላህ አሸናፊ የመበቀል ባለቤት ነው፡፡ 14|48|ምድር በሌላ ምድር የምትለወጥበትን ሰማያትም (እንደዚሁ) አንድ አሸናፊ ለኾነው አላህም (ፍጡራን ሁሉ) የሚገለጹበት ቀን (አስታውሱ)፡፡ 14|49|አመጸኞችንም በዚያ ቀን በሰንሰለቶች ተቆራኝተው ታያቸዋለህ፡፡ 14|50|ቀሚሶቻቸው ከካትራም ናቸው፡፡ ፊቶቻቸውንም እሳት ትሸፍናቸዋለች፡፡ 14|51|አላህ ነፍስን ሁሉ የሠራችውን ይመነዳ ዘንድ (ይህንን አደረገ)፡፡ አላህ ምርመራው ፈጣን ነው፡፡ 14|52|ይህ (ቁርኣን) ለሰዎች ገላጭ ነው፡፡ (ሊመከሩበት)፣ በእርሱም ሊስፈራሩበት፣ እርሱም አንድ አምላክ ብቻ መኾኑን ሊያውቁበት፣ የአእምሮ ባለቤቶችም ሊገሰፁበት (የተወረደ) ነው፡፡ 15|1|አ.ለ.ረ (አሊፍ ላም ራ) ይህች (አናቅጽ) ከመጽሐፉ አንቀጾችና ገላጭ ከኾነው ቁርኣን ናት፡፡ 15|2|እነዚያ የካዱት (በትንሣኤ ቀን) ሙስሊሞች በኾኑ ኖሩ በብዛት ይመኛሉ፡፡ 15|3|ተዋቸው ይብሉ፤ ይጠቀሙም፡፡ ተስፋም ያዘናጋቸው፡፡ በእርግጥም (መጥፎ ፍጻሜያቸውን) ያውቃሉ፡፡ 15|4|ማንኛይቱንም ከተማ ለእርሷ የተወሰነ መጽሐፍ (ጊዜያት) ያላት ኾና እንጂ አላጠፋንም፡፡ 15|5|ማንኛይቱም ሕዝብ ጊዜዋን ምንም አትቀድምም፡፡ (ከእርሱ) አይቆዩምም፡፡ 15|6|«አንተ ያ በእርሱ ላይ ቁርኣን የተወረደለት ሆይ! አንተ በእርግጥ ዕብድ ነህ» አሉም፡፡ 15|7|«ከእውነተኞቹ እንደ ኾንክ በመላእክት (መስካሪ) ለምን አትመጣንም» (አሉ)፡፡ 15|8|መላእክትን በእውነት (በቅጣት) እንጂ አናወርድም፡፡ ያን ጊዜም የሚቆዩ አይደሉም፡፡ 15|9|እኛ ቁርኣንን እኛው አወረድነው፡፡ እኛም ለእርሱ ጠባቂዎቹ ነን፡፡ 15|10|ከአንተም በፊት በነበሩት በመጀመሪያዎቹ ሕዝቦች ውስጥ (መልክተኞችን) በእርግጥ ልከናል፡፡ 15|11|ማንኛውም መልእክተኛ በእርሱ የሚያላግጡበት ኾነው እንጅ አይመጣቸውም ነበር፡፡ 15|12|እንደዚሁ (ማስተባበልን) በአመጸኞቹ ልቦች ውስጥ እናገባዋለን፡፡ 15|13|በእርሱ አያምኑበትም፡፡ የቀድሞዎቹም ድርጊት በእርግጥ አልፋለች፤ (እንደጠፉ ይጠፋሉ)፡፡ 15|14|በእነርሱም ላይ ከሰማይ ደጃፍን በከፈትንላቸውና በእርሱ ሲወጡ በዋሉ ኖሮ፤ 15|15|«የተዘጉት ዓይኖቻችን ናቸው፡፡ እንዲያውም እኛ የተደገመብን ሰዎች ነን» ባሉ ነበር፡፡ 15|16|በሰማይም ላይ ቡርጆችን በእርግጥ አድርገናል፡፡ ለተመልካቾችም (በከዋክብት) አጊጠናታል፡፡ 15|17|ከተባረረ ሰይጣንም ሁሉ ጠብቀናታል፡፡ 15|18|ግን (ወሬ) መስማትን የሚሰርቅ ወዲየውኑ አብሪ ችቦ ይከተለዋል፡፡ (ያቃጥለዋል)፡፡ 15|19|ምድርንም ዘረጋናት፡፡ በውስጧም ኮረብታዎችን ጣልናባት፡፡ በውስጧም (የተለካን) በቃይ ሁሉ አበቀልንባት፡፡ 15|20|በእርሷም ውስጥ ለእናንተ መኖሪያዎችንና ለእርሱ መጋቢዎቹ ያልኾናችሁትንም (እንስሳትን) አደረግንላችሁ፡፡ 15|21|መካዚኖቹም (መክፈቻቸው) እኛ ዘንድ ያልሆነ ምንም ነገር የለም፡፡ በተወሰነም ልክ እንጂ አናወርደውም፡፡ 15|22|ነፋሶችንም (ደመናን) ተሸካሚዎች አድርገን ላክን፡፡ ከሰማይም (ከደመና) ዝናብን አወረድን፡፡ እርሱንም አጠጣናችሁ፡፡ እናንተም ለእርሱ አድላቢዎች አይደላችሁም፡፡ 15|23|እኛም ሕያው የምናደርግና የምንገድል እኛው ብቻ ነን፡፡ እኛም (ፍጡርን ሁሉ ) የምንወርስ (ቀሪ) ነን፡፡ 15|24|ከእናንተም ተቀዳሚዎቹን በእርግጥ ዐውቀናል፡፡ ወደ ኋላም ቀሪዎቹን በእርግጥ ዐውቀናል፡፡ 15|25|ጌታህም እርሱ ይሰበስባችኋል፡፡ እርሱ ጥበበኛ ዐዋቂ ነውና፡፡ 15|26|ሰውንም ከሚቅጨለጨል ሸክላ ከሚገማ ጥቁር ጭቃ በእርግጥ ፈጠርነው፡፡ 15|27|ጃንንም (ከሰው) በፊት ከእሳት ነበልባል ፈጠርነው፡፡ 15|28|ጌታህም ለመላእክት ባለጊዜ (አስታውስ)፡፡ እኔ ሰውን ከሚቅጨለጨል ሸክላ ከሚገማ ጭቃ እፈጥራለሁ፡፡ 15|29|(ፍጥረቱን) ባስተካከልኩትና በውስጡ ከመንፈሴ በነፋሁበትም ጊዜ ለእርሱ ሰጋጆች ኾናችሁ ውደቁ፡፡ 15|30|መላእክትም መላውም ተሰብስበው ሰገዱ፡፡ 15|31|ኢብሊስ (ዲያብሎስ) ብቻ ሲቀር፡፡ ከሰጋጆቹ ጋር ከመኾን እንቢ አለ፡፡ 15|32|(አላህም) «ኢብሊስ ሆይ! ከሰጋጆቹ ጋር የማትኾን ላንተ ምን ምክንያት አለህ» አለው፡፡ 15|33|«ከሚቅጨለጨል ሸክላ ከግም ጭቃ ለፈጠርከው ሰው ልሰግድ አይገባኝም» አለ፡፡ 15|34|(አላህ) አለው «ከርሷም ውጣ፡፡ አንተ የተባረርክ እርጉም ነህና፡፡» 15|35|«ባንተ ላይም እስከ ፍርዱ ቀን ድረስ እርግማን አለብህ፡፡» 15|36|«ጌታዬ ሆይ! እንግዲውያስ (ሰዎች) እስከሚቀሰቀሱበት ቀን ድረስ አቆየኝ» አለ፡፡ 15|37|(አላህም) አለ «አንተ ከሚቆዩት ነህ፡፡ 15|38|«እስከታወቀው ወቅት ቀን ድረስ፡፡» 15|39|(ኢብሊስ) አለ «ጌታዬ ሆይ! እኔን በማጥመምህ ይኹንብኝ ለነርሱ በምድር ላይ (ኀጢአትን) እሸልምላቸዋለሁ፡፡ ሁሉንም አጠማቸዋለሁም፡፡» 15|40|«ከነርሱ ፍጹሞቹ ባሮችህ ብቻ ሲቀሩ፡፡» 15|41|(አላህም) አለ «ይህ በእኔ ላይ (መጠበቁ የተገባ) ቀጥተኛ መንገድ ነው፡፡» 15|42|«እነሆ ባሮቼ በእነሱ ላይ ላንተ ስልጣን የለህም፡፡ ከጠማሞቹ የተከተለህ ሰው ብቻ ሲቀር፡፡» 15|43|«ገሀነምም (ለርሱና ለተከተሉት) ለመላውም በእርግጥ ቀጠሯቸው ናት፡፡ 15|44|«ለእርሷ ሰባት ደጃፎች አሏት፡፡ ለየደጀፉም ሁሉ ከእነሱ የተከፈለ ፋንታ አለ፡፡ 15|45|«እነዚያ (ከኀጢአት) የተጠነቀቁት በአትክልቶችና በምንጮች ውስጥ ናቸው፡፡ 15|46|«ጸጥተኞች ኾናችሁ በሰላም ግቧት (ይባላሉ)፡፡ 15|47|«ባልጋዎችም ላይ ፊት ለፊት የሚቅጣጩ ወንድማማቾች ኾነው በደረቶቻቸው ውስጥ ከቂም ያለውን ሁሉ እናስወግዳለን፡፡ 15|48|«በእርሷም ውስጥ ድካም አይነካቸውም፡፡ እነሱም ከእርሷ የሚወጡ አይደሉም፡፡» 15|49|ባሮቼን እኔ መሓሪው አዛኙ እኔው ብቻ መኾኔን ንገራቸው፡፡ 15|50|ቅጣቴም እርሱ አሳማሚ ቅጣት መኾኑን (ንገራቸው)፡፡ 15|51|ከኢብራሂም እንግዶችም (ወሬ) ንገራቸው፡፡ 15|52|በእርሱ ላይ በገቡና ሰላም ባሉት ጊዜ የኾነውን (አስታውስ)፡፡ (እርሱም) «እኛ ከእናንተ ፈሪዎች ነን» አላቸው፡፡ 15|53|«አትፍራ፤ እኛ ዐዋቂ በኾነ ወንድ ልጅ እናበስርሃለን» አሉት፡፡ 15|54|«እርጅና የደረሰብኝ ከመኾኔ ጋር አበሰራችሁኝን በምን ታበስሩኛላችሁ» አለ፡፡ 15|55|«በእውነት አበሰርንህ፡፡ ከተሰፋ ቆራጮችም አትኹን» አሉ፡፡ 15|56|«ከጠማማዎችም በስተቀር ከጌታው እዝነት ተስፋን የሚቆርጥ ማነው» አለ፡፡ 15|57|«እናንተ መልክተኞች ሆይ! ኧረ ለመኾኑ ነገራችሁ ምንድን ነው» አለ፡፡ 15|58|«እኛ አመጸኞች ወደ ኾኑ ሕዝቦች ተልከናል» አሉት፡፡ 15|59|«የሉጥ ቤተሰቦች ብቻ ሲቀሩ፡፡ (እነርሱን) እኛ ሁላቸውንም በእርግጥ የምናድናቸው ነን፡፡ 15|60|«ሚስቱ ብቻ ስትቀር፡፡ እርሷን (በቅጣቱ ውስጥ) ከሚቀሩት መኾኗን ወሰነናል» (አሉ)፡፡ 15|61|መልክተኞቹም የሉጥን ቤተሰቦች በመጡባቸው ጊዜ፤ 15|62|(ሉጥ) «እናንተ የተሳታችሁ ሕዝቦች ናችሁ» አላቸው፡፡ 15|63|«አይደለም እኛ ሕዝቦችህ በርሱ ይጠራጠሩበት በነበሩት ቅጣት መጣንህ» አሉት፡፡ 15|64|«እውነትንም ይዘን መጣንህ፡፡ እኛም በእርግጥ እውነተኞች ነን፡፡ 15|65|ከቤተሰብህም ጋር በሌሊቱ ከፊል ኺድ፡፡ ከኋላቸውም ተከተል፡፡ ከእናንተም አንድም ሰው ወደ ኋላው አይገላመጥ፡፡ ወደ ታዘዛችሁበትም ስፍራ እለፉ» (አሉት)፡፡ 15|66|ወደርሱም ያንን ትእዛዝ አወረድን፡፡ (እርሱም) የእነዚህ (ሕዝቦች) መጨረሻ ያነጉ ሲኾኑ (ሥራቸው) መቆረጥ ነው፡፡ 15|67|የከተማይቱም ሰዎች የሚበሳሰሩ ኾነው መጡ፡፡ 15|68|(ሉጥም) አለ «እነዚህ እንግዶቼ ናቸውና አታጋልጡኝ፡፡ 15|69|«አላህንም ፍሩ፤ አታሳፍሩኝም፡፡» 15|70|«ከዓለማት (ማንንም እንዳታስተናግድ) አልከለከልንህምን» አሉት፡፡ 15|71|(ሉጥም) «እነኝህ ሴቶች ልጆቼ ናቸው፡፡ ሠሪዎች ብትኾኑ (አግቧቸው)» አለ፡፡ 15|72|በዕድሜህ እንምላለን እነሱ በእርግጥ በስከራቸው ውስጥ ይዋልላሉ፡፡ 15|73|ጩኸቲቱም ፀሐይ የወጣችባቸው ሲኾኑ ያዘቻቸው፡፡ 15|74|ላይዋንም ከታችዋ አደረግን፡፡ በእነሱም ላይ የሸክላ ደንጊያዎችን አዘነብንባቸው፡፡ 15|75|በዚህ ውስጥ ለተመልካቾች በእርግጥ መገምገሚያዎች አሉበት፡፡ 15|76|እሷም (ከተማይቱ) በቀጥታ መንገድ ላይ ናት፡፡ 15|77|በዚህ ውስጥ በእርግጥ ለምእምናን መገሰጫ አለ፡፡ 15|78|እነሆ የአይከት ሰዎችም በእርግጥ በዳዮች ነበሩ፤ 15|79|ከነሱም ተበቀልን ሁለቱም (የሉጥና የአይከት ሕዝቦች ከተሞች) በእርግጥ በግልጽ መንገድ ላይ ናቸው፡፡ 15|80|የሒጅርም ሰዎች መልክተኞቹን በእርግጥ አስተባበሉ፡፡ 15|81|ተዓምራታችንንም ሰጠናቸው፡፡ ከእርሷም ዘንጊዎች ነበሩ፡፡ 15|82|ከኮረብታዎችም ቤቶችን ጸጥተኞች ኾነው ይጠርቡ ነበር፡፡ 15|83|ያነጉም ሲኾኑ ጩኸት ያዘቻቸው፤ (ወደሙ)፡፡ 15|84|ይሠሩትም የነበሩት ሕንጻ ምንም አልጠቀማቸውም፡፡ 15|85|ሰማያትንና ምድርንም በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ በእውነት እንጂ (በላግጣ) አልፈጠርንም፡፡ ሰዓቲቱም በእርግጥ መጪ ናት፡፡ መልካምንም ይቅርታ አድርግላቸው፡፡ 15|86|ጌታህ እርሱ (ያልነበረን) ፈጣሪው ዐዋቂው ነው፡፡ 15|87|ከሚደጋገሙ የኾኑን ሰባትንና ታላቁንም ቁርኣን (በሙሉ) በእርግጥ ሰጠንህ፡፡ 15|88|ከእነርሱ (ከከሓዲዎች) ብዙዎችን ወገኖች በእርሱ ወደ አጣቀምንበት ጸጋ ዓይኖችህን አትዘርጋ፡፡ በእነሱም ላይ (ባያምኑ) አትዘን፡፡ ክንፍህንም ለምእምናን አለዝብ፡፡ 15|89|በልም «እኔ ግልጽ አስፈራሪው እኔ ነኝ፡፡» 15|90|(ሰዎችን ለማገድ የመካን በሮች) በተከፋፈሉት ላይ እንደ አወረድነው (በኾነ ቅጣት አሰፈራሪያችሁ ነኝ በል)፡፡ 15|91|(እነርሱም) እነዚያ ቁርኣንንን ክፍልፍሎች ያደረጉ ናቸው፡፡ 15|92|በጌታህም እንምላለን፡፡ ሁላቸውንም እንጠይቃቸዋለን፤ 15|93|ይሠሩት ከነበሩት ነገር ሁሉ፡፡ 15|94|የታዘዝክበትንም ነገር በይፋ ግለጽ፡፡ አጋሪዎችንም ተዋቸው፡፡ 15|95|ተሳላቂዎችን ሁሉ እኛ በቅተንሃል፡፡ 15|96|(እነሱም) እነዚያ ከአላህ ጋር ሌላ አምላክን ያደረጉ ናቸው፡፡ በእርግጥም (ፍጻሜያቸውን) ወደፊት ያውቃሉ፡፡ 15|97|አንተም በሚሉት ነገር ልብህ የሚጠብ መኾኑን በእርግጥ እናውቃለን፡፡ 15|98|ጌታህንም ከማመስገን ጋር አጥራው ከሰጋጆቹም ኹን፡፡ 15|99|እውነቱም (ሞት) እስኪመጣህ ድረስ ጌታህን ተገዛ፡፡ 16|1|የአላህ ትዕዛዝ መጣ፤ ስለዚህ አታስቸኩሉት፤ ከማይገባው ሁሉ ጠራ ከሚያጋሩትም ሁሉ ላቀ፤ 16|2|ከባሮቹ በሚሻው ሰው ላይ መላእክትን ከራእይ ጋር በፈቃዱ ያወርዳል (ከሓዲዎችን በቅጣት) አስጠንቅቁ፤ እነሆ ከኔ በቀር ሌላ አምላክ የለም፤ ፍሩኝም ማለትን (አስታውቁ በማለት ያወርዳል)፡፡ 16|3|ሰማያትንና ምድርን በእውነት ፈጠረ ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ፡፡ 16|4|ሰውን ከፍትወት ጠብታ ፈጠረው፡፡ ከዚያም እርሱ ወዲያውኑ (ትንሣኤን በመካድ) ግልጽ ተከራካሪ ይኾናል፡፡ 16|5|ግመልን፣ ከብትን፣ ፍየልንም በርሷ (ብርድ መከላከያ) ሙቀት ጥቅሞችም ያሉባት ስትኾን ለእናንተ ፈጠረላችሁ፡፡ ከርሷም ትበላላችሁ፡፡ 16|6|ለእናንተም በእርሷ ወደ ማረፊያዋ በምትመልሷት ጊዜ በምታሰማሩዋትም ጊዜ ውበት አላችሁ፡፡ 16|7|ጓዞቻችሁንም በነፍሶች ችግር እንጂ ወደማትደርሱበት አገር ትሸከማለች፡፡ ጌታችሁ በእርግጥ ሩኅሩኅ አዛኝ ነውና፡፡ 16|8|ፈረሶችንም፣ በቅሎዎችንም፣ አህዮችንም ልትቀመጡዋቸውና ልታጌጡባቸው (ፈጠረላችሁ)፡፡ የማታውቁትንም ድንቅ ነገር ይፈጥራል፡፡ 16|9|በአላህም ላይ (በችሮታው) ቀጥተኛውን መንገድ መግለጽ አለበት፡፡ ከእርሷም (ከመንገድ) ጠማማ አልለ፡፡ በሻም ኖሮ ሁላችሁንም በእርግጥ ባቀናችሁ ነበር፡፡ 16|10|እርሱ ያ ከሰማይ ውሃን ያወረደ ነው፡፡ ከእርሱ ለእናንተ መጠጥ አላችሁ፡፡ ከእርሱም (እንስሳዎችን) በእርሱ የምታሰማሩበት ዛፍ (ይበቅልበታል)፡፡ 16|11|በእርሱ ለእናንተ አዝመራን፣ (የዘይት) ወይራንም፣ ዘምባባዎችንም (ተምርን)፣ ወይኖችንም፣ ከፍሬዎችም ሁሉ ያበቅልላችኋል፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች በእርግጥ ተዓምርአልለ፡፡ 16|12|ለእናንተም ሌሊትንና ቀንን፣ ፀሐይንና ጨረቃንም ገራላችሁ፡፡ ከዋክብትም በፈቃዱ የተገሩ ናቸው፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚያውቁ ሕዝቦች በእርግጥ ተዓምራቶች አልሉ፡፡ 16|13|በምድርም ላይ መልኮቹ የተለያዩ ኾኖ ለእናንተ የፈጠረላችሁን ሁሉ (ገራላችሁ)፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚገሰጹ ሕዝቦች በእርግጥ ተዓምር አልለ፡፡ 16|14|እርሱም ያ ባሕርን ከእርሱ እርጥብ ስጋን ልትበሉና ከእርሱም የምትለብሱትን ጌጣጌጥ ታወጡ ዘንድ የገራ ነው፡፡ መርከቦችንም በውስጡ (ውሃውን) ቀዳጆች ኾነው (ሲንሻለሉ) ታያለህ፡፡ ከችሮታው ልትፈልጉና ልታመሰግኑም (ገራላችሁ)፡፡ 16|15|በምድርም ውስጥ በእናንተ እንዳታረገርግ ተራራዎችን ጣለባት፡፡ ጂረቶችንም፣ መንገዶችንም ትመሩ ዘንድ (አደረገ)፡፡ 16|16|ምልክቶችንም (አደረገ)፡፡ በከዋክብትም እነሱ ይምመራሉ፡፡ 16|17|የሚፈጥር እንደማይፈጥር ነውን አትገሰጹምን 16|18|የአላህንም ጸጋ ብትቆጥሩ አትዘልቋትም፡፡ አላህ በእርግጥ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 16|19|አላህም የምትደብቁትንና የምትገልጹትን ሁሉ ያውቃል፡፡ 16|20|እነዚያም ከአላህ ሌላ የምትገዟቸው ምንንም አይፈጥሩም፡፡ እነርሱም ይፈጠራሉ፤ 16|21|ሕያው ያልኾኑ ሙታን ናቸው፡፡ መቼ እንደሚቀሰቀሱም አያውቁም፡፡ 16|22|አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው፡፡ እነዚያም በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ልቦቻቸው ከሓዲዎች ናቸው፡፡ እነሱም የኮሩ ናቸው፤ (አያምኑም)፡፡ 16|23|አላህ የሚደብቁትንና የሚገልጹትን ሁሉ የሚያውቅ ለመኾኑ ጥርጣሬ የለበትም፡፡ እርሱ ኩሩዎችን አይወድም፡፡ 16|24|ለእነርሱም «ጌታችሁ (በሙሐመድ ላይ) ምንን አወረደ» በተባሉ ጊዜ «(እርሱ) የመጀመሪያዎቹ ሕዝቦች ተረቶች ነው» ይላሉ፡፡ 16|25|(ይህንንም የሚሉት) በትንሣኤ ቀን ኀጢኣቶቻቸውን በሙሉ ከእነዚያም ያለ ዕውቀት ኾነው ከሚያጠሟቸው ሰዎች ኀጢአቶች ከፊሉን ሊሸከሙ ነው፡፡ ንቁ! የሚሸከሙት ኃጢኣት ምንኛ ከፋ! 16|26|እነዚያ ከእነሱ (ከቁረይሾች) በፊት የነበሩት በእርግጥ መከሩ፡፡ አላህም ሕንጻዎቻቸውን ከመሠረቶቻቸው አፈረሰ፡፡ ጣሪያውም በእነሱ ላይ ከበላያቸው ወደቀባቸው፡፡ ቅጣቱም ከማያውቁት ሥፍራ መጣባቸው፡፡ 16|27|ከዚያም በትንሣኤ ቀን ያዋርዳቸዋል፡፡ እነዚያም «በእነሱ (ጉዳይ) ትከራከሩኝ የነበራችሁት ተጋሪዎቼ የት ናቸው» ይላቸዋል፡፡ «እነዚያ ዕውቀትን የተሰጡት ዛሬ ሐፍረቱና ቅጣቱ በእርግጥ በከሓዲዎች ላይ ነው» ይላሉ፡፡ 16|28|(እነርሱ) «እነዚያ ነፍሶቻቸውን በዳይ ኾነው መላእክት የሚገድሏቸው ናቸው፡፡ ከክፉ ሥራ ምንም ነገር የምንሠራም አልነበርን» (ሲሉ) ታዛዥነታቸውን ይገልጻሉ፡፡ «በእውነት አላህ ትሰሩት የነበራችሁትን ነገር ዐዋቂ ነው» (ይባላሉ)፡፡ 16|29|«የገሀነምንም ደጃፎች በውስጧ ዘውታሪዎች ስትኾኑ ግቡ» (ይባላሉ)፡፡ የኩሩዎችም መኖሪያ (ገሀነም) በእርግጥ ከፋች! 16|30|ለእነዚያም ለተጠነቀቁት «ጌታችሁ ምንን ነገር አወረደ» ተባሉ፡፡ «መልካምን ነገር» አሉ፡፡ ለእነዚያ ደግ ለሠሩት በዚሀች በቅርቢቱ ዓለም መልካም ኑሮ አላቸው፡፡ የመጨረሻይቱም አገር በእርግጥ በላጭ ናት፡፡ የጥንቁቆቹም አገር ምን ታምር! 16|31|(እርሷም) የሚገቡዋትና በሥርዋ ወንዞች የሚፈሱባት ስትኾን የመኖሪያ አትክልቶች ናት፡፡ ለእነሱም በወስጧ የሚሹት ሁሉ አላቸው፡፡ እንደዚሁ አላህ ጥንቁቆችን ይመነዳል፡፡ 16|32|እነዚያ በመልካም ኹኔታ ላይ ኾነው መላእክት «ሰላም በእናንተ ላይ» እያሉ የሚገድሏቸው ናቸው፡፡ «ትሠሩት በነበራችሁት ሥራ ገነትን ግቡ» (ይባላሉ)፡፡ 16|33|(ከሓዲዎች) መላእክት ወደ እነሱ መምጣትን ወይም የጌታህ ትእዛዝ መምጣቱን እንጂ አይጠባበቁም፡፡ ከእነሱ በፊት የነበሩት እንደዚህ ሠርተዋል፡፡ አላህም አልበደላቸውም፤ ግን ነፍሶቻቸውን የሚበድሉ ነበሩ፡፡ 16|34|የሠሩዋቸውም ኀጢአቶች (ቅጣት) አገኛቸው፡፡ በእርሱም ይሳለቁበት የነበሩት ሁሉ በነሱ ላይ ወረደባቸው፡፡ 16|35|እነዚያም (ጣዖታትን) ያጋሩት «አላህ በሻ ኖሮ ከእርሱ ሌላ እኛም አባቶቻችንም ምንንም ባልተገዛን ነበር፤ ያለእርሱም (ትእዛዝ) ምንንም እርም ባላደረግን ነበር አሉ፡፡» እነዚያም ከነሱ በፊት የነበሩት እነደዚሁ ሠሩ፡፡ በመልክተኞቹም ላይ ግልፅ ማድረስ ብቻ እንጂ ሌላ የለባቸውም፡፡ 16|36|በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ «አላህን ተገዙ፤ ጣዖትንም ራቁ» በማለት መልክተኛን በእርግጥ ልከናል፡፡ ከእነሱም ውስጥ አላህ ያቀናው ሰው አልለ፡፡ ከእነሱም ውስጥ በእርሱ ላይ ጥመት የተረጋገጠበት ሰው አልለ፡፡ በምድርም ላይ ኺዱ፤ የአስተባባዮችም መጨረሻ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከቱ፡፡ 16|37|በመቅናታቸው ላይ ብትጓጓ (ምንም ልታደርግ አትችልም)፡፡ አላህ የሚጠመውን ሰው አያቀናውምና፡፡ ለእነሱም ከረዳቶች ምንም የላቸውም፡፡ 16|38|መሓሎቻቸውምን አላህ የሚሞትን ሰው አያስነሳም ሲሉ በአላህ ስም ማሉ፡፡ ሐሰት ነው (ያስነሳቸዋል)፡፡ በእርሱ ላይ ቃል ኪዳን ገብቷል፡፡ አረጋግጧል፤ ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 16|39|(የሚቀሰቅሳቸውም) ለእነሱ ያንን በእርሱ የሚለያዩበትን ሊገልጽላቸው፤ እነዚያ የካዱትም እነሱ ውሸታሞች የነበሩ መኾናቸውን እንዲያውቁ ነው፡፡ 16|40|ለማንኛውም ነገር (መኾኑን) በሻነው ጊዜ ቃላችን ለእርሱ «ኹን» ማለት ብቻ ነው፤ ወዲውም ይኾናል፡፡ 16|41|እነዚያም ከተበደሉ በኋላ በአላህ (መንገድ ላይ) የተሰደዱት በቅርቢቱ ዓለም መልካሚቱን አገር (መዲናን) በእርግጥ እናሰፍራቸዋለን፡፡ የመጨረሻይቱም ዓለም ምንዳ ታላቅ ነው፡፡ (ከሓዲዎች) ቢያውቁ ኖሮ (በተከተሏቸው ነበር)፡፡ 16|42|(እነርሱ) እነዚያ የታገሱት በጌታቸውም ላይ የሚጠጉት ናቸው፡፡ 16|43|ከአንተም በፊት ወደእነሱ ወሕይን (ራእይን) የምናወርድላቸውን ሰዎችን እንጂ ሌላን አልላክንም፡፡ የማታውቁም ብትኾኑ የዕውቀትን ባለቤቶች ጠይቁ፡፡ 16|44|በግልጽ ማስረጃዎችና በመጻሕፍት (ላክናቸው)፡፡ ወደ አንተም ለሰዎች ወደእነሱ የተወረደውን (ፍች) ልትገልጽላቸውና ያስተነትኑም ዘንድ ቁርኣንን አወረድን፡፡ 16|45|እነዚያ መጥፎዎችን የዶለቱ አላህ በእነሱ ምድርን የሚገለብጥባቸው ወይም ከማያውቁት ስፍራ ቅጣት የሚመጣባቸው መኾኑን አይፈሩምን 16|46|ወይም (ካገር ወደ አገር) በሚዛወሩበት ጊዜ የሚይዛቸው መኾኑን (አይፈሩምን) እነሱም አሸናፊዎች አይደሉም፡፡ 16|47|ወይም ቀስ በቀስ በማጉደል ላይ የሚይዛቸው መኾኑን (አይፈሩምን) ጌታችሁም በእርግጥ ርኅሩኅ አዛኝ ነው፡፡ 16|48|ወደዚያ ከማንኛውም ነገር አላህ ወደ ፈጠረው ጥላዎቹ እነርሱ የተዋረዱ ሲኾኑ ለአላህ ሰጋጆች ኾነው ከቀኝና ከግራዎች ወደሚዛወሩት አላዩምን 16|49|ለአላህም በሰማያት ያለው ከተንቀሳቃሽም በምድር ያለው ሁሉ፣ መላእክትም ይሰግዳሉ፡፡ እነርሱም አይኮሩም፡፡ 16|50|ጌታቸውን ከበላያቸው ሲኾን ይፈሩታል፡፡ የታዘዙትንም ሁሉ ይሠራሉ፡፡ 16|51|አላህም አለ «ሁለት አማልክትን አትያዙ፡፡ እርሱ አንድ አምላክ ብቻ ነው፡፡ እኔንም ብቻ ፍሩ፡፡» 16|52|በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የርሱ ብቻ ነው፡፡ መገዛትም ዘወትር ሲኾን ለርሱ ብቻ ነው፡፡ ከአላህም ሌላ ያለን ትፈራላችሁን 16|53|ማንኛውም በእናንተ ላይ ያለው ጸጋ ከአላህ ነው፡፡ ከዚያም ችግር በደረሰባችሁ ጊዜ ወደርሱ ብቻ ትጮሃላችሁ፡፡ 16|54|ከዚያም ከእናንተ ላይ ችግርን ባነሳላችሁ ጊዜ ከእናንተው የኾኑ ጭፍሮች ወዲያውኑ በጌታቸው (ጣዖትን) ያጋራሉ፡፡ 16|55|(የሚያጋሩትም) በሰጠናቸው ሊክዱ ነው፡፡ ተጠቀሙም ወደ ፊትም (የሚደርስባችሁን) በእርግጥ ታውቃላችሁ፡፡ 16|56|ለማያውቁትም (ጣዖታት) ከሰጠናቸው ሲሳይ ፈንታን ያደርጋሉ፡፡ በአላህ እምላለሁ፤ ትቀጣጥፉት ከነበራችሁት ሁሉ በእርግጥ ትጠየቃላችሁ፡፡ 16|57|ለአላህም (ከመላእክት) ሴቶች ልጆችን ያደርጋሉ፡፡ ጥራት ተገባው፡፡ ለእነርሱም የሚፈልጉትን (ወንዶች ልጆችን) ያደርጋሉ፡፡ 16|58|አንዳቸውም በሴት ልጅ በተበሰረ ጊዜ እርሱ የተቆጨ ኾኖ ፊቱ ጠቁሮ ይውላል፡፡ 16|59|በእርሱ ከተበሰረበት ነገር መጥፎነት በውርደት ላይ ኾኖ ይያዘውን ወይስ በዐፈር ውስጥ ይደብቀውን (በማለት እያምታታ) ከሰዎች ይደበቃል፡፡ ንቁ! የሚፈርዱት (ፍርድ) ምንኛ ከፋ! 16|60|ለእነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም ለማያምኑት መጥፎ ጠባይ አላቸው፡፡ ለአላህም ታላቅ ባሕርይ አለው፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 16|61|አላህም ሰዎችን በበደላቸው በያዛቸው ኖሮ በርሷ (በምድር ላይ) ከተንቀሳቃሽ ምንንም ባልተወ ነበር፡፡ ግን እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ ያቆያቸዋል፡፡ ጊዜያቸውም በመጣ ወቅት አንዲትን ሰዓት አይቆዩም፤ አይቀደሙምም፡፡ 16|62|ለአላህም የሚጠሉትን ነገር ያደረጋሉ፡፡ ለእነሱም መልካሚቱ (አገር) አለቻቸው በማለት ምላሶቸቸው ውሸትን ይናገራሉ፡፡ ለእነሱ እሳት ያለቻቸው መኾናቸውና እነሱም (ወደርሷ) በቅድሚያ የሚነዱ መኾናቸው ጥርጥር የለበትም፡፡ 16|63|በአላህ እንምላለን፤ ካንተ በፊት ወደ ነበሩት ሕዝቦች በእርግጥ (መልክተኞችን) ልከናል፡፡ ሰይጣንም ለእነርሱ ሥራዎቻቸውን ሸለመላቸው፡፡ እርሱም ዛሬ ረዳታቸው ነው፡፡ ለእነሱም (ኋላ) አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 16|64|ባንተም ላይ መጽሐፉን አላወረድንም፤ ያንን በርሱ የተለያዩበትን ለነርሱ ልታብራራላቸውና ለሚያምኑትም ሕዝቦች መሪና እዝነት ሊኾን እንጂ፡፡ 16|65|አላህም ከሰማይ ውሃን አወረደ፡፡ በእርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው አደረገ፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚሰሙ ሕዝቦች በእርግጥ ተዓምር አልለ፡፡ 16|66|ለናንተም በግመል፣ በከብት፣ በፍየል በእርግጥ መገምገሚያ አልላችሁ፡፡ በሆዶቹ ውስጥ ካለው ከፈረስና ከደም መካከል ጥሩ ወተትን ለጠጪዎች ተዋጭ ሲሆን እናጠጣችኋለን፡፡ 16|67|ከዘምባባዎችና ከወይኖችም ፍሬዎች (እንመግባችኋለን)፡፡ ከእርሱ ጠጅንና መልካም ምግብንም ትሠራላችሁ፡፡ በዚህም ውስጥ ለሚያስቡ ሕዝቦች በእርግጥ ተዓምር አልለ፡፡ 16|68|ጌታህም ወደ ንብ እንዲህ ሲል አስታወቀ «ከተራራዎች፣ ከዛፍም፣ (ሰዎች) ከሚሠሩትም (ቀፎ) ቤቶችን ያዢ፡፡ 16|69|«ከዚያም ከፍሬዎች ሁሉ ብይ፡፡ የጌታሽንም መንገዶች (ላንቺ) የተገሩ ሲኾኑ ግቢ፡፡» ከሆዶችዋ መልኮቹ የተለያዩ መጠጥ ይወጣል፡፡ በእርሱ ውስጥ ለሰዎች መድኃኒት አለበት፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች በእርግጥ ተዓምር አልለበት፡፡ 16|70|አላህም ፈጠራችሁ፤ ከዚያም ይገድላችኋል፡፡ ከእናንተም ከዕወቅት በኋላ ምንንም ነገር እንዳያውቅ ወደ ወራዳ ዕድሜ የሚመለስ ሰው አልለ፡፡ አላህ ዐዋቂ ቻይ ነው፡፡ 16|71|አላህም ከፊላችሁን በከፊሉ ላይ በሲሳይ አበለጠ፡፡ እነዚያም በላጭ የተደረጉት ሲሳያቸውን እጆቻቸው በያዙዋቸው (ባሮች) ላይ እነሱ በእርሱ ይተካከሉ ዘንድ መላሾች አይደሉም፡፡ ታዲያ በአላህ ጸጋ (ለእርሱ ተጋሪ በማድረግ) ይክዳሉን 16|72|አላህም ከነፍሶቻችሁ (ከጎሶቻችሁ) ለእናንተ ሚስቶችን አደረገ፡፡ ለእናንተም ከሚስቶቻችሁ ወንዶች ልጆችን፣ የልጅ ልጆችንም አደረገላችሁ፡፡ ከመልካሞችም ጸጋዎች ሰጣችሁ፡፡ ታድያ በውሸት (በጣኦት) ያምናሉን በአላህም ጸጋ እነሱ ይክዳሉን 16|73|ከአላህም ሌላ ከሰማያትም ከምድርም ምንንም ሲሳይ የማይሰጧቸውን (ምንንም) የማይችሉትንም ይግገዛሉ፡፡ 16|74|ለአላህም አምሳያዎችን አታድርጉ፡፡ አላህ (መሳይ እንደሌለው) ያውቃል፡፡ እናንተ ግን አታውቁም፡፡ 16|75|በምንም ላይ የማይችለውን በይዞታ ያለውን ባሪያና ከእኛ መልካም ሲሳይን የሰጠነውን እርሱም ከእርሱ (ከሰጠነው) በምስጢርና በግልጽ የሚለግሰውን (ነጻ) ሰው አላህ (ለጣዖትና ለርሱ) ምሳሌ አደረገ፡፡ (ሁለቱ) ይተካከላሉን ምስጋና ለአላህ ይኹን፡፡ በእውነቱ አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 16|76|አላህም ሁለትን ወንዶች (ለከሓዲና ለምእመን) ምሳሌ አደረገ፡፡ አንደኛቸው በምንም ነገር ላይ የማይችል ዲዳ ነው፡፡ እርሱም በጌታው ላይ ሸክም ነው፡፡ ወደ የትም ቢያዞረው በደግ ነገር አይመጣም፡፡ እርሱና ያ እርሱ በቀጥተናው መንገድ ላይ ኾኖ በማስተካከል የሚያዘው ሰው ይስተካከላሉን 16|77|በሰማያትና በምድርም ያለው ሩቅ ምስጢር የአላህ ነው፡፡ የሰዓቲቱም ነገር (መምጣቷ) እንደዓይን ቅጽበት እንጂ አይደለም፡፡ ወይ እርሱ ይበልጥ የቀረበ ነው፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 16|78|አላህም ከእናቶቻችሁ ሆዶች ምንም የማታውቁ ሆናችሁ አወጣችሁ፡፡ ታመሰግኑም ዘንድ ለእናንተ መስሚያን ማያዎችንም ልቦችንም አደረገላችሁ፡፡ 16|79|ወደ በራሪዎች በሰማይ አየር ውስጥ (ለመብረር) የተገሩ ሲኾኑ (ከመውደቅ) አላህ እንጂ ሌላ የማይዛቸው ኾነው አይመለከቱምን በዚህ ውስጥ ለሚያምኑ ሕዝቦች በእርግጥ ተዓምራቶች አሉ፡፡ 16|80|አላህም ከቤቶቻችሁ ለእናንተ መርጊያን አደረገላችሁ፡፡ ከእንስሳዎችም ቆዳዎች በጉዟችሁ ቀን በመቀመጫችሁም ቀን የምታቀልላቸውን ቤቶች ለናንተ አደረገላችሁ፡፡ ከበግዋ ሱፎች፣ ከግመልዋም ጠጉሮች፣ ከፍየልዋም ጠጉሮች የቤት ዕቃዎችን እስከ ጊዜም ድረስ መጠቃቀሚያን (አደረገላችሁ)፡፡ 16|81|አላህም ከፈጠረው ነገር ለእናንተ ጥላዎችን አደረገላችሁ፡፡ ከጋራዎችም ለእናንተ መከለያዎችን አደረገላችሁ፡፡ ሐሩርንም (ብርድንም) የሚጠብቋችሁን ልብሶች የጦራችሁንም አደጋ የሚጠብቋችሁን ጥሩሮች ለእናንተ አደረገላችሁ፡፡ እንደዚሁ ትሰልሙ ዘንድ ጸጋውን በእናንተ ላይ ይሞላል፡፡ 16|82|(ከኢስላም) ቢሸሹም ባንተ ላይ ያለብህ ግልጽ ማድረስ ብቻ ነው፡፡ 16|83|የአላህን ጸጋ ያውቃሉ፡፡ ከዚያም ይክዷታል፡፡ አብዛኞቻቸውም ከሓዲዎቹ ናቸው፡፡ 16|84|ከየሕዝቡም ሁሉ መስካሪን የምንቀሰቅስበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ ከዚያም ለእነዚያ ለካዱት (ንግግር) አይፈቀድላቸውም፡፡ እነሱም በወቀሳ አይታለፉም፡፡ 16|85|እነዚያም የበደሉት ቅጣቱን ባዩ ጊዜ ከእነሱ (ቅጣቱ) አይቀለልላቸውም፡፡ እነሱም ጊዜ አይስሰጡም፡፡ 16|86|እነዚያም ያጋሩት የሚያጋሩዋቸውን ባዩ ጊዜ «ጌታችን ሆይ! እነዚህ ከአንተ ሌላ እንገዛቸው የነበርነው ተጋሪዎቻችን ናቸው» ይላሉ፡፡ (አማልክቶች) «እናንተ በእርግጥ ውሸታሞች ናችሁ» የማለትንም ቃል ወደእነሱ ይጥላሉ፡፡ 16|87|(አጋሪዎቹ) በዚያ ቀንም ታዛዥነታቸውን ወደ አላህ ያቀርባሉ፡፡ ይቀጣጥፉት የነበሩትም ሁሉ ከእነርሱ ይጠፋቸዋል፡፡ 16|88|እነዚያ የካዱ፣ ከአላህም መንገድ የከለከሉ ያጠፉ በነበሩት ምክንያት ቅጣትን በቅጣት ላይ ጨመርንባቸው፡፡ 16|89|በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ ከጎሳቸው በእነሱ ላይ መስካሪን የምንቀሰቅስበትን አንተንም በእነዚህ (ሕዝቦች) ላይ መስካሪ አድርገን የምናመጣህን ቀን (አስታውስ)፡፡ መጽሐፉንም ለሁሉ ነገር አብራሪ፣ መሪም፣ እዝነትም፣ ለሙስሊሞችም አብሳሪ ኾኖ ባንተ ላይ አወረድነው፡፡ 16|90|አላህ በማስተካከል፣ በማሳመርም፣ ለዝምድና ባለቤት በመስጠትም ያዛል፡፡ ከአስከፊም (ከማመንዘር)፣ ከሚጠላም ነገር ሁሉ፣ ከመበደልም ይከለክላል፡፡ ትገነዘቡ ዘንድ ይገስጻችኋል፡፡ 16|91|ቃል ኪዳንም በገባችሁ ጊዜ በአላህ ቃል ኪዳን ሙሉ፡፡ መሓሎቻችሁንም ከአጠነከራችኋት በኋላ አላህን በእናንተ ላይ በእርግጥ መስካሪ ያደረጋችሁ ስትኾኑ አታፍርሱ፡፡ አላህ የምትሠሩትን ሁሉ ያውቃልና፡፡ 16|92|(ቃል ኪዳናችሁን በማፍረስ አንዲቱ) ሕዝብ እርሷ ከ(ሌላይቱ) ሕዝብ የበዛች ለመኾንዋ በመካከላችሁ መሓሎቻችሁን (ለክዳት) መግቢያ አድርጋችሁ የምትይዙ ስትኾኑ እንደዚያች ፈትልዋን ከጠነከረ በኋላ ትርትሮች አድርጋ እንዳፈረሰችው (ሴት) አትኹኑ፡፡ አላህ በእርሱ ይሞክራችኋል፤ በትንሣኤ ቀንም በእርሱ ትለያዩበት የነበራችሁትን ነገር ለእናንተ በእርግጥ ያብራራላችኋል፡፡ 16|93|አላህም በሻ ኖሮ አንዲት ሕዝብ ባደረጋችሁ ነበር፡፡ ግን የሚሻውን ሰው ያጠማል፡፡ የሚሻውንም ሰው ያቀናል፡፡ ትሠሩት ከነበራችሁትም ሁሉ በእርግጥ ትጠየቃላችሁ፡፡ 16|94|ጫማዎች ከተደላደሉ በኋላ እንዳይንዳለጡ ከአላህም መንገድ በመከልከላችሁ ምክንያት ቅጣትን እንዳትቀምሱ መሓሎቻችሁን በመካከላችሁ ለክዳት መግቢያ አድርጋችሁ አትያዙ፡፡ ለእናንተም (ያን ጊዜ) ታላቅ ቅጣት አላችሁ፡፡ 16|95|በአላህም ቃል ኪዳን ጥቂትን ዋጋ አትግዙ፡፡ የምታውቁ ብትኾኑ አላህ ዘንድ ያለው ምንዳ እርሱ ለእናንተ በላጭ ነውና፡፡ 16|96|እናንተ ዘንድ ያለው ሁሉ ያልቃል፡፡ አላህ ዘንድ ያለው ግን (ዘለዓለም) ቀሪ ነው፡፡ እነዚያንም የታገሱትን ይሠሩት በነበሩት በመልካሙ ምንዳቸውን እንመነዳቸዋለን፡፡ 16|97|ከወንድ ወይም ከሴት እርሱ አማኝ ኾኖ በጎን የሰራ መልካም ኑሮን በእርግጥ እናኖረዋለን፡፡ ይሠሩትም ከነበሩት ነገር በመልካሙ ምንዳቸውን እንመነዳቸዋለን፡፡ 16|98|ቁርኣንንም ባነበብህ ጊዜ እርጉም ከኾነው ሰይጣን በአላህ ተጠበቅ፡፡ 16|99|እርሱ በእነዚያ ባመኑትና በጌታቸው ላይ በሚጠጉት ላይ ለእርሱ ስልጣን የለውምና፡፡ 16|100|ስልጣኑ በእነዚያ በሚታዘዙት ላይና በእነዚያም እነርሱ በእርሱ (ምክንያት) አጋሪዎች በኾኑት ላይ ብቻ ነው፡፡ 16|101|በአንቀጽም ስፍራ አንቀጽን በለወጥን ጊዜ አላህም የሚያወርደውን ነገር አዋቂ ነው፡፡ «አንተ ቀጣፊ እንጂ ሌላ አይደለህም» ይላሉ፡፡ በእውነቱ አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 16|102|እነዚያን ያመኑትን ለማረጋጋት ሙስሊሞቹንም ለመምራትና ለማብሰር (ቁርኣንን) ቅዱሱ መንፈስ (ጂብሪል) እውነተኛ ሲኾን ከጌታህ አወረደው በላቸው፡፡ 16|103|እነርሱም «እርሱን (ቁርኣንን) የሚያስተምረው ሰው ብቻ ነው» ማለታቸውን በእርግጥ እናውቃለን፡፡ የዚያ ወደርሱ የሚያስጠጉበት ሰው ቋንቋ ዐጀም ነው፡፡ ይህ (ቁርአን) ግን ግልጽ ዐረብኛ ቋንቋ ነው፡፡ 16|104|እነዚያን በአላህ አንቀጾች የማያምኑትን አላህ አይመራቸውም፤ ለነሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 16|105|ውሸትን የሚቀጣጥፉት እነዚያ በአላህ አንቀጾች የማያምኑት ብቻ ናቸው፡፡ እነዚያም ውሸታሞቹ እነሱ ብቻ ናቸው፡፡ 16|106|ከእምነቱ በኋላ በአላህ የካደ ሰው (ብርቱ ቅጣት አልለው)፡፡ ልቡ በእምነት የረጋ ኾኖ (በክህደት ቃል በመናገር) የተገደደ ሰው ብቻ ሲቀር፡፡ ግን ልባቸውን በክሕደት የከፈቱ ሰዎች በነሱ ላይ ከአላህ ቁጣ አለባቸው፡፡ ለእነሱም ታላቅ ቅጣት አልላቸው፡፡ 16|107|ይህ (ቅጣት) እነሱ ቅርቢቱን ሕይወት ከመጨረሻይቱ በመምረጣቸው ምክንያትና አላህም ከሓዲዎችን ሕዝቦች የማያቀና በመኾኑ ነው፡፡ 16|108|እነዚያ እነርሱ በልቦቻቸው፣ በዓይኖቻቸውም፣ በጆሮዎቻቸውም ላይ አላህ ያተመባቸው ናቸው፡፡ እነዚያም ዝንጉዎቹ እነሱ ናቸው፡፤ 16|109|እነርሱ በመጨረሻይቱ ዓለም ከሳሪዎቹ እነሱ ለመኾናቸው ጥርጥር የለም፡፡ 16|110|ከዚያም ጌታህ ለእነዚያ ከተፈተኑ በኋላ ለተሰደዱት ከዚያም ለታገሉትና ለታገሱት (መሓሪ አዛኝ ነው)፡፡ ጌታህ ከእርሷ (ከፈተናዋ) በኋላ በእርግጥ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 16|111|ነፍስ ሁሉ ከራሷ ላይ የምትከራከር ኾና የምትመጣበትን ነፍስም ሁሉ የሠራችውን (ዋጋ) የምትቀበልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 16|112|አላህ ጸጥተኛ፣ የረካች፣ ሲሳይዋ ሰፊ ኾኖ ከየስፍራው ይመጣላት የነበረችውንና በአላህ ጸጋዎች የካደችውን አላህም ይሠሩት በነበሩት ኃጢኣት የረኃብንና የፍርሃትን ቅጣቶች ያቀመሳትን ከተማ (መካን) ምሳሌ አደረገ፡፡ 16|113|ከእነርሱ ውስጥ የኾነ መልክተኛም በእርግጥ መጣላቸው፡፡ አስተባበሉትም፡፡ እነሱም በዳዮች ኾነው ቅጣቱ ያዛቸው፡፡ 16|114|አላህም ከሰጣችሁ ሲሳይ የተፈቀደ ንጹሕ ሲኾን ብሉ፡፡ የአላህንም ጸጋ እርሱን የምትገዙት ብትሆኑ አመስግኑ፡፡ 16|115|በእናንተ ላይ እርም ያደረገው በክትንና ደምን፣ የአሳማንም ስጋ፣ ያንንም (በመታረድ ጊዜ) በእርሱ ከአላህ ስም ሌላ የተነሳበትን ብቻ ነው፡፡ አመጸኛም ወሰን አላፊም ሳይኾን (ለመብላት) የተገደደ ሰው (ይፈቀድለታል)፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 16|116|በአላህም ላይ ውሸትን ልትቀጣጥፉ ምላሶቻችሁ በሚመጥኑት ውሸት «ይህ የተፈቀደ ነው፤ ይህም እርም ነው» አትበሉ፡፡ እነዚያ በአላህ ላይ ውሸትን የሚቀጣጥፉ አይድኑም፡፡ 16|117|ጥቂት መጣቀም አላቸው፡፡ ለእነሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 16|118|በእነዚያም ይሁዳውያን በኾኑት ላይ ከአሁን በፊት በአንተ ላይ የተረክነውን ነገር እርም አድርገንባቸዋል፡፡ እኛም አልበደልናቸውም፡፡ ግን ነፍሶቻቸውን ይበድሉ ነበሩ፡፡ 16|119|ከዚያም ጌታህ ለእነዚያ በስሕተት መጥፎን ለሠሩና ከዚያም ከዚህ በኋላ ለተጸጸቱ ሥራቸውንም ላበጁ ጌታህ ከእርሷ በኋላ በእርግጥ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 16|120|ኢብራሂም ለአላህ ታዛዥ ወደ ቀጥተኛ ሃይማኖት ተዘንባይ ሕዝብ ነበር፡፡ ከአጋሪዎቹም አልነበረም፡፡ 16|121|ለጸጋዎቹ አመስጋኝ ነበር፤ መረጠው፡፡ ወደ ቀጥተኛውም መንገድ መራው፡፡ 16|122|በቅርቢቱም ዓለም በጎን ነገር ሰጠነው፡፡ እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም በእርግጥ ከመልካሞቹ ነው፡፡ 16|123|ከዚያም ወደ አንተ የኢብራሂምን ሃይማኖት ቀጥተኛ ሲኾን ተከተል፤ ከአጋሪዎቹም አልነበረም ማለት አወረድን፡፡ 16|124|ሰንበት (ክልክል) የተደረገው በእነዚያ በእርሱ በተለያዩበት ሰዎች ላይ ብቻ ነው፡፡ ጌታህም በትንሣኤ ቀን ይለያዩበት በነበሩት ነገር በመካከላቸው በእርግጥ ይፈርዳል፡፡ 16|125|ወደ ጌታህ መንገድ በብልሃትና በመልካም ግሳጼ (በለዘብታ ቃል) ጥራ፡፡ በዚያችም እርሷ መልካም በኾነችው (ዘዴ) ተከራከራቸው፡፡ ጌታህ እርሱ ከመንገዱ የተሳሳተውን ሰው ዐዋቂ ነው፡፡ እርሱም ቅን የኾኑትን ሰዎች ዐዋቂ ነው፡፡ 16|126|ብትበቀሉም በርሱ በተቀጣችሁበት ብጤ ተበቀሉ፡፡ ብትታገሱም እርሱ ለታጋሾች በእርግጥ በላጭ ነው፡፡ 16|127|ታገስም፤ መታገስህም በአላህ (ማስቻል) እንጂ አይደለም፡፡ በእነርሱም ላይ (ባያምኑ) አትተክዝ፡፡ (ባንተ ላይ) ከሚመክሩትም ተንኮል በጭንቀት ውስጥ አትኹን፡፡ 16|128|አላህ ከእነዚያ ከሚፈሩትና ከእነዚያም እነሱ መልካም ሠሪዎች ከኾኑት ጋር ነውና፡፡ 17|1|ያ ባሪያውን ከተከበረው መስጊድ ወደዚያ ዙሪያውን ወደ ባረክነው ወደ ሩቁ መስጊድ በሌሊት ውስጥ ያስኼደው (ጌታ) ጥራት ይገባው፡፡ ከተዓምራቶቻችን ልናሳየው (አስኼድነው)፡፡ እነሆ እርሱ (አላህ) ሰሚው ተመልካቺው ነው፡፡ 17|2|ሙሳንም መጽሐፉን ሰጠነው፡፡ ለእስራኤልም ልጆች መሪ አደረግነው፡፡ ከእኔ ሌላ መጠጊያን አትያዙ፤ (አልናቸውም)፡፡ 17|3|እናንተ ከኑሕ ጋር (በመርከቢቱ) የጫናቸው ዘሮች ሆይ! (አላህን ተገዙ) እርሱ በብዙ አመስጋኝ ባሪያ ነበርና፡፡ 17|4|ወደ እስራኤልም ልጆች በመጽሐፉ ውስጥ (እንዲህ በማለት) አወረድን፡፡ በምድር ላይ በእርግጥ ሁለት ጊዜ ታጠፋላችሁ፡፡ ትልቅንም ኩራት ትኮራላችሁ፡፡ 17|5|ከሁለቱ (ጊዜያቶች) የመጀመሪያይቱ ቀጠሮ በመጣም ጊዜ ለእኛ የኾኑን ባሮች የብርቱ ኃይል ባለቤቶች የኾኑትን በእናንተ ላይ እንልካለን፡፡ በቤቶችም መካከል ይመላለሳሉ፤ (ይበረብሩታል፡፡) ይህ ተፈጻሚ ቀጠሮም ነበር፡፡ 17|6|ከዚያም (በኋላ) ለእናንተ በእነሱ ላይ ድልን መለስንላችሁ፡፡ በገንዘቦችና በወንዶች ልጆችም ጨመርንላችሁ፡፡ በወገንም የበዛችሁ አደረግናችሁ፡፡ 17|7|መልካም ብትሠሩ ለነፍሶቻችሁ መልካምን ሠራችሁ፡፡ መጥፎንም ብትሠሩ በነርሱ (በነፍሶቻችሁ) ላይ ነው፤ (አልን)፡፡ የኋለኛይቱም (ጊዜ) ቀጠሮ በመጣ ጊዜ ፊቶቻችሁን ሊያስከፉ፣ መስጊዱንም በመጀመሪያ ጊዜ እንደገቡት ሊገቡ፣ ያሸነፉትንም ሁሉ (ፈጽመው) ማጥፋትን እንዲያጠፉ (እንልካቸዋልን)፡፡ 17|8|(በመጽሐፉም አልን) «ብትጸጸቱ፡- ጌታችሁ ሊያዝንላችሁ ይከጀላል፡፡ (ወደ ማጥፋት) ብትመለሱም እንመለሳለን፡፡ ገሀነምንም ለከሓዲዎች ማሰሪያ አደርገናል፡፡ 17|9|ይህ ቁርኣን ወደዚያች እርሷ ቀጥተኛ ወደ ኾነችው መንገድ ይመራል፡፡ እነዚያንም በጎ የሚሠሩትን ምእመናን ለእነሱ ታላቅ ምንዳ ያላቸው መኾኑን ያበስራል፡፡ 17|10|እነዚያም በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ለእነሱ አሳማሚ ቅጣትን አዘጋጅተንላቸዋል፤ 17|11|ሰው መልካምን ነገር እንደሚለምን ሁሉ፤ መጥፎንም ነገር ይለምናል፡፡ ሰውም ቸኳላ ነው፡፡ 17|12|ሌሊትንና ቀንንም (ለችሎታችን) ምልክቶች አደረግን፡፡ የሌሊትን ምልክትም አበስን፡፡ የቀንን ምልክትም የምታሳይ አደረግን፡፡ (ይህም የኾነበት) ከጌታችሁ ትርፍን ልትፈልጉ የዓመታትንም ቁጥርና ሒሳብንም ታውቁ ዘንድ ነው፡፡ ነገሩንም ሁሉ ለያይተን ዘረዘርነው፡፡ 17|13|ሰውንም ሁሉ በራሪውን (ሥራውን) በአንገቱ አስያዝነው፡፡ ለእርሱም በትንሣኤ ቀን የተዘረጋ ኾኖ የሚያገኘው የኾነን መጽሐፍ እናወጣለታለን፡፡ 17|14|«መጽሐፍህን አንብብ፡፡ ዛሬ ባንተ ላይ ተቆጣጣሪነት በነፍስህ በቃ» (ይባላል)፡፡ 17|15|የተመራ ሰው የሚመራው ለራሱ ብቻ ነው፡፡ የተሳሳተም ሰው የሚሳሳተው (ጉዳቱ) በእርሷ ላይ ነው፡፡ ተሸካሚም (ነፍስ) የሌላይቱን ኃጢኣት አትሸከምም፡፡ መልዕክተኛንም እስከምንልክ ድረስ የምንቀጣ አይደለንም፡፡ 17|16|ከተማንም ለማጥፋት በፈለግን ጊዜ ባለ ጸጋዎችዋን እናዛለን፡፡ በውስጧም ያምጻሉ፡፡ በእርሷም ላይ ቃሉ (ቅጣቱ) ይፈጸምባታል፡፡ ማጥፋትንም እናጠፋታለን፡፡ 17|17|ከኑሕም በኋላ ከክፍለ ዘመናት ሰዎች ያጠፋናቸው ብዙዎች ናቸው፡፡ የባሮቹንም ኃጢኣቶች ውስጠ ዐዋቂ ተመልካች መኾን በጌታህ በቃ፡፡ 17|18|ቸኳይቱን ዓለም (በሥራው) የሚፈልግ ሰው ለእርሱ በርሷ ውስጥ የሻነውን (ጸጋ) ለምንሻው ሰው እናስቸኩልለታለን፡፡ ከዚያም ለእርሱ ገሀነምን (መኖሪያ) አድርገንለታል፡፡ ተወቃሽ ብራሪ ኾኖ ይገባታል፡፡ 17|19|መጨረሻይቱንም ዓለም የፈለገ ሰው እርሱ አማኝ ኾኖ ለርሷ (ተገቢ) ሥራዋን የሠራም ሰው እነዚህ ሥራቸው የተመሰገነ ይኾናል፡፡ 17|20|ሁሉንም እነዚህንና እነዚያን ከጌታህ ስጦታ (በዚህ ዓለም) እንጨምርላቸዋለን፡፡ የጌታህም ስጦታ (በዚች ዓለም) ክልክል አይደለም፡፡ 17|21|ከፊላቸውን በከፊሉ ላይ እንዴት እንዳበለጥን ተመልከት፡፡ የመጨረሻያቱም አገር በማዕረጎች በጣም የከበረችና በመብለጥም የተለቀች ናት፡፡ 17|22|ከአላህ ጋር ሌላን አምላክ አታድርግ የተወቀስክ ረዳት የሌለህ ትኾናለህና፤ 17|23|ጌታህም (እንዲህ ሲል) አዘዘ፡- እርሱን እንጂ ሌላን አትገዙ፡፡ በወላጆቻችሁም መልካምን ሥሩ፡፡ በአንተ ዘንድ ኾነው አንዳቸው ወይም ሁለታቸው እርጅናን ቢደርሱ ፎህ አትበላቸው፡፡ አትገላምጣቸውም፡፡ ለእነርሱም መልካምን ቃል ተናገራቸው፡፡ 17|24|ለሁለቱም ከእዝነትህ የመዋረድን ክንፍ ዝቅ አድርግላቸው፡፡ «ጌታዬ ሆይ! በሕፃንነቴ (በርኅራኄ) እንዳሳደጉኝ እዘንልላቸውም» በል፡፡ 17|25|ጌታችሁ በነፍሶቻችሁ ውስጥ ያለውን ሁሉ አዋቂ ነው፡፡ ታዛዦችም ብትኾኑ (በመሳሳትም ብታጠፉ) እርሱ ለተመላሾች መሓሪ ነው፡፡ 17|26|ለዝምድና ባለቤትም መብቱን ስጥ፡፡ ለምስኪንና ለመንገደኛም (ስጥ)፡፡ ማባከንንም አታባክን፡፡ 17|27|አባካኞች የሰይጣናት ወንድሞች ናቸውና፡፡ ሰይጣንም ለጌታው ብርቱ ከሓዲ ነው፡፡ 17|28|ከጌታህም የምትከጅላትን ጸጋ ለማጣት ከእነርሱ ብትዞር ለእነሱ ልዝብን ቃል ተናገራቸው፡፡ 17|29|እጅህንም ወደ አንገትህ የታሰረች አታድርግ፡፡ መዘርጋትንም ሁሉ አትዘርጋት፤ የተወቀስክ የተቆጨኽ ትኾናለህና፡፡ 17|30|ጌታህ ሲሳይን ለሚሻው ሰው ያሰፋል፤ ያጠባልም፡፡ እርሱ በባሮቹ ኹኔታ ውስጠ ዐዋቂ ተመልካች ነውና፡፡ 17|31|ልጆቻችሁንም ድኽነትን ለመፍራት አትግደሉ፡፡ እኛ እንመግባቸዋለን፡፡ እናንተንም (እንመግባለን)፡፡ እነርሱን መግደል ታላቅ ኃጢኣት ነውና፡፡ 17|32|ዝሙትንም አትቅረቡ፡፡ እርሱ በእርግጥ መጥፎ ሥራ ነውና፡፡ መንገድነቱም ከፋ! 17|33|ያቺንም አላህ ያወገዛትን ነፍስ ያለ ሕግ አትግደሉ፡፡ የተበደለም ኾኖ የተገደለ ሰው ለዘመዱ (በገዳዩ ላይ) በእርግጥ ስልጣንን አድርገናል፡፡ በመግደልም ወሰንን አይለፍ፤ እርሱ የተረዳ ነውና፡፡ 17|34|የየቲምንም ገንዘብ የብርታቱን ጊዜ እስኪደርስ ድረስ በዚያች እርሷ መልካም በኾነች ኹኔታ እንጂ አትቅረቡ፡፡ በኪዳናችሁም ሙሉ፡፡ ኪዳን የሚጠየቁበት ነውና፡፡ 17|35|በሰፈራችሁም ጊዜ ስፍርን ሙሉ፡፡ በትክክለኛው ሚዛንም መዝኑ፡፡ ይህ መልካም ነገር ነው፡፡ መጨረሻውም ያማረ ነው፡፡ 17|36|ለአንተም በርሱ ዕውቀት የሌለህን ነገር አትከተል፡፡ መስሚያ፣ ማያም፣ ልብም እነዚህ ሁሉ (ባለቤታቸው) ከእነሱ ተጠያቂ ነውና፡፡ 17|37|በምድርም ላይ የተንበጣረረክ ሆነህ፤ አትሂድ፡፡ አንተ ፈጽሞ ምድርን አትሰረጉድምና በርዝመትም ፈጽሞ ጋራዎችን አትደርስምና፡፡ 17|38|ይህ ሁሉ መጥፎው (አሥራ ሁለቱ ክልክሎች) እጌታህ ዘንድ የተጠላ ነው፡፡ 17|39|ይህ ጌታህ ከጥበቡ ወደ አንተ ካወረደው ነገር ነው፡፡ ከአላህም ጋር ሌላን አምላክ አታድርግ የተወቀስክ የተባረርክ ኾነህ በገሀነም ውስጥ ትጣላለህና፡፡ 17|40|ጌታችሁ በወንዶች ልጆች መረጣችሁና ከመላእክት ሴቶችን (ልጆች) ያዝን እናንተ ከባድን ቃል በእርግጥ ትናገራላችሁ፡፡ 17|41|ይገሰጹም ዘንድ በዚህ ቁርኣን ውስጥ ደጋግመን በእርግጥ ገለጽን፡፡ መበርገግንም እንጂ ሌላን አይጨመርላቸውም፡፡ 17|42|(ሙሐመድ ሆይ) በላቸው «እንደምትሉት ከእርሱ ጋር አማልክት በነበሩ ኖሮ ያን ጊዜ ወደ ዐርሹ ባለቤት መንገድን በፈለጉ ነበር፡፡» 17|43|ጥራት ይገባው፡፡ ከሚሉትም ነገር ሁሉ ከፍ ያለን ልቅና ላቀ፡፡ 17|44|ሰባቱ ሰማያትና ምድርም በውስጣቸውም ያለው ሁሉ ለእርሱ ያጠራሉ፡፡ ከነገርም ሁሉ ከማመስገን ጋር የሚያጠራው እንጂ አንድም የለም፡፡ ግን ማጥራታቸውን አታውቁትም፡፡ እርሱ ታጋሽ መሓሪ ነው፡፡ 17|45|ቁርኣንንም ባነበብክ ጊዜ ባንተና በእነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም በማያምኑት ሰዎች መካከል የሚሸሸግን ግርዶሽ አድርገናል፡፡ 17|46|እንዳያውቁትም በልቦቻቸው ላይ ሽፋንን በጆሮቻቸውም ውስጥ ድንቁርናን አደረግን፡፡ ጌታህንም ብቻውን ኾኖ በቁርኣን ባወሳኸው ጊዜ የሚሸሹ ኾነው በጀርባዎቻቸው ላይ ይዞራሉ፡፡ 17|47|እኛ ወደ አንተ በሚያዳምጡ ጊዜ እነሱም በሚንሾካሾኩ ጊዜ በዳዮች (እርስ በርሳቸው) የተደገመበትን ስው እንጂ አትከተሉም በሚሉ ጌዜ በእርሱ የሚያዳምጡበትን ምክንያት ዐዋቂ ነን፡፡ 17|48|ምሳሌዎችን ለአንተ እንዴት እንዳደረጉልህና እንደ ተሳሳቱ ተመልከት፡፡ (ወደ እውነቱ ለመድረስ) መንገድንም አይችሉም፡፡ 17|49|አሉም «እንዴት አጥንቶችና ብስብሶች በኾን ጊዜ እኛ አዲስ ፍጥረት ኾነን በእርግጥ ተቀስቃሾች ነን» 17|50|በላቸው «ድንጋዮችን ወይም ብረትን ሁኑ» 17|51|«ወይም በልቦቻችሁ ውስጥ የሚተልቅን ፍጥረት (ኹኑ መቀስቀሳችሁ አይቀርም)፡፡» «የሚመልሰንም ማነው» ይላሉ፡፡ ያ በመጀመሪያ ጊዜ የፈጠራችሁ ነው» በላቸው፡፡ ወደ አንተም ራሶቻቸውን ይነቀንቃሉ፡፡ «እርሱም መቼ ነው» ይላሉ፡፡ «(እርሱ) ቅርብ ሊኾነን ይቻላል በላቸው፡፡ 17|52|(እርሱም) የሚጠራችሁና (አላህን) አመስጋኞቹ ኾናችሁ ጥሪውን የምትቀበሉበት ጥቂትንም (ቀኖች) እንጂ ያልቆያችሁ መኾናችሁን የምትጠራጠሩበት ቀን ነው፤ (በላቸው)፡፡ 17|53|ለባሮቼም በላቸው፡- ያችን እርሷ መልካም የኾነችውን (ቃል) ይናገሩ፡፡ ሰይጣን በመካከላቸው ያበላሻልና፡፡ ሰይጣን ለሰው ግልጽ ጠላት ነውና፡፡ 17|54|ጌታችሁ በእናንተ (ኹኔታ) ዐዋቂ ነው፡፡ ቢሻ ያዝንላችኋል፤ ወይም ቢሻ ይቀጣችኋል፡፡ በእነሱም ላይ ኃላፊ ኾነህ አላክንህም፡፡ (አታስገድዳቸውም)፡፡ 17|55|ጌታህም በሰማያትና በምድር ያለውን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ ከፊሉንም ነቢያት በከፊሉ ላይ በእርግጥ አብልጠናል፡፡ ዳውድንም ዘቡርን ሰጥተነዋል፡፡ 17|56|«እነዚያን ከእርሱ ሌላ (አማልክት) የምትሏቸውን ጥሩ፡፡ ከእናንተም ላይ ጉዳትን ማስወገድን (ወደ ሌላ) ማዞርንም አይችሉም» በላቸው፡፤ 17|57|እነዚያ እነርሱ የሚግገዟቸው ማንኛቸውም (ወደ አላህ) በጣም ቀራቢያቸው ወደ ጌታቸው መቃረቢያን (ሥራ) ይፈልጋሉ፡፡ እዝነቱንም ይከጅላሉ፡፡ ቅጣቱንም ይፈራሉ፡፡ የጌታህ ቅጣት የሚፈራ ነውና፡፡ 17|58|አንዲትም ከተማ የለችም እኛ ከትንሣኤ ቀን በፊት አጥፊዎችዋ ወይም ብርቱን ቅጣት ቀጭዎችዋ ብንኾን እንጂ፡፡ ይህ በመጽሐፉ የተጻፈ ነው፡፡ 17|59|ታምራቶችንም ከመላክ የቀድሞዎቹ ሰዎች በእርሷ ማስተባበልና (መጥፋት) እንጂ ሌላ አልከለከለንም፡፡ ለሰሙድም ግመልን ግልጽ ተዓምር ኾና ሰጠናቸው፡፡ በእርሷም በደሉ፡፡ ተዓምራቶችንም ለማስፈራራት እንጂ አንንልክም፡፡ 17|60|ላንተም ጌታህ (ዕውቀቱ) በሰዎቹ ከበበ ባልንህ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ያችንም (በሌሊቱ ጉዞ በዓይንህ) ያሳየንህን ትርዕይት ለሰዎች ፈተና እንጂ አላደረግናትም፡፡ በቁርኣንም የተረገመችውን ዛፍ (እንደዚሁ ፈተና እንጂ አላደረግንም)፡፡ እናስፈራራቸዋለንም፤ ታላቅንም ጥመት እንጂ አይጨምርላቸውም፡፡ 17|61|ለመላእክትም ለአደም ስገዱ ባልናቸው ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ወዲያውም ሰገዱ፤ ኢብሊስ ብቻ ሲቀር፡፡ «ከጭቃ ለፈጠርከው ሰው እሰግዳለሁን» አለ፡፡ 17|62|«ንገረኝ ይህ ያ በእኔ ላይ ያበለጥከው ነውን እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ ብታቆየኝ ዘሮቹን ጥቂቶች ሲቀሩ ወደ ስህተት በእርግጥ እስባቸዋለሁ» አለ፡፡ 17|63|(አላህም) አለው «ኺድ፤ ከእነሱም የተከተለህ ገሀነም የተሟላች ቅጣት ስትኾን ፍዳችሁ ናት፡፡ 17|64|«ከእነሱ የቻልከውንም ሰው በድምጽህ አታል፡፡ በእነሱም ላይ በፈረሰኞችህ፣ በእግረኞችህም ኾነህ ለልብ፡፡ በገንዘቦቻቸውም፣ በልጆቻቸውም ተጋራቸው፣ ተስፋ ቃልም ግባላቸው፡፡ ሰይጣንም ማታለልን እንጂ ተስፋ ቃልን አይገባላቸውም፡፡ 17|65|«ባሮቼ በእነሱ ላይ ፈጽሞ ላንተ ስልጣን የለህም፡፡ መጠጊያም በጌታህ በቃ፡፡» 17|66|ጌታችሁ ያ ከችሮታው ትፈልጉ ዘንድ መርከቦችን በባሕር ለይ ለእናንተ የሚነዳላችሁ ነው፡፡ እነሆ እርሱ ለናንተ አዛኝ ነውና፡፡ 17|67|በባሕሩም ውስጥ ጉዳት ባገኛችሁ ጊዜ የምትጠሩዋቸው (አማልክት) ሁሉ ከእርሱ (ከአላህ) በቀር ይጠፋሉ፡፡ ወደ የብስም በማድረስ ባዳናችሁ ጊዜ (እምነትን) ትተዋላችሁ፡፡ ሰውም በጣም ከሓዲ ነው፡፡ 17|68|የየብሱን በኩል (ምድርን) በእናንተ መገልበጡን ወይም ጠጠርን የያዘ ንፋስን በእናንተ ላይ መላኩን ከዚያም ለእናንተ ጠባቂ አለማግኘታችሁን አትፈሩምን 17|69|ወይስ ሌላ ጊዜ ወደ እርሱ (ወደ ባሕር) የሚመልሳችሁ ወዲያውም በእናንተ ላይ ብርቱን ነፋስ የሚልክ በክሕደታችሁም ምክንያት የሚያሰጥማችሁ መኾኑን ከዚያም በኛ ላይ በእርሱ ተከታይን (ረዳትን) ለእናንተ የማታገኙ መኾናችሁን አትፈሩምን 17|70|የአደምንም ልጆች በእርግጥ (ከሌላው ፍጡር) አከበርናቸው፡፡ በየብስና በባህርም አሳፈርናቸው፡፡ ከመልካሞችም (ሲሳዮች) ሰጠናቸው፡፡ ከፈጠርናቸውም ፍጡሮች በብዙዎቹ ላይ ማብለጥን አበለጥናቸው፡፡ 17|71|ሰዎችን ሁሉ በመሪያቸው የምንጠራበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ መጽሐፉንም በቀኙ የተሰጠ ሰው እነዚያ መጽሐፋቸውን ያነባሉ፡፡ በተምር ፍሬ ስንጥቅ ላይ ያለውን ክር ያክል እንኳ አይበደሉም፡፡ 17|72|በዚህችም ዓለም (ልበ) ዕውር የኾነ ሰው እርሱ በመጨረሻይቱም (ዓለም) ይበልጥ ዕውር ነው፡፡ መንገድንም በጣም የተሳሳተ ነው፡፤ 17|73|እነሆ ከዚያም ወደ አንተ ካወረድነው ሌላን በእኛ ላይ ትዋሽ ዘንድ ሊፈትኑህ በእርግጥ ተቃረቡ፡፡ ያን ጊዜም ወዳጅ አድርገው በያዙህ ነበር፡፡ 17|74|ባላረጋንህም ኖሮ ወደነሱ ጥቂትን (ዝንባሌ) ልትዘነበል በእርግጥ በተቃረብክ ነበር፡፡ 17|75|ያን ጊዜ የሕይወትን ድርብ (ቅጣት) የሞትንም ድርብ (ቅጣት) ባቀመስንህ ነበር፡፡ ከዚያም ላንተ በኛ ላይ ረዳትን አታገኝም ነበር፡፡ 17|76|ከምድሪቱም (ከዓረብ ምድር) ከርሷ ያወጡህ ዘንድ ሊያሸብሩህ በእርግጥ ተቃረቡ፡፡ ያን ጊዜም ከአንተ በኋላ ጥቂትን ጊዜ እንጂ አይቆዩም ነበር፡፡ 17|77|ከመልክተኞቻችን ካንተ በፊት በእርግጥ እንደላክናቸው ሰዎች ልማድ ብጤ (ይጠፉ ነበር)፡፡ ለልማዳችንም መለወጥን አታገኝም፡፡ 17|78|ሶላትን ከፀሐይ መዘንበል እስከ ሌሊት ጨለማ ድረስ ስገድ፡፡ የጎህንም ሶላት ስገድ፡፡ የጎህ ሶላት (መላእክት) የሚጣዱት ነውና፡፡ 17|79|ከሌሊትም ላንተ ተጨማሪ የኾነችን ሶላት በእርሱ (በቁርኣን) ስገድ፡፡ ጌታህ ምስጉን በኾነ ስፍራ በእርግጥ ያቆምሃል፡፡ 17|80|በልም ጌታዬ ሆይ! የተወደደን ማግባት አግባኝ፡፡ የተወደደንም ማውጣት አውጣኝ፡፡ ለእኔም ከአንተ ዘንድ የተረዳን ስልጣን አድርግልኝ፡፡ 17|81|በልም «እውነት መጣ ውሸትም ተወገደ፤ እነሆ ውሸት ተወጋጅ ነውና፡፡» 17|82|ከቁርኣንም ለምእመናን መድኀኒትና እዝነት የኾነን እናወርዳለን፡፡ በዳዮችንም ከሳራን እንጂ ሌላ አይጨምርላቸውም፡፡ 17|83|በሰውም ላይ ጸጋችንን በለገስን ጊዜ (ከምስጋና) ይዞራል፡፡ ጎኑንም (ከእውነት) ያርቃል፡፡ ችግርም በነካው ጊዜ ተስፋ ቆራጭ ይኾናል፡፡ 17|84|«ሁሉም በሚመስለው መንገዱ ላይ ይሠራል፡፡ ጌታችሁም እርሱ መንገዱ ቀጥተኛ የኾነውን ሰው ዐዋቂ ነው በላቸው፡፡ 17|85|ከሩሕም ይጠይቁሃል፡፡ «ሩሕ ከጌታዬ ነገር ነው ከዕውቀትም ጥቂትን እንጂ አልተሰጣችሁም» በላቸው፡፡ 17|86|ብንሻም ያንን ወዳንተ ያወረድነውን በእርግጥ እናስወግዳለን፡፡ ከዚያም ላንተ በእኛ ላይ በርሱ (ለማስመለስ) ተያዢን አታገኝም፡፡ 17|87|ግን ከጌታህ በኾነው እዝነት (ጠበቅነው)፡፡ ችሮታው ባንተ ላይ ታላቅ ነውና፡፤ 17|88|«ሰዎችም ጋኔኖችም የዚህን ቁርኣን ብጤ በማምጣት ላይ ቢሰበሰቡ ከፊላቸው ለከፊሉ ረዳት ቢሆንም እንኳ ብጤውን አያመጡም» በላቸው፡፡ 17|89|በዚህም ቁርኣን ውስጥ ከምሳሌው ሁሉ ለሰዎች በእርግጥ መላለስን፡፡ አብዛኞቹም ሰዎች ክህደትን እንጂ ሌላን እምቢ አሉ፡፡ 17|90|አሉም «ለኛ ከምድር ምንጭን እስከምታፈነዳን ለአንተ አናምንም፡፡» 17|91|«ወይም ከዘምባባዎችና ከወይን የኾነች አትክልት ለአንተ እስከምትኖርህና በመካከልዋም ጂረቶችን በብዛት እስከምታንቧቧ፡፡ 17|92|«ወይም እንደምትለው ከሰማይ ቁራጮችን በኛ ላይ እስከምታወድቅ፤ ወይም አላህንና መላእክትን በግልጽ እስከምታመጣ፡፡ 17|93|«ወይም ከወርቅ የኾነ ቤት ላንተ እስከሚኖርህ፤ ወይም በሰማይ እስከምትወጣ፤ ለመውጣትህም በእኛ ላይ የምናነበው የኾነን መጽሐፍ እስከምታወርድልን ድረስ ፈጽሞ አናምንልህም» (አሉ)፡፡ «ጌታዬ ጥራት ይገባው፤ እኔ ሰው መልክተኛ እንጂ ሌላ አይደለሁም» በላቸው፡፡ 17|94|ሰዎችንም መሪ (ቁርኣን) በመጣላቸው ጊዜ ከማመን «አላህ ሰውን መልክተኛ አድርጎ ላከን» ማለታቸው እንጂ ሌላ አልከለከላቸውም፡፡ 17|95|«በምድር ላይ ረግተው የሚኼዱ መላእክት በነበሩ ኖሮ በእነሱ ላይ (ከጎሳቸው) የመልአክን መልክተኛ ባወረድን ነበር» በላቸው፡፡ 17|96|«በእኔና በእናንተ መካከል መስካሪ በአላህ በቃ፡፡ እርሱ በባሮቹ (ነገር) ውስጥ ዐዋቂ ተመልካች ነውና» በላቸው፡፡ 17|97|አላህም ያቀናው ሰው ቅኑ እርሱ ብቻ ነው፡፡ ያጠመማቸውም ሰዎች ከእርሱ ሌላ ለእነርሱ ፈጽሞ ረዳት አታገኝላቸውም፡፡ በትንሣኤ ቀንም ዕውሮች፣ ዲዳዎችም ደንቆሮዎችም ኾነው በፊቶቻቸው ላይ (እየተጎተቱ) እንሰበስባቸዋለን፡፡ መኖሪያቸው ገሀነም ናት፡፡ (ነዲድዋ) በደከመች ቁጥር መንቀልቀልን እንጨምርባቸዋለን፡፤ 17|98|ይህ (ቅጣት)፤ እነርሱ በአንቀጾቻችን ስለ ካዱና «አጥንቶችና ብስብሶች በኾን ጊዜ እኛ አዲስ ፍጥረት ኾነን ተቀስቃሾች ነን» ስላሉም ፍዳቸው ነው፡፡ 17|99|ያ ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ አላህ ብጤያቸውን በመፍጠር ላይ ቻይ መኾኑን በእርሱ ጥርጣሬ የሌለበትም ጊዜ (ለሞትም ለትንሣኤም) ለእነርሱ የወሰነ መኾኑን አላወቁምን በደለኞችም ከክህደት በቀር እምቢ አሉ፡፡ 17|100|«እናንተ የጌታዬን የችሮታ መካዚኖች ብትይዙ ኖሮ ያን ጊዜ በማውጣታችሁ ማለቋን በመፍራት በጨበጣችሁ ነበር፡፡ ሰውም በጣም ቆጣቢ ነው፡፡» 17|101|ለሙሳም ግልጽ የኾኑን ዘጠኝ ተዓምራቶች በእርግጥ ሰጠነው፡፡ በመጣቸውም ጊዜ የእስራኤልን ልጆች (ከፈርዖን እንዲለቀቁ) ጠይቅ (አልነው)፡፡ ፈርዖንም «ሙሳ ሆይ! እኔ የተደገመብህ መኾንህን በእርግጥ እጠረጥራለሁ» አለው፡፡ 17|102|(ሙሳም) «እነዚህን (ተዓምራቶች) መገሰጫዎች ሲኾኑ የሰማያትና የምድር ጌታ እንጂ ሌላ እንዳላወረዳቸው በእርግጥ ዐውቀሃል፡፡ እኔም ፈርዖን ሆይ! የምትጠፋ መኾንህን በእርግጥ እጠረጥርሃለሁ» አለው፡፡ 17|103|ከምድርም ሊቀሰቅሳቸው አሰበ፡፡ እርሱንና ከእርሱ ጋር የነበሩትንም ሰዎች ሁሉንም አሰጠምናቸው፡፡ 17|104|ከእርሱም በኋላ ለእሰራኤል ልጆች «ምድሪቱን ተቀመጡባት የኋለኛይቱም (ሰዓት) ቀጠሮ በመጣ ጊዜ እናንተን የተከማቻችሁ ስትኾኑ እናመጣችኋለን» አልናቸው፡፡ 17|105|(ቁርኣንን) በውነትም አወረድነው፡፡ በእውነትም ወረደ፡፡ አንተንም አብሳሪና አስጠንቃቂ አድርገን እንጂ አልላክንህም፡፡ 17|106|ቁርኣንንም በሰዎች ላይ በዝግታ ላይ ኾነህ ታነበው ዘንድ ከፋፈልነው፡፡ ቀስ በቀስ ማውረድንም አወረድነው፡፡ 17|107|«በእርሱ እመኑ ወይም አትመኑ» በላቸው፤ እነዚያ ከእርሱ በፊት ዕውቀትን የተሰጡት በእነሱ ላይ በተነበበ ጊዜ ሰጋጆች ኾነው በሸንጎበቶቻቸው ላይ ይወድቃሉ፤ 17|108|ይላሉም «ጌታችን ጥራት ይገባው! እነሆ የጌታችን ተስፋ ተፈጻሚ ነው፡፡» 17|109|እያለቀሱም በሸንጎበቶቻቸው ላይ ይወድቃሉ (አላህን) መፍራትንም ይጨምራላቸዋል፡፡ 17|110|«አላህን ጥሩ፤ ወይም አልረሕማንን ጥሩ፤ (ከሁለቱ) ማንኛውንም ብትጠሩ (መልካም ነው)፡፡ ለእርሱ መልካም ስሞች አሉትና» በላቸው፡፡ በስግደትህም (ስታነብ) አትጩህ፡፡ በእርሷም ድምጽህን ዝቅ አታድርግ በዚህም መካከል መንገድን ፈልግ፡፡ 17|111|«ምስጋና ለአላህ ለዚያ ልጅን ላልያዘው፣ ለእርሱም በንግሥናው ተጋሪ ለሌለው፣ ለእርሱም ከውርደት ረዳት ለሌለው ይገባው በልም፡፡ ማክበርንም አክብረው፡፡» 18|1|ምስጋና ለአላህ ለዚያ መጽሐፉን በውስጡ መጣመምን ያላደረገበት ሲሆን በባሪያው ላይ ላወረደው ይገባው፡፡ 18|2|ቀጥተኛ ሲሆን ከእርሱ ዘንድ የኾነን ብርቱን ቅጣት ሊያስፈራራበት፣ እነዚያንም በጎ ሥራዎችን የሚሠሩትን ምእመናን ለነሱ መልካም ምንዳ ያላቸው መኾኑን ሊያበስርበት፤ (አወረደው)፡፡ 18|3|በእርሱ ውስጥ ዘለዓለም የሚቆዩበት ሲኾኑ (ያላቸው መኾኑን)፡፡ 18|4|እነዚያንም «አላህ ልጅን ይዟል» ያሉትን ሊያስፈራራበት (አወረደው)፡፡ 18|5|ለእነሱም ለአባቶቻቸውም በርሱ ምንም እውቀት የላቸውም፡፡ ከአፎቻቸው የምትወጣውን ቃል ምን አከበዳት! ውሸትን እንጂ አይናገሩም፡፡ 18|6|በዚህም ንግግር (በቁርኣን) ባያምኑ በፈለጎቻቸው ላይ በቁጭት ነፍስህን አጥፊ ልትሆን ይፈራልሃል፡፡ 18|7|እኛ ማንኛቸው ሥራው ያማረ መኾኑን ልንፈትናቸው በምድር ላይ ያለን ሁሉ ለእርሷ ጌጥ አደረግን፤ 18|8|እኛም በእርሷ ላይ ያለውን (በመጨረሻ) በእርግጥ በቃይ የሌለበት ምልጥ ዐፈር አድራጊዎች ነን፡፡ 18|9|የዋሻውና የሰሌዳው ባለቤቶች ከተዓምራቶቻችን ሲሆኑ ግሩም መሆናቸውን አሰብክን 18|10|ጎበዞቹ ወደ ዋሻው በተጠጉና «ጌታችን ሆይ! ከአንተ ዘንድ እዝነትን ስጠን፤ ለእኛም ከነገራችን ቅንን አዘጋጅልን» ባሉ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 18|11|በዋሻውም ውስጥ የተቆጠሩን ዓመታት በጆሮዎቻቸው ላይ መታንባቸው፡፡ 18|12|ከዚያም ከሁለቱ ክፍሎች ለቆዩት ጊዜ ልክ ያረጋገጠው ማንኛው መሆኑን ልናውቅ አስነሳናቸው፡፡ 18|13|እኛ ወሬያቸውን በአንተ ላይ በእውነት እንተርካለን፡፡ እነሱ በጌታቸው ያመኑ ጎበዞች ናቸው፡፡ መመራትንም ጨመርንላቸው፡፡ 18|14|(በንጉሣቸው ፊት) በቆሙና «ጌታችን የሰማያትና የምድር ጌታ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክን አንገዛም፡፡ ያን ጊዜ (ሌላን ብናመልክ) ወሰን ያለፈን (ንግግር) በእርግጥ ተናገርን፡፡» ባሉ ጊዜ ልቦቻቸውን አጠነከርን፡፡ 18|15|«እነዚህ ሕዝቦቻችን ከእርሱ ሌላ አማልክትን ያዙ፤ (እውነተኞች ከኾኑ) በእነርሱ ላይ ግልጽ ማስረጃን ለምን አያመጡም በአላህም ላይ ውሸትን ከሚቀጣጥፍ ይበልጥ በዳይ ማነው» (አሉ)፡፡ 18|16|«እነርሱንና ያንን ከአላህ ሌላ የሚግገዙትን በተለያችሁ ጊዜ ወደ ዋሻው ተጠጉ፡፡ ጌታችሁ ለእናንተ ከችሮታው ይዘረጋላችኋልና፤ ከነገራችሁም ለእናንተ መጠቃቀሚያን ያዘጋጅላችኋል» (ተባባሉ)፡፡ 18|17|ፀሐይንም በወጣች ጊዜ ከዋሻቸው ወደ ቀኝ ጎን ስታዘነብል ታያታለህ፡፡ በገባችም ጊዜ እነርሱ ከእርሱ በሰፊው ስፍራ ውስጥ ኾነው ሳሉ ወደ ግራ በኩል ትተዋቸዋለች፡፡ ይህ ከአላህ ተዓምራቶች ነው፡፡ አላህ የሚያቀናው ሰው ቅኑ እርሱ ብቻ ነው፡፡ የሚያጠመውም ሰው ለርሱ አቅኝን ረዳት አታገኝለትም፡፡ 18|18|እነሱም የተኙ ሆነው ሳሉ (ዓይኖቻቸው በመከፈታቸው) ንቁዎች ናቸው ብለህ ታስባቸዋለህ፡፡ ወደ ቀኝ ጎንና ወደ ግራ ጎንም እናገላብጣቸዋለን፡፡ ውሻቸውም ሁለት ክንዶቹን በዋሻው በር ላይ ዘርግቷል፡፡ በእነሱ ላይ ዘልቀህ ብታይ ኖሮ የምትሸሽ ኾነህ በዞርክ ነበር፡፡ ከእነሱም በእርግጥ ፍርሃትን በተመላህ ነበር፡፡ 18|19|እንዲሁም በመካከላቸው እንዲጠያየቁ ቀሰቀስናቸው፡፡ ከእነሱ አንድ ተናጋሪ «ምን ያክል ቆያችሁ» አለ፡፡ «አንድን ቀን ወይም የቀንን ከፊል ቆየን» አሉ፡፡ «ጌታችሁ የቆያችሁትን ጊዜ ልክ ዐዋቂ ነው፡፡ ከዚህችም ብራችሁ ጋር አንዳችሁን ወደ ከተማይቱ ላኩ፡፡ ከምግቦቿ የትኛዋ ንጹሕ መሆኗንም ይመልከት፡፡ ከእርሱም (ከንጹሑ) ምግብን ያምጣላችሁ፡፡ ቀስም ይበል፡፡ በእናንተም አንድንም ሰው አያሳውቅ» አሉ፡፡ 18|20|«እነሱ በእናንተ ላይ ቢዘልቁ ይቀጠቅጧችኋልና፡፡ ወይም ወደ ሃይማኖታቸው ይመልሷችኋል፡፡ ያንጊዜም በፍጹም ፍላጎታችሁን አታገኙም» (ተባባሉ)፡፡ 18|21|እንደዚሁም የአላህ ቀጠሮ እርግጠኛ መሆኑን ሰዓቲቱም በርሷ ጥርጣሬ የሌለ መሆኑን ያውቁ ዘንድ በእነርሱ ላይ (ሰዎችን) አሳወቅን፡፡ (አማኞቹና ከሓዲዎቹ) ነገራቸውን በመካከላቸው ሲከራከሩ (የሆነውን አስታውስ፤ ከሓዲዎቹ)፡- «በእነሱ ላይም ግንብን ገንቡ» አሉ፡፡ ጌታቸው በእነሱ ይበልጥ ዐዋቂ ነው፡፡ እነዚያ በነገራቸው ላይ ያሸነፉት (ምእመናን) «በእነሱ ላይ በእርግጥ መስጊድን እንሠራለን» አሉ፡፡ 18|22|በሩቅ ወርዋሪዎች ሆነው (በጥርጣሬ) «ሦስት ናቸው፤ አራተኛቸው ውሻቸው ነው» ይላሉ፡፡ «አምስት ናቸው፤ ስድስተኛቸው ውሻቸው ነውም» ይላሉ፡፡ «ሰባት ናቸው፤ ስምንተኛቸውም ውሻቸው ነው» ይላሉም፡፡ «ጌታዬ ቁጥራቸውን ዐዋቂ ነው፡፡ ጥቂት (ሰው) እንጂ አያውቃቸውም» በላቸው፡፡ በእነሱም ነገር ግልጽን ክርክር እንጂ (ጠልቀህ) አትከራከር፡፡ በእነሱም ጉዳይ ከነሱ (ከመጽሐፉ ሰዎች) አንድንም አትጠይቅ፡፡ 18|23|ለማንኛውም ነገር «እኔ ይህንን ነገ ሠሪ ነኝም» አትበል፡፡ 18|24|«አላህ የሻ እንደ ሆነ (እሰራዋለሁ)» ብትል እንጂ፡፡ በረሳህም ጊዜ ጌታህን አውሳ፡፡ «ጌታዬም ከዚህ ይበልጥ ለቀጥታ የቀረበን ሊመራኝ ይከጀላል» በላቸው፡፡ 18|25|በዋሻቸውም ውስጥ ሶስት መቶ ዓመታትን ቆዩ፡፡ ዘጠኝንም ጨመሩ፡፡ 18|26|«አላህ የቆዩትን ልክ ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ የሰማያትና የምድር ምስጢር የእሱ ብቻ ነው፡፡ እርሱ ምን ያይ! ምን ይሰማም! ለእነርሱ ከእርሱ በቀር ምንም ረዳት የላቸውም፡፡ በፍርዱም አንድንም አያጋራም፡፡ 18|27|ከጌታህም መጽሐፍ ወደ አንተ የተወረደውን አንብብ፡፡ ለቃላቶቹ ለዋጭ የላቸውም፡፡ ከእርሱም በቀር መጠጊያን በፍጹም አታገኝም፡፡ 18|28|ነፍስህንም፤ ከእነዚያ ጌታቸውን ፊቱን (ውዴታውን) የሚሹ ኾነው በጧትና በማታ ከሚግገዙት ጋር አስታግስ፡፡ የቅርቢቱንም ሕይወት ሽልማት የምትሻ ሆነህ ዓይኖችህ ከእነሱ (ወደ ሌላ) አይለፉ፡፡ ልቡንም እኛን ከማስታወስ ያዘነጋነውን ፍላጎቱንም የተከተለውን ነገሩም ሁሉ ወሰን ማለፍ የሆነውን ሰው አትታዘዝ፡፡ 18|29|«እውነቱም ከጌታችሁ ነው፡፡ የሻም ሰው ይመን፤ የሻም ሰው ይካድ» በላቸው፡፡ እኛ ለበደለኞች አጥሯ በእነሱ የከበበ የኾነችውን እሳት አዘጋጅተናል፡፡ (ከጥም) እርዳታንም ቢፈልጉ እንደ ዘይት ዝቃጭ ባለ ፊቶችን በሚጠብስ ውሃ ይረዳሉ፡፡ መጠጡ ከፋ! መደገፊያይቱም ምንኛ አስከፋች! 18|30|እነዚያ ያመኑና መልካም ሥራዎችንም የሠሩ እኛ ሥራን ያሳመረን ሰው ምንዳ አናጠፋም፡፡ 18|31|እነዚያ ለእነሱ የመኖሪያ ገነቶች ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው አሏቸው፡፡ በእርሷ ውስጥ ከወርቅ የኾኑን አንባሮች ይሸለማሉ፡፡ ከቀጭን ሐርና ከወፍራም ሐርም አረንጓዴን ልብሶች ይለብሳሉ፡፡ በውስጧ በባለ አጎበር አልጋዎች ላይ የተደገፉ ኾነው (ይቀመጣሉ)፡፡ ምንዳቸው ምን ያምር! መደገፊያይቱም ምንኛ አማረች! 18|32|ለእነሱም የሁለትን ሰዎች ምሳሌ ግለጽላቸው፡፡ ለአንደኛቸው (ለከሓዲው) ከወይኖች የኾኑን ሁለት አትክልቶች አደረግንለት፡፡ በዘምባባም አከበብናቸው፡፡ በመካከላቸውም አዝመራን አደረግን፡፡ 18|33|ሁለቱም አትክልቶች ሰብላቸውን ሰጡ፡፡ ከእርሱም ምንም አላጎደሉም፡፡ በመካከላቸውም ወንዝን አፈሰስን፡፡ 18|34|ለእርሱም (ከአትክልቶቹ ሌላ ፍሬያማ) ሀብት ነበረው፡፡ ለጓደኛውም (ለአማኙ) እርሱ የሚወዳደረው ሲኾን «እኔ ካንተ በገንዘብ ይበልጥ የበዛሁ በወገንም ይበልጥ የበረታሁ ነኝ» አለው፡፡ 18|35|እርሱም ነፍሱን በዳይ ኾኖ ወደ አትክልቱ ገባ፡፡ «ይህች ዘለዓለም ትጠፋለች ብዬ አልጠረጥርም» አለ፡፡ 18|36|«ሰዓቲቱንም ቋሚ (ኋኝ) ናት ብዬ አልጠረጥርም፡፡ (እንደምትለው) ወደ ጌታዬም ብመለስ ከእርሷ የበለጠን መመለሻ በእርግጥ አገኛለሁ» (አለው)፡፡ 18|37|ጓደኛው (አማኙ) እርሱ ለእርሱ የሚመላለሰው ሲኾን «በዚያ ከዐፈር፣ ከዚያም ከፍትወት ጠብታ ከፈጠረህ፣ ከዚያም ሰው ባደረገህ (አምላክ) ካድክን» አለው፡፡ 18|38|«እኔ ግን እርሱ አላህ ጌታዬ ነው፤ (እላለሁ)፡፡ በጌታዬም አንድንም አላጋራም፡፡ 18|39|«አትክልትህንም በገባህ ጊዜ አላህ የሻው ይኾናል፤ በአላህ ቢኾን እንጂ ኀይል የለም፤ አትልም ኖሯልን እኔን በገንዘብም በልጅም ካንተ በጣም ያነስኩ ሆኜ ብታየኝ፡፡ 18|40|«ጌታዬ ከአትክልትህ የበለጠን ሊሰጠኝ በርሷም (በአትክልትህ) ላይ ከሰማይ መብረቆችን ሊልክባትና የምታንዳልጥ ምልጥ ምድር ልትኾን ይቻላል፡፡ 18|41|ወይም ውሃው ሠራጊ ሊኾን (ይችላል)፡፡ ያን ጊዜ ለርሱ መፈለግን ፈጽሞ አትችልም» (አለው)፡፡ 18|42|ሀብቱም ተጠፋ፡፡ እርሷ በዳሶቿ ላይ የወደቀች ኾና በእርሷ ባወጣው ገንዘብ ላይ (እየተጸጸተ) መዳፎቹን የሚያገላብጥና «ወይ ጸጸቴ! በጌታዬ አንድም ባላጋራሁ» የሚል ኾነ፡፡ 18|43|ለእርሱም ከአላህ ሌላ የሚረዱት ጭፍሮች አልነበሩትም፡፡ ተረጂም አልነበረም፡፡ 18|44|እዚያ ዘንድ (በትንሣኤ ቀን) ስልጣኑ እውነተኛ ለኾነው አላህ ብቻ ነው፡፡ እርሱ በመመንዳት የበለጠ ፍጻሜንም በማሳመር የበለጠ ነው፡፡ 18|45|ለእነሱም የቅርቢቱን ሕይወት ምሳሌ አውሳላቸው፡፡ (እርሷ) ከሰማይ እንዳወረድነው ውሃ በእርሱም የምድር በቃይ እንደ ተቀላቀለበት (ከተዋበ በኋላ ደርቆ) ነፋሶችም የሚያበኑት ደቃቅ እንደ ኾነ ብጤ ናት፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 18|46|ገንዘብና ወንዶች ልጆች የቅርቢቱ ሕይወት ጌጦች ናቸው፡፡ መልካሞቹም ቀሪዎች (ሥራዎች) እጌታህ ዘንድ በምንዳ በላጭ ናቸው፡፡ በተስፋም በላጭ ናቸው፡፤ 18|47|ተራራዎችንም የምናስኼድበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ ምድርንም ግልጽ ኾና ታያታለህ፡፡ እንሰበስባቸዋለንም፡፡ ከእነሱም አንድንም አንተውም፡፡ 18|48|የተሰለፉም ኾነው በጌታህ ላይ ይቀረባሉ፡፡ (ይባላሉም) «በመጀመሪያ ጊዜ እንደ ፈጠርናችሁ (ራቁታችሁን) በእርግጥ መጣችሁን በእውነቱ ለእናንተ (ለመቀስቀሻ) ጊዜን አናደርግም መስሏችሁ ነበር፡፡» 18|49|(ለሰው ሁሉ) መጽሐፉም ይቀርባል፡፡ ወዲያውም ከሓዲዎችን በውስጡ ካለው ነገር ፈሪዎች ኾነው ታያቸዋለህ፡፡ «ዋ ጥፋታችን! ለዚህ መጽሐፍ (ከሥራ) ትንሽንም ትልቅንም የቆጠራት ቢኾን እንጂ የማይተወው ምን አለው» ይላሉም፡፡ የሰሩትንም ነገር ሁሉ ቀራቢ ኾኖ ያገኙታል፡፡ ጌታህም አንድንም አይበድልም፡፡ 18|50|ለመላእክትም ለአደም ስገዱ ባልናቸው ጊዜ (የኾነውን አስታውስ)፡፡ ወዲያውም ሰገዱ፤ ኢብሊስ ብቻ ሲቀር፡፡ ከጋኔን (ጎሳ) ነበር፡፡ ከጌታውም ትእዛዝ ወጣ፡፡ እርሱንና ዘሮቹን እነርሱ ለእናንተ ጠላቶች ሲኾኑ ከእኔ ላይ ረዳቶች አድርጋችሁ ትይዛላችሁን ለበዳዮች ልዋጭነቱ ከፋ! 18|51|የሰማያትንና የምድርን አፈጣጠር አላሳየኋቸውም፡፡ የነፍሶቻቸውንም አፈጣጠር (እንደዚሁ)፡፡ አሳሳቾችንም ረዳቶች አድርጌ የምይዝ አይደለሁም፡፡ 18|52|«እነዚያንም (አምላክ) የምትሏቸውን ተጋሪዎቼን ጥሩ» የሚልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ ይጠሯቸዋልም ግን አይመልሱላቸውም፡፡ በመካከላቸውም መጥፊያን ስፍራ (ገሀነምን) አደረግን፡፡ 18|53|ከሓዲዎችም እሳትን ያያሉ፡፡ እነርሱም በውስጧ ወዳቂዎች መኾናቸውን ያረጋግጣሉ፡፡ ከእርሷም መሸሻን አያገኙም፡፡ 18|54|በዚህም ቁርኣን ውስጥ ከየምሳሌው ሁሉ ለሰዎች መላልሰን ገለጽን፡፡ ሰውም ከነገሩ ሁሉ ይበልጥ ክርክረ ብዙ ነው፡፡ 18|55|ሰዎችንም መምሪያ በመጣላቸው ጊዜ ከማመንና ጌታቸውንም ምሕረትን ከመለመን የመጀመሪዎቹ (ሕዝቦች) ልማድ (መጥፋት) ልትመጣባቸው ወይም ቅጣቱ በያይነቱ ሊመጣባቸው (መጠባበቅ) እንጂ ሌላ አልከለከላቸውም፡፡ 18|56|መልክተኞችንም አብሳሪዎችና አስፈራሪዎች ኾነው እንጂ አንልክም፡፡ እነዚያ የካዱትም በውሸት እውነቱን በእሱ ሊያበላሹ ይከራከራሉ፡፡ አንቀጾቼንና በእርሱ የተስፈራሩበትንም ነገር ማላገጫ አድርገው ያዙ፡፡ 18|57|በጌታውም አንቀጾች ከተገሰጸና ከእርሷ ከዞረ እጆቹም ያስቀደሙትን ነገር ከረሳ ሰው ይበልጥ በዳይ ማነው እኛ በልቦቻቸው ላይ እንዳያውቁት ሺፋኖችን በጆሮዎቻቸውም ውስጥ ድንቁርናን አደረግን፡፡ ወደ መመራትም ብትጠራቸው ያን ጊዜ ፈጽሞ አይምመሩም፡፡ 18|58|ጌታህም በጣም መሃሪው የእዝነት ባለቤቱ ነው፡፡ በሠሩት ሥራ ቢይዛቸው ኖሮ ቅጣቱን ለእነሱ ባስቸኮለባቸው ነበር፡፡ ግን ለእነሱ ከእርሱ ሌላ መጠጊያን ፈጽሞ የማያገኙበት ቀጠሮ አላቸው፡፡ 18|59|እነዚህ ከተሞችም በበደሉ ጊዜ አጠፋናቸው፡፡ ለመጥፊያቸውም የተወሰነ ጊዜን አደረግን፡፡ 18|60|ሙሳም ለወጣቱ «የሁለቱን ባሕሮች መገናኛ እስከምደርስ ወይም ብዙን ጊዜ እስከምኼድ ድረስ (ከመጓዝ) አልወገድም» ያለውን (አስታውስ)፡፡ 18|61|የሁለቱን መገናኛ በደረሱም ጊዜ ዐሣቸውን ረሱ፡፡ (ዐሣው) መንገዱንም በባህሩ ውስጥ ቀዳዳ አድርጎ ያዘ፡፡ 18|62|ባለፉም ጊዜ ለወጣቱ «ምሳችንን ስጠን፡፡ ከዚህ ጉዟችን በእርግጥ ድካምን አግኝተናልና» አለ፡፡ 18|63|«አየህን ወደ ቋጥኝዋ በተጠጋን ጊዜ እኔ ዐሣውን ረሳሁ፡፡ ማስታወሱንም ሰይጣን እንጂ ሌላ አላስረሳኝም፡፡ በባሕሩም ውስጥ መንገዱን አስደናቂ (መንገድ) አድርጎ ያዘ» አለ፡፡ 18|64|(ሙሳም) ይህ እንፈልገው የነበርነው ነው አለው፡፡ በፈለጎቻቸውም ላይ እየተከተሉ ተመለሱ፡፡ 18|65|ከባሮቻችንም ከእኛ ዘንድ ችሮታን የሰጠነውን ከእኛም ዘንድ ዕውቀትን ያስተማርነውን አንድን ባሪያ (ኸድርን) አገኙ፡፡ 18|66|ሙሳ ለእርሱ «ከተማርከው ነገር ቀጥተኛን (ዕውቀት) ታስተምረኝ ዘንድ ልከተልህን» አለው፡፡ 18|67|(ባሪያውም) አለ «አንተ ከእኔ ጋር መታገስን በጭራሽ አትችልም፡፡ 18|68|«በዕውቀትም በእርሱ ባላዳረስከው ነገር ላይ እንዴት ትታገሳለህ» 18|69|(ሙሳ) «አላህ የሻ እንደ ኾነ ታጋሽና ላንተ ትዕዛዝን የማልጥስ ኾኜ ታገኘኛለህ» አለው፡፡ 18|70|«ብትከተለኝም ለአንተ ከእርሱ ማውሳትን እስከምጀምርልህ ድረስ ከምንም ነገር አትጠይቀኝ» አለው፡፡ 18|71|ኼዱም፡፡ በመርከቢቱም በተሳፈሩ ጊዜ ቀደዳት፡፡ «ባለ ቤቶቿን ልታሰጥም ቀደድካትን ትልቅ ነገርን በእርግጥ ሠራህ» አለው፡፡ 18|72|«አንተ ከኔ ጋር ትእግሥትን ፈጽሞ አትችልም አላልኩምን» አለ፡፡ 18|73|«በረሳሁት ነገር አትያዘኝ፡፡ ከነገሬም ችግርን አታሸክመኝ» አለው፡፡ 18|74|(ወርደው) ተጓዙም፡፡ ወጣትንም ልጅ ባገኙና በገደለው፤ «ጊዜ ያለ ነፍስ (መግደል) ንጹሕን ነፍስ ገደልክን በእርግጥ መጥፎን ነገር ሥራህ» አለው፡፡ 18|75|«አንተ ከኔ ጋር ትእግሥትን ፈጽሞ አትችልም አላልኩህምን» አለ፡፡ 18|76|«ከርሷ (ከአሁኒቱ ጊዜ) በኋላ ከምንም ነገር ብጠይቅህ አትጎዳኘኝ፡፡ ከእኔ የይቅርታን መጨረሻ በእርግጥ ደርሰሃል» አለው፡፡ 18|77|ኼዱም፡፡ ወደ አንዲት ከተማ ሰዎች በመጡም ጊዜ ነዋሪዎቿን ምግብን ጠየቁ፡፡ ከማስተናገዳቸውም እምቢ አሉ፡፡ በእርሷም ውስጥ ለመውደቅ የተቃረበን ግድግዳ አገኙ፡፡ (ኸድር) አቆመውም፡፡ (ሙሳም) «በሻህ ኖሮ በእርሱ ላይ ዋጋን በተቀበልክ ነበር» አለው፡፡ 18|78|(ኸድር) አለ «ይህ በእኔና በአንተ መካከል መለያያ ነው፡፡ በእርሱ ላይ መታገስን ያልቻልክበትን ፍች እነግርሃለሁ፡፡ 18|79|«መርከቢቱማ በባሕር ለሚሠሩ ምስኪኖች ነበረች፡፡ ከኋላቸውም መርከብን ሁሉ በቅሚያ የሚይዝ ንጉሥ ነበረና፤ (እንዳይቀማቸው) ላነውራት ፈቀድኩ፡፡ 18|80|«ወጣቱም ልጅማ ወላጆቹ ምእመናን ነበሩ፡፡ (ቢያድግ) ትእቢትንና ክህደትንም የሚያስገድዳቸው መኾኑን ፈራን፡፡ 18|81|«ጌታቸውም በንጹሕነት ከእርሱ በላጭን በእዝነትም ከእርሱ በጣም ቀራቢን ልጅ ሊለውጥላቸው ፈለግን፡፡ 18|82|«ግድግዳውማ በከተማይቱ ውስጥ የነበሩ የሁለት የቲሞች ወጣቶች ነበር፡፡ በሥሩም ለእነርሱ የኾነ (የተቀበረ) ድልብ ነበረ፡፡ አባታቸውም መልካም ሰው ነበር፡፡ ጌታህም ለአካለ መጠን እንዲደርሱና ከጌታህ ችሮታ ድልባቸውን እንዲያወጡ ፈቀደ፡፡ በፈቃዴም አልሠራሁትም፡፡ ይህ በእርሱ ላይ መታገስን ያልቻልከው ነገር ፍች ነው» (አለው)፡፡ 18|83|ከዙልቀርነይንም ይጠይቁሃል፡፡ «በእናንተ ላይ ከእርሱ ወሬን አነባለሁ፤» በላቸው፡፡ 18|84|እኛ ለእርሱ በምድር አስመቸነው፡፡ ከነገሩም ሁሉ (መዳረሻ) መንገድን ሰጠነው፡፡ 18|85|መንገድንም (ወደ ምዕራብ) ተከተለ፡፡ 18|86|ወደ ፀሐይ መግቢያም በደረሰ ጊዜ ጥቁር ጭቃ ባላት ምንጭ ውስጥ ስትጠልቅ አገኛት፡፡ ባጠገቧም ሕዝቦችን አገኘ፡፡ «ዙልቀርነይን ሆይ! ወይም (በመግደል) ትቀጣለህ ወይም በእነርሱ መልካም ነገርን (መማረክን) ትሠራለህ» አልነው፡፤ 18|87|«የበደለውን ሰውማ ወደፊት እንቀጣዋለን፡፡ ከዚያም ወደ ጌታው ይመለሳል፡፡ ብርቱንም ቅጣት ይቀጣዋል» አለ፡፡ 18|88|«ያመነም ሰውማ መልካምንም ሥራ የሠራ ለእርሱ ከምንዳ በኩል መልካሚቱ (ገነት) አለችው፡፡ ለእርሱም ከትእዛዛችን ገርን ነገር እናዘዋለን» (አለ)፡፡ 18|89|ከዚያም መንገድን (ወደ ምሥራቅ) ቀጠለ፡፡ 18|90|ወደ ፀሐይ መውጫ በደረሰም ጊዜ ለእነሱ ከበታችዋ መከለያን ባላደረግንላቸው ሕዝቦች ላይ ስትወጣ አገኛት፡፡ 18|91|(ነገሩ) እንደዚሁ ነው፡፡ እርሱም ዘንድ ባለው ነገር ሁሉ በእርግጥ በዕውቀት ከበብን፡፡ 18|92|ከዚያም (ወደ ሰሜን አቅጣጫ) መንገድን ቀጠለ፡፡ 18|93|በሁለቱ ጋራዎችም መካከል በደረሰ ጊዜ በአቅራቢያቸው ንግግርን ለማወቅ የማይቃረቡ ሕዝቦችን አገኘ፡፡ 18|94|«ዙልቀርነይን ሆይ! የእጁጅና መእጁጅ በምድር ላይ አበላሺዎች ናቸውና በእኛና በእነሱ መካከል ግድብን ታደርግልን ዘንድ ግብርን እናድርግልህን» አሉ፡፡ 18|95|አለ «ጌታዬ በእርሱ ያስመቸኝ ሀብት (ከናንተ ግብር) በላጭ ነው፡፡ ስለዚህ በጉልበት እገዙኝ፡፡ በእናንተና በእነሱ መካከል ብርቱን ግድብ አደርጋለሁና፡፡ 18|96|«የብረትን ታላላቅ ቁራጮች ስጡኝ» (አላቸው)፡፡ በሁለቱ ኮረብታዎች (ጫፍ) መካከልም ባስተካከለ ጊዜ አናፉ አላቸው፡፡ (ብረቱን) እሳትም ባደረገው ጊዜ «የቀለጠውን ነሐስ ስጡኝ፤ በርሱ ላይ አፈስበታለሁና» አላቸው፡፡ 18|97|(የእጁጅና መእጁጅ) ሊወጡትም አልቻሉም፡፡ ለእርሱ መሸንቆርንም አልቻሉም፡፡ 18|98|«ይህ (ግድብ) ከጌታዬ ችሮታ ነው፡፡ የጌታየም ቀጠሮ በመጣ ጊዜ ትክክል ምድር ያደርገዋል፡፡ የጌታዬም ቀጠሮ ተረጋገጠ ነው» አለ፡፡ 18|99|በዚያም ቀን ከፊላቸውን በከፊሉ የሚቀላቀሉ አድርገን እንተዋቸዋለን፡፡ በቀንዱም ይነፋል መሰብሰብንም እንሰበስባቸዋለን፡፤ 18|100|ገሀነምንም በዚያ ቀን ለከሓዲዎች በጣም ማቅረብን እናቀርባታለን፡፡ 18|101|ለዚያ ዓይኖቻቸው ከግሳጼዬ በሺፋን ውስጥ ለነበሩትና መስማትንም የማይችሉ ለነበሩት (እናቀርባታለን)፡፡ 18|102|እነዚያ የካዱት ባሮቼን ከእኔ ሌላ አማልክት አድርገው መያዛቸውን (የማያስቆጣኝ አድርገው) አሰቡን እኛ ገሀነምን ለከሓዲዎች መስተንግዶ አዘጋጅተናል፡፡ 18|103|«በሥራዎች በጣም ከሳሪዎቹን እንንገራችሁን» በላቸው፡፡ 18|104|እነዚያ እነሱ ሥራን የሚያሳምሩ የሚመስላቸው ሲሆኑ በቅርቢቱ ሕይወት ሥራቸው የጠፋባቸው ናቸው፡፡ 18|105|እነዚያ እነርሱ በጌታቸው ማስረጃዎችና በመገናኘቱ የካዱት ናቸው፡፡ ሥራዎቻቸውም ተበላሹ፡፡ ለእነሱም በትንሣኤ ቀን (ጠቃሚ) ሚዛንን አናቆምላቸውም፡፡ 18|106|(ነገሩ) ይህ ነው፡፡ በክህደታቸው አንቀጾቼንና መልክተኞቼንም መሳለቂያ አድርገው በመያዛቸው ፍዳቸው ገሀነም ነው፡፡ 18|107|እነዚያ ያመኑና መልካም ሥራዎችን የሠሩ የፊርደውስ ገነቶች ለእነሱ መስፈሪያ ናቸው፡፡ 18|108|በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ከእርሷ መዛወርን የማይፈልጉ ሲኾኑ፤ (መስፈሪያቸው ነው)፡፡ 18|109|«ባሕሩ ለጌታዬ ቃላት (መጻፊያ) ቀለሞችን በሆነ ኖሮ ብጤውን ጭማሪ ብናመጣም እንኳን የጌታዬ ቃላት ከማለቋ በፊት ባሕሩ ባለቀ ነበር» በላቸው፡፡ 18|110|«እኔ አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው ማለት ወደኔ የሚወረድልኝ ቢጤያችሁ ሰው ብቻ ነኝ፡፡ የጌታውንም መገናኘት የሚፈልግ ሰው፤ መልካም ሥራን ይሥራ፡፡ በጌታውም መገዛት አንድንም አያጋራ» በላቸው፡፡ 19|1|ከ.ሀ.የ.ዐ.ጸ (ካፍ ሃ ያ ዓይን ሷድ) 19|2|(ይህ) ጌታህ ባሪያውን ዘከሪያን በችሮታው ያወሳበት ነው፡፡ 19|3|ጌታውን የምስጢርን ጥሪ በተጣራ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 19|4|አለ «ጌታዬ ሆይ! እኔ አጥንቴ ደከመ፤ ራሴም በሺበት ተንቀለቀለ፤ አንተም በመለመኔ ጌታዬ ሆይ! (ምንጊዜም) ዕድለ ቢስ አልሆንኩም፡፡ 19|5|«እኔም ከበኋላዬ ዘመዶቼን በእርግጥ ፈራሁ፡፡ ሚስቴም መካን ነበረች ስለዚህ ከአንተ ዘንድ ለኔ ልጅን ስጠኝ፡፡ 19|6|«የሚወርሰኝ ከያዕቆብ ቤተሰቦችም የሚወርስ የሆነን (ልጅ)፡፡ ጌታዬ ሆይ! ተወዳጅም አድርገው፡፡» 19|7|«ዘከሪያ ሆይ! እኛ በወንድ ልጅ ስሙ የሕያ በኾነ ከዚህ በፊት ሞክሼን ባላደረግንለት እናበስርሃለን» (አለው)፡፡ 19|8|«ጌታዬ ሆይ! ሚስቴ መካን የነበረች ስትኾን እኔም ከእርጅና ድርቀትን በእርግጥ የደረስኩ ስኾን እንዴት ልጅ ይኖረኛል!» አለ፡፡ 19|9|(ጅብሪል) አለ «(ነገሩ) እንደዚሁ ነው፡፡ ጌታህ፡- ከአሁን በፊት ምንም ያልነበርከውን የፈጠርኩህ ስኾን እርሱ በእኔ ላይ ቀላል ነው» አለ፡፡ 19|10|«ጌታዬ ሆይ! (እንግዲያውስ) ለእኔ ምልክትን አድርግልኝ አለ፡፡ ምልክትህ ጤናማ ሆነህ ሳለህ ሦስት ሌሊትን (ከነቀናቸው) ሰዎችን ለማነጋገር አለመቻልህ ነው» አለው፡፡ 19|11|ከምኩራቡም በሕዝቦቹ ላይ ወጣ፡፡ በ×ትና በማታ (ጌታችሁን) አወድሱ በማለትም ወደነሱ ጠቀሰ፡፡ 19|12|«የሕያ ሆይ! መጽሐፉን በጥብቅ ያዝ!» (አልነው)፡፡ ጥበብንም በሕፃንነቱ ሰጠነው፡፡ 19|13|ከእኛም የሆነን ርኅራኄ ንጽሕናንም (ሰጠነው)፡፡ ጥንቁቅም ነበር፡፡ 19|14|ለወላጆቹም በጎ ሠሪ ነበር፡፡ ትዕቢተኛ አመጸኛም አልነበረም፡፡ 19|15|በተወለደበት ቀንና በሚሞትበትም ቀን፣ ሕያው ሆኖ በሚነሳበትም ቀን ሰላም በእሱ ላይ ይሁን፡፡ 19|16|በመጽሐፉ ውስጥ መርየምንም ከቤተሰቧ ወደ ምሥራቃዊ ስፍራ በተለይች ጊዜ (የሆነውን ታሪኳን) አውሳ፡፡ 19|17|ከእነሱም መጋረጃን አደረገች፡፡ መንፈሳችንምም (ጂብሪልን) ወደርሷ ላክን፡፡ ለእርሷም ትክክለኛ ሰው ሆኖ ተመሰለላት፡፡ 19|18|«እኔ ከአንተ በአልረሕማን እጠበቃለሁ፡፡ ጌታህን ፈሪ እንደ ሆንክ (አትቅረበኝ)» አለች፡፡ 19|19|«እኔ ንጹሕን ልጅ ለአንቺ ልሰጥሽ የጌታሽ መልክተኛ ነኝ» አላት፡፡ 19|20|«(በጋብቻ) ሰው ያልነካኝ ሆኜ አመንዝራም ሳልሆን ለእኔ እንዴት ልጅ ይኖረኛል!» አለች፡፡ 19|21|አላት «(ነገሩ) እንደዚህሽ ነው፡፡» ጌታሽ «እርሱ በእኔ ላይ ገር ነው፡፡ ለሰዎችም ታምር ከእኛም ችሮታ ልናደርገው (ይህንን ሠራን) የተፈረደም ነገር ነው» አለ፤ (ነፋባትም)፡፡ 19|22|ወዲያውኑም አረገዘችው፡፡ በእርሱም (በሆዷ ይዛው) ወደ ሩቅ ስፍራ ገለል አለች፡፡ 19|23|ምጡም ወደ ዘንባባይቱ ግንድ አስጠጋት፡፡ «ዋ ምኞቴ! ምነው ከዚህ በፊት በሞትኩ፡፡ ተረስቼም የቀረሁ በሆንኩ» አለች፡፡ 19|24|ከበታቿም እንዲህ ሲል ጠራት «አትዘኝ፡፡ ጌታሽ ከበታችሽ ትንሽን ወንዝ በእርግጥ አድርጓል፡፡ 19|25|«የዘምባባይቱንም ግንድ ወዳንቺ ወዝውዣት ባንቺ ላይ የበሰለን የተምር እሸት ታረግፍልሻለችና፡፡ 19|26|«ብይም፣ ጠጭም፣ ተደሰችም፡፡ እኔ ለአልረሕማን ዝምታን ተስያለሁ፤ ዛሬም ሰውን በፍጹም አላነጋግርም» በይ፡፡ 19|27|በእርሱም የተሸከመቺው ሆና ወደ ዘመዶቿ መጣች፡፡ «መርየም ሆይ! ከባድን ነገር በእርግጥ ሠራሽ» አሏት፡፡ 19|28|«የሃሩን እኅት ሆይ! አባትሽ መጥፎ ሰው አልነበረም፡፡ እናትሽም አመንዝራ አልነበረችም» አሏት፡፡ 19|29|ወደርሱም ጠቀሰች፡፡ «በአንቀልባ ያለን ሕጻን እንዴት እናናግራለን!» አሉ፡፡ 19|30|(ሕፃኑም) አለ «እኔ የአላህ ባሪያ ነኝ፡፡ መጽሐፍን ሰጥቶኛል ነቢይም አድርጎኛል፡፡» 19|31|«በየትም ስፍራ ብሆን ብሩክ አድርጎኛል፡፡ በሕይወትም እስካለሁ ሶላትን በመስገድ ዘካንም በመስጠት አዞኛል፡፡» 19|32|«ለእናቴም ታዛዥ (አድርጎኛል)፡፡ ትዕቢተኛ እምቢተኛም አላደረገኝም፡፡ 19|33|«ሰላምም በእኔ ላይ ነው፡፡ በተወለድሁ ቀን፣ በምሞትበትም ቀን፣ ሕያው ኾኜ በምቀሰቀስበትም ቀን፡፡» 19|34|ይህ የመርየም ልጅ ዒሳ ነው፡፡ ያ በርሱ የሚጠራጠሩበት እውነተኛ ቃል ነው፡፡ 19|35|ለአላህ ልጅን መያዝ አይገባውም፡፡ (ከጉድለት ሁሉ) ጠራ፡፡ ነገርን በሻ ጊዜ ለርሱ የሚለው «ኹን» ነው ወዲያውም ይኾናል፡፡ 19|36|(ዒሳ አለ) «አላህም ጌታዬ ጌታችሁም ነውና ተገዙት፡፡ ይህ ቀጥተኛ መንገድ ነው፡፡» 19|37|ከመካከላቸውም አሕዛቦቹ በእርሱ ነገር ተለያዩ፡፡ ለእነዚያም ለካዱት ሰዎች ከታላቁ ቀን መጋፈጥ ወዮላቸው፡፡ 19|38|በሚመጡን ቀን ምን ሰሚ ምንስ ተመልካች አደረጋቸው! ግን አመጸኞች ዛሬ (በዚህ ዓለም) በግልጽ ስህተት ውስጥ ናቸው፡፤ 19|39|እነሱም (አሁን) በዝንጋቴ ላይ ኾነው ሳሉ እነሱም የማያምኑ ሲኾኑ ነገሩ በሚፈረድበት ጊዜ የቁልጭቱን ቀን አስፈራራቸው፡፡ 19|40|እኛ ምድርን በእርሷም ላይ ያለውን ሁሉ እኛ እንወርሳለን፡፡ ወደኛም ይመለሳሉ፡፡ 19|41|በመጽሐፉ ውስጥ ኢብራሂምንም አውሳ፡፡ እርሱ በጣም እውነተኛ ነቢይ ነበርና፡፡ 19|42|ለአባቱ ባለ ጊዜ (አስታውስ) «አባቴ ሆይ! የማይሰማንና የማያይን ከአንተም ምንንም የማይጠቅምህን (ጣዖት) ለምን ትግገዛለህ 19|43|«አባቴ ሆይ! እኔ ከዕውቀት ያልመጣልህ ነገር በእርግጥ መጥቶልኛልና ተከተለኝ፡፡ ቀጥተኛውን መንገድ እመራሃለሁና፡፡ 19|44|«አባቴ ሆይ! ሰይጣንን አትግገዛ፡፡ ሰይጣን ለአልረሕማን አመጸኛ ነውና፡፡ 19|45|«አባቴ ሆይ! እኔ ከአልረሕማን ቅጣት ሊያገኝህ ለሰይጣንም ጓደኛ ልትኾን እፈራለሁ፡፡» 19|46|(አባቱም) «ኢብራሂም ሆይ! አንተ አምላኮቼን ትተህ የምትዞር ነህን ባትከለከል በእርግጥ እወግርሃለሁ፡፡ ረዥም ጊዜንም ተወኝ» አለ፡፡ 19|47|«ደህና ኹን፡፡ ወደፊት ከጌታዬ ምሕረትን እለምንልሃለሁ፡፡ እርሱ ለኔ በጣም ርኅሩኅ ነውና» አለ፡፡ 19|48|«እናንተንም ከአላህ ሌላ የምትግገዙትንም እርቃለሁ፡፡ ጌታዬንም እግገዛለሁ፡፡ ጌታዬን በመገዛት የማፍር አለመኾኔን እከጅላለሁ፡፡» 19|49|እነርሱንም ከአላህ ሌላ የሚግገዙትንም በራቀ ጊዜ ለእርሱ ኢስሐቅንና ያዕቆብን ሰጠነው፡፡ ሁሉንም ነቢይ አደረግንም፡፡ 19|50|ለእነሱም ከችሮታችን ሰጠናቸው፡፡ ለእነርሱም ከፍ ያለ ምስጉን ዝናን አደረግንላቸው፡፡ 19|51|በመጽሐፉ ውስጥ ሙሳንም አውሳ፡፡ እርሱ ምርጥ ነበርና፡፡ መልክተኛ ነቢይም ነበር፡፡ 19|52|ከጡር ቀኝ ጎን በኩልም ጠራነው፡፡ ያነጋገርነውም ሲኾን አቀረብነው፡፡ 19|53|ከችሮታችንም ወንድሙን ሃሩንን ነቢይ አድርገን ሰጠነው፡፡ 19|54|በመጽሐፉ ኢስማዒልንም አውሳ፡፡ እርሱ ቀጠሮን አክባሪ ነበረና፡፡ መልክተኛ ነቢይም ነበር፡፡ 19|55|ቤተሰቦቹንም በሶላትና በዘካ ያዝ ነበር፡፡ እጌታውም ዘንድ ተወዳጅ ነበር፡፡ 19|56|በመጽሐፉ ኢድሪስንም (ሄኖክን) አውሳ፡፡ እርሱ እውነተኛ ነቢይ ነበርና፡፡ 19|57|ወደ ከፍተኛም ስፍራ አነሳነው፡፡ 19|58|እነዚህ (ዐሥሩ) እነዚያ አላህ በእነሱ ላይ የለገሰላቸው ከነቢያት ከአዳም ዘር ከኑሕ ጋር (በመርከቢቱ ላይ) ከጫናቸውም (ዘሮች) ከኢብራሂምና ከእስራኤልም ዘሮች ከመራናቸውና ከመረጥናቸውም የኾኑት የአልረሕማን አንቀጾች በነሱ ላይ በተነበቡ ጊዜ ሰጋጆችና አልቃሾች ኾነው ይወድቃሉ፡፡ 19|59|ከእነሱም በኋላ ሶላትን ያጓደሉ (የተዉ) ፍላጎቶችንም የተከተሉ መጥፎ ምትኮች ተተኩ! የገሀነምንም ሸለቆ በእርግጥ ያገኛሉ፡፡ 19|60|ግን የተጸጸተና ያመነም በጎንም ሥራ የሠራ ሰው እነዚህ ገነትን ይገባሉ፡፡ አንዳችንም አይበደሉም፡፡ 19|61|የመኖሪያን ገነቶች ያችን አልረሕማን ለባሮቹ በሩቅ ኾነው ሳሉ ተስፋ ቃል የገባላቸውን (ይገባሉ)፡፡ እርሱ ተስፋው ተፈጻሚ ነውና፤ 19|62|በእርሷ ሰላምን እንጂ ውድቅን ነገር አይሰሙም፡፡ ለእነሱም በርሷ ውስጥ ጧትም ማታም ሲሳያቸው አላቸው፡፡ 19|63|ይህች ያቺ ከባሮቻችን ጥንቁቆች ለኾኑት የምናወርሳት ገነት ናት፡፡ 19|64|(ጂብሪል አለ) «በጌታህም ትእዛዝ እንጅ አንወርድም፡፡ በፊታችን ያለው፣ በኋላችንም ያለው በዚህም መካከል ያለው ሁሉ የርሱ ነው፡፡ ጌታህም ረሺ አይደለም፡፡ 19|65|(እርሱ) የሰማያትና የምድር በሁለቱም መካከል ላለው ሁሉ ጌታ ነውና ተገዛው፡፡ እርሱን በመገዛትም ላይ ታገስ፡፡ ለእርሱ ሞክሼን ታውቃለህን 19|66|ሰውም «በሞትኩ ጊዜ ወደፊት ሕያው ኾኜ (ከመቃብር) እወጣለሁን» ይላል፡፡ 19|67|ሰው ከአሁን በፊት ምንም ነገር ያልነበረ ሲኾን እኛ የፈጠርነው መኾኑን አያስታውስምን 19|68|በጌታህ እንምላለን ሰይጣናት ጋር በእርግጥ እንሰበስባቸዋለን፡፡ ከዚያም በገሀነም ዙሪያ የተንበረከኩ ኾነው፤ በእርግጥ እናቀርባቸዋለን፡፡ 19|69|ከዚያም ከየጭፍሮቹ ሁሉ ከእነርሱ ያንን (እርሱ) በአልረሕማን ላይ በድፍረት በጣም ብርቱ የኾነውን እናወጣለን፡፡ 19|70|ከዚያም እኛ እነዚያን እነርሱ በእርሷ ለመግባት ተገቢ የኾኑትን እናውቃለን፡፡ 19|71|ከእናንተም ወደ እርሷ ወራጅ እንጂ አንድም የለም፡፡ (መውረዱም) ጌታህ የፈረደው ግዴታ ነው፡፡ 19|72|ከዚያም እነዚያን የተጠነቀቁትን እናድናለን፡፡ አመጸኞቹንም የተንበረከኩ ኾነው በውስጧ እንተዋቸዋለን፡፡ 19|73|በእነሱም ላይ አንቀጾቻችን ግልጽ መስረጃዎች ኾነው በተነበቡ ጊዜ እነዚያ የካዱት ለእነዚያ ላመኑት «ከሁለቱ ክፍሎች መኖሪያው የሚበልጠውና ሸንጎውም ይበልጥ የሚያምረው ማንኛው ነው» ይላሉ፡፡ 19|74|ከእነሱም በፊት ከክፍለ ዘመናት ሕዝቦች እነሱ በቁሳቁስና በትርኢትም በጣም ያማሩትን ብዙዎችን አጥፍተናል፡፡ 19|75|«በስሕተት ውስጥ የኾነ ሰው አልረሕማን ለእርሱ ማዘግየትን ያዘገየዋል፡፡ የሚዛትባቸውንም ወይም ቅጣቱን ወይም ሰዓቲቱን ባዩ ጊዜ እርሱ ስፍራው መጥፎና ሰራዊቱ ደካማ የኾነው ሰው ማን እንደኾነ በእርግጥ ያውቃሉ» በላቸው፡፡ 19|76|እነዚያንም የቀኑትን ሰዎች አላህ ቅንነትን ይጨምርላቸዋል፡፡ መልካሞቹ ቀሪዎች (ሥራዎች) እጌታህ ዘንድ በምንዳ በላጭ ናቸው፡፡ በመመለሻም የተሻሉ ናቸው፡፡ 19|77|ያንንም በአንቀጾቻችን የካደውን «(በትንሣኤ ቀን) ገንዘብም ልጅም በእርግጥ እስሰጣለሁ ያለውንም አየህን» 19|78|ሩቁን ምስጢር ዐወቀን ወይስ አልረሕማን ዘንድ ቃል ኪዳንን ያዘ 19|79|ይከልከል (አይሰጠውም)፡፡ የሚለውን ሁሉ በእርግጥ እንጽፋለን፡፡ ለእርሱም ከቅጣት ጭማሬን እንጨምርለታለን፡፡ 19|80|(አልለኝ) የሚለውንም ሁሉ እንወርሰዋለን፡፡ ብቻውንም ኾኖ ይመጣናል፡፡ 19|81|ከአላህም ሌላ አማልክትን ለእነሱ መከበሪያ (አማላጅ) እንዲኾኑዋቸው ያዙ፡፡ 19|82|ይከልከሉ፤ መገዛታቸውን በእርግጥ ይክዷቸዋል፡፡ በእነሱም ላይ ተቃራኒ ይኾኑባቸዋል፡፡ 19|83|እኛ ሰይጣናትን በከሓዲዎች ላይ (በመጥፎ ሥራ) ማወባራትን የሚያወባሩዋቸው ሲኾኑ የላክን መኾናችንን አለየህምን 19|84|በእነሱም (መቀጣት) ላይ አትቻኮል፡፡ ለእነሱ (ቀንን) መቁጠርን እንቆጥርላቸዋለንና፡፡ 19|85|ምእምናንን የተከበሩ ጭፍሮች ኾነው ወደ አልረሕማን የምንሰበስብበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 19|86|ከሓዲዎችንም የተጠሙ ኾነው ወደ ገሀነም የምንነዳበትን (ቀን አስታውስ)፡፡ 19|87|አልረሕማን ዘንድ ቃል ኪዳንን የያዘ ሰው ቢኾን እንጂ ማማለድን አይችሉም፡፡ 19|88|«አልረሕማንም ልጅን ያዘ (ወለደ)» አሉ፡፡ 19|89|ከባድ መጥፎን ነገር በእርግጥ አመጣችሁ፡፡ 19|90|ከእርሱ (ከንግግራቸው) ሰማያት ሊቀደዱ፣ ምድርም ልትሰነጠቅ፣ ጋራዎችም ተንደው ሊወድቁ ይቃረባሉ፡፡ 19|91|ለአልረሕማን ልጅ አልለው ስለአሉ፡፡ 19|92|ለአልረሕማን ልጅን መያዝ አይገባውም፡፡ 19|93|በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ (በትንሣኤ ቀን) ለአልራሕማን ባሪያ ኾነው የሚመጡ እንጂ ሌላ አይደሉም፡፡ 19|94|በእርግጥ (በዕውቀቱ) ከቧቸዋል፡፡ መቁጠርንም ቆጥሯቸዋል፡፡ 19|95|ሁሉም በትንሣኤ ቀን ለየብቻ ኾነው ወደርሱ መጪዎች ናቸው፡፡ 19|96|እነዚያ ያመኑና በጎ ሥራዎችን የሠሩ አልረሕማን ለእነሱ ውዴታን ይሰጣቸዋል፡፡ 19|97|በምላስህም (ቁርኣንን) ያገራነው በእርሱ ጥንቁቆቹን ልታበስርበት በእርሱም ተከራካሪዎችን ሕዝቦች ልታስፈራራበት ነው፡፡ 19|98|ከእነሱም በፊት ከክፍለ ዘመናት ሕዝቦች ብዙዎችን አጥፍተናል፡፡ ከእነሱ አንድን እንኳ ታያለህን ወይስ ለእነሱ ሹክሹክታን ትሰማለህን 20|1|ጠ.ሀ. (ጣ ሃ) 20|2|ቁርኣንን ባንተ ላይ እንድትቸገር አላወረድንም፡፡ 20|3|ግን አላህን ለሚፈራ ሰው መገሰጫ ይኾን ዘንድ (አወረድነው)፡፡ 20|4|ምድርንና የላይኛዎቹን ሰማያት ከፈጠረ አምላክ ተወረደ፡፡ 20|5|(እርሱ) አልረሕማን ነው በዐርሹ ላይ (ስልጣኑ) ተደላደለ፡፡ 20|6|በሰማያት ያለው፣ በምድርም ያለው፣ በመካከላቸውም ያለው፣ ከዐፈር በታችም ያለው ሁሉ የርሱ ብቻ ነው፡፡ 20|7|በንግግር ብትጮህ (አላህ ከጩኸቱ የተብቃቃ ነው)፡፡ እርሱ ምስጢርን በጣም የተደበቀንም ያውቃልና፡፡ 20|8|አላህ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ ለእርሱ መልካሞች የኾኑ ስሞች አልሉት፡፡ 20|9|የሙሳም ወሬ በእርግጥ መጥቶሃል፡፡ 20|10|እሳትን ባየና ለቤተሰቦቹ፡- (እዚህ) «ቆዩ፤ እኔ እሳትን አየሁ፡፡ ከእርሷ ችቦን ላመጣላችሁ፤ ወይም እሳቲቱ ዘንድ መሪን ላገኝ እከጅላለሁ» ባለጊዜ (አስታውስ)፡፡ 20|11|በመጣትም ጊዜ «ሙሳ ሆይ» በማለት ተጠራ፡፡ 20|12|«እኔ ጌታህ እኔ ነኝ መጫሚያዎችህንም አውልቅ፡፡ አንተ በተቀደሰው ሸለቆ በጡዋ ነህና፡፡ 20|13|«እኔም መረጥኩህ፤ የሚወረድልህንም ነገር አዳምጥ፡፡ 20|14|«እኔ አላህ እኔ ነኝ ያለ እኔ አምላክ የለምና ተገዛኝ፡፡ ሶላትንም (በእርሷ) እኔን ለማውሳት ስገድ፡፡ 20|15|«ሰዓቲቱ በእርግጥ መጪናት፡፡ ልደብቃት እቃረባለሁ፡፡ ነፍስ ሁሉ በምትሠራው ነገር ትመነዳ ዘንድ (መጭ ናት)፡፡ 20|16|«በእርሷ የማያምነውና ዝንባሌውን የተከተለውም ሰው ከእርሷ አያግድህ ትጠፋለህና፡፤ 20|17|«ሙሳ ሆይ! ይህችም በቀኝ እጅህ ያለችው ምንድን ናት» (ተባለ)፡፡ 20|18|«እርሷ በትሬ ናት፡፡ በእርሷ ላይ እደገፍባታለሁ፣ በእርሷም ለፍየሎቼ ቅጠልን አረግፍባታለሁ፣ ለእኔም በእርሷ ሌሎች ጉዳዮች አሉኝ» አለ፡፡ 20|19|(አላህም) «ሙሳ ሆይ! ጣላት» አለው፡፡ 20|20|ጣላትም፡፡ ወዲያውም እርሷ የምትሮጥ እባብ ኾነች፡፡ 20|21|«ያዛት፤ አትፍራም፡፡ ወደ መጀመሪያ ጠባይዋ እንመልሳታለን» አለው፡፡ 20|22|«እጅህንም ወደ ብብትህ አግባ፡፡ ሌላ ተዓምር ስትኾን ያለነውር ነጭ ኾና ትወጣለችና፡፡ 20|23|«ከተዓምራቶቻችን ታላቋን እናሳይህ ዘንድ (ይህን ሠራን)፡፡ 20|24|«ወደ ፈርዖን ኺድ፡፡ እርሱ ወሰን አልፏልና፡፡» 20|25|(ሙሳም) አለ «ጌታዬ ሆይ! ልቤን አስፋልኝ፡፡ 20|26|«ነገሬንም ለእኔ አግራልኝ፡፡ 20|27|«ከምላሴም መኮላተፍን ፍታልኝ፡፡ 20|28|«ንግግሬን ያውቃሉና፡፡ 20|29|«ከቤተሰቦቼም ለእኔ ረዳትን አድርግልኝ፡፡ 20|30|«ሃሩንን ወንድሜን፡፡ 20|31|«ኅይሌን በእርሱ አበርታልኝ፡፡ 20|32|«በነገሬም አጋራው፡፡ 20|33|«በብዙ እናጠራህ ዘንድ፡፡ 20|34|«በብዙም እንድናወሳህ፡፡ 20|35|«አንተ በእኛ ነገር ዐዋቂ ነህና፡፡» 20|36|(አላህም) አለ «ሙሳ ሆይ! ልመናህን በእርግጥ ተሰጠህ፡፡ 20|37|«በሌላም ጊዜ ባንተ ላይ በእርግጥ ለግሰናል፡፡ 20|38|«ወደናትህ በልብ የሚፈስን ነገር ባሳወቅን ጊዜ፡፡ 20|39|«(ሕፃኑን) በሳጥኑ ውስጥ ጣይው፡፡ እርሱንም (ሳጥኑን) በባሕር ላይ ጣይው፡፡ ባሕሩም በዳርቻው ይጣለው፡፡ ለእኔ ጠላት ለእርሱም ጠላት የኾነ ሰው ይይዘዋልና በማለት (ባሳወቅን ጊዜ ለገስንልህ)፡፡ ባንተ ላይም ከእኔ የኾነን መወደድ ጣልኩብህ፡፡ (ልትወደድና) በእኔም ጥበቃ ታድግ ዘንድ፡፡ 20|40|«እኅትህም በምትኼድና የሚያሳድገውን ሰው ላመላክታችሁን በምትል ጊዜ (መወደድን ጣልኩብህ)፡፡ ወደ እናትህም ዓይንዋ እንዲረጋ (እርሷ) እንዳታዝንም መለስንህ፡፡ ነፍስንም ገደልክ፡፡ ከጭንቅም አዳንንህ፡፡ ፈተናዎችንም ፈተንህ፡፡ በመድየን ቤተሰቦችም ውስጥ (ብዙ) ዓመታትን ተቀመጥክ፡፡ ከዚያም ሙሳ ሆይ! በተወሰነ ጊዜ ላይ መጣህ፡፡ 20|41|«ለነፍሴም (በመልእክቴ) መረጥኩህ፡፡ 20|42|«አንተም ወንድምህም በተዓምራቶቼ ኺዱ፡፡ እኔንም ከማውሳት አትቦዝኑ፡፡ 20|43|«ወደ ፈርዖን ኺዱ፡፡ እርሱ ወሰን አልፏልና፡፡ 20|44|«እርሱም ይገሰጽ ወይም ይፈራ ዘንድ፤ ለእርሱ ልዝብን ቃል ተናገሩት፡፡» 20|45|«ጌታችን ሆይ! እኛ በእኛ ላይ ክፋት በመሥራት መቸኮሉን ወይም ኩራትን መጨመሩን እንፈራለን» አሉ፡፡ 20|46|(አላህም) አለ «አትፍሩ፡፡ እኔ በእርግጥ ከእናንተ ጋር ነኝና፡፡ እሰማለሁ፤ አያለሁም፡፡ 20|47|«ወደርሱም ኺዱ፤ በሉትም፡- ‹እኛ የጌታህ መልክተኞች ነን፡፡› የእስራኤልንም ልጆች ከኛ ጋር ልቀቅ፡፡ አታሰቃያቸውም፡፡ ከጌታህ በኾነው ተዓምር በእርግጥ መጥተንሃልና፡፡ ሰላምም ቀጥታን በተከተለ ሰው ላይ ይኹን፡፡ 20|48|«እኛ ቅጣቱ ባስተባበለና እምቢ ባለ ሰው ላይ ነው ማለት በእርግጥ ተወረደልን፡፡» 20|49|(ፈርዖንም) «ሙሳ ሆይ! ጌታችሁ ማነው» አለ፡፡ 20|50|«ጌታችን ያ ለፍጥረቱ ነገርን ሁሉ (የሚያስፈልገውን) የሰጠ ከዚያም የመራው ነው» አለው፡፡ 20|51|(ፈርዖንም) «የመጀመሪያይቱ ዘመናት ሕዝቦች ኹኔታ ምንድን ነው» አለ፡፡ 20|52|(ሙሳም) «ዕውቀትዋ እጌታዬ ዘንድ በመጽሐፍ የተመዘገበ ነው፡፡ ጌታዬ አይሳሳትም አይረሳምም» አለው፡፡ 20|53|(እርሱ) ያ ምድርን ለእናንተ ምንጣፍ ያደረገላችሁ፣ በእርሷም ውስጥ ለእናንተ መንገድን ያገራላችሁ፣ ውሃንም ከሰማይ ያወረደ ነው (አለ)፡፡ በርሱም ከተለያየ በቃይ ዓይነቶችን አወጣንላችሁ፡፡ 20|54|ብሉ እንስሳዎቻችሁንም አግጡ፤ (ባዮች ኾነን አወጣንላችሁ)፡፡ በዚህ ውስጥ ለአእምሮ ባለቤቶች በእርግጥ ተዓምራት አለበት፡፡ 20|55|ከእርሷ (ከምድር) ፈጠርናችሁ፡፡ በእርሷም ውስጥ እንመልሳችኋለን፡፡ ከእርሷም በሌላ ጊዜ እናወጣችኋለን፡፡ 20|56|ተዓምራቶቻችንንም ሁሏንም (ለፈርዖን) በእርግጥ አሳየነው፡፡ አስተባበለም፡፡ እምቢም አለ፡፡ 20|57|«ከምድራችን በድግምትህ ልታወጣን መጣህብን ሙሳ ሆይ!» አለ፡፡ 20|58|«መሰሉንም ድግምት እናመጣብሃለን፡፡ በእኛና ባንተም መካከል እኛም አንተም የማንጥሰው የኾነ ቀጠሮን በመካከለኛ ስፍራ አድርግልን» አለ፡፡ 20|59|«ቀጠሯችሁ በማጌጫው ቀን ሰዎቹም በረፋድ በሚሰበሰቡበት ነው» አለ፡፡ 20|60|ፈርዖንም ዞረ፡፡ ተንኮሉንም ሰበሰበ፡፡ ከዚያም መጣ፡፡ 20|61|ሙሳ ለእነሱ አላቸው «ወዮላችሁ በአላህ ላይ ውሸትን አትቅጠፉ፡፡ በቅጣት ያጠፋችኋልና፡፡ የቀጠፈም ሰው በእርግጥ አፈረ፡፡» 20|62|(ድግምተኞቹ) በመካከላቸውም ነገራቸውን ተጨቃጨቁ፡፡ ውይይትንም ደበቁ፡፡ 20|63|«እነዚህ በእርግጥ ደጋሚዎች ናቸው፡፡ ከምድራችሁ በድግምታቸው ሊያወጧችሁ በላጪቱንም መንገዳችሁን ሊያስወግዱባችሁ ይሻሉ» አሉ፡፡ 20|64|«ተንኮላችሁንም አጠንክሩ፡፡ ከዚያም ተሰልፋችሁ ኑ፡፡ ዛሬ ያሸነፈም ሰው ምኞቱን አገኘ» (ተባባሉ)፡፡ 20|65|«ሙሳ ሆይ! ወይ ትጥላለህ ወይም በመጀመሪያ የምንጥል እንኾናለን» (ምረጥ) አሉ፡፡ 20|66|«አይደለም ጣሉ» አላቸው፡፡ ወዲያውም ገመዶቻቸውና ዘንጎቻቸው ከድግምታቸው የተነሳ እነርሱ የሚሮጡ (እባቦች) ኾነው ወደርሱ ተመለሱ፡፡ 20|67|ሙሳም በነፍሱ ውስጥ ፍርሃትን አሳደረ፡፡ 20|68|«አትፍራ አንተ የበላዩ አንተ ነህና» አልነው፡፡ 20|69|«በቀኝ እጅህ ያለቸውንም በትር ጣል፡፡ ያንን የሠሩትን ትውጣለችና፡፡ ያ የሠሩት ሁሉ የድግምተኛ ተንኮል ነውና፡፡ ድግምተኛም በመጣበት ስፍራ ሁሉ አይቀናውም» (አልን)፡፡ 20|70|ድግምተኞቹም ሰጋጆች ኾነው ወደቁ፡፡ «በሃሩንና በሙሳ ጌታ አመንን» አሉ፡፡ 20|71|(ፈርዖንም) «ለእናንተ ሳልፈቅድላችሁ በፊት ለእርሱ አመናችሁን እርሱ በእርግጥ ያ ድግምትን ያስተማራችሁ ትልቃችሁ ነው፡፡ እጆቻችሁንና እግሮቻችሁን በማናጋት (ግራናቀኝን በማፈራረቅ) እቆራርጣችኋለሁ፡፡ በዘምባባም ግንዶች ለይ እሰቅላችኋለሁ፡፡ ማንኛችንም ቅጣቱ በጣም ብርቱ የሚቆይም መኾኑን ታውቃላችሁ» አላቸው፡፡ 20|72|ከመጡልን ታምራቶች ከዚያም ከፈጠረን(አምላክ) ፈጽሞ አንመርጥህም፤ አንተም የምትፈርደውን ፍረድ፤ የምትፈርደው በዚች በአነስተኛይቱ ሕይወት ብቻ ነው አሉ፡፡ 20|73|«ኃጢአቶቻችንንና ከድግምትም በእርሱ ላይ ያስገደድከንን ለእኛ ይምረን ዘንድ እኛ በጌታችን አምነናል፡፡ አላህም በጣም በላጭ ነው፤ (ቅጣቱም) በጣም የሚዘወትር ነው» አሉ፡፡ 20|74|እነሆ ከሓዲ ኾኖ ወደ ጌታው የሚመጣ ሰው ለእርሱ ገሀነም አለችው፡፡ በውስጧም አይሞትም ሕያውም አይኾን፡፡ 20|75|በጎ ሥራዎችን በእርግጥ የሠራ ምእመን ኾኖ የመጣውም ሰው እነዚያ ለእነሱ ከፍተኛ ደረጃዎች አሏቸው፡፡ 20|76|ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው የመኖሪያ ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ (አሏቸው)፡፡ ይህም የተጥራራ ሰው ምንዳ ነው፡፡ 20|77|ወደ ሙሳም «ባሮቼን ይዘህ በሌሊት ኺድ፡፡ ለእነሱም በባሕር ውስጥ ደረቅ መንገድን አድርግላቸው፡፡ መገኘትን አትፍራ፡፡ (ከመስጠም) አትጨነቅም፡፡» ስንል በእርግጥ ላክንበት፡፡ 20|78|ፈርዖንም ከሰራዊቱ ጋር ኾኖ ተከተላቸው፡፡ ከባህሩም የሚሸፍን ሸፈናቸው፡፡ 20|79|ፈርዖንም ሕዝቦቹን አሳሳታቸው፡፡ ቅኑንም መንገድ አልመራቸውም፡፡ 20|80|የእስራኤል ልጆች ሆይ! ከጠላታችሁ በእርግጥ አዳንናችሁ፡፡ በጡርም ቀኝ ጎን ቀጠሮ አደረግንላችሁ፡፡ በእናንተም ላይ መናንና ድርጭትን አወረድንላችሁ፡፡ 20|81|ከሰጠናችሁ ሲሳይ፤ ከመልካሙ ብሉ፡፡ በእርሱም ወሰንን አትለፉ፡፡ ቁጣዬ በእናንተ ላይ ይወርድባችኋልና፡፡ በእርሱም ላይ ቁጣዬ የሚወርድበት ሰው በእርግጥ ይጠፋል፡፡ 20|82|እኔም ለተጸጸተ፣ ላመነም፣ መልካምንም ለሠራ፣ ከዚያም ለተመራ ሰው በእርግጥ መሓሪ ነኝ፡፡ 20|83|«ሙሳ ሆይ! ከሕዝቦችህ ምን አስቸኮለህም» (ተባለ)፡፡ 20|84|«እነሱ እነዚህ፤ በዱካዬ ላይ ያሉ ናቸው፡፡ ጌታዬ ሆይ! ትወድልንም ዘንድ ወደ አንተ ቸኮልኩ» አለ፡፡ 20|85|(አላህ) «እኛም ከአንተ በኋላ ሰዎችህን በእርግጥ ፈትተን፡፡ ሳምራዊውም አሳሳታቸው» አለው፡፡ 20|86|ሙሳም ወደ ሰዎቹ የተቆጣ ያዘነ ኾኖ ተመለሰ፡፡ «ሕዝቦቼ ሆይ! ጌታችሁ መልካም ተስፋን አልቀጠራችሁምን ቀጠሮው በእናንተ ላይ ረዘመባችሁን» ወይስ በእናንተ ላይ ከጌታችሁ ቅጣት ሊወርድባችሁ ፈለጋችሁና ቀጠሮየን አፈረሳችሁን አላቸው፡፡ 20|87|«ቀጠሮህን በፈቃዳችን አልጣስንም፡፡ ግን እኛ ከሕዝቦቹ ጌጥ ሸክሞችን ተጫን (በእሳት ላይ) ጣልናትም፡፡ ሳምራዊውም እንደዚሁ ጣለ» አሉት፡፡ 20|88|ለእነሱም አካል የኾነ ጥጃን ለእርሱ መጓጎር ያለውን አወጣላቸው፡፡ (ተከታዮቹ) «ይህ አምላካችሁ የሙሳም አምላክ ነው ግን ረሳው» አሉም፡፡ 20|89|ወደእነሱ ንግግርን የማይመልስ ለእነሱም ጉዳትንና ጥቅምን የማይችል መኾኑን አያዩምን 20|90|ሃሩንም ከዚህ በፊት በእርግጥ አላቸው፡- «ሕዝቦቼ ሆይ! (ይህ) በእርሱ የተሞከራችሁበት ብቻ ነው፡፡ ጌታችሁም አልረሕማን ነው፡፡ ተከተሉኝም፡፡ ትዕዛዜንም ስሙ፡፡» 20|91|«ሙሳ ወደእኛ እስከሚመለስ በእርሱ (መገዛት) ላይ ከመቆየት ፈጽሞ አንወገድም» አሉ፡፡ 20|92|(ሙሳ) አለ፡- «ሃሩን ሆይ! ተሳስተው ባየሃቸው ጊዜ ምን ከለከልህ 20|93|«እኔን ከመከተል ትዕዛዜን ጣስክን» 20|94|«የእናቴ ልጅ ሆይ! ጢሜንም ራሴንም አትያዝ፡፡ እኔ በእስራኤል ልጆች መካከል ለያየህ፤ ቃሌንም አልጠበቅህም ማለትህን ፈራሁ» አለው፡፡ 20|95|(ሙሳ) «ሳምራዊው ሆይ! ነገርህም ምንድን ነው» አለ፡፡ 20|96|ያላዩትን ነገር አየሁ፡፡ ከመልክተኛው (ከፈረሱ ኮቴ) ዱካም ጭብጥ አፈርን ዘገንኩ፡፡ (በቅርጹ ላይ) ጣልኳትም፡፡ እንደዚሁም ነፍሴ ሸለመችልኝ» አለ፡፡ 20|97|አለው «ኺድ፤ ላንተም በሕይወትህ (ለአየኸው ሰው ሁሉ) መነካካት የለም ማለት አለህ፡፡ ለአንተም ፈጽሞ የማትጣሰው ቀጠሮ አለህ፡፡ ወደዚያም በእርሱ ላይ ተገዢው ኾነህ ወደ ቆየህበት አምላክህ ተመልከት፡፡ በእርግጥ እናቃጥለዋለን፡፡ ከዚያም በባሕሩ ውስጥ መበተንን እንበትነዋለን፡፡» 20|98|ጌታችሁ ያ ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ የሌለ የኾነው አላህ ብቻ ነው፡፡ እውቀቱ ነገርን ሁሉ አዳረሰ፡፡ 20|99|እንደዚሁ በእርግጥ ካለፉት ወሬዎች ባንተ ላይ እንተርካለን፡፡ ከእኛም ዘንድ ቁረኣንን በእርግጥ ሰጠንህ፡፡ 20|100|ከእርሱ ያፈገፈገ ሰው እርሱ በትንሣኤ ቀን ከባድን ቅጣት ይሸከማል፡፡ 20|101|በእርሱ ውስጥ ዘውታሪዎች ኾነው (ይሸከማሉ)፡፡ በትንሣኤም ቀን ለእነሱ የኾነው ሸክም ከፋ! 20|102|በቀንዱ በሚነፋ ቀን (ሸክማቸው ከፋ)፤ ከሓዲዎችንም በዚያ ቀን (ዓይኖቻቸው) ሰማያዊዎች ሆነው እንሰበስባቸዋለን፡፡ 20|103|«ዐሥርን (ቀን) እንጂ አልቆያችሁም» በመባባል በመካከላቸው ይንሾካሾካሉ፡፡ 20|104|በሐሳብ ቀጥተኛው «አንድን ቀን እንጅ አልቆያችሁም» በሚል ጊዜ የሚሉትን ነገር እኛ ዐዋቂዎች ነን፡፡ 20|105|ከጋራዎችም ይጠይቁሃል፤ በላቸው «ጌታዬ መበተንን ይበትናቸዋል፡፡ 20|106|«ትክክል ሜዳም ኾና ይተዋታል፡፡ 20|107|«በርሷ ዝቅታና ከፍታን አታይም፡፡» 20|108|በዚያ ቀን (ለመሰብሰብ) ጠሪውን ለእርሱ መጣመም የሌለውን መከተል ይከተላሉ፡፡ ድምጾችም ለአልረሕማን ጸጥ ይላሉ፡፡ ስለዚህ ሹክሹክታን እንጂ አትሰማም፡፡ 20|109|በዚያ ቀን ለእርሱ አልረሕማን የፈቀደለትንና ለእርሱም ቃልን የወደደለትን ሰው ቢኾን እንጅ ምልጃ (አንድንም) አትጠቅምም፡፡ 20|110|በስተፊታቸው ያለውን በስተኋላቸውም ያለውን ሁሉ ያውቃል፡፡ በእርሱም ዕውቀትን አያካብቡም፤ (አያውቁም)፡፡ 20|111|ፊቶችም ሁሉ ሕያው አስተናባሪ ለኾነው (አላህ) ተዋረዱ፡፡ በደልንም የተሸከመ ሰው በእርግጥ ከሰረ፡፡ 20|112|እርሱ አማኝ ኾኖ ከመልካም ሥራዎችም የሠራ ሰው በደልንም መጉደልንም አይፈራም፡፡ 20|113|እንደዚሁም ዐረብኛ ቁርኣን ኾኖ አወረድነው፡፡ አላህንም ይፈሩ ዘንድ ወይም ለእነሱ ግሣጼን ያድስላቸው ዘንድ ከዛቻ ደጋግመን በውስጡ ገለጽን፡፡ 20|114|እውነተኛው ንጉስ አላህም (ከሓዲዎች ከሚሉት) ላቀ፡፡ ወደ አንተ መወረዱም ከመፈጸሙ በፊት በማንበብ አትቸኩል፡፡ «ጌታዬ ሆይ! ዕውቀትንም ጨምርልኝ» በል፡፡ 20|115|ወደ አደምም ከዚህ በፊት ኪዳንን በእርግጥ አወረድን፡፡ ረሳም፡፡ ለእርሱም ቆራጥነትን አላገኘንለትም፡፡ 20|116|ለመላእክትም ለአዳም ስገዱ ባልን ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ሰገዱም፤ ኢብሊስ ብቻ ሲቀር እምቢ አለ፡፡ 20|117|አልንም «አደም ሆይ! ይህ ላንተም ለሚስትህም በእርግጥ ጠላት ነው፡፡ ስለዚህ ከገነት አያውጣችሁ፤ ትለፋለህና፡፡ 20|118|ለአንተ በእርሷ ውስጥ አለመራብና አለመታረዝ አለህ፡፡ 20|119|አንተም በርሷ ውስጥ አትጠማም፤ ፀሐይም አትተኮስም፡፡ 20|120|ሰይጣንም ወደርሱ ጎተጎተ «አደም ሆይ! በመዘውተሪያ ዛፍ በማይጠፋ ንግሥናም ላይ ላመላክትህን አለው፡፡ 20|121|ከእርሷም በልሉ፡፡ ለእነርሱም ኀፍረተ ገላቸው ተገለጸች፡፡ ከገነትም ቅጠል በላያቸው ላይ ይለጥፉ ጀመር፡፡ አደምም የጌታውን ትእዛዝ (ረስቶ) ጣሰ፡፡ (ከፈለገው መዘውተር) ተሳሳተም፡፡ 20|122|ከዚያም ጌታው መረጠው ከእርሱም ጸጸቱን ተቀበለው መራውም፡፡ 20|123|አላቸው «ከፊላችሁም ለከፊሉ ጠላት ሲኾን ሁላችሁም ከእርሷ ውረዱ ከእኔም የኾነ መሪ ቢመጣላችሁ መሪየን የተከተለ አይሳሳትም አይቸገርምም፡፡ 20|124|«ከግሣጼዬም የዞረ ሰው ለእርሱ ጠባብ ኑሮ አለው፡፡ በትንሣኤም ቀን ዕውር ኾኖ እንቀሰቅሰዋለን፡፡ 20|125|«ጌታዬ ሆይ! ለምን ዕውር አድርገህ አስነሳኸኝ በእርግጥ የማይ የነበርኩ ስኾን» ይላል፡፡ 20|126|(ነገሩ) እንደዚሁ ነው፡፡ «ታምራታችን መጣችልህ፡፡ ተውካትም፡፡ እንደዚሁም ዛሬ ትተዋለህ» ይለዋል፡፡ 20|127|እንደዚሁም ያጋራንና በጌታው አንቀጾች ያላመነን ሰው እንቀጣዋለን፡፡ የመጨረሻይቱም ዓለም ቅጣት በጣም ብርቱ ሁልጊዜ ዘውታሪም ነው፡፡ 20|128|(ቁረይሾች) ከእነሱ በፊት ከክፍለ ዘመናት ሕዝቦች ብዙዎችን ያጠፋን መኾናችን በመኖሪያዎቻቸው የሚኼዱ ኾነው ሳሉ ለእነርሱ አልተገለጸላቸውምን በዚህ ውስጥ ለአእምሮ ባለቤቶች በእርግጥ መልክቶች አሉበት፡፡ 20|129|ከጌታህ ያለፈች ቃልና የተወሰነ ጊዜ ባልነበረ ኖሮ (ቅጣቱ አሁኑኑ) የሚይዛቸው ይኾን ነበር፡፡ 20|130|በሚሉትም ላይ ታገስ፡፡ ጌታህንም ፀሐይ ከመውጣትዋ በፊት ከመግባትዋም በፊት የምታመሰግን ኾነህ አጥራው፤ (ስገድ)፡፡ ከሌሊት ሰዓቶችም በቀን ጫፎችም አጥራው፡፡ (በሚሰጥህ ምንዳ) ልትወድ ይከጀላልና፡፡ 20|131|ዓይኖችህንም ከእነርሱ (ከሰዎቹ) ክፍሎችን በእርሱ ልንፈትናቸው ወደ አጣቀምንበት፤ ወደ ቅርቢቱ ሕይወት ጌጦች አትዘርጋ፡፡ የጌታህ ሲሳይም በጣም በላጭ ዘውታሪም ነው፡፡ 20|132|ቤተሰብህንም በስግደት እዘዝ፡፡ በእርሷም ላይ ዘውትር፤(ጽና)፡፡ ሲሳይን አንጠይቅህም፡፡ እኛ እንሰጥሃለን፡፡ መልካሚቱ መጨረሻም ለጥንቁቆቹ ናት፡፡ 20|133|«ከጌታውም በኾነ ተዓምር አይመጣንምን» አሉ በመጀመሪያዎቹ ጽሑፎች ውስጥ ያለችው ማስረጃ አልመጣቻቸውምን 20|134|እኛም ከእርሱ (ከሙሐመድ መላክ) በፊት በቅጣት ባጠፋናቸው ኖሮ «ጌታችን ሆይ! ከመዋረዳችንና ከማፈራችን በፊት አንቀጾችህን እንከተል ዘንድ ወደኛ መልከተኛን አትልክም ነበርን» ባሉ ነበር፡፡ 20|135|«ሁሉም ተጠባባቂ ነው፡፡ ተጠባበቁም፡፡ የቀጥታውም መንገድ ባለቤቶች እነማን እንደሆኑ እነማንም እንደ ተመሩ ወደ ፊት ታውቃላችሁ» በላቸው፡፡ 21|1|ለሰዎች እነርሱ በዝንጋቴ ውስጥ (መሰናዳትን) የተው ኾነው ሳሉ ምርመራቸው ቀረበ፡፡ 21|2|ከጌታቸው አዲስ የተወረደ ቁርኣን አይመጣላቸውም፡፡ እነሱ የሚያላግጡ ሆነው የሚያደምጡት ቢሆኑ እንጂ፡፡ 21|3|ልቦቻቸው ዝንጉዎች ኾነው (የሚያዳምጡት ቢኾኑ እንጅ)፡፡ እነዚያም የበደሉት ሰዎች መንሾካሾክን ደበቁ፡፡ «ይህ ብጤያችሁ ሰው እንጅ ሌላ ነውን እናንተም የምታዩ ስትኾኑ ድግምትን ለመቀበል ትመጣላችሁን» (አሉ)፡፡ 21|4|(ሙሐመድም) «ጌታዬ ቃልን ሁሉ በሰማይና በምድር ውስጥ ያለ ሲኾን ያውቃል እርሱም ሰሚው ዐዋቂው ነው» አለ፡፡ 21|5|«በእውነቱ (ቁርኣኑ) የሕልሞች ቅዠቶች ነው፡፡ ይልቁንም ቀጠፈው እንዲያውም እርሱ ቅኔን ገጣሚ ነው፡፡ የቀድሞዎቹም እንደተላኩ (መልክተኛ ከኾነ) በተዓምር ይምጣብን» አሉ፡፡ 21|6|ከእነሱ በፊት ያጠፋናት ከተማ አላመነችም፡፡ ታዲያ እነሱ ያምናሉን 21|7|ከአንተም በፊት ወደእነሱ የምናወርድላቸው የኾነን ሰዎችን እንጂ ሌላን አላክንም፡፡ የማታውቁም ብትኾኑ የመጽሐፉን ባለቤቶች ጠይቁ፡፡ 21|8|ምግብን የማይበሉ አካልም አላደረግናቸውም፡፡ ዘውታሪዎችም አልነበሩም፡፡ 21|9|ከዚያም ቀጠሮን ሞላንላቸው፡፡ አዳንናቸውም፡፡ የምንሻውንም ሰው (አዳን)፡፡ ወሰን አላፊዎቹንም አጠፋን፡፡ 21|10|ክብራችሁ በውስጡ ያለበትን መጽሐፍ ወደእናንተ በእርግጥ አወረድን፡፡ አታውቁምን 21|11|በዳይም ከነበረች ከተማ ያጠፋናትና ከኋላዋም ሌሎችን ሕዝቦች ያስገኘነው ብዙ ናት፡፡ 21|12|ቅጣታችንም በተሰማቸው ጊዜ እነርሱ ወዲያውኑ ከእርሷ (ለመሸሽ) ይገሠግሣሉ፡፡ 21|13|አትገሥግሡ፤ ትለመኑም ይኾናልና፡፡ በእርሱ ወደ ተቀማጠላችሁበት ጸጋ ወደ መኖሪያዎቻችሁም ተመለሱ (ይባላሉ)፡፡ 21|14|«ዋ ጥፋታችን! እኛ በእርግጥ በዳዮች ነበርን» ይላሉ፡፡ 21|15|የታጨዱ ሬሳዎችም እስካደረግናቸው ድረስ ይህቺ ጠሪያቸው ከመኾን አልተወገደችም፡፡ 21|16|ሰማይንና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ ቀላጆች ኾነን አልፈጠርንም፡፡ 21|17|መጫወቻን (ሚስትና ልጅን) ልንይዝ በሻን ኖሮ ከእኛ ዘንድ በያዝነው ነበር፡፡ (ግን) ሠሪዎች አይደለንም፡፡ 21|18|በእርግጥ እውነትን በውሸት ላይ እንጥላለን፡፡ አንጎሉን ያፈርሰዋልም፡፡ ወዲያውም እርሱ ጠፊ ነው፡፡ ለእናንተም ከዚያ (ሚስትና ልጅ አለው በማለት) ከምትመጥኑት ነገር ብርቱ ቅጣት አላችሁ፤ (ወዮላችሁ)፡፡ 21|19|በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉም የእርሱ ነው፡፡ እርሱ ዘንድ ያሉትም (መላእክት) እርሱን ከመገዛት አይኮሩም፡፡ አይሰለቹምም፡፡ 21|20|በሌሊትና በቀንም ያጠሩታል፤ አያርፉም፡፡ 21|21|ይልቁንም ከምድር የኾኑን እነርሱ ሙታንን የሚያስነሱን አማልክት ያዙን (የለም)፡፡ 21|22|በሁለቱ (በሰማያትና በምድር) ውስጥ ከአላህ ሌላ አማልክት በነበሩ ኖሮ በተበላሹ ነበር፡፡ የዐርሹ ጌታ አላህም ከሚሉት ሁሉ ጠራ፡፡ 21|23|ከሚሠራው ሁሉ አይጠየቅም፡፡ እነርሱ (ፍጥረቶቹ) ግን ይጠየቃሉ፡፡ 21|24|ይልቁንም ከእርሱ ሌላ አማልክትን ያዙን «አስረጃችሁን አምጡ፡፡ ይህ (ቁርኣን) እኔ ዘንድ ያለው ሕዝብ መገሰጫ ከእኔ በፊትም የነበሩት ሕዝቦች መገሰጫ ነው» በላቸው፡፡ በውነቱ አብዛኞቻቸው እውነቱን አያውቁም፡፡ ስለዚህ እነሱ እምቢተኞች ናቸው፡፡ 21|25|ከአንተ በፊትም እነሆ ከእኔ ሌላ አምላክ የለምና ተገዙኝ በማለት ወደርሱ የምናወርድለት ቢኾን እንጅ ከመልክተኛ አንድንም አልላክንም፡፡ 21|26|«አልረሕማንም (ከመላእክት) ልጅን ያዘ» አሉ፡፡ ጥራት ተገባው፡፡ አይደለም (መላእክት) የተከበሩ ባሮች ናቸው፡፡ 21|27|በንግግር አይቀድሙትም፤ (ያላለውን አይሉም)፡፡ እነርሱም በትእዛዙ ይሠራሉ፡፡ 21|28|በፊታቸው ያለውንና በኋላቸው ያለውንም ሁሉ ያውቃል፡፡ ለወደደውም ሰው እንጅ ለሌላው አያማልዱም፡፡ እነርሱም እርሱን ከመፍራታቸው የተነሳ ተጨናቂዎች ናቸው፡፡ 21|29|ከእነሱም «እኔ ከእርሱ ሌላ አምላክ ነኝ» የሚል ያንን ገሀነምን እንመነዳዋለን፡፡ እንደዚሁ በዳዮችን እንመነዳለን፡፡ 21|30|እነዚያም የካዱት ሰማያትና ምድር የተጣበቁ የነበሩና የለያየናቸው መኾናችንን አያውቁምን ሕያው የኾነንም ነገር ሁሉ ከውሃ ፈጠርን፡፡ አያምኑምን 21|31|በምድርም ውስጥ በእነሱ እንዳታረገርግ ጋራዎችን አደረግን፡፡ ይመሩም ዘንድ በእርሷ ውስጥ ሰፋፊ መንገዶችን አደረግን፡፡ 21|32|ሰማይንም (ከመውደቅ) የተጠበቀ ጣራ አደረግን፡፡ እነርሱም ከተዓምራቶቿ ዘንጊዎች ናቸው፡፡ 21|33|እርሱም ሌሊትንና ቀንን፣ ፀሐይንና ጨረቃንም የፈጠረ ነው፡፡ ሁሉም በፈለካቸው ውስጥ ይዋኛሉ፡፡ 21|34|(ሙሐመድ ሆይ!) ካንተ በፊት ለማንም ሰው ዘለዓለም መኖርን አላደረግንም፡፡ ታዲያ ብትሞት እነሱ ዘውታሪዎች ናቸውን 21|35|ነፍስ ሁሉ ሞትን ቀማሽ ናት፡፡ ለመፈተንም በክፉም በበጎም እንሞክራችኋለን፡፡ ወደኛም ትመለሳላችሁ፡፡ 21|36|እነዚያም የካዱት ሰዎች ባዩህ ጊዜ መሳለቂያ አድርገው እንጂ አይይዙህም፡፡ እነሱ በአልረሕማን መወሳት እነርሱ ከሓዲዎች ሲሆኑ «ያ አማልክቶቻችሁን (በክፉ) የሚያነሳው ይህ ነውን» (ይላሉ)፡፡ 21|37|ሰው ቸኳይ ሆኖ ተፈጠረ፡፡ ተዓምራቶቼን በእርግጥ አሳያችኋለሁና አታቻኩሉኝ፡፡ 21|38|«ይህ ቀጠሮም መቼ ነው እውነተኞች ከኾናችሁ (አምጡት)» ይላሉ፡፡ 21|39|እነዚያ የካዱት ከፊቶቻቸውና ከጀርባዎቻቸው ላይ እሳትን የማይከለክሉበትን እነሱም የማይረዳዱበትን ጊዜ ቢያውቁ ኖሮ (ይህንን አይሉም ነበር)፡፡ 21|40|ይልቁንም (ሰዓቲቱ) በድንገት ትመጣቸዋለች፤ ታዋልላቸዋለችም፡፡ መመለሷንም አይችሉም፡፡ እነሱም አይቆዩም፡፡ 21|41|ከአንተ በፊትም የነበሩት መልክተኞች በእርግጥ ተቀለደባቸው፡፡ በእነዚያም ከእነሱ ይቀልዱ በነበሩት በርሱ ይሳለቁበት የነበሩት (ቅጣት) ሰፈረባቸው፡፡ 21|42|«ከአልረሕማን (ቅጣት) በሌሊትና በቀን የሚጠብቃችሁ ማነው» በላቸው፡፡ በእውነቱ እነሱ ከጌታቸው ግሳጼ (ከቁርአን) ዘንጊዎች ናቸው፡፡ 21|43|ለእነሱ ከእኛ ሌላ የምትከላከልላቸው አማልክት አለቻቸውን ነፍሶቻቸውን መርዳትን አይችሉም፡፡ እነርሱም (ከሓዲዎቹ) ከእኛ አይጠበቁም፡፡ 21|44|በእውነት እነዚህንና አባቶቻቸውን በእነሱ ላይ ዕድሜ እስከ ረዘመባቸው ድረስ አጣቀምናቸው፡፡ (ተታለሉም)፡፡ እኛ ምድርን ከጫፎችዋ የምናጎላት ኾነን ስንመጣባት አያዩምን እነሱ አሸናፊዎች ናቸውን 21|45|«የማስፈራራችሁ በተወረደልኝ ብቻ ነው፡፡ ግን ደንቆሮዎች በሚስፈራሩ ጊዜ ጥሪን አይሰሙም» በላቸው፡፡ 21|46|ከጌታህ ቅጣትም ወላፈን ብትነካቸው «ዋ ጥፋታችን! እኛ በዳዮች ነበርን» ይላሉ፡፡ 21|47|በትንሣኤም ቀን ትክክለኛ ሚዛኖችን እናቆማለን፡፡ ማንኛይቱም ነፍስ ምንንም አትበደልም፡፡ (ሥራው) የሰናፍጭ ቅንጣት ያክል ቢኾንም እርሷን እናመጣታለን፡፡ ተቆጣጣሪዎችም በኛ በቃ፡፡ 21|48|ለሙሳና ለሃሩንም እውነትንና ውሸትን የሚለይን ብርሃንንም ለጥንቁቆችም መገሰጫን በእርግጥ ሰጠናቸው፡፡ 21|49|ለእነዚያ ጌታቸውን በሩቅ ለሚፈሩት እነሱም ከሰዓቲቱ ተጨናቂዎች ለኾኑ (መገሰጫን ሰጠን)፡፡ 21|50|ይህም (ቁርኣን) ያወረድነው የኾነ ብሩክ መገሰጫ ነው፡፡ ታዲያ እናንተ ለእርሱ ከሓዲዎች ናችሁን 21|51|ለኢብራሂምም ከዚያ በፊት ቅን መንገዱን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ እኛም በእርሱ (ተገቢነት) ዐዋቂዎች ነበርን፡፡ 21|52|ለአባቱና ለሕዝቦቹ «ይህቺ ቅርጻ ቅርጽ ያቺ እናንተ ለእርሷ ተገዢዎች የኾናችሁት ምንድን ናት» ባለ ጊዜ (መራነው)፡፡ 21|53|«አባቶቻችንን ለእርሷ ተገዢዎች ኾነው አገኘን» አሉት፡፡ 21|54|«እናንተም አባቶቻችሁም በእርግጥ በግልጽ ስህተት ውስጥ ነበራችሁ» አላቸው፡፡ 21|55|«በምሩ መጣህልን ወይንስ አንተ ከሚቀልዱት ነህ» አሉት፡፡ 21|56|«አይደለም ጌታችሁ የሰማያትና የምድር ጌታ ያ የፈጠራቸው ነው፡፡ እኔም በዚህ ላይ ከመስካሪዎቹ ነኝ» አለ፡፡ 21|57|«በአላህም እምላለሁ ዟሪዎች ኾናችሁ ከሄዳችሁ በኋላ ጣዖቶቻችሁን ተንኮል እሠራባቸዋለሁ» (አለ)፡፡ 21|58|(ዘወር ሲሉ) ስብርብሮችም አደረጋቸው፡፡ ለእነሱ የኾነ አንድ ታላቅ (ጣዖት) ብቻ ሲቀር ወደርሱ ይመለሱ ዘንድ (እርሱን ተወው)፡፡ 21|59|«በአማልክቶቻችን ይህንን የሠራ ማነው እርሱ በእርግጥ ከበደለኞች ነው» አሉ፡፡ 21|60|«ኢብራሂም የሚባል ጎበዝ (በመጥፎ) ሲያነሳቸው ሰምተናል» ተባባሉ፡፡ 21|61|«ይመሰክሩበት ዘንድ በሰዎቹ ዓይን (ፊት) ላይ አምጡት» አሉ፡፡ 21|62|«ኢብራሂም ሆይ! በአማልክቶቻችን ይህንን የሠራህ አንተ ነህን» አሉት፡፡ 21|63|«አይደለም ይህ ታላቃቸው ሠራው፡፡ ይናገሩም እንደ ኾነ ጠይቋቸው» አለ፡፡ 21|64|ወደ ነፍሶቻቸውም ተመለሱ፡፡ «እናንተ (በመጠየቃችሁ) በዳዮቹ እናንተው ናችሁም» ተባባሉ፡፡ 21|65|ከዚያም በራሶቻቸው ላይ ተገለበጡ፡፡ «እነዚህ የሚናገሩ አለመኾናቸውን በእርግጥ ዐውቀሃል፤» (አሉ)፡፡ 21|66|«ታዲያ ለእናንተ ምንም የማይጠቅማችሁንና የማይጎዳችሁን ነገር ከአላህ ሌላ ትገዛላችሁን» አላቸው፡፡ 21|67|«ፎህ! ለእናንተ ከአላህ ሌላ ለምትገዙትም ነገር፤ አታውቁምን» (አለ)፡፡ 21|68|«ሠሪዎች እንደ ኾናችሁ አቃጥሉት፡፡ አማልክቶቻችሁንም እርዱ» አሉ፡፡ (በእሳት ላይ ጣሉትም)፡፡ 21|69|«እሳት ሆይ! በኢብራሂም ላይ ቀዝቃዛ፤ ሰላምም ሁኚ» አልን፡፡ 21|70|በእርሱም ተንኮልን አሰቡ፡፡ በጣም ከሳሪዎችም አደረግናቸው፡፡ 21|71|እርሱንና ሉጥንም ወደዚያች፤ በውስጧ ለዓለማት በረከትን ወደ አደረግንባት ምድር (በመውሰድ) አዳን፡፡ 21|72|ለእርሱም ኢስሐቅን ያዕቆብንም ተጨማሪ አድርገን ሰጠነው፡፡ ሁሉንም መልካሞች አደረግን፡፤ 21|73|በትዕዛዛችንም ወደ በጎ ሥራ የሚመሩ መሪዎች አደረግናቸው፡፡ ወደእነሱም መልካም ሥራዎችን መሥራትን፣ ሶላትንም መስገድን፣ ዘካንም መስጠትን አወረድን፡፡ ለእኛ ተገዢዎችም ነበሩ፡፡ 21|74|ሉጥንም ፍርድንና ዕውቀትን ሰጠነው፡፡ ከዚያችም መጥፎ ሥራዎችን ትሠራ ከነበረችው ከተማ አዳንነው፡፡ እነሱ ክፉ ሰዎች አመጸኞች ነበሩና፡፡ 21|75|በችሮታችንም ውስጥ አገባነው፡፡ እርሱ ከመልካሞቹ ነውና፡፡ 21|76|ኑሕንም ከዚያ በፊት (ጌታውን) በጠራ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ለእርሱም (ጥሪውን) ተቀበልነው፡፡ እርሱንም ቤተሰቦቹንም ከከባድ ጭንቅ አዳን፡፡ 21|77|ከነዚያም በታምራቶቻችን ከአስተባበሉት ሕዝቦች (ተንኮል) ጠበቅነው፡፡ እነሱ ክፉ ሕዝቦች አመጸኞች ነበሩና፡፡ ሁሉንም አሰጠምናቸውም፡፡ 21|78|ዳውድንና ሱለይማንንም በአዝመራው ነገር በሚፈርዱ ጊዜ የሕዝቦቹ ፍየሎች ሌሊት በርሱ ውስጥ በተሰማሩ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ፍርዳቸውንም ዐዋቂዎች ነበርን፡፡ 21|79|ለሱለይማንም (ትክክለኛይቱን ፍርድ) አሳወቅናት፡፡ ለሁሉም ጥበብንና ዕውቀትን ሰጠን፡፡ ተራራዎችን ከዳውድ ጋር የሚያወድሱ ሲኾኑ ገራን፡፡ አእዋፍንም (እንደዚሁ ገራን)፡፡ ሠሪዎችም ነበርን፡፡ 21|80|የብረት ልብስንም ሥራ ለእናንተ ከጦራችሁ ትጠብቃችሁ ዘንድ አስተማርነው፡፡ እናንተ አመስጋኞች ናችሁን 21|81|ለሱለይማንም ነፋስን በኀይል የምትነፍስ በትዕዛዙ ወደዚያች በእርሷ ውስጥ በረከትን ወደ አደረግንባት ምድር (ወደ ሻም) የምትፈስ ስትኾን (ገራንለት)፡፡ በነገሩ ሁሉም ዐዋቂዎች ነበርን፡፡ 21|82|ከሰይጣናትም ለእርሱ (ሉልን ለማውጣት) የሚጠልሙንና ከዚያም ሌላ ያለን ሥራ የሚሠሩን (ገራንለት)፡፡ ለእነሱም ተጠባባቂዎች ነበርን፡፡ 21|83|አዩብንም (ኢዮብን) ጌታውን «እኔ መከራ አገኘኝ አንተም ከአዛኞች ሁሉ ይበልጥ አዛኝ ነህ» ሲል በተጣራ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 21|84|ለእርሱም ጥሪውን ተቀበልነው፡፡ ከጉዳትም በእርሱ ላይ የነበረውን ሁሉ አስወገድን፡፡ ቤተሰቦቹንም ከእነሱም ጋር መሰላቸውን ከእኛ ዘንድ ለችሮታና ለተገዢዎች ለማስገንዘብ ሰጠነው፡፡ 21|85|ኢስማዒልንም ኢድሪስንም ዙልኪፍልንም (አስታውስ)፡፡ ሁሉም ከታጋሾቹ ናቸው፡፡ 21|86|ከችሮታችንም ውስጥ አገባናቸው፡፡ እነሱ ከመልካሞቹ ናቸውና፡፡ 21|87|የዓሳውንም ባለቤት ተቆጥቶ በኼደ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ በእርሱም ላይ ፈጽሞ የማንፈርድበት መኾናችንን ጠረጠረ፡፡ (ዓሳም ዋጠው)፡፡ በጨለማዎችም ውስጥ ኾኖ ከአንተ በቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ ጥራት ይገባህ፡፡ እኔ በእርግጥ ከበዳዮቹ ነበርኩ በማለት ተጣራ፡፡ 21|88|ለርሱም ጥሪውን ተቀበልነው፡፡ ከጭንቅም አዳነው፡፡ እንደዚሁም ምእመናንን እናድናለን፡፡ 21|89|ዘከሪያንም «ጌታዬ ሆይ! ብቻዬን አትተወኝ፡፡ አንተም ከወራሾች ሁሉ በላጭ ነህ ሲል» ጌታውን በተጣራ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 21|90|ለእርሱም ጥሪውን ተቀበልነው፡፡ ለእርሱም የሕያን ሰጠነው፡፡ ለእርሱም ሚስቱን አበጀንለት፡፡ እነርሱ በበጎ ሥራዎች የሚቻኮሉ ከጃዮችና ፈሪዎች ኾነው የሚለምኑንም ነበሩ፡፡ ለእኛ ተዋራጆችም ነበሩ፡፡ 21|91|ያችንም ብልቷን የጠበቀቺውን በርሷም ውስጥ ከመንፈሳችን የነፋንባትን እርሷንም ልጅዋንም (እንደዚሁ) ለዓለማት ተዓምር ያደረግናትን (መርየምን አስታውስ)፡፡ 21|92|ይህች (ሕግጋት) አንዲት መንገድ ስትሆን በእርግጥ ሃይማኖታችሁ ናት፡፡ እኔም ጌታችሁ ነኝና ተገዙኝ፡፡ 21|93|በሃይማኖታቸውም ነገር በመካከላቸው ተለያዩ፡፡ ሁሉም ወደኛ ተመላሾች ናቸው፡፡ 21|94|እርሱ ያመነ ኾኖ ከበጎ ሥራዎች ማንኛውንም የሚሠራም ሰው፤ ምንዳውን አይነፈግም፡፡ እኛም ለእርሱ መዝጋቢዎች ነን፡፡ 21|95|ባጠፋናትም ከተማ ላይ እነሱ (ወደኛ) የማይመለሱ መኾናቸው እብለት ነው፤ (ይመለሳሉ)፡፡ 21|96|የእጁጅና መእጁጅም እነርሱ ከየተረተሩ የሚንደረደሩ ሲኾኑ (ግድባቸው) በተከፈተች ጊዜ፥ 21|97|እውነተኛውም ቀጠሮ በቀረበ ጊዜ፥ ያን ጊዜ እነሆ የእነዚያ የካዱት ሰዎች ዓይኖች ይፈጥጣሉ፡፡ «ዋ ጥፋታችን! ከዚህ (ቀን) በእርግጥ በዝንጋቴ ላይ ነበርን፤ በእውነትም በዳዮች ነበርን» (ይላሉ)፡፡ 21|98|እናንተ ከአላህ ሌላ የምትግገዟቸውም (ጣዖታት) የገሀነም ማገዶዎች ናችሁ፡፡ እናንተ ለእርሷ ወራጆች ናችሁ፡፡ 21|99|እነዚህ (ጣዖታት) አማልክት በነበሩ ኖሮ አይገቧዋትም ነበር፡፡ ግን ሁሉም በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 21|100|ለእነርሱ በእርሷ ውስጥ መንሰቅሰቅ አላቸው፡፡ እነርሱም በውስጧ (ምንንም) አይሰሙም፡፡ 21|101|እነዚያ ከእኛ መልካሟ ቃል ለእነርሱ ያለፈችላቸው እነዚያ ከርሷ የተራቁ ናቸው፡፡ 21|102|ድምጽዋን አይሰሙም፡፡ እነርሱም ነፍሶቻቸው በሚሹት ነገር ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 21|103|ታላቁ ድንጋጤ አያስተክዛቸውም፡፡ መላእክትም ይህ ያ ትቀጠሩ የነበራችሁት ቀናችሁ ነው፤ እያሉ ይቀበሏቸዋል፡፡ 21|104|ለመጽሐፎች የኾኑ ገጾች እንደሚጠቀለሉ ሰማይን የምንጠቀልልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ የመጀመሪያን ፍጥረት እንደ ጀመርን እንመልሰዋለን፡፡ (መፈጸሙ) በእኛ ላይ የኾነን ቀጠሮ ቀጠርን፡፡ እኛ (የቀጠርነውን) ሠሪዎች ነን፡፡ 21|105|ምድንም መልካሞቹ ባሮቼ ይወርሷታል ማለትን ከመጽሐፉ (ከተጠበቀው ሰሌዳ) በኋላ በመጽሐፎቹ በእርግጥ ጽፈናል፡፡ 21|106|በዚህ (ቁርኣን) ውስጥ ለተገዢዎች ሕዝቦች በቂነት አልለ፡፡ 21|107|(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም፡፡ 21|108|«ያ ወደኔ የሚወረደው አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው ማለት ነው፤ ታዲያ እናንተ ፍጹም ታዛዦች ናችሁን» በላቸው፡፡ 21|109|እምቢም ቢሉ (በማወቅ) በእኩልነት ላይ ኾነን (የታዘዝኩትን) አስታውቅኋችሁ፡፡ «የምትስፈራሩበትም ነገር ቅርብ ወይም ሩቅ መኾኑን አላውቅም፤» በላቸው፡፡ 21|110|እርሱ ከንግግር ጩኸትን ያውቃል፡፡ የምትደብቁትንም ሁሉ ያውቃል፡፡ 21|111|እርሱም (ቅጣትን ማቆየት) ምናልባት ለእናንተ ፈተናና እስከ ጊዜው መጠቃቀሚያ እንደሆነም አላውቅም፤ (በላቸው)፡፡ 21|112|«ጌታዬ ሆይ! በእውነት ፍረድ፤ ጌታችንም እጅግ በጣም ሩኅሩኅ በምትሉት ነገር ላይ መታገዣ ነው» አለ፡፡ 22|1|እናንተ ሰዎች ሆይ! ጌታችሁን ፍሩ የሰዓቲቱ እንቅጥቃጤ በጣም ከባድ ነገር ነውና፡፡ 22|2|በምታዩዋት ቀን አጥቢ ሁሉ ከአጠባችው ልጅ ትፈዝዛለች፡፡ የእርግዝና ባለቤት የኾነችም ሁሉ እርጉዟን ትጨነግፋለች፡፡ ሰዎቹንም (በድንጋጤ ብርታት) የሰከሩ ኾነው ታያለህ፡፡ እነርሱም (ከመጠጥ) የሰከሩ አይደሉም፡፡ ግን የአላህ ቅጣት ብርቱ ነው፡፡ 22|3|ከሰዎቹም ያለ ዕውቀት በአላህ ነገር የሚከራከር፤ ሞገደኛ ሰይጣንንም ሁሉ የሚከተል ሰው አልለ፡፡ 22|4|እነሆ! የተከተለውን ሰው እርሱ ያጠመዋል፡፡ ወደ ነዳጅ እሳት ስቃይም ይመራዋል ማለት በርሱ ላይ ተጽፏል፡፡ 22|5|እናንተ ሰዎች ሆይ! ከመቀስቀስ በመጠራጠር ውስጥ እንደ ሆናችሁ (አፈጣጠራችሁን ተመልከቱ)፡፡ እኛም ከዐፈር ፈጠርናችሁ፣ ከዚያም ከፍትወት ጠብታ፣ ከዚያም ከረጋ ደም፣ ከዚያም ከቁራጭ ሥጋ፣ ፍጥረትዋ ሙሉ ከሆነችና ሙሉ ካልሆነች (ችሎታችንን) ለናንተ ልንገልጽላችሁ ፈጠርናችሁ፡፡ የምንሻውንም እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ በማሕፀን ውስጥ እናረጋዋለን፡፡ ከዚያም ሕፃን ሆናችሁ እናወጣችኋለን፡፡ ከዚያም ሙሉ ጥንካሪያችሁን ትደርሱ ዘንድ (እናሳድጋችኋለን)፡፡ ከእናንተም የሚሞት ሰው አልለ፡፡ ከእናንተም ከዕውቀት በኋላ ምንንም እንዳያውቅ ወደ ወራዳ ዕድሜ የሚመለስ ሰው አልለ፡፡ ምድርንም ደረቅ ሆና ታያታለህ፡፡ በእርሷም ላይ ውሃን ባወረድን ጊዜ ትላወሳለች፡፡ ትነፋፋለችም፡፡ ውበት ካለው ጎሳ ሁሉ ታበቅላለችም፡፡ 22|6|ይህ አላህ እርሱ መኖሩ የተረጋገጠ፣ እርሱም ሙታንን ሕያው የሚያደርግ፣ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ በመሆኑ ነው፡፡ 22|7|ሰዓቲቱም መጪ ፣ በእርሷ ፈጽሞ ጥርጣሬ የሌለባት በመሆኗ፣ አላህም በመቃብሮች ውስጥ ያለን ሁሉ የሚቀሰቅስ በመሆኑ ነው፡፡ 22|8|ከሰዎችም ውስጥ ያለ ዕውቀት፣ ያለ ማስረጃም፣ ያለ አብራሪ መጽሐፍም በአላህ ነገር የሚከራከር ሰው አልለ፡፡ 22|9|ጎኑን ያጠፈ ሆኖ ከአላህ መንገድ ሊያሳስት (ይከራከራል)፡፡ በቅርቢቱ ዓለም ለእርሱ ውርደት አልለው፡፡ በትንሳኤ ቀንም አቃጣይን ቅጣት እናቀምሰዋለን፡፡ 22|10|ይህ እጆችህ ባስቀደሙት ኀጢአት አላህም ለባሮቹ ፈጽሞ በዳይ ባለመሆኑ ነው (ይባላል)፡፡ 22|11|ከሰዎችም (ከሃይማኖት) በጫፍ ላይ ሆኖ አላህን የሚግገዛ ሰው አልለ፡፡ ታዲያ መልካም ነገር ቢያገኘው በእርሱ ይረጋል፡፡ መከራም ብታገኘው በፊቱ ላይ ይገለበጣል፡፡ የቅርቢቱን ዓለምም የመጨረሻይቱንም ከሰረ፡፡ ይህ እርሱ ግልጽ ከሳራ ነው፡፡ 22|12|ከአላህ ሌላ የማይጎዳውንና የማይጠቅመውን ይግገዛል፡፡ ይህ እርሱ (ከእውነት) የራቀ ስህተት ነው፡፡ 22|13|ያንን ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚቀርብን ይግገዛል፡፡ ረዳቱ ምንኛ ከፋ! 22|14|አላህ እነዚያን ያመኑትንና መልካም ሥራዎችን የሠሩትን በሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች ያገባቸዋል፡፡ አላህ የሚሻውን ነገር በእርግጥ ይሠራል፡፡ 22|15|አላህ (መልክተኛውን) በቅርቢቱም በመጨረሻይቱም ዓለም አይረዳውም ብሎ የሚያስብ ሰው ገመድን ወደ ሰማይ ይዘርጋ፡፡ ከዚያም (ትንፋሹ እስኪቆረጥ) ይታነቅ፡፡ ተንኮሉ የሚያስቆጨውን ነገር ያስወግድለት እንደሆነም ይመልከት፡፡ 22|16|እንደዚሁም (ቁርኣንን) የተብራሩ አንቀጾች አድርገን አወረድነው፡፡ አላህም የሚሻውን ሰው ይመራል፡፡ 22|17|እነዚያ ያመኑት፣ እነዚያም ይሁዳውያን የሆኑ፣ ሳቢያኖችም፣ ክርስቲያኖችም፣ መጁሶችም እነዚያም (ጣዖታትን በአላህ) ያጋሩ አላህ በትንሣኤ ቀን በመካከላቸው በፍርድ ይለያል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ በእርግጥ ዐዋቂ ነውና፡፡ 22|18|አላህ በሰማያት ያለው ሁሉ፣ በምድርም ያለው ሁሉ፣ ፀሐይና ጨረቃም፣ ከዋክብትም፣ ተራራዎችም፣ ዛፎችም፣ ተንቀሳቃሾችም ከሰዎች ብዙዎችም፣ ለርሱ የሚሰግዱለት መሆኑን አታውቁምን ብዙውም በርሱ ላይ ቅጣት ተረጋገጠበት፡፡ አላህ የሚያዋርደውም ሰው ለእርሱ ምንም አክባሪ የለውም፡፡ አላህ የሻውን ይሠራልና፡፡ 22|19|እነዚህ በጌታቸው የተከራከሩ ሁለት ባላጋራዎች ናቸው፡፡ እነዚያም የካዱት ለእነርሱ የእሳት ልብሶች ተለክተውላቸዋል፡፡ ከራሶቻቸው በላይ የፈላ ውሃ ይምቧቧቸዋል፡፡ 22|20|በሆዶቻቸው ውስጥ ያሉ ቆዳዎቻቸውም በእርሱ ይቀለጣሉ፡፡ 22|21|ለእነሱም (መቅጫ) ከብረት የሆኑ መዶሻዎች አልሉ፡፡ 22|22|ከጭንቀት ብርታት የተነሳ ከእርሷ ለመውጣት በፈለጉ ቁጥር ከእርሷ ውስጥ እንዲመለሱ ይደረጋሉ፡፡ «በጣም የሚያቃጥልንም ቅጣት ቅመሱ» (ይባላሉ)፡፡ 22|23|አላህ እነዚያን ያመኑትንና መልካም ሥራዎችን የሠሩትን ሰዎች በሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈስሱባቸውን ገነቶች ያገባቸዋል፡፡ በእርሷ ውስጥ ከወርቅ የሆኑን አንባሮችና ሉልን ይሸለማሉ፡፡ በእርሷ ውስጥ ልብሶቻቸውም ሐር ናቸው፡፡ 22|24|ከንግግርም ወደ መልካሙ ተመሩ፡፡ ወደ ምስጉንም መንገድ ተመሩ፡፡ 22|25|እነዚያ የካዱ ከአላህም መንገድና ከዚያም ለሰዎች በውስጡ ነዋሪ ለሆኑትም፣ ከሩቅ ለሚመጡትም እኩል ካደረግነው ከተከበረው መስጊድ (ሰዎችን) የሚከለክሉ (አሳማሚን ቅጣት እናቀምሳቸዋለን)፡፡ በእርሱም ውስጥ (ከትክክለኛ መንገድ) በመዘንበል በዳይ ሆኖ (ማንኛውንም ነገር) የሚፈልግ ሰው ከአሳማሚ ቅጣት እናቀምሰዋለን፡፡ 22|26|ለኢብራሂምም የቤቱን (የካዕባን) ስፍራ መመለሻ ባደረግንለት ጊዜ «በእኔ ምንንም አታጋራ፣ ቤቴንም ለሚዞሩትና ለሚቆሙበት ለሚያጎነብሱትና በግንባራቸውም ለሚደፉት ንጹሕ አድርግላቸው» (ባልነው ጊዜ አስታውስ)፡፡ 22|27|(አልነውም)፡- በሰዎችም ውስጥ በሐጅ ትዕዛዝ ጥራ፡፡ እግረኞች ከየሩቅ መንገድ በሚመጡ ከሲታ ግመሎችም ሁሉ ላይ ሆነው ይመጡሃልና፡፡ 22|28|ለእነሱ የሆኑ ጥቅሞችን ይጣዱ ዘንድ በታወቁ ቀኖችም ውስጥ ከለማዳ እንስሳዎች በሰጣቸው ሲሳይ ላይ የአላህን ስም ያወሱ ዘንድ (ይመጡሃል)፡፡ ከርሷም ብሉ፡፡ ችግረኛ ድሃንም አብሉ፡፡ 22|29|ከዚያም (እንደ ጠጉርና ጥፍር ያሉትን) ትርፍ አካላቸውንና ዕድፋቸውን ያስወግዱ፡፡ ስለቶቻቸውንም ይሙሉ፤ በጥንታዊውም ቤት ይዙሩ፡፡ 22|30|(ነገሩ) ይህ ነው፡፡ የአላህንም ሕግጋት የሚያከብር ሰው እርሱ ጌታው ዘንድ ለእርሱ በጣም የተሻለ ነው፡፡ የቤት እንስሳትም (ግመል ከብት በግና ፍየል) በናንተ ላይ (እርም መሆኑ) ከሚነበብላችሁ በስተቀር ለእናንተ ተፈቅዳላችኋለች፡፡ ከጣዖታትም ርክሰት ተጠንቀቁ፡፡ ሐሰትንም ቃል ራቁ፡፡ 22|31|ለአላህ ታዛዦች በእርሱ የማታገሩ ሆናችሁ (ከሐሰት ራቁ)፡፡ በአላህም የሚያጋራ ሰው፤ ከሰማይ እንደ ወደቀና በራሪ እንደምትነጥቀው፣ ወይም ነፋስ እርሱን በሩቅ ስፍራ እንደምትጥለው ብጤ ነው፡፡ 22|32|(ነገሩ) ይህ ነው፡፡ የአላህንም የሃይማኖት ምልክቶች የሚያከብር ሰው እርሷ ከልቦች የኾነች ጥንቃቄ ናት፡፡ 22|33|ለእናንተ በእርሷ እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ ጥቅሞች አሏችሁ፡፡ ከዚያም (የማረጃ) ስፍራዋ እጥንታዊው ቤት አጠገብ ነው፡፡ 22|34|ለሕዝብም ሁሉ (ወደ አላህ) መስዋዕት ማቅረብን ደነገግን፡፡ ከቤት እንስሳት በሰጣቸው ሲሳይ ላይ የአላህን ስም ብቻ ያወሱ ዘንድ (አዘዝናቸው)፡፡ አምላካችሁም አንድ አምላክ ብቻ ነው፡፡ ለእርሱም ብቻ ታዘዙ፡፡ ለአላህ ተዋራጆችንም አብስራቸው፡፡ 22|35|እነዚያን አላህ በተወሳ ጊዜ ልቦቻቸው የሚጨነቁትን፣ በደረሰባቸውም (መከራ) ላይ ታጋሾችን፣ ሶላትንም አስተካክለው ሰጋጆችን፣ ከሰጠናቸውም ሲሳይ የሚለግሱትን (አብስር)፡፡ 22|36|ግመሎችንም ለእናንተ ከአላህ ሃይማኖት ምልክቶች አደረግናቸው፡፡ በእርሷ ለእናንተ መልካም ጥቅም አላችሁ፡፡ በእርሷም ላይ (ስታርዷት) በሶስት እግሮችዋ ቆማ የተሰለፈች ሆና የአላህን ስም አውሱ፡፡ ጎኖቻቸውም በወደቁ ጊዜ ከእርሷ ብሉ፡፡ ለማኝንም ለልመና የሚያገዳድምንም አብሉ፡፡ እንደዚሁ ታመሰግኑ ዘንድ ለእናንተ ገራናት፡፡ 22|37|አላህን ሥጋዎቿም ደሞቿም ፈጽሞ አይደርሰውም፡፡ ግን ከእናንተ የሆነው ፍራቻ ይደርሰዋል፡፡ እንደዚሁ አላህን በመራችሁ ላይ ልታከብሩት ለእናንተ ገራት፡፡ በጎ ሠሪዎችንም አብስር፡፡ 22|38|አላህ ከእነዚያ ካመኑት ላይ ይከላከልላቸዋል፡፡ አላህ ከዳተኛን ውለታቢስን ሁሉ አይወድም፡፡ 22|39|ለእነዚያ ለሚገደሉት (ምእመናን) እነርሱ የተበደሉ በመኾናቸው (መጋደል) ተፈቀደላቸው፡፡ አላህም እነርሱን በመርዳት ላይ በእርግጥ ቻይ ነው፡፡ 22|40|ለእነዚያ «ጌታችን አላህ ነው» ከማለታቸው በስተቀር ያለ አግባብ ከአገራቸው የተባረሩ ለሆኑት (ተፈቀደ)፡፡ አላህ ሰዎችን ከፊላቸውን በከፊሉ መገፍተሩ ባልነበረ ኖሮ ገዳማት፣ ቤተክርስቲያኖችም፣ ምኩራቦችም በውስጣቸው የአላህ ስም በብዛት የሚወሳባቸው መስጊዶችም፤ በተፈረሱ ነበር፡፡ አላህም ሃይማኖቱን የሚረዳውን ሰው በእርግጥ ይረዳዋል፡፡ አላህ ብርቱ አሸናፊ ነውና፡፡ 22|41|(እነርሱም) እነዚያ በምድር ላይ ብናስመቻቸው ሶላትን እንደሚገባ የሚያስተካክሉ፣ ዘካንም የሚሰጡ፣ በደግ ነገርም የሚያዝዙ፣ ከመጥፎ ነገርም የሚከለክሉ ናቸው፡፡ የነገሮቹም ሁሉ መጨረሻ ወደ አላህ ነው፡፡ 22|42|ቢያስተባብሉህም ከእነሱ በፊት የኑሕ ሕዝቦች ዓድና ሰሙድም በእርግጥ አስተባብለዋል፡፡ 22|43|የኢብራሂምም ሕዝቦች የሉጥም ሕዝቦች (አስተባብለዋል)፡፡ 22|44|የመድየንም ሰዎች (አስተባብለዋል)፡፡ ሙሳም ተስተባብሏል፡፡ ለከሓዲዎቹም ጊዜ ሰጠኋቸው፡፡ ከዚያም ያዝቸው፡፡ ጥላቻዬም እንዴት ነበረ! 22|45|ከከተማም እርሷ በደለኛ ሆና ያጠፋናትና እርሷ በጣሪያዎቿ ላይ ወዳቂ የሆነችው ብዙ ናት፡፡ ከተራቆተችም የውሃ ጉድጓድ ከተገነባም ሕንፃ (ያጠፋነው ብዙ ነው)፡፡ 22|46|ለእነርሱም በእነርሱ የሚያውቁባቸው ልቦች ወይም በእነርሱ የሚሰሙባቸው ጆሮች ይኖሯቸው ዘንድ በምድር ላይ አይሄዱምን እነሆ ዓይኖች አይታወሩም ግን እነዚያ በደረቶች ውስጥ ያሉት ልቦች ይታወራሉ፡፡ 22|47|አላህም ቀጠሮውን በፍጹም የማይጥስ ሲሆን በቅጣት ያቻኩሉሃል፡፡ እጌታህም ዘንድ አንዱ ቀን ከምትቆጥሩት (ቀን) እንደ ሺሕ ዓመት ነው፡፡ 22|48|ከከተማ እርሷ በዳይ ሆና ለእርሷ ጊዜ የሰጠኋትና ከዚያም የያዝኳት ብዙ ናት፡፡ መመለሻም ወደኔ ብቻ ነው፡፡ 22|49|«እናንተ ሰዎች ሆይ! እኔ ለእናንተ ግልጽ አስጠንቃቂ ብቻ ነኝ» በላቸው፡፡ 22|50|እነዚያም ያመኑ መልካም ሥራዎችንም የሠሩ ለእነርሱ ምህረትና ያማረ ሲሳይ አላቸው፡፡ 22|51|እነዚያም የሚያመልጡ መስሏቸው ተዓምራቶቻችንን በመንቀፍ የተጉ እነሱ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ 22|52|ከመልክተኛና ከነቢይም ከአንተ በፊት አንድንም አላክንም ባነበበ (እና ዝም ባለ) ጊዜ ሰይጣን በንባቡ ላይ (ማጥመሚያን ቃል) የሚጥል ቢሆን እንጅ፡፡ ወዲያውም አላህ ሰይጣን የሚጥለውን ያስወግዳል፡፡ ከዚያም አላህ አንቀጾቹን ያጠነክራል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 22|53|ሰይጣን የሚጥለውን ነገር ለእነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ላለባቸው ልቦቻቸውም ደረቆች ለሆኑት ፈተና ሊያደርግ (ይጥላል)፡፡ በዳዮችም ከእውነት በራቀ ጭቅጭቅ ውስጥ ናቸው፡፡ 22|54|እነዚያም ዕውቀትን የተሰጡት እርሱ (ቁርኣን) ከጌታህ የኾነ እውነት መኾኑን እንዲያውቁና በእርሱ እንዲያምኑ ልቦቻቸውም ለእርሱ እንዲረኩ (ያጠነክራል)፡፡ አላህም እነዚያን ያመኑትን ወደ ቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ መሪ ነው፡፡ 22|55|እነዚያ የካዱት ሰዎች ሰዓቲቱ በድንገት እስከምትመጣባቸው ወይም (ከደግ ነገር) መካን የሆነው ቀን ቅጣት እስከሚመጣባቸው ድረስ ከእርሱ (ከቁርኣን) በመጠራጠር ውስጥ ከመሆን አይወገዱም፡፡ 22|56|በዚያ ቀን ንግሥናው የአላህ ብቻ ነው፡፡ በመካከላቸው ይፈርዳል፡፡ እነዚያም ያመኑት መልካም ሥራዎችንም የሠሩት በመደሰቻ ገነቶች ውስጥ ናቸው፡፡ 22|57|እነዚያም የካዱት በአንቀጾቻችንም ያስተባበሉት እነዚያ ለእነርሱ አዋራጅ ቅጣት አላቸው፡፡ 22|58|እነዚያም በአላህ ሃይማኖት የተሰደዱ ከዚያም የተገደሉ ወይም የሞቱ አላህ መልካምን ሲሳይ በእርግጥ ይሰጣቸዋል፡፡ አላህም እርሱ ከሰጪዎች ሁሉ በላጭ ነው፡፡ 22|59|የሚወዱትን መግቢያ (ገነትን) በእርግጥ ያገባቸዋል፡፡ አላህም በእርግጥ ዐዋቂ ታጋሽ ነው፡፡ 22|60|(ነገሩ) ይህ ነው፡፡ በእሱ በተበደለበትም ብጤ የተበቀለ ሰው ከዚያም በእርሱ ላይ ግፍ የተዋለበት አላህ በእርግጥ ይረዳዋል፡፡ አላህ ይቅር ባይ መሓሪ ነውና፡፡ 22|61|ይህ አላህ ሌሊትን በቀን ውስጥ የሚያስገባ ቀንንም በሌሊት ውስጥ የሚያስገባ (ቻይ) አላህም ሰሚ ተመልካች በመሆኑ ነው፡፡ 22|62|ይህ አላህ እርሱ እውነት በመሆኑ ከእርሱም ሌላ የሚግገዙት ነገር እርሱ ፍጹም ውሸት በመሆኑ አላህም እርሱ የሁሉ በላይ ታላቅ በመኾኑ ነው፡፡ 22|63|አላህ ከሰማይ ውሃን ማውረዱንና ምድር የምትለመልም መኾኗን አታይምን አላህ ሩኅሩኅ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 22|64|በሰማያት ውስጥ ያለውና በምድር ውስጥ ያለው ሁሉ የርሱ ብቻ ነው፡፡ አላህም እርሱ ተብቃቂው ምስጉኑ ነው፡፡ 22|65|አላህ በምድር ውስጥ ያለን ሁሉ ለእናንተ የገራላችሁ፣ መርከቦችንም በባሕር ውስጥ በፈቃዱ የሚንሻለሉ ሲኾኑ (የገራላችሁ) መኾኑን፣ ሰማይንም በፈቃዱ ካልኾነ በምድር ላይ እንዳትወድቅ የሚይዛት መኾኑን አላየህምን አላህ ለሰዎች በእርግጥ ሩኅሩኅ አዛኝ ነው፡፡ 22|66|እርሱም ያ ሕያው ያደረጋችሁ ነው፡፡ ከዚያም ይገድላችኋል፡፡ ከዚያም ሕያው ያደርጋችኋል፡፡ ሰው በእርግጥ በጣም ከሓዲ ነው፡፡ 22|67|ለየሕዝቡ ሁሉ እነሱ የሚሠሩበት የኾነን ሥርዓተ ሃይማኖት አድርገናል፡፡ ስለዚህ በነገሩ አይከራከሩህ፡፡ ወደ ጌታህ መንገድም ጥራ፡፡ አንተ በእርግጥ በቅኑ መንገድ ላይ ነህና፡፡ 22|68|ቢከራከሩህም «አላህ የምትሰሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 22|69|አላህ በትንሣኤ ቀን በዚያ በእርሱ ትለያዩበት በነበራችሁት ሁሉ በመካከላችሁ ይፈርዳል፡፡ 22|70|አላህ በሰማይና በምድር ውስጥ ያለን ሁሉ በእርግጥ የሚያውቅ መኾኑን አታውቅምን ይህ በመጽሐፍ ውስጥ (የተመዘገበ) ነው፡፡ ይህ በአላህ ላይ ገር ነው፡፡ 22|71|ከአላህ ሌላም በእርሱ ማስረጃን ያላወረደበትን ለእነርሱም በእርሱ ዕውቀት የሌላቸውን ነገር ይግገዛሉ፡፡ ለባዳዮችም ምንም ረዳት የላቸውም፡፡ 22|72|አንቀጾቻችንም የተብራሩ ኾነው በእነሱ ላይ በሚነበቡ ጊዜ በእነዚያ በካዱት ሰዎች ፊቶች ላይ ጥላቻን ታውቃለህ፡፡ በእነዚያ በእነሱ ላይ አንቀጾቻችንን በሚያነቡት ላይ በኃይል ሊዘልሉባቸው ይቃረባሉ፡፡ «ከዚህ ይልቅ የከፋን ነገር ልንገራችሁን» በላቸው፡፡ «(እርሱም) እሳት ናት፡፡ አላህ ለእነዚያ ለካዱት ሰዎች ቀጥሯታል፡፡ ምን ትከፋም መመለሻ!» 22|73|እናንተ ሰዎች ሆይ! አስደናቂ ምሳሌ ተገለጸላችሁ፡፡ ለእርሱም አድምጡት፡፡ እነዚያ ከአላህ ሌላ የምትግገዟቸው (ጣዖታት) ዝንብን ፈጽሞ አይፈጥሩም፡፡ እርሱን (ለመፍጠር) ቢሰበሰቡም እንኳን (አይችሉም)፡፡ አንዳችንም ነገር ዝንቡ ቢነጥቃቸው ከእርሱ አያስጥሉትም፡፡ ፈላጊውም ተፈላጊውም ደከሙ፡፡ 22|74|አላህን ተገቢ ክብሩን አላከበሩትም፡፡ አላህ በጣም ኃያል አሸናፊ ነው፡፡ 22|75|አላህ ከመላእክት ውስጥ መልክተኞችን ይመርጣል፡፡ ከሰዎችም (እንደዚሁ)፤ አላህ ሰሚ ተመልካች ነው፡፡ 22|76|በስተፊታቸው ያለን በስተኋላቸውም ያለን ሁሉ ያውቃል፡፡ ወደ አላህም ነገሮች ሁሉ ይመለሳሉ፡፡ 22|77|እናንተ ያመናችሁ ሰዎች ሆይ! (በስግደታችሁ) አጎንብሱ፣ በግንባራችሁም ተደፉ፣ ጌታችሁንም ተገዙ፣ በጎንም ነገር ሥሩ፣ ልትድኑ ይከጀልላችኋልና፡፡ 22|78|በአላህም ሃይማኖት ተገቢውን ትግል ታገሉ፡፡ እርሱ መርጧችኋል፡፡ በናንተም ላይ በሃይማኖቱ ውስጥ ምንም ችግር አላደረገባችሁም፡፡ የአባታችሁን የኢብራሂምን ሃይማኖት ተከተሉ፡፡ እርሱ ከዚህ በፊት ሙስሊሞች ብሎ ሰይሟችኋል፡፡ በዚህም (ቁርኣን)፤ መልክተኛው በእናንተ ላይ መስካሪ እንዲሆን እናንተም በሰዎቹ ላይ መስካሪዎች እንድትኾኑ (ሙስሊሞች ብሎ ሰይሟችኋል)፡፡ ሶላትንም አስተካክላችሁ ስገዱ፣ ዘካንም ስጡ፣ በአላህም ተጠበቁ፣ እርሱ ረዳታችሁ ነው፡፡ (እርሱ) ምን ያምር ጠባቂ! ምን ያምርም ረዳት! 23|1|ምእምናን ፍላጎታቸውን ሁሉ በእርግጥ አገኙ (ዳኑ)፡፡ 23|2|እነዚያ እነርሱ በስግደታቸው ውስጥ (አላህን) ፈሪዎች፡፡ 23|3|እነዚያም እነርሱ ከውድቅ ንግግር ራቂዎች፡፡ 23|4|እነዚያም እነርሱ ዘካን ሰጭዎች፡፡ 23|5|እነዚያም እነርሱ ብልቶቻቸውን ጠባቂዎች የሆኑት (አገኙ)፡፡ 23|6|በሚስቶቻቸው ወይም እጆቻቸው በያዟቸው (ባሪያዎች) ላይ ሲቀር፡፡ እነርሱ (በነዚህ) የማይወቀሱ ናቸውና፡፡ 23|7|ከዚህም ወዲያ የፈለጉ ሰዎች እነዚያ እነርሱ ወሰን አላፊዎች ናቸው፡፡ 23|8|እነዚያም እነርሱ ለአደራዎቻቸውና ለቃል ኪዳናቸው ጠባቂዎች፡፡ 23|9|እነዚያም እነሱ በስግደቶቻቸው ላይ የሚጠባበቁ የኸኑት (አገኙ)፡፡ 23|10|እነዚያ ወራሾቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 23|11|እነዚያ ፊርደውስን (ላዕላይ ገነትን)፤ የሚወርሱ ናቸው፡፡ እነርሱ በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 23|12|በእርግጥም ሰውን ከነጠረ ጭቃ ፈጠርነው፡፡ 23|13|ከዚያም በተጠበቀ መርጊያ ውስጥ የፍትወት ጠብታ አደረግነው፡፡ 23|14|ከዚያም ጠብታዋን (በአርባ ቀን) የረጋ ደም አድርገን ፈጠርን፡፡ የረጋውንም ደም ቁራጭ ሥጋ አድርገን ፈጠርን፡፡ ቁራጯንም ሥጋ አጥንቶች አድርገን ፈጠርን፡፡ አጥንቶቹንም ሥጋን አለበስናቸው፡፡ ከዚያም (ነፍስን በመዝራት) ሌላ ፍጥረትን አድርገን አስገኘነው፡፡ ከሰዓሊዎችም ሁሉ በላጭ የሆነው አላህ ላቀ፡፡ 23|15|ከዚያም እናንተ ከዚህ በኋላ በእርግጥ ሟቾች ናችሁ፡፡ 23|16|ከዚያም እናንተ በትንሣኤ ቀን ትቀሰቀሳላችሁ፡፡ 23|17|በእርግጥም ከበላያችሁ ሰባትን ሰማያት ፈጠርን፡፡ ከፍጥረቶቹም ዘንጊዎች አይደለንም፡፡ 23|18|ከሰማይም ውሃን በልክ አወረድን፡፡ በምድርም ውስጥ አስቀመጥነው፡፡ እኛም እርሱን በማስወገድ ላይ በእርግጥ ቻዮች ነን፡፡ 23|19|በእርሱም ከዘምባባዎችና ከወይኖች የኾኑን አትክልቶች ለእናንተ አስገኘንላችሁ፡፡ በውስጧ ለእናንተ ብዙ ፍራፍሬዎች አሏችሁ፡፡ ከእርሷም ትበላላችሁ፡፡ 23|20|ከሲና ተራራም የምትወጣን ዛፍ በቅባትና ለበይዎችም መባያ በሚኾን (ዘይት) ተቀላቅላ የምትበቅልን (አስገኘንላችሁ)፡፡ 23|21|ለእናንተም በግመል፣ በከብት፣ በፍየልና በበግ መገምገሚያ አልላችሁ፡፡ በሆዶችዋ ውስጥ ካለው (ወተት) እናጠጣችኋለን፡፡ ለእናንተም በእርሷ ብዙ ጥቅሞች አሏችሁ፡፡ ከእርሷም ትበላላችሁ፡፡ 23|22|በእርሷም ላይ በመርከብም ላይ ትጫናላችሁ፡፡ 23|23|ኑሕንም ወደ ሕዝቦቹ በእርግጥ ላክነው፡፡ ወዲያውም «ሕዝቦቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ ከእርሱ ሌላ ምንም አምላክ የላችሁም፡፡ አትጠነቀቁምን» አላቸው፡፡ 23|24|ከሕዝቦቹም እነዚያ ታላላቆቹ ሰዎች አሉ «ይህ ብጤያችሁ ሰው እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ በእናንተ ላይ መብለጥን ይፈልጋል፡፡ አላህም በሻ ኖሮ መላእክትን ባወረደ ነበር፡፡ ይህንንም (የሚለውን) በመጀመሪያዎቹ አባቶቻችን አልሰማንም፡፡ 23|25|«እርሱ በእርሱ ዕብደት ያለበት ሰው እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ በእርሱም እስከ ጊዜ (ሞቱ) ድረስ ተጠባበቁ» (አሉ)፡፡ 23|26|(ኑሕም) «ጌታዬ ሆይ! ባስተባበሉኝ ምክንያት እርዳኝ» አለ፡፡ 23|27|ወደርሱም (እንዲህ ስንል) ላክን «በተመልካችነታችንና በትእዛዛችንም ታንኳን ሥራ በመጣና እቶኑ በፈለቀ ጊዜ በውስጧ ከሁሉም ሁለት ዓይነቶችን ቤተሰቦችህንም ከነሱ (ጠፊ በመኾን) ቃል ያለፈበት ብቻ ሲቀር፤ አግባ፡፡ በእነዚያም በበደሉት ሰዎች ነገር አታነጋግረኝ፡፡ እነሱ ተሰጣሚዎች ነቸውና፡፡ 23|28|አንተም አብረውህ ካሉት ጋር በታንኳይቱ ላይ በተደላደልክ ጊዜ «ምስጋና ለዚያ ከበደለኞች ሕዝቦች ላዳነን አላህ ይገባው» በል፡፡ 23|29|በልም «ጌታዬ ሆይ! ብሩክ የኾነን ማውረድ አውርደኝ፡፡ አንተም ከአውራጆች ሁሉ በላጭ ነህ፡፡» 23|30|በዚህ ውስጥ (ለከሃሊነታችን) ምልከቶች አልሉበት፡፡ እነሆ! (የኑሕን ሰዎች) በእርግጥም ፈትታኞች ነበርን፡፡ 23|31|ከዚያም ከኋላቸው ሌሎችን የክፍለ ዘመን ሕዝቦች አስገኘን፡፡ 23|32|በውስጣቸውም ከእነሱ የኾነን መልክተኛ አላህን ተገዙ ከእርሱ ሌላ አምላክ የላችሁም አትጠነቀቁምን በማለት ላክን፡፡ 23|33|ከሕዝቦቹም እነዚያ የካዱት በመጨረሻይቱም ቀን መገናኘት ያስተባበሉት በቅርቢቱም ሕይወት ያቀማጠልናቸው ታላላቅ ሰዎች «ይህ ብጤያችሁ ሰው እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ ከርሱ ከምትበሉት ምግብ ይበላል፡፡ ከምትጠጡትም ውሃ ይጠጣል» አሉ፡፡ 23|34|«ብጤያችሁም የኾነን ሰው ብትታዘዙ እናንተ ያን ጊዜ በእርግጥ የተሞኛችሁ ናቸሁ» (አሉ)፡፡ 23|35|«እናንተ በሞታችሁና ዐፈርና አጥንቶችም በኾናችሁ ጊዜ እናንተ (ከመቃብር) ትወጣላችሁ በማለት ያስፈራራችኋልን 23|36|«ያ የምትስፈራሩበት ነገር ራቀ፤ በጣም ራቀ፡፡ 23|37|«እርሷ (ሕይወት) ቅርቢቱ ሕይወታችን እንጂ ሌላ አይደለችም፡፡ እንሞታለን፤ (ልጆቻችን ስለሚተኩ) ሕያውም እንኾናለን፡፡ እኛም ተቀስቃሾች አይደለንም፡፡ 23|38|«እርሱ በአላህ ላይ ውሸትን የቀጠፈ ሰው እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ እኛም ለእርሱ አማኞች አይደለንም» (አሉ)፡፡ 23|39|(መልክተኛውም) «ጌታዬ ሆይ! ስላስተባበሉኝ እርዳኝ» አለ፡፡ 23|40|(አላህም) «ከጥቂት ጊዜ በኋላ (በጥፋታቸው) በእርግጥ ተጸጻቾች ይኾናሉ» አለው፡፡ 23|41|ወዲያውም (የጥፋት) ጩኸቲቱ በእውነት ያዘቻቸው፡፡ እንደ ጎርፍ ግብስባሽም አደረግናቸው፡፡ ለበደለኞች ሕዝቦችም (ከእዝነት) መራቅ ተገባቸው፡፡ 23|42|ከዚያም ከእነሱ በኋላ ሌሎችን የክፍለ ዘመናት ሕዝቦች አስገኘን፡፡ 23|43|ማንኛይቱም ሕዝብ ጊዜያዋን አትቀድምም፤ አይቅቆዩምም፡፡ 23|44|ከዚያም መልክተኞቻችንን የሚከታተሉ ኾነው ላክን፡፡ ማንኛይቱንም ሕዝብ መልክተኛዋ በመጣላት ቁጥር አስተባበሉት፡፡ ከፊላቸውንም በከፊሉ (በጥፋት) አስከታተለን፡፡ ወሬዎችም አደረግናቸው፡፡ ለማያምኑም ሕዝቦች (ከእዝነታችን) መራቅ ተገባቸው፡፡ 23|45|ከዚያም ሙሳንና ወንድሙን ሃሩንን በተዓምራታችንና በግልጽ አስረጅ ላክን፡፡ 23|46|ወደ ፈርዖንና ወደ ጭፍሮቹ (ላክናቸው)፡፡ ኮሩም፡፡ የተንበጣረሩ ሕዝቦችም ነበሩ፡፡ 23|47|«ብጤያችንም ለኾኑ ሁለት ሰዎች ሕዝቦቻቸው ለእኛ ተገዢዎች ኾነው ሳሉ እናምናለን» አሉ፡፡ 23|48|አስተባበሉዋቸውም፡፡ ከጠፊዎቹም ኾኑ፡፡ 23|49|ሙሳንም (ነገዶቹ) ይምመሩ ዘንድ መጽሐፍን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ 23|50|የመርየምን ልጅና እናቱንም ተዓምር አደረግናቸው፡፡ የመደላደልና የምንጭ ባለቤት ወደ ኾነች ከፍተኛ ስፍራም አስጠጋናቸው፡፡ 23|51|እናንተ መልክተኞች ሆይ! ከተፈቀዱት ምግቦች ብሉ፡፡ በጎ ሥራንም ሥሩ፡፡ እኔ የምተሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነኝ፡፡ 23|52|ይህችም (በአንድ አምላክ የማመን ሕግጋት) አንድ መንገድ ስትኾን ሃይማኖታችሁ ናት፡፡ እኔም ጌታችሁ ነኝና ፍሩኝ፡፡ 23|53|(ከዚያ ተከታዮቻቸው) የሃይማኖት ነገራቸውንም በመካከላቸው ክፍልፍሎች አድርገው ቆራረጡ፡፡ ሕዝብ ሁሉ እነርሱ ዘንድ ባለው ሃይማኖት ተደሳቾች ናቸው፡፡ 23|54|እስከ ጊዜያቸውም ድረስ በጥምመታቸው ውስጥ ተዋቸው፡፡ 23|55|ከገንዘብና ከልጆች በእርሱ የምንጨምርላቸውን ያስባሉን 23|56|በበጎ ነገሮች የምንቻኮልላቸው መኾንን (ያስባሉን) አይደለም፤ (ለማዘንጋት መኾኑን) አያውቁም፡፡ 23|57|እነዚያ እነርሱ ጌታቸውን ከመፍራት የተነሳ ተጨናቂዎች የኾኑት፡፡ 23|58|እነዚያም እነርሱ በጌታቸው ተዓምራቶች ከሚያምኑት፡፡ 23|59|እነዚያም እነርሱ በጌታቸው (ጣዖትን) የማያጋሩት፡፡ 23|60|እነዚያም የሚሰጡትን ነገር እነርሱ ወደ ጌታቸው ተመላሾች መኾናቸውን ልቦቻቸው የሚፈሩ ኾነው የሚሰጡት፡፡ 23|61|እነዚያ በመልካም ሥራዎች ይጣደፋሉ፡፡ እነሱም ለርሷ ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ 23|62|ማንኛይቱንም ነፍስ ችሎታዋን እንጂ አናስገድዳትም፡፡ እኛም ዘንድ በእውነት የሚናገር መጽሐፍ አልለ፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 23|63|በእውነቱ (ከሓዲዎች) ልቦቻቸው ከዚያ (መጽሐፍ) በዝንጋቴ ውስጥ ናቸው፡፡ ለእነሱም ከዚህ ሌላ እነሱ ለርሷ ሠሪዎችዋ የኾኑ (መጥፎ) ሥራዎች አሏቸው፡፡ 23|64|ቅምጥሎቻቸውንም በቅጣት በያዝናቸው ጊዜ ወዲያውኑ እነርሱ ይወተውታሉ፡፡ 23|65|ዛሬ አትወትውቱ፤ እናንተ ከእኛ ዘንድ አትረዱም፡፡ 23|66|አንቀጾቹ በእናንተ ላይ በእርግጥ ይነበቡላችሁ ነበር፡፡ በተረከዞቻችሁም ላይ ወደ ኋላችሁ ትመለሱ ነበራችሁ፡፡ 23|67|በእርሱ (በክልሉ ቤት) ኩሩዎች ሌሊት ተጫዋቾች (ቁርኣንንም) የምትተው ኾናችሁ (ትመለሱ ነበራችሁ ይባላሉ)፡፡ 23|68|(የቁርኣንን) ንግግሩንም አያስተነትኑምን ወይስ ለመጀመሪያዎቹ አባቶቻቸው ያልመጣ ነገር መጣባቸውን 23|69|ወይስ መልክተኛቸውን አላወቁምን ስለዚህ እነርሱ ለእርሱ ከሓዲዎች ናቸውን 23|70|ወይስ በእርሱ ዕብደት አለበት ይላሉን አይደለም፡፡ እውነትን ይዞ መጣላቸው፡፡ አብዛኞቻቸውም እውነትን ጠይዎች ናቸው፡፡ 23|71|አላህም ዝንባሌዎቻቸውን በተከተለ ኖሮ ሰማያትና ምድር በውስጣቸውም ያለው ሁሉ በእርግጥ በተበላሸ ነበር፡፡ ይልቁንም ክብራቸው ያለበትን ቁርኣን አመጣንላቸው፡፡ እነርሱም ከክብራቸው ዘንጊዎች ናቸው፡፡ 23|72|ወይስ ግብርን ትጠይቃቸዋለህን የጌታህም ችሮታ በላጭ ነው፡፡ እርሱም ከሰጪዎች ሁሉ በላጭ ነው፡፡ 23|73|አንተም ወደ ቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ ትጠራቸዋለህ፡፡ 23|74|እነዚያም በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ከትክክለኛው መንገድ ተዘንባዮች ናቸው፡፡ 23|75|ባዘንንላቸውና ከጉዳትም በእነርሱ ያለውን ባነሳንላቸው ኖሮ በጥመታቸው ውስጥ የሚዋልሉ ኾነው ይዘወትሩ ነበር፡፡ 23|76|በእርግጥም በቅጣት ያዝናቸው፡፡ ታዲያ ለጌታቸው አልተናነሱም፡፡ አይዋደቁምም፡፡ 23|77|በእነሱም ላይ የብርቱ ቅጣት ባለቤት የኾነ ደጃፍን በከፈትንባቸው ጊዜ እነርሱ ያን ጊዜ በእርሱ ተስፋ ቆራጮች ናቸው፡፡ 23|78|እርሱም ያ መስሚያዎችንና ማያዎችን ልቦችንም ለእናንተ የፈጠረላችሁ ነው፡፡ ጥቂትን እንጅ አታመሰግኑም፡፡ 23|79|እርሱም ያ በምድር ውስጥ የበተናችሁ ነው፡፡ ወደርሱም ትሰበሰባላችሁ፡፡ 23|80|እርሱም ያ ሕያው የሚያደርግ የሚገድልም ነው፡፡ የሌሊትና የቀን መተካካትም የእርሱ ነው፡፡ አታውቁምን 23|81|ይልቁንም (የመካ ከሓዲዎች) የፊተኞቹ ሕዝቦች እንዳሉት ብጤ አሉ፡፡ 23|82|«በሞትንና ዐፈርና አጥንቶች በኾን ጊዜ እኛ ተቀስቃሾች ነን» አሉ፡፡ 23|83|«ይህንን እኛም ከእኛ በፊትም የነበሩት አባቶቻችን በእርግጥ ተቀጥረናል፡፡ ይህ የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ተረቶች እንጂ ሌላ አይደለም» (አሉ)፡፡ 23|84|«ምድርና በውስጥዋ ያለው ሁሉ የማን ነው የምታውቁ ብትኾኑ (ንገሩኝ)» በላቸው፡፡ 23|85|«በእርግጥ የአላህ ነው» ይሉሃል፡፡ «ታዲያ አትገሰጹምን» በላቸው፡፡ 23|86|«የሰባቱ ሰማያት ጌታና የታላቁ ዐርሽ ጌታ ማን ነው» በላቸው፡፡ 23|87|«በእርግጥ አላህ ነው» ይሉሃል፡፡ «እንግዲያ አትፈሩትምን» በላቸው፡፡ 23|88|«የነገሩ ሁሉ ግዛት በእጁ የኾነ እርሱ የሚጠብቅ በእርሱ ላይ የማይጠበቅ ማን ነው የምታውቁ እንደኾናችሁ (መልሱልኝ)» በላቸው፡፡ 23|89|«በእርግጥ አላህ ነው» ይሉሃል፡፡ «ታዲያ እንዴት ትታለላላችሁ» በላቸው፡፡ 23|90|ይልቁንም እውነትን አመጣንላቸው፡፡ እነርሱም (በመካዳቸው) ውሸታሞች ናቸው፡፡ 23|91|አላህ ምንም ልጅን አልያዘም (አልወለደም)፡፡ ከእርሱም ጋር አንድም አምላክ የለም፡፡ ያን ጊዜ (ሌላ አምላክ በነበረ) አምላክ ሁሉ በፈጠረው ነገር በተለየ ነበር፡፡ ከፊላቸውም በከፊሉ ለይ በላቀ ነበር፡፡ አላህ ከሚመጥኑት ሁሉ ጠራ፡፡ 23|92|ሩቁንና ቅርቡንም ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ (በእርሱ) ከሚያጋሩትም ሁሉ ከፍ አለ፡፡ 23|93|(ሙሐመድ ሆይ!) በል «ጌታዬ ሆይ! የሚያስፈራሩበትን (ቅጣት) ብታሳየኝ፡፡ 23|94|«ጌታዬ ሆይ! በበደለኞች ሕዝቦች ውስጥ አታድርገኝ፡፡» 23|95|እኛም የምናስፈራራቸውን ነገር ልናሳይህ በእርግጥ ቻዮች ነን፡፡ 23|96|በዚያች እርስዋ መልካም በኾነችው (ጠባይ) መጥፎይቱን ነገር ገፍትር፡፡ እኛ የሚሉትን ሁሉ ዐዋቂዎች ነን፡፡ 23|97|በልም «ጌታዬ ሆ! ከሰይጣናት ጉትተጎታዎች በአንተ እጠበቃለሁ፡፡ 23|98|«ባንተም ጌታዬ ሆይ! (በነገሮቼ) ወደእኔ ከመጣዳቸው እጠበቃለሁ፡፡» 23|99|አንዳቸውንም ሞት በመጣበት ጊዜ እንዲህ ይላል «ጌታዬ ሆይ! (ወደ ምድረ ዓለም) መልሱኝ፡፡ 23|100|«በተውኩት ነገር በጎን ሥራ ልሠራ እከጅላለሁና፡፡» (ይህን ከማለት) ይከልከል፡፡ እርስዋ እርሱ ተናጋሪዋ የኾነች ከንቱ ቃል ናት፡፡ ከስተፊታቸውም እስከሚቀሰቀሱበት ቀን ድረስ ግርዶ አልለ፡፡ 23|101|በቀንዱም በተነፋ ጊዜ በዚያ ቀን በመካከላቸው ዝምድና የለም፡፡ አይጠያየቁምም፡፡ 23|102|ሚዛኖቹም የከበዱለት ሰው እነዚያ እነርሱ ፍላጎታቸውን ያገኙ ናቸው፡፡ 23|103|ሚዛኖቹም የቀለሉበት ሰው እነዚያ እነርሱ ነፍሶቻቸውን ያከሰሩ ናቸው፡፡ በገሀነም ውስጥ ዘመውታሪዎች ናቸው፡፡ 23|104|ፊቶቻቸውን እሳት ትገርፉቸዋለች፡፡ እነርሱም በእርሷ ውስጥ ከንፈሮቻቸው የተኮማተሩ ናቸው፡፡ 23|105|«አንቀጾቼ በእናንተ ላይ የሚነበቡላችሁና በእነርሱ የምታስተባብሉ አልነበራችሁምን» (ይባላሉ)፡፡ 23|106|ይላሉ «ጌታችን ሆይ! በእኛ ላይ መናጢነታችን አሸነፈችን፡፡ ጠማማዎችም ሕዝቦች ነበርን፡፡ 23|107|«ጌታችን ሆይ! ከእርሷ አውጣን፡፡ (ወደ ክህደት) ብንመለስም እኛ በደዮች ነን፡፡» 23|108|(አላህም) «ወራዶች ኾናችሁ በውስጥዋ እርጉ፡፡ አታናግሩኝም» ይላቸዋል፡፡ 23|109|እነሆ ከባሮቼ «ጌታችን ሆይ! አምነናልና ማረን፡፡ እዘንልንም አንተም ከአዛኞች ሁሉ ይበልጥ አዛኝ ነህ» የሚሉ ክፍሎች ነበሩ፡፡ 23|110|እኔንም ማውሳትን እስካስረሷችሁ ድረስም ማላገጫ አድርጋችሁ ያዛችኋቸው፡፡ በእነርሱም የምትስቁ ነበራችሁ፡፡ 23|111|እኔ ዛሬ በትዕግስታቸው ምክንያት እነሱ ፍላጎታቸውን የሚያገኙት እነርሱ ብቻ በመኾን መነዳኋቸው፤ (ይላቸዋል)፡፡ 23|112|«በምድር ውስጥ ከዓመታት ቁጥር ስንትን ቆያችሁ» ይላቸዋል፡፡ 23|113|«አንድ ቀንን ወይም ከፊል ቀንን ቆየን፡፡ ቆጣሪዎቹንም ጠይቅ» ይላሉ፡፡ 23|114|«እናንተ (የቆያችሁትን መጠን) የምታውቁ ብትኾኑ ኖሮ (በእሳት ውስጥ በምትቆዩት አንፃር) ጥቂትን ጊዜ እንጂ አልቆያችሁም» ይላቸዋል፡፡ 23|115|«የፈጠርናችሁ ለከንቱ መኾኑን እናንተም ወደኛ የማትመለሱ መኾናችሁን ጠረጠራችሁን» (ለከንቱ የፈጠርናችሁ መሰላችሁን) 23|116|የእውነቱም ንጉስ አላህ ከፍተኛነት ተገባው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ የሚያምረው ዐርሽ ጌታ ነው፡፡ 23|117|ከአላህም ጋር ሌላን አምላክ ለእርሱ በእርሱ ማስረጃ የሌለውን የሚገዛ ሰው ምርመራው እጌታው ዘንድ ብቻ ነው፡፡ እነሆ ከሓዲዎች አይድኑም፡፡ 23|118|በልም «ጌታዬ ሆይ ማር፤ እዘንም፡፡ አንተም ከአዛኞች ሁሉ በላጭ ነህ፡፡» 24|1|(ይህች) ያወረድናትና የደነገግናት ምዕራፍ ናት፡፡ በእርሷም ውስጥ ትገሰፁ ዘንድ ግልጾችን አንቀጾች አውርደናል፡፡ 24|2|ዝሙተኛይቱና ዝሙተኛው ከሁለቱ እያንዳንዳቸውን (ያላገቡ እንደኾኑ) መቶ ግርፋትን ግረፉዋቸው፤ በእነርሱም በአላህ ፍርድ ርኅራኄ አትያዛችሁ፡፡ በአላህና በመጨረሻው ቀን የምታምኑ እንደኾናችሁ (አትራሩ)፡፡ ቅጣታቸውንም ከምእምናን ጭፍሮች ይገኙበት፡፡ 24|3|ዝሙተኛው ዝሙተኛይቱን ወይም አጋሪይቱን እንጂ አያገባም፡፡ ዝሙተኛይቱንም ዝሙተኛ ወይም አጋሪ እንጂ አያገባትም፡፡ ይህም በምእምናን ላይ ተከልክሏል፡፡ 24|4|እነዚያም ጥብቆችን ሴቶች (በዝሙት) የሚሰድቡ ከዚያም አራትን ምስክሮች ያላመጡ ሰማኒያን ግርፋት ግረፏቸው፡፡ ከእነርሱም ምስክርነትን ሁልጊዜ አትቀበሉ እነዚያም እነሱ አመጸኞች ናቸው፡፡ 24|5|እነዚያ ከዚህ በኋላ የተጸጸቱና ሥራቸውን ያሳመሩ ሲቀሩ፡፡ አላህ በጣም መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 24|6|እነዚያም ሚስቶቻቸውን (በዝሙት) የሚሰድቡ ለእነሱም ከነፍሶቻቸው በስተቀር ምስክሮች የሌሏቸው የኾኑ የአንዳቸው ምስክርነት እርሱ ከውነተኞች ለመኾኑ በአላህ ስም አራት ጊዜ ምሎ መመስከር ነው፡፡ 24|7|አምስተኛይቱም ከውሸታሞች ቢኾን በእርሱ ላይ የአላህ እርግማን ይኑርበት (ብሎ መመስከር) ነው፡፡ 24|8|እርሱም ከውሸታሞች ነው ብላ አራት ጊዜ መመስከሮችን በአላህ ስም መመስከርዋ ከእርስዋ ላይ ቅጣትን ይገፈትርላታል፡፡ 24|9|አምስተኛይቱም እርሱ ከውነተኞች ቢኾን በእርስዋ ላይ የአላህ ቁጣ ይኑርባት (ብላ መመስከርዋ) ነው፡፡ 24|10|በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ አላህም ጸጸትን ተቀባይ ጥበበኛ ባልኾነ ኖሮ (ውሸታሙን ይገልጸው ነበር)፡፡ 24|11|እነዚያ መጥፎን ውሸት ያመጡ ከናንተው የኾኑ ጭፍሮች ናቸው፡፡ ለእናንተ ክፉ ነገር ነው ብላችሁ አታስቡት፡፡ በእውነቱ እርሱ ለእናንተ መልካም ነገር ነው፡፡ ከእነርሱ (ከጭፍሮቹ) ለያንዳንዱ ሰው ከኀጢአት የሠራው ሥራ ዋጋ አለው፡፡ ያም ከእነሱ ትልቁን ኀጢአት የተሸከመው ለእርሱ ከባድ ቅጣት አለው፡፡ 24|12|(ውሸቱን) በሰማችሁት ጊዜ ምእምናንና ምእምናት በጎሶቻቸው ለምን ደግን ነገር አልጠረጠሩም ለምንስ ይህ ግልጽ ውሸት ነው አላሉም 24|13|በእርሱ ላይ ለምን አራትን ምስክሮች አላመጡም ምስክሮቹንም ካላመጡ እነዚያ አላህ ዘንድ ውሸታሞቹ እነሱ ናቸው፡፡ 24|14|በቅርቢቱም በመጨረሻይቱም ዓለም በእናንተ ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ ኖሮ በውስጡ በገባችሁበት ወሬ ምክንያት ታላቅ ቅጣት በእርግጥ በደረሰባችሁ ነበር፡፡ 24|15|በምላሶቻችሁ በምትቅበባሉት ጊዜ ለእናንተም በእርሱ ዕውቀት በሌላችሁ ነገር በአፎቻችሁ በተናገራችሁና እርሱ አላህ ዘንድ ከባድ ኀጢአት ኾኖ ሳለ ቀላል አድርጋችሁ ባሰባችሁት ጊዜ (ከባድ ቅጣት በነካችሁ ነበር)፡፡ 24|16|በሰማችሁትም ጊዜ በዚህ ልንናገር ለእኛ አይገባንም፡፡ ጥራት ይገባህ፡፡ ይህ ከባድ ቅጥፈት ነው፤ አትሉም ነበርን 24|17|ምእመናን እንደኾናችሁ ወደ ብጤው በፍፁም እንዳትመለሱ አላህ ይገስጻችኋል፡፡ 24|18|ለእናንተም አላህ አንቀጾችን ይገልጽላችኋል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 24|19|እነዚያ በእነዚያ ባመኑት ሰዎች ውስጥ መጥፎ ወሬ እንድትስፋፋ የሚወዱ ለእነሱ በቅርቢቱም በመጨረሻይቱም ዓለም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ አላህም ያውቃል እናንተ ግን አታውቁም፡፡ 24|20|በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታውና እዝነቱ ባልነበረ አላህም ሩኅሩኅና አዛኝ ባልኾነ ኖሮ (ቶሎ ባጠፋችሁ ነበር)፡፡ 24|21|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! የሰይጣንን እርምጃዎች አትከተሉ፡፡ የሰይጣንንም እርምጃዎች የሚከተል ሰው (ኀጢአትን ተሸከመ)፡፡ እርሱ በመጥፎና በሚጠላ ነገር ያዛልና፡፡ በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ ኖሮ ከናንተ አንድም ፈጽሞ ባልጠራ ነበር፡፡ ግን አላህ የሚሻውን ሰው ያጠራል፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 24|22|ከእናንተም የችሮታና የክብረት ባለቤቶች የኾኑት ለቅርብ ዘመዶችና ለድኾች በአላህም መንገድ ለተሰደዱ ሰዎች ላይሰጡ አይማሉ፡፡ ይቅርታም ያድርጉ፡፡ (ጥፋተኞቹን) ይለፉም፡፡ አላህ ለእናንተ ሊምር አትወዱምን አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 24|23|እነዚያ ጥብቆቹን ከዝሙት ዘንጊዎቹን ምእምናት የሚሰድቡ፤ በቅርቢቱም በመጨረሻይቱም ዓለም ተረገሙ፡፡ ለእነርሱም ታላቅ ቅጣት አላቸው፡፡ 24|24|በእነሱ ላይ ምላሶቻቸው፣ እጆቻቸውና እግሮቻቸውም ይሠሩት በነበሩት ነገር በሚመሰክሩባቸው ቀን (ከባድ ቅጣት አላቸው)፡፡ 24|25|በዚያ ቀን አላህ እውነተኛ ዋጋቸውን ይሞላላቸዋል፡፡ አላህም እርሱ መኖሩ የተረጋገጠ (ሁሉን ነገር) ገላጭ መኾኑን ያውቃሉ፡፡ 24|26|መጥፎዎቹ ሴቶች ለመጥፎዎች ወንዶች መጥፎዎቹ ወንዶችም ለመጥፎዎቹ ሴቶች የተገቡ ናቸው፡፡ ጥሩዎቹ ሴቶችም ለጥሩዎቹ ወንዶች ጥሩዎቹ ወንዶችም ለጥሩዎቹ ሴቶች የሚገቡ ናቸው፡፡ እነዚያ (መጥፎዎቹ) ከሚሉት ነገር ንጹሕ የተደረጉ ናቸው፡፡ ለእነርሱ ምህረትና መልካም ሲሳይ አላቸው፡፡ 24|27|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እስከምታስፈቅዱና በባለቤቶቿ ላይ ሰላምታን እስከምታቀርቡ ድረስ ከቤቶቻችሁ ሌላ የኾኑን ቤቶች አትግቡ፡፡ ይህ ለእናንተ መልካም ነው፡፡ እናንተ ትገነዘቡ ዘንድ (በዚህ ታዘዛችሁ)፡፡ 24|28|በውስጧም አንድንም ሰው ባታገኙ ለእናንተ እስከሚፈቀድላችሁ ድረስ አትግቧት፡፡ ለእናንተ ተመለሱ ብትባሉም ተመለሱ፡፡ እርሱ ለእናንተ የተሻለ ነው፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 24|29|መኖሪያ ያልኾኑን ቤቶች በውስጣቸው ለእናንተ ጥቅም ያላችሁን (ሳታስፈቅዱ) ብትገቡ በእናንተ ላይ ኀጢአት የለባችሁም፡፡ አላህም የምትገልጹትንና የምትደብቁትን ሁሉ ያውቃል፡፡ 24|30|ለምእመናን ንገራቸው፡- ዓይኖቻቸውን (ያልተፈቀደን ከማየት) ይከልክሉ፤ ብልቶቻቸውንም ይጠብቁ፤ ይህ ለነሱ የተሻለ ነው፤ አላህ በሚሠሩት ሁሉ ውስጥ ዐዋቂ ነው፡፡ 24|31|ለምእምናትም ንገራቸው፡- ዓይኖቻቸውን ይከልክሉ፡፡ ብልቶቻቸውንም ይጠብቁ፡፡ ጌጣቸውንም ከእርሷ ግልጽ ከኾነው በስተቀር አይግለጡ፡፡ ጉፍታዎቻቸውንም በአንገትጌዎቻቸው ላይ ያጣፉ፡፡ (የውስጥ) ጌጣቸውንም ለባሎቻቸው ወይም ለአባቶቻቸው ወይም ለባሎቻቸው አባቶች ወይም ለወንዶች ልጆቻቸው ወይም ለባሎቻቸው ወንዶች ልጆች ወይም ለወንድሞቻቸው ወይም ለወንድሞቻቸው ወንዶች ልጆች ወይም ለእህቶቻቸው ወንዶች ልጆች ወይም ለሴቶቻቸው ወይም እጆቻቸው ለያዙት (ባሪያ) ወይም ከወንዶች ለሴት ጉዳይ የሌላቸው ለኾኑ ተከታዮች ወይም ለነዚያ በሴቶች ሐፍረተ ገላ ላይ ላላወቁ ሕፃኖች ካልኾነ በስተቀር አይግለጹ፡፡ ከጌጣቸውም የሚሸፍኑት ይታወቅ ዘንድ በእግሮቻቸው አይምቱ፡፡ ምእመናኖች ሆይ! ትድኑ ዘንድ ሁላችሁም ወደ አላህ (በመመለስ) ተጸጸቱ፡፡ 24|32|ከናንተም ትዳር የሌላቸውን አጋቡ፡፡ ከወንዶች ባሮቻችሁና ከሴቶች ባሮቻችሁም ለጋብቻ ብቁ የኾኑትን (አጋቡ)፡፡ ድኾች ቢኾኑ አላህ ከችሮታው ያከብራቸዋል፡፡ አላህም ስጦታው ሰፊ ዐዋቂ ነው፡፡ 24|33|እነዚያም የማግቢያን ጣጣ የማያገኙ አላህ ከችሮታው እስከሚያከብራቸው ድረስ ይጠበቁ፡፡ እነዚያንም እጆቻችሁ ከጨበጧቸው አገልጋዮች (ገንዘብ ሰጥተው ነጻ ለመውጣት) መጻጻፍን የሚፈልጉትን ከእነሱ መልካምን ነገር ብታውቁ ተጻጻፉዋቸው፡፡ ከአላህም ገንዘብ ከዚያ ከሰጣችሁ ስጧቸው፡፡ ሴቶች ባሮቻችሁንም መጥጠበቅን ቢፈልጉ የቅርቢቱን ሕይወት ጥቅም ለመፈለግ ብላችሁ በዝሙት ላይ አታስገድዱዋቸው፡፡ የሚያስገድዳቸውም ሰው አላህ ከመገደዳቸው በኋላ (ለተገደዱት) መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 24|34|ወደእናንተም አብራሪ የኾኑን አንቀጾች ከእነዚያ ከበፊታችሁ ካለፉትም (ምሳሌዎች ዓይነት) ምሳሌን ለጥንቁቆቹ መገሰጫንም በእርግጥ አወረድን፡፡ 24|35|አላህ የሰማያትና የምድር አብሪ ነው፡፡ የብርሃኑ ምሳሌ በውስጧ መብራት እንዳለባት (ዝግ) መስኮት፣ መብራቱ በብርጭቆ ውስጥ የኾነ፣ ብርጭቆይቱ ፍፁም ሉላዊ ኮከብ የምትመሰል፣ ምሥራቃዊው ምዕራባዊም ካልኾነች ከተባረከች የወይራ ዛፍ ዘይቷ እሳት ባይነካውም እንኳ ሊያበራ የሚቀርብ ከኾነች (ዘይት) የሚቃጠል እንደ ሆነ (መብራት) ነው፡፡ (ይህ) በብርሃን ላይ የኾነ ብርሃን ነው፡፡ አላህ ወደ ብርሃኑ የሚሻውን ሰው ይመራል፡፡ አላህም ለሰዎች ምሳሌዎችን ያቀርባል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 24|36|አላህ እንድትከበርና ስሙ በውስጧ እንዲወሳ ባዘዘው ቤቶች ውስጥ (አወድሱት)፡፡ በውስጧ በጧትና በማታ ለእርሱ ያጠራሉ፡፡ 24|37|አላህን ከማውሳትና ሶላትን ከመስገድ ዘካንም ከመስጠት ንግድም ሽያጭም የማያታልላቸው ልቦችና ዓይኖች በእርሱ የሚገላበጡበትን ቀን የሚፈሩ የኾኑ ሰዎች (ያጠሩታል)፡፡ 24|38|አላህ የሠሩትን ሥራ መልካሙን ሊመነዳቸው ከችሮታውም ሊጨመርላቸው (ያጠሩታል)፡፡ አላህም ለሚሻው ሰው ያለ ግምት ይሰጣል፡፡ 24|39|እነዚያም የካዱት ሰዎች ሥራዎቻቸው (መልካሞቹ) በበረሃ ሜዳ እንዳለ ሲሪብዱ የጠማው ሰው ውሃ ነው ብሎ እንደሚያስበው በመጣውም ጊዜ ምንም ነገር ኾኖ እንደማያገኘው ነው፡፡ (ከሓዲው) አላህንም እሠራው ዘንድ ያገኘዋል፡፡ ምርመራውንም (ቅጣቱን) ይሞላለታል፡፡ አላህም ምርመራው ፈጣን ነው፡፡ 24|40|ወይም (መጥፎ ሥራዎቻቸውን) ከበላዩ ደመና ያለበት ማዕበል በሚሸፈነው ጥልቅ ባህር ውስጥ እንዳሉ ጨለማዎች ነው፡፡ (እነዚያ) ከፊላቸው ከከፊሉ በላይ ድርብርብ የኾኑ ጨለማዎች ናቸው፡፡ (በዚህች) የተሞከረ (ሰው) እጁን ባወጣ ጊዜ ሊያያት አይቀርብም፡፡ አላህም ለእርሱ ብርሃንን ያላደረገለት ሰው ለእርሱ ምንም ብርሃን የለውም፡፡ 24|41|አላህ በሰማያትና በምድር ያለ ሁሉ በራሪዎችም ክንፎቻቸውን (በአየር ላይ) ያንሳፈፉ ኾነው ለእርሱ የሚያጠሩ (የሚያወድሱ) መኾናቸውን አላወቅህምን ሁሉም ስግደቱንና ማጥራቱን በእርግጥ ዐወቀ፡፡ አላህም የሚሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 24|42|የሰማያትና የምድርም ግዛት የአላህ ነው፡፡ መመለሻም ወደ አላህ ነው፡፡ 24|43|አላህ ደመናን የሚነዳ መኾኑን አላየህምን ከዚያም ከፊሉን ከከፊሉ ያገናኛል፡፡ ከዚያም የተደራረበ ያደርገዋል፡፡ ዝናቡንም ከመካከሉ የሚወጣ ኾኖ ታየዋለህ፡፡ ከሰማይም (ከደመና) በውስጧ ካሉት ጋራዎች በረዶን ያወርዳል፡፡ በእርሱም የሚሻውን ሰው (በጉዳት) ይነካል፡፡ ከሚሻውም ሰው ላይ ይመልሰዋል፡፡ የብልጭታው ብርሃን ዓይኖችን ሊወስድ ይቀርባል፡፡ 24|44|አላህ ሌሊትንና ቀንን ያገላብጣል፡፡ በዚህም ለባለ ውስጥ ዓይኖች በእርግጥ ማስረጃ አልለበት፡፡ 24|45|አላህም ተንቀሳቃሽን ሁሉ ከውሃ ፈጠረ፡፡ ከእነሱም በሆዱ ላይ የሚኼድ አልለ፡፡ ከእነሱም በሁለት እግሮች ላይ የሚኼድ አልለ፡፡ አላህ የሚሻውን ሁሉ ይፈጥራል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና፡፡ 24|46|አብራሪን አንቀጾች በእርግጥ አወረድን፡፡ አላህም የሚሻውን ሰው ወደ ቀጥተኛ መንገድ ይመራዋል፡፡ 24|47|በአላህና በመልክተኛውም አምነናል ታዘናልም ይላሉ፡፡ ከዚያም ከዚህ በኋላ ከእነሱ ከፊሉ ይሸሻል፡፡ እነዚያም ምእምናን አይደሉም፤ 24|48|ወደ አላህና ወደ መልክተኛውም በመካከላቸው ሊፈርድ በተጠሩ ጊዜ ከእነሱ ከፊሉ ወዲያውኑ ይሸሻሉ፡፡ 24|49|እውነቱም (ሐቁ) ለእነሱ ቢኾን ወደርሱ ታዛዦች ኾነው ይመጣሉ፡፡ 24|50|በልቦቻቸው ውስጥ በሺታ አለን ወይስ (በነቢይነቱ) ተጠራጠሩን ወይስ አላህና መልክተኛው በእነሱ ላይ የሚበድሉ መኾንን ይፈራሉን ይልቁንም፤ እነዚያ እነሱ በዳዮቹ ናቸው፡፡ 24|51|የምእምናን ቃል የነበረው ወደ አላህና ወደ መልክተኛው በመካከላቸው ሊፈርድ በተጠሩ ጊዜ ሰማን፤ ታዘዝንም ማለት ብቻ ነው፡፡ እነዚህም እነሱ የፈለጉትን የሚያገኙ ናቸው፡፡ 24|52|አላህንና መልክተኛውን የሚታዘዝም ሰው፣ አላህንም የሚፈራና የሚጠነቀቀው ሰው፤ እነዚያ እነርሱ ፍለጎታቸውን የሚያገኙ ናቸው፡፡ 24|53|(ለዘመቻ) ብታዛቸውም በእርግጥ ሊወጡ የጠነከሩ መሓሎቻቸውን በአላህ ስም ይምላሉ፡፡ «አትማሉ፤ የታወቀች (የንፍቅና) መታዘዝ ናትና፡፡ አላህ በምትሠሩት ነገር ሁሉ ውስጥ ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 24|54|«አላህን ተገዙ፡፡ መልክተኛውንም ታዘዙ፤ ብትሸሹም (አትጎዱትም)፡፡ በእርሱ ላይ ያለበት የተገደደውን ማድረስ ብቻ ነው፡፡ በእናንተም ላይ ያለባችሁ የተገደዳችሁት (መታዘዝ) ብቻ ነው፡፡ ብትታዘዙትም ትምመራላችሁ፡፡ በመልእክተኛውም ላይ ግልጽ ማድረስ እንጂ ሌላ የለበትም» በላቸው፡፡ 24|55|አላህ እነዚያን ከእናንተ ያመኑትንና መልካም ሥራዎችን የሠሩትን እነዚያን ከእነሱ በፊት የነበሩትን እንደተካ በምድር ለይ በእርግጥ ሊተካቸው፣ ለእነሱም ያንን የወደደላቸውን ሃይማኖታቸውን ሊያደላድልላቸው፣ ከፍርሃታቸውም በኋላ ጸጥታን ሊለውጥላቸው ተስፋን ቃል ሰጥቷቸዋል፡፡ በእኔ ምንንም የማያጋሩ ኾነው ይግገዙኛል፡፡ ከዚያም በኋላ የካደ ሰው እነዚያ እነርሱ አመጸኞች ናቸው፡፡ 24|56|ሶላትንም አስተካክላችሁ ስገዱ፡፡ ምጽዋትንም ስጡ፡፡ መልክተኛውንም ታዘዙ፡፡ ለእናንተ ሊታዘንላችሁ ይከጀላልና፡፡ 24|57|እነዚያን የካዱትን በምድር ውስጥ የሚያቅቱ አድርገህ አታስብ፡፡ መኖሪያቸውም እሳት ናት፡፡ በእርግጥም የከፋች መመለሻ ናት፡፡ 24|58|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እነዚያ እጆቻችሁ የጨበጧቸው (ባሮች) እነዚያም ከእናንተ ለአካላ መጠን ያልደረሱት ከጎህ ስግደት በፊት፣ በቀትርም ልብሶቻችሁን በምታወልቁ ጊዜ ከምሽት ስግደትም በኋላ ሦስት ጊዜያት (ለመግባት ሲፈልጉ) ያስፈቅዷችሁ፡፡ (እነዚህ) ለእናንተ የኾኑ ሦስት የሐፍረተ ገላ መገለጫ ጊዜያቶች ናቸውና፡፡ ከእነዚህ በኋላ በእናንተም በእነርሱም ላይ (ያለፈቃድ በመግባት) ኀጢአት የለም፡፡ በእናንተ ላይ (ለማገልገል) ዙዋሪዎች ናቸውና፡፡ ከፊላችሁ በከፊሉ ላይ ዙዋሪ ነው፡፡ እንደዚሁ አላህ ለእናንተ ሕግጋትን ይገልጽላችኋል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 24|59|ከእናንተም ሕፃናቶቹ አቅመ አዳምን በደረሱ ጊዜ እነዚያ ከእነሱ በፊት የነበሩት (ታላላቆቹ) እንዳስፈቀዱ ያስፈቅዱ፡፡ እንደዚሁ አላህ ለእናንተ አንቀጾቹን ያብራራል፤ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 24|60|ከሴቶችም እነዚያ ጋብቻን የማይፈልጉት ተቀማጮች (ባልቴቶች)፤ በጌጥ የተገለፁ ሳይኾኑ የላይ ልብሶቻቸውን ቢጥሉ በእነሱ ላይ ኀጢአት የለባቸውም፡፡ ግን መጠበቃቸው ለእነርሱ የተሻለ ነው፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡ 24|61|(ከሰዎች ጋር በመብላት) በዕውር ላይ ኀጢአት የለበትም፡፡ በአንካሳም ላይ ኀጢአት የለበትም፡፡ በበሽተኛም ላይ ኀጢአት የለበትም፡፡ በነፍሶቻችሁም ላይ ከቤቶቻችሁ ወይም ከአባቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከእናቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከወንድሞቻችሁ ቤቶች ወይም ከእኅቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከአጎቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከአክስቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከየሹሞቻችሁ ቤቶች ወይም ከየሹሜዎቻችሁ ቤቶች ወይም መክፈቻዎቹን ከያዛችሁት ቤት ወይም ከወዳጃችሁ ቤት (ብትበሉ) ኀጢአት የለባችሁም፡፡ ተሰብስባችሁ ወይም ተለያይታችሁ ብትበሉ በእናንተ ላይ ኀጢአት የለባችሁም፡፡ ቤቶችንም በገባችሁ ጊዜ፤ ከአላህ ዘንድ የኾነችን የተባረከች መልካም ሰላምታ በነፍሶቻችሁ ላይ ሰላም በሉ፡፡ እንደዚሁ አላህ አንቀጾችን ለእናንተ ያብራራል፡፡ ልታውቁ ይከጀላልና፡፡ 24|62|ምእመናን ማለት እነዚያ በአላህና በመልክተኛው ያመኑት፤ ከእርሱ ጋር በሚሰበሰብ ጉዳይ ላይ በኾኑ ጊዜ እስከሚያስፈቅዱ ድረስ የማይኼዱት ብቻ ናቸው፡፡ እነዚያ የሚያስፈቅዱህ እነርሱ እነዚያ በአላህና በመልክተኛው የሚያምኑት ናቸው፡፡ ለግል ጉዳያቸውም ፈቃድ በጠየቁህ ጊዜ ከእነሱ ለሻኸው ሰው ፍቀድለት፡፡ ለእነሱም አላህን ምሕረትን ለምንላቸው አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 24|63|በመካከላችሁ የመልክተኛውን ጥሪ ከፊላችሁ ከፊሉን እንደ መጥራት አታድርጉት፡፡ ከእናንተ ውስጥ እነዚያን እየተከለሉ በመስለክለክ የሚወጡትን አላህ በእርግጥ ያውቃቸዋል፡፡ እነዚያም ትዕዛዙን የሚጥሱ መከራ እንዳትደርስባቸው ወይም አሳማሚ ቅጣት እንዳያገኛቸው ይጠንቀቁ፡፡ 24|64|ንቁ! በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ብቻ ነው፡፡ እናንተ በእርሱ ላይ ያላችሁበትን ኹኔታ በእርግጥ ያውቃል፡፡ ወደእርሱ የሚመለሱበትን ቀንም (ያውቃል)፡፡ የሠሩትንም ሁሉ ይነግራቸዋል፡፡ አላህም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 25|1|ያ ፉርቃንን በባሪያው ላይ ለዓለማት አስፈራሪ ይኾን ዘንድ ያወረደው (አምላክ) ክብርና ጥራት ተገባው፡፡ 25|2|(እርሱ) ያ የሰማያትና የምድር ንግሥና የእርሱ ብቻ የኾነ፣ ልጅንም ያልያዘ፣ በንግሥናውም ተጋሪ የሌለው፣ ነገሩንም ሁሉ የፈጠረና በትክክልም ያዘጋጀው ነው፡፡ 25|3|(ከሓዲዎች) ከእርሱም ሌላ ምንንም የማይፈጥሩን፣ እነርሱም የሚፈጠሩን፣ ለነፍሶቻቸውም ጉዳትን ለመከላከል ጥቅምንም ለማምጣት የማይችሉን ሞትንና ሕይወትንም መቀስቀስንም የማይችሉን፣ አማልክት ያዙ፡፡ 25|4|እነዚያም የካዱት ይህ (ቁርኣን ሙሐመድ) የቀጠፈው በእርሱም ላይ ሌሎች ሕዝቦች ያገዙት የኾነ ውሸት እንጂ ሌላ አይደለም አሉ፡፡ በእርግጥም በደልንና እብለትን ሠሩ፡፡ 25|5|አሉም «የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ተረቶች ናት፡፡ አስጻፋት፡፡ እርሷም በእርሱ ላይ ጧትና ማታ ትነበብለታለች፡፡» 25|6|«ያ በሰማያትና በምድር ውስጥ ያለን ምስጢር የሚያውቀው አወረደው፡፡ እርሱ መሓሪ አዛኝ ነውና» በላቸው፡፡ 25|7|ለዚህም መልክተኛ ምግብን የሚበላ፣ በገበያዎችም የሚኼድ ሲኾን ምን (መልክተኛነት) አለው ከርሱ ጋር አስፈራሪ ይኾን ዘንድ ወደርሱ መልአክ (ገሃድ) አይወረድም ኖሯልን አሉ፡፡ 25|8|«ወይም ወደእርሱ ድልብ አይጣልለትምን ወይም ከእርሷ የሚበላላት አትክልት ለእርሱ አትኖረውምን» (አሉ)፡፡ በዳዮቹም (ላመኑት) «የተደገመበትን ሰው እንጂ ሌላ አትከተሉም» አሉ፡፡ 25|9|ላንተ ምሳሌዎችን እንዴት እንዳደረጉልህና እንደተሳሳቱ ተመልከት፡፡ (ወደ እውነት ለመድረስ) መንገድንም አይችሉም፡፡ 25|10|ያ ቢሻ ከዚህ (ካሉት) የተሻለን ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን አትክልቶች ላንተ የሚያደርግልህ ሕንጻ ቤቶችንም ላንተ የሚያደርግልህ ጌታ ችሮታው በዛ፡፡ 25|11|ይልቁንም በትንሣኤ አስተባበሉ፡፡ በትንሣኤ ላስተባበለም ሰው ሁሉ ነዳጅን እሳት አዘጋጅተናል፡፡ 25|12|ከሩቅ ስፍራ ባየቻቸው ጊዜ ለእርሷ የቁጭት መገንፈልንና ማናፋትን ይሰማሉ፡፡ 25|13|እጅ ከፍንጅ የታሠሩ ኾነውም ከእርሷ በጠባብ ስፍራ በተጣሉ ጊዜ በዚያ ስፍራ ጥፋትን ይጠራሉ፤ (ዋ ጥፋታችን ይላሉ)፡፡ 25|14|፡-ዛሬ አንድን ጥፋት ብቻ አትጥሩ ብዙንም ጥፋት ጥሩ (ይባላሉ)፡፡ 25|15|(እንዲህ) በላቸው «ይህ የተሻለ ነውን ወይስ ጥንቁቆቹ ተስፋ የተሰጧት የዘለዓለሟ ገነት» ለእነርሱ ምንዳና መመለሻ ኾነች፡፡ 25|16|ለእነሱ በውስጧ ዘውታሪዎች ኾነው የሚፈልጉት ሁሉ አልላቸው፡፡ (ይህም) ተስፋ ከጌታህ ተለማኝ ተስፋ ነው፡፡ 25|17|እነርሱንና ከአላህ ሌላ የሚግገዟቸውንም የሚሰበስብባቸውንና «እናንተ እነዚህን ባሮቼን አሳሳታችሁን ወይስ እነሱው መንገድን ሳቱ» የሚልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 25|18|«ጥራት ይገባህ፤ ካንተ ሌላ ረዳቶችን ልንይዝ ለእኛ ተገቢያችን አልነበረም፡፡ ግን እነርሱንም አባቶቻቸውንም መገንዘብን እስከተዉ ድረስ አጣቀምካቸው፡፡ ጠፊ ሕዝቦችም ኾኑ» ይላሉ፡፡ 25|19|በምትሉትም (አማልክቶቻችሁ) አስዋሹዋችሁ፡፡ ቅጣቴን መገፍተርንም መርዳትንም አትችሉም፡፡ ከእናንተም የሚበድለውን ታላቅን ቅጣት እናቀምሰዋለን፤ (ይባላሉ)፡፡ 25|20|ከአንተ በፊትም ከመልክተኞች እነሱ በእርግጥ ምግብን የሚበሉ በገበያዎችም የሚኼዱ ኾነው በስተቀር አልላክንም፡፡ ከፊላችሁንም ለከፊሉ ፈተና አድርገናል፡፡ ትታገሳላችሁን ጌታህም ተመልካች ነው፡፡ 25|21|እነዚያም መገናኘታችንን የማይፈሩት በእኛ ላይ ለምን መላእክት አልወረደም፡፡ ወይም ጌታችንን ለምን አናይም አሉ፡ በነፍሶቻቸው ውስጥ በእርግጥ ኮሩ፡፡ ታላቅንም አመጽ አመፁ፡፡ 25|22|መላእክትን በሚያዩበት ቀን በዚያ ጊዜ ለአመጸኞች ምስራች የላቸውም፡፡ «የተከለከለ ክልክልም አድርገን» ይላሉ፡፡ 25|23|ከሥራም ወደ ሠሩት እናስባለን፡፡ የተበተነ ትቢያም እናደርገዋለን፡፡ 25|24|የገነት ሰዎች በዚያ ቀን በመርጊያ የተሻሉ በማረፊያም በጣም ያማሩ ናቸው፡፡ 25|25|ሰማይም በደመና የምትቀደድበትንና መላእክትም መወረድን የሚወርድበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 25|26|እውነተኛው ንግሥና በዚያ ቀን ለአልራሕማን ብቻ ነው፡፡ በከሓዲዎችም ላይ አስቸጋሪ ቀን ነው፡፡ 25|27|በዳይም «ከመልክተኛው ጋር ቀጥተኛን መንገድ ይዤ በኾነ ዋ ምኞቴ!» እያለ (በጸጸት) ሁለት እጆቹን የሚነክስበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 25|28|«ዋ ጥፋቴ! እገሌን ወዳጅ ባልያዝኩ ኖሮ እመኛለሁ፡፡ 25|29|(የእምነት ቃልን) ከመጣልኝ በኋላ ከማስታወስ በእርግጥ አሳሳተኝ» (ይላል)፡፡ ሰይጣንም ለሰው አጋላጭ ነው፡፡ 25|30|መልክተኛውም «ጌታዬ ሆይ! ሕዝቦቼ ይህንን ቁርኣን የተተወ ነገር አድርገው ያዙት» አለ፡፡ 25|31|እንደዚሁም ለነቢዩ ሁሉ ከአመጸኞች የኾነ ጠላትን አድርገናል፡፡ መሪና ረዳትም በጌታህ በቃ፡፡ 25|32|እነዚያ የካዱትም «ቁርኣን በእርሱ ላይ ለምን በጠቅላላ አንድ ጊዜ አልተወረደም» አሉ፡፡ እንደዚሁ በእርሱ ልብህን ልናረጋ (ከፋፍለን አወረድነው)፡፡ ቀስ በቀስ መለያየትንም ለየነው፡፡ 25|33|በጥያቄም አይመጡብህም እውነተኛውን (መልስ) መልካምን ፍችም የምናመጣልህ ብንኾን እንጅ፡፡ 25|34|እነዚያ በፊቶቻቸው ለይ (እየተጎተቱ) ወደ ገሀነም የሚሰበሰቡ ናቸው፡፡ እነዚያ ስፍራቸው የከፋ መንገዳቸውም የጠመመ ናቸው፡፡ 25|35|በእርግጥም ለሙሳ መጽሐፍን ሰጠነው፡፡ ከእርሱም ጋር ወንድሙን ሃሩንን ረዳት አደረግንለት፡፡ 25|36|«ወደእነዚያም በተዓምራቶቻችን ወደ አስተባበሉት ሕዝቦች ኺዱ» አልናቸው፡፡ (አስዋሿቸውም) ማጥፋትንም አጠፋናቸው፡፡ 25|37|የኑሕን ሰዎችም መልክተኞችን ባስተባበሉ ጊዜ አሰጠምናቸው፡፡ ለሰዎችም መገሰጫ አደረግናለቸው፡፡ ለበደለኞችም አሳማሚን ቅጣት አዘጋጅተናል፡፡ 25|38|ዓድንም ሰሙድንም የረስን ሰዎችም በዚህ መካከል የነበሩትንም ብዙን የክፍለ ዘመናት ሕዝቦች (አጠፋን)፡፡ 25|39|ሁሉንም (ገሠጽን) ለእነሱ ምሳሌዎችን ገለጽን፡፡ ሁሉንም ማጥፋትን አጠፋናቸውም፡፡ 25|40|በዚያችም ክፉ ዝናምን በተዘነመችው ከተማ ላይ (የመካ ከሐዲዎች) በእርግጥ መጥተዋል፡፡ የሚያዩዋት አልነበሩምን በእውነቱ መቀስቀስን የማይፈሩ ነበሩ፡፡ 25|41|ባዩህም ጊዜ ያ አላህ መልእክተኛ አድርጎ የላከው ይህ ነውን እያሉ መሳለቂያ እንጂ ሌላ አያደርጉህም፡፡ 25|42|«እነሆ በእርሷ ላይ መታገሳችን ባልነበረ ኖሮ ከአማልክቶቻችን ሊያሳስተን ቀርቦ ነበር» (ሲሉም ይሳለቃሉ)፡፡ ወደፊትም ቅጣቱን በሚያዩ ጊዜ መንገድን በጣም ተሰሳቹ ማን እንደኾነ በእርግጥ ያውቃሉ፡፡ 25|43|ፍላጎቱን አምላኩ አድርጎ የያዘውን ሰው አየህን አንተ በእርሱ ላይ ጠባቂ ትኾናለህን 25|44|ይልቁንም አብዛኛዎቻቸው የሚሰሙ ወይም የሚያውቁ መኾናቸውን ታስባለህን እነርሱ እንደ እንስሳዎች እንጂ ሌላ አይደሉም፡፡ ከቶውንም እነሱ ይልቅ መንገድን የተሳሳቱ ናቸው፡፡ 25|45|ወደ ጌታህ (ሥራ) ጥላን እንዴት እንደ ዘረጋ አላየህምን በሻም ኖሮ የረጋ ባደረገው ነበር፡፡ ከዚያም ፀሐይን በእርሱ ላይ ምልክት አደረግን፡፡ 25|46|ከዚያም ቀስ በቀስ ወደእኛ ሰብሰብነው፡፡ 25|47|እርሱም ያ ለእናንተ ሌሊትን ልብስ እንቅልፍንም ማረፊያ ያደረገ፤ ቀንንም መበተኛ ያደረገላችሁ ነው፡፡ 25|48|እርሱም ያ ነፋሶችን አብሳሪዎች ሲኾኑ ከዝናሙ በስተፊት የላከ ነው፡፡ ከሰማይም አጥሪ ውሃን አወረድን፡፡ 25|49|በእርሱ የሞተችን አገር ሕያው ልናደርግበት ከፈጠርነውም ፍጡር እንስሳዎችንና ብዙ ሰዎችንም ልናጠጣው (አወረድነው)፡፡ 25|50|(ጸጋችንን) ይገነዘቡም ዘንድ በመካከላቸው ከፋፈልነው፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች ክህደትን እንጂ እንቢ አሉ፡፡ 25|51|በሻንም ኖሮ በየከተማይቱ አስፈራሪን በላክን ነበር፡፡ 25|52|ከሓዲዎችንም አትታዘዛቸው፡፡ በእርሱም (በቁርኣን) ታላቅን ትግል ታገላቸው፡፡ 25|53|እርሱም ያ ሁለቱን ባሕሮች አጎራብቶ የለቀቀ ነው፡፡ ይህ ጥምን የሚቆርጥ ጣፋጭ ነው፡፡ ይህም የሚመረግግ ጨው ነው፡፡ በመካከላቸውም (ከመቀላቀል) መለያንና የተከለለን ክልል ያደረገ ነው፡፡ 25|54|እርሱም ያ ከውሃ ሰውን የፈጠረ፣ የዝምድናና የአማችም ባለቤት ያደረገው ነው፡፡ ጌታህም ቻይ ነው፡፡ 25|55|ከአላህም ሌላ የማይጠቅማቸውንና የማይጎዳቸውን ይግገዛሉ፤ ከሓዲም በጌታው ላይ (በማመጽ ለሰይጣን) ረዳት ነው፡፡ 25|56|አብሳሪና አስፈራሪም አድርገን እንጂ አልላክንህም፡፡ 25|57|«በእርሱ ላይ ዋጋን በፍጹም አልጠይቃችሁም፡፡ ግን ወደ ጌታው (መልካም) መንገድን ለመያዝ የሻ ሰው (ይሥራ)» በላቸው፡፡ 25|58|በዚያም በማይሞተው ሕያው አምላክ ላይ ተመካ፡፡ ከማመስገንም ጋር አጥራው፡፡ በባሮቹ ኀጢኣቶችም ውስጠ ዐዋቂ በእርሱ በቃ፡፡ 25|59|ያ ሰማያትና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ፣ ከዚያም በዐርሹ ላይ (ሥልጣኑ) የተደላደለ አልረሕማን ነው፡፡ ከእርሱም ዐዋቂን ጠይቅ፡፡ 25|60|ለእነርሱም ለአልረሕማን ስገዱ በተባሉ ጊዜ አልረሕማን ማነው ለምታዘን (እና ለማናውቀው) እንሰግዳለን ይላሉ፡፡ (ይህ) መራቅንም ጨመራቸው፡፡ 25|61|ያ በሰማይ ቡሩጆችን ያደረገና በእርሷም አንጸባራቂን (ፀሐይ) አብሪ ጨረቃንም ያደረገ ጌታ ክብሩ በጣም ላቀ፡፡ 25|62|እርሱም ያ (ያመለጠውን ሥራ) ማስታወስን ለሚፈልግ ወይም ማመስገንን ለሚፈልግ ሰው ሌሊትንና ቀንን ተተካኪ ያደረገ ነው፡፡ 25|63|የአልረሕማንም ባሮች እነዚያ በምድር ላይ በዝግታ የሚኼዱት፣ ባለጌዎችም (በክፉ) ባነጋገሩዋቸው ጊዜ ሰላም የሚሉት ናቸው፡፡ 25|64|እነዚያም ለጌታቸው በግንባራቸው ተደፊዎችና ቋሚዎች ኾነው የሚያድሩት ናቸው፡፡ 25|65|እነዚያም «ጌታችን ሆይ! የገሀነምን ቅጣት ከእኛ ላይ መልስልን ቅጣቷ የማይለቅ ነውና» የሚሉት ናቸው፡፡ 25|66|እርሷ መርጊያና መቀመጫ በመኾን ከፋች! (ይላሉ)፡፡ 25|67|እነዚያም በለገሱ ጊዜ የማያባክኑ የማይቆጥቡትም ናቸው፡፡ በዚህም መካከል (ልግስናቸው) ትክክለኛ የኾነ ነው፡፡ 25|68|እነዚያም ከአላህ ጋር ሌላን አምላክ የማይገዙት፣ ያችንም አላህ እርም ያደረጋትን ነፍስ ያለ ሕግ የማይገድሉት፣ የማያመነዝሩትም ናቸው፡፡ ይህንንም የሚሠራ ሰው ቅጣትን ያገኛል፡፡ 25|69|በትንሣኤ ቀን ቅጣቱ ለእርሱ ይደራረባል፡፡ በእርሱም ውስጥ የተዋረደ ኾኖ ይኖራል፡፡ 25|70|ተጸጽቶ የተመለሰና ያመነ መልካምንም ሥራ የሠራ ሰው ብቻ ሲቀር፡፡ እነዚያም አላህ መጥፎ ሥራዎቻቸውን በመልካም ሥራዎች ይለውጣል፡፡ አላህም እጅግ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 25|71|ተጸጽቶ የተመለሰም ሰው መልካምንም የሠራ እርሱ የተወደደን መመለስ ወደ አላህ ይመለሳል፡፡ 25|72|እነዚያም እብለትን የማይመሰክሩ፤ በውድቅ ቃልም (ተናጋሪ አጠገብ) ባለፉ ጊዜ የከበሩ ኾነው የሚያልፉት ናቸው፡፡ 25|73|እነዚያም በጌታቸው አንቀጾች በተገሰጹ ጊዜ (የተረዱ ተቀባዮች ኾነው እንጂ) ደንቆሮዎችና ዕውሮች ኾነው በእርሷ ላይ የማይደፉት ናቸው፡፡ 25|74|እነዚያም «ጌታችን ሆይ! ከሚስቶቻችንና ከዘሮቻችን ለዓይኖች መርጊያን ለእኛ ስጠን፡፡ አላህን ለሚፈሩትም መሪ አድርገን» የሚሉት ናቸው፡፡ 25|75|እነዚያ በመታገሳቸው የገነትን ሰገነቶች ይምመነዳሉ፡፡ በእርሷም ውስጥ ውዳሴንና ሰላምታን ይስሰጣሉ፡፡ 25|76|በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ኾነው (ይስሰጣሉ)፡፡ መርጊያና መኖሪያይቱ አማረች፡፡ 25|77|«ጸሎታችሁ ባልነበረ ኖሮ ጌታዬ እናንተን ከምንም አይቆጥራችሁም ነበር፡፡ በእርግጥም አስተባበላችሁ፤ ወደ ፊትም (ቅጣቱ) ያዣችሁ ይኾናል» በላቸው፡፡ 26|1|ጠ.ሰ.መ. (ጧ ሲን ሚም)፡፡ 26|2|ይህች ግልጽ ከኾነው መጽሐፍ አንቀጾች ናት፡፡ 26|3|አማኞች ባለመኾናቸው፤ (በቁጭት) ነፍስህን ገዳይ መኾን ይፈራልሃል፡፡ 26|4|ብንሻ በእነሱ ላይ ከሰማይ ተዓምረን እናወርድና አንገቶቻቸው (መሪዎቻቸው) ለእርሷ ተዋራጆች ይኾናሉ፡፡ 26|5|ከአልረሕማንም ዘንድ ኣዲስ የተወረደ ቁርኣን አይመጣላቸውም፤ ከእርሱ የሚሸሹ ቢኾኑ እንጂ፡፡ 26|6|በእርግጥም አስተባበሉ፡፡ የዚያም በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩት ወሬዎች (ፍጻሜ) ይመጣባቸዋል፡፡ 26|7|ወደ ምድርም በውስጧ ከመልካም (በቃይ) ጎሳ ሁሉ ብዙን እንዳበቀልን አላዩምን፡፡ 26|8|በዚህ አስደናቂ ምልክት አልለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም አማኞች አልነበሩም፡፡ 26|9|ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊ አዛኝ ነው፡፡ 26|10|ጌታህም ሙሳን «ወደ በደለኞቹ ሕዝቦች ኺድ» በማለት በጠራው ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 26|11|«ወደ ፈርዖን ሕዝቦች (ኺድ) አላህን አይፈሩምን» (አለው)፡፡ 26|12|(ሙሳም) አለ «ጌታዬ ሆይ! እኔ ሊያስተባብሉኝ እፈራለሁ፡፡ 26|13|«ልቤም ይጠብባል፡፡ ምላሴም አይፈታም፡፡ ስለዚህ ወደ ሃሩን ላክ፡፡ 26|14|«ለእነርሱም በእኔ ላይ (የደም) ወንጀል አልለ፡፡ ስለዚህ እንዳይገድሉኝ እፈራለሁ፡፡» 26|15|(አላህ) አለ «ተው! (አይነኩህም)፡፡ በተዓምራቶቻችንም ኺዱ፡፡ እኛ ከእናንተ ጋር ሰሚዎች ነንና፡፡ 26|16|«ወደ ፈርዖንም ኺዱ፡፡ በሉትም፡- እኛ የዓለማት ጌታ መልክተኞች ነን፡፡ 26|17|«የእስራኤልን ልጆች ከእኛ ጋር ልቀቅ፡፡» 26|18|(ፈርዖንም) አለ «ልጅ ኾነህ በእኛ ውስጥ አላሳደግንህምን በእኛ ውስጥም ከዕድሜህ ብዙ ዓመታትን አልተቀመጥክምን 26|19|«ያችንም የሠራሃትን ሥራህን አልሠራህምን አንተም ከውለታ ቢሶቹ ነህ» (አለ)፡፡ 26|20|(ሙሳም) አለ «ያን ጊዜ እኔም ከተሳሳቱት ኾኜ ሠራኋት፡፡ 26|21|«በፈራኋችሁም ጊዜ ከእንናተ ሸሸሁ፡፡ ጌታየም ለእኔ ጥበብን ሰጠኝ፡፡ ከመልክተኞቹም አደረገኝ፡፡ 26|22|«ይህችም የእስራኤልን ልጆች ባሪያ በማድረግህ በእኔ ላይ የምትመጻደቅባት ጸጋ ነት፡፡» 26|23|ፈርዖን አለ «(ላከኝ የምትለው) የዓለማትም ጌታ ምንድነው» 26|24|(ሙሳ) «የሰማያትና የምድር በመካከላቸውም ያለው ሁሉ ጌታ ነው፡፡ የምታረጋግጡ ብትኾኑ (ነገሩ ይህ ነው)፤» አለው፡፡ 26|25|(ፈርዖንም) በዙሪያው ላሉት ሰዎች «አትሰሙምን» አለ፡፡ 26|26|(ሙሳ) «ጌታችሁና የመጀመሪያዎቹ አባቶቻችሁም ጌታ ነው» አለው፡፡ 26|27|(ፈርዖን) «ያ ወደእናንተ የተላከው መልክተኛችሁ በእርግጥ ዕብድ ነው» አለ፡፡ 26|28|(ሙሳ) «የምሥራቅና የምዕራብ በመካከላቸውም ያለው ነገር ሁሉ ጌታ ነው፡፡ ታውቁ እንደኾናችሁ (እመኑበት)» አለው፡፡ 26|29|(ፈርዖን) «ከእኔ ሌላ አምላክን ብትይዝ በውነቱ ከእስረኞቹ አደርግሃለሁ» አለ፡፡ 26|30|(ሙሳ) «በግልጽ አስረጅ ብመጣህም እንኳ» አለው፡፡ 26|31|«እንግዲያውስ ከእውነተኞች እንደኾንክ (አስረጁን) አምጣው» አለ፡፡ 26|32|በትሩንም ጣለ፡፡ እርሷም ወዲያውኑ ግልጽ እባብ ኾነች፡፡ 26|33|እጁንም አወጣ፡፡ ወዲያውም እርሷ ለተመልካቾች (የምታበራ) ነጭ ኾነች፡፡ 26|34|(ፈርዖን) በዙሪያው ላሉት መማክርት «ይህ በእርግጥ ዐዋቂ ድግምተኛ ነው» አለ፡፡ 26|35|«ከምድራችሁ በድግምቱ ሊያወጣችሁ ይፈልጋልና ምንን ታዛላችሁ» (አላቸው)፡፡ 26|36|አሉት «እርሱን ወንድሙንም አቆይና በየከተሞቹ ሰብሳቢዎችን ላክ፡፡ 26|37|«በጣም ዐዋቂ ድግምተኞችን ሁሉ ያመጡልሃልና፡፡» 26|38|ድግምተኞቹም በታወቀ ቀን ቀጠሮ ተሰበሰቡ፡፡ 26|39|ለሰዎቹም «እናንተ ተሰብስባችኋልን» ተባለ፡፡ 26|40|«ድግምተኞቹን እነሱ አሸናፊዎች ቢኾኑ እንከተል ዘንድ» (ተባለ)፡፡ 26|41|«ድግምተኞቹም በመጡ ጊዜ ለፈርዖን እኛ አሸናፊዎች ብንሆን ለእኛ በእርግጥ ዋጋ አለን» አሉት፡፡ 26|42|«አዎን፤ እናንተም ያን ጊዜ ከባለሟሎቹ ትኾናላችሁ» አላቸው፡፡ 26|43|ሙሳ «ለእነርሱ እናንተ የምትጥሉትን ጣሉ» አላቸው፡፡ 26|44|ገመዶቻቸውንና በትሮቻቸውንም ጣሉ፡፡ «በፈርዖንም ክብር ይኹንብን፡፡ እኛ በእርግጥ አሸናፊዎቹ እኛ ነን» አሉ፡፡ 26|45|ሙሳም በትሩን ጣለ፡፡ ወዲያውም እርሷ የሚያስመስሉትን ሁሉ ትውጣለች፡፡ 26|46|ድግምተኞቹም ሰጋጆች ኾነው ወደቁ፡፡ 26|47|(እነሱም) አሉ «በዓለማት ጌታ አመንን፡፡ 26|48|«በሙሳና በሃሩን ጌታ፡፡» 26|49|(ፈርዖንም) «ለእናንተ ሳልፈቅድላችሁ በፊት ለእርሱ አመናችሁን እርሱ ያ ድግምትን ያስተማራችሁ ታላቃችሁ ነው፡፡ ወደፊትም (የሚያገኛችሁን) በእርግጥ ታውቃላችሁ፡፡ እጆቻችሁንና እግሮቻችሁን (ቀኝና ግራን) በማናጋት እቆረርጣለሁ፡፡ ሁላችሁንም እሰቅላችኋለሁም» አለ፡፡ 26|50|(እነርሱም) አሉ «ጉዳት የለብንም፡፡ እኛ ወደ ጌታችን ተመላሾች ነን፡፡ 26|51|«እኛ የምእምናን መጀመሪያ በመኾናችን ጌታችን ኀጢአቶቻችንን ለእኛ ሊምር እንከጅላለን፡፡» 26|52|ወደ ሙሳም «ባሮቼን ይዘህ ሌሊት ኺድ፡፡ እናንተ የሚከተሉዋችሁ ናችሁና» ስንል ላክን፡፡ 26|53|ፈርዖንም በየከተሞቹ ሰብሳቢዎችን (እንዲህ ሲል) ላከ፡፡ 26|54|«እነዚህ ጥቂቶች ጭፈሮች ናቸው፡፡ 26|55|«እነርሱም ለእኛ አስቆጪዎች ናቸው፡፡ 26|56|«እኛም ብዙዎች ጥንቁቆች ነን፤» (አለ)፡፡ 26|57|አወጣናቸውም፡፡ ከአትክልቶችና ከምንጮች፡፡ 26|58|ከድልቦችም ከመልካም መቀመጫዎችም፡፡ 26|59|እንደዚሁ ለእስራኤል ልጆች አወረስናትም፡፡ 26|60|ፀሐይዋ ስትወጣም ተከተሉዋቸው፡፡ 26|61|ሁለቱ ጭፍሮችም በተያዩ ጊዜ የሙሳ ጓዶች «እኛ(የፈርዖን ሰዎች) የሚደርሱብን ነን» አሉ፡፡ 26|62|(ሙሳ) «ተዉዉ! ጌታዬ ከእኔ ጋር ነው፡፡ በእርግጥ ይመራኛል» አለ፡፡ 26|63|ወደ ሙሳም «ባሕሩን በበትርህ ምታው» ስንል ላክንበት፡፡ (መታውና) ተከፈለም፡፡ ክፍሉም ሁሉ እንደ ታላቅ ጋራ ኾነ፡፡ 26|64|እዚያም ዘንድ ሌሎችን አቀረብን፡፡ 26|65|ሙሳንም ከእርሱ ገር ያሉትንም ሰዎች ሁሉንም አዳን፡፡ 26|66|ከዚያም ሌሎቹን አሰጠምን፡፡ 26|67|በዚህ ውስጥ ታላቅ ታምር አለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም አማኞች አልነበሩም፡፡ 26|68|ጌታህም እርሱ አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 26|69|በእነሱም (በሕዝቦችህ) ላይ የኢብራሂምን ወሬ አንብብላቸው፡፡ 26|70|ለአባቱና ለሕዝቦቹ «ምንን ትግገዛላችሁ» ባለ ጊዜ፡፡ 26|71|«ጣዖታትን እንገዛለን፤ እርሷንም በመገዛት ላይ እንቆያለን» አሉ፡፡ 26|72|(እርሱም) አለ «በጠራችኋቸው ጊዜ ይሰሟችኋልን 26|73|«ወይስ ይጠቅሟችኋልን ወይስ ይጎዷችኋልን» 26|74|«የለም! አባቶቻችን እንደዚሁ ሲሠሩ አገኘን» አሉት፡፡ 26|75|«ትግገዙት የነበራችሁትን አስተዋላችሁን 26|76|«እናንተም የቀድሞዎቹ አባቶቻችሁም (የተግገዛችሁትን)፡፡» 26|77|«እነሱም (ጣዖቶቹ) ለእኔ ጠላቶች ናቸው፡፡ ግን የዓለማት ጌታ ሲቀር (እርሱ ወዳጄ ነው)፡፡ 26|78|«(እርሱ) ያ የፈጠረኝ ነው፡፡ እርሱም ይመራኛል፡፡ 26|79|«ያም እርሱ የሚያበላኝና የሚያጠጣኝ ነው፡፡ 26|80|«በታመምኩም ጊዜ እርሱ ያሽረኛል፡፡ 26|81|«ያም የሚገድለኝ ከዚያም ሕያው የሚያደርገኝ ነው፡፡ 26|82|ያም በፍርዱ ቀን ኀጢአቴን ለእኔ ሊምር የምከጅለው ነው፡፡ 26|83|ጌታዬ ሆይ! ዕውቀትን ስጠኝ! በደጋጎቹም ሰዎች አስጠጋኝ፡፡ 26|84|በኋለኞቹም ሕዝቦች ውስጥ ለእኔ መልካም ዝናን አድርግልኝ፡፡ 26|85|የጸጋይቱን ገነት ከሚወርሱትም አድርገኝ፡፡ 26|86|ለአባቴም ማር፡፡ እርሱ ከተሳሳቱት ነበረና፡፡ 26|87|በሚቀሰቀሱበት ቀንም አታዋርደኝ፡፡ 26|88|ገንዘብም ልጆችም በማይጠቅሙበት ቀን፡፡ 26|89|ወደ አላህ በንጹህ ልብ የመጣ ሰው ቢኾን እንጅ፡፡» 26|90|ገነትም ለፈሪዎች በምትቀረብበት (ቀን)፡፡ 26|91|ገሀነምም ለጠመሞች በምትገለጽበት (ቀን)፡፡ 26|92|ለእነሱም በሚባል ቀን «ትግገዟቸው የነበራችሁት የት ናቸው» 26|93|«ከአላህ ሌላ ሲኾኑ ይረዱዋችኋልን ወይስ (ለራሳቸው) ይርረዳሉን» 26|94|በውስጧም እነሱና ጠማሞቹ በፊቶቻቸው ተጥለው ይንከባለላሉ፡፡ 26|95|የሰይጣንም ሰራዊቶች መላውም (ይጣላሉ)፡፡ 26|96|እነርሱም በእርሷ ውስጥ የሚከራከሩ ኾነው ይላሉ፡- 26|97|በአላህ እንምላለን፤ እኛ በግልጽ መሳሳት ውስጥ ነበርን፡፡ 26|98|(ጣዖቶቹን) በዓለማት ጌታ ባስተካከልናችሁ ጊዜ፡፡ 26|99|አመጸኞቹም እንጅ ሌላ አላሳሳተንም፡፡ 26|100|ከአማላጆችም ለእኛ ምንም የለንም፡፡ 26|101|አዛኝ ወዳጂም (የለንም)፡፡ 26|102|ለእኛም አንዲት ጊዜ መመለስ በኖረችንና ከአማኞቹ በኾን እንመኛለን (ይላሉ)፡፡ 26|103|በዚህ ውስጥ አስደናቂ ግሳጼ አልለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም አማኞች አልነበሩም፡፡ 26|104|ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 26|105|የኑሕ ሕዝቦች መልክተኞችን አስተባበሉ፡፡ 26|106|ወንድማቸው ኑሕ ለእነሱ ባላቸው ጊዜ «አትጠነቀቁምን 26|107|«እኔ ለእናንተ ታማኝ መልክተኛ ነኝ፡፡ 26|108|«አላህንም ፍሩ ታዘዙኝም፡፡ 26|109|«በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም፡፡ ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ 26|110|«አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም፡፡» 26|111|(እነርሱም) «ወራዶቹ የተከተሉህ ኾነህ ለአንተ እናምናለን» አሉት፡፡ 26|112|(እርሱም) አላቸው «ይሠሩት በነበሩት ነገር ምን ዕውቀት አለኝ፡፡ 26|113|«ምርመራቸው በጌታዬ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ ብታውቁ ኖሮ (ይህንን ትርረዱ ነበር)፡፡ 26|114|«እኔም አማኞችን አባራሪ አይደለሁም፡፡ 26|115|«እኔ ግልጽ አስፈራሪ እንጅ ሌላ አይደለሁም፡፡» 26|116|«ኑሕ ሆይ! (ከምትለው) ባትከለከል በእርግጥ ከሚወገሩት ትኾናለህ» አሉት፡፡ 26|117|(እርሱም) አለ «ጌታዬ ሆይ! ሕዝቦቼ አስተባበሉኝ፡፡ 26|118|«በእኔና በእነርሱም መካከል (ተገቢ) ፍርድን ፍረድ፡፡ አድነኝም፡፡ ከእኔ ጋር ያሉትንም ምእምናን፡፡» 26|119|እርሱንም ከእርሱ ጋር ያለውንም ሁሉ በተመላው መርከብ ውስጥ አዳን፡፡ 26|120|ከዚያም በኋላ ቀሪዎቹን አሰጠምን፡፡ 26|121|በዚህ ውስጥ ታላቅ ግሳጼ አለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም አማኞች አልነበሩም፡፡ 26|122|ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 26|123|ዓድ መልክተኞችን አስተባበለች፡፡ 26|124|ወንድማቸው ሁድ ለነርሱ ባላቸው ጊዜ «አትጠነቀቁምን 26|125|«እኔ ለናንተ ታማኝ መልክተኛ ነኝ፡፡ 26|126|«አላህንም ፍሩ ታዘዙኝም፡፡ 26|127|«በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አለምናችሁም፡፡ ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ 26|128|«የምትጫወቱ ኾናችሁ በከፍተኛ ስፍራ ሁሉ ላይ ምልክትን ትገነባላችሁን 26|129|«የውሃ ማጠራቀሚያዎችንና ሕንፃዎችንም ዘላለም መኖርን የምትከጅሉ ኾናችሁ ትሠራላችሁን 26|130|«በቀጣችሁም ጊዜ ጨካኞች ኾናችሁ ትቀጣላችሁን 26|131|«አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም፡፡ 26|132|«ያንንም በምታውቁት (ጸጋ) ያጣቀማችሁን ፍሩ፡፡ 26|133|«በእንስሳዎችና በልጆች ያጣቀማችሁን፡፡ 26|134|«በአትክልቶችና በምንጮችም፡፡ 26|135|«እኔ በእናንተ ላይ የታላቅን ቀን ቅጣት እፈራለሁና፡፡» 26|136|(እነርሱም) አሉ «ብትገስጽም ወይም ከገሳጮቹ ባትኾንም በእኛ ላይ እኩል ነው፤ (ያለንበትን አንለቅም)፡፡ 26|137|«ይህ የፊተኞቹ ሰዎች ፀባይ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ 26|138|«እኛም የምንቅቀጣ አይደለንም» (አሉ)፡፡ 26|139|አስተባበሉትም፡፡ አጠፋናቸውም፡፡ በዚህም ውስጥ እርግጠኛ ግሳጼ አለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም ምእመናን አልነበሩም፡፡ 26|140|ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 26|141|ሰሙድ መልክተኞችን አስተባበለች፡፡ 26|142|ወንድማቸው ሷሊህ ለእነርሱ ባላቸው ጊዜ «አትጠነቀቁምን 26|143|«እኔ ለእናንተ ታማኝ መልክተኛ ነኝ፡፡ 26|144|«አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም፡፡ 26|145|«በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልለምናችሁም፡፡ ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ 26|146|«በዚያ እዚህ ባለው (ጸጋ) ውስጥ የረካችሁ ኾናችሁ ትተዋላችሁን 26|147|«በአትክልቶችና በምንጮች ውስጥ፡፡ 26|148|«በአዝመራዎችም ፍሬዋ የበሰለ በኾነች ዘንባባም፤ (ውስጥ ትተዋላችሁን) 26|149|«ብልሆች ኾናችሁ ከጋራዎች ቤቶችንም ትጠርባላችሁ፡፡ 26|150|«አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም፡፡ 26|151|«የወሰን አላፊዎችንም ትዕዛዝ አትከተሉ፡፡ 26|152|«የእነዚያን በምድር ላይ የሚያጠፉትንና የማያበጁትን፡፡» 26|153|(እነሱም) አሉ «አንተ በብዙ ከተደገመባቸው ሰዎች ብቻ ነህ፡፡ 26|154|«አንተ ብጤያችን ሰው እንጅ ሌላ አይደለህም፡፡ ከእውነተኞቹም እንደኾንክ ተዓምርን አምጣ፡፡» 26|155|(እርሱም) አለ «ይህች ግመል ናት፡፡ ለእርሷ የመጠጥ ፋንታ አላት፡፡ ለእናንተም የታወቀ ቀን ፋንታ አላችሁ፡፡ 26|156|«በክፉም አትንኳት፡፡ የታላቅ ቀን ቅጣት ይይዛችኋልና፡፡» 26|157|ወጓትም፡፡ ወዲያውም ተጸጻቾች ኾነው አነጉ፡፡ 26|158|ቅጣቱም ያዛቸው፡፡ በዚህም ውስጥ ግሳፄ አልለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም ምእመናን አልነበሩም፡፡ 26|159|ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 26|160|የሉጥ ሕዝቦች መልክተኞችን አስተባባሉ፡፡ 26|161|ወንድማቸው ሉጥ ለእነርሱ ባለ ጊዜ «አትጠነቀቁምን 26|162|«እኔ ለእናንተ ታማኝ መልክተኛ ነኝ፡፡ 26|163|«አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም፡፡ 26|164|«በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልለምናችሁም፡፡ ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ 26|165|«ከዓለማት ሰዎች ወንዶችን ትመጣላችሁን 26|166|«ከሚስቶቻችሁም ጌታችሁ ለናንተ የፈጠረላችሁን ትተዋላችሁን በእውነቱ እናንተ ወሰን አላፊዎች ሕዝቦ ናችሁ፡፡» 26|167|(እነርሱም) አሉ «ሉጥ ሆይ! ባትከለከል በእርግጥ (ከአገር) ከሚወጡት ትኾናለህ፡፡» 26|168|(እርሱም) አለ «እኔ ሥራችሁን ከሚጠሉት ሰዎች ነኝ፡፡ 26|169|«ጌታዬ ሆይ! እኔንም ቤተሰቦቼንም ከሚሠሩት ሥራ (ቅጣት) አድነን፡፡» 26|170|እርሱንም ቤተሰቦቹንም በጠቅላላ አዳንናቸው፡፡ 26|171|በቀሪዎቹ ውስጥ የኾነች አሮጊት ብቻ ስትቀር (እርሷ ጠፋች)፡፡ 26|172|ከዚያም ሌሎቹን አጠፋን፡፡ 26|173|በእነሱም ላይ (የድንጋይን) ዝናምን አዘነምንባቸው፡፡ የተስፈራሪዎቹም ዝናም (ምንኛ) ከፋ፡፡ 26|174|በዚህ ውስጥ አስደናቂ ተዓምር አልለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም ምእመናን አልነበሩም፡፡ 26|175|ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 26|176|የአይከት ሰዎች መልክተኞችን አስተባበሉ፤ 26|177|ሹዕይብ ለእነርሱ ባላቸው ጊዜ «አትጠነቀቁምን 26|178|«እኔ ለእናንተ ታማኝ መልክተኛ ነኝ፡፡ 26|179|«አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም፡፡ 26|180|«በርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም፡፡ ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ 26|181|«ስፍርን ሙሉ፡፡ ከአጉዳዮቹም አትኹኑ፡፡ 26|182|«በትክክለኛ ሚዛንም መዝኑ፡፡ 26|183|«ሰዎችንም ነገሮቻቸውን አታጉድሉባቸው፡፡ በምድርም ላይ አጥፊዎች ኾናችሁ አታበላሹ፡፡ 26|184|«ያንንም የፈጠራችሁን የቀድሞዎቹንም ፍጡሮች (የፈጠረውን) ፍሩ፡፡» 26|185|አሉ «አንተ በብዛት ከተደገመባቸው ሰዎች ነህ፡፡ 26|186|«አንተም ብጤያችን ሰው እንጅ ሌላ አይደለህም፡፡ እነሆ ከውሸታሞች ነህ ብለን እንጠረጥርሃለን፡፡ 26|187|«ከእውነተኞቹም እንደኾንክ በእኛ ላይ ከሰማይ ቁራጭን ጣልብን፡፡» 26|188|«ጌታዬ የምትሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው፤» አላቸው፡፡ 26|189|አስተባበሉትም፡፡ የጥላይቷ ቀን ቅጣትም ያዛቸው፡፡ እርሱ የከባድ ቀን ቅጣት ነበርና፡፡ 26|190|በዚህ ውስጥ አስደናቂ ተዓምር አልለበት፡፡ አብዛኞቻቸውም ምእምናን አልነበሩም፡፡ 26|191|ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 26|192|እርሱም (ቁርኣን) በእርግጥ ከዓለማት ጌታ የተወረደ ነው፡፡ 26|193|እርሱን ታማኙ መንፈስ (ጂብሪል) አወረደው፤ 26|194|ከአስፈራሪዎቹ (ነቢያት) ትኾን ዘንድ በልብህ ላይ (አወረደው)፡፡ 26|195|ግልጽ በኾነ ዐረብኛ ቋንቋ፡፡ 26|196|እርሱም (ቁርኣን) በቀድሞዎቹ መጻሐፍት ውስጥ (የተወሳ ነው)፡፡ 26|197|የእስራኤል ልጆች ሊቃውንት የሚያውቁት መኾኑ ለእነርሱ (ለመካ ከሓዲዎች) ምልክት አይኾናቸውምን 26|198|ከአዕጀሞች ባንዱ ላይ ባወረድነውም ኖሮ፤ 26|199|በእነርሱ ላይ ባነበበውም በእርሱ አማኞች አይኾኑም ነበር፡፡ 26|200|እንደዚሁ (ማስተባበልን) በተንኮለኞች ልቦች ውስጥ አስገባነው፡፡ 26|201|አሳማሚ ቅጣትን እስከሚያዩ ድረስ በእርሱ አያምኑም፡፡ 26|202|እነርሱ የማያውቁ ሲኾኑ (ቅጣቱ) ድንገት እስከሚመጣባቸውም ድረስ (አያምኑም)፡፡ 26|203|(በመጣባቸው ጊዜ) «እኛ የምንቆይ ነን» እስከሚሉም (አያምኑም)፡፡ 26|204|በቅጣታችን ያቻኩላሉን 26|205|አየህን ብዙ ዓመታትን ብናጣቅማቸው፤ 26|206|ከዚያም ያ ይስፈራሩበት የነበሩት ቢመጣባቸው፤ 26|207|ይጣቀሙበት የነበሩት ሁሉ ከእነሱ ምንም አያብቃቃቸውም፡፡ 26|208|አንዲትንም ከተማ ለእርሷ አስፈራሪዎች ያሏት (እና ያስተባበለች) ኾና እንጅ አላጠፋንም፡፡ 26|209|(ይህች) ግሳፄ ናት፡፡ በዳዮችም አልነበርንም፡፡ 26|210|ሰይጣናትም እርሱን (ቁርኣንን) አላወረዱትም፡፡ 26|211|ለእነርሱም አይገባቸውም፤ አይችሉምም፡፡ 26|212|እነርሱ (የመላእክትን ንግግር) ከመስማት ተከለከሉ ናቸው፡፡ 26|213|ከአላህም ጋር ሌላን አምላክ አትግገዛ፤ ከሚቀጡት ትኾናለህና፡፡ 26|214|ቅርቦች ዘመዶችህንም አስጠንቅቅ፡፡ 26|215|ከምእምናንም ለተከተሉህ ሰዎች ክንፍህን ዝቅ አድርግ፤ (ልዝብ ኹን)፡፡ 26|216|«እንቢ» ቢሉህም «እኔ ከምትሠሩት ንጹሕ ነኝ» በላቸው፡፡ 26|217|አሸናፊ አዛኝ በኾነው (ጌታህ) ላይም ተጠጋ፡፡ 26|218|በዚያ ለሶላት በምትቆም ጊዜ በሚያይህ፡፡ 26|219|በሰጋጆች ውስጥ መዘዋወርህንም (በሚያየው ጌታህ ላይ ተጠጋ)፡፡ 26|220|እነሆ እርሱ ሰሚው ዐዋቂው ነውና፡፡ 26|221|ሰይጣናት በማን ላይ እንደሚወርዱ ልንገራችሁን 26|222|በውሸታም ኀጢአተኛ ሁሉ ላይ ይወርዳሉ፡፡ 26|223|የሰሙትን (ወደ ጠንቋዮች) ይጥላሉ፡፡ አብዛኞቻቸውም ውሸታሞች ናቸው፡፡ 26|224|ባለ ቅኔዎችንም ጠማማዎቹ ይከተሉዋቸዋል፡፡ 26|225|እነርሱ በ(ንግግር) ሸለቆ ሁሉ የሚዋልሉ መኾናቸውን አታይምን 26|226|እነሱም የማይሠሩትን ነገር የሚናገሩ መኾናቸውን (አታይምን)፤ 26|227|እነዚያ ያመኑና መልካም ሥራዎችን የሠሩ አላህንም በብዛት ያወሱ ከተበደሉም በኋላ (በቅኔ) የተከላከሉ ሲቀሩ፤ (እነርሱ አይወቀሱም)፡፡ እነዚያም የበደሉ (ከሞቱ በኋላ) እንዴት ያለን መመለስ እንደሚመለሱ በእርግጥ ያውቃሉ፡፡ 27|1|ጠ.ሰ (ጣ ሲን) ይህቺ ከቁርኣኑና ከገላጩ መጽሐፍ አንቀጾች ናት፡፡ 27|2|ለምእምናን መሪና ብስራት ናት፡፡ 27|3|ለእነዚያ ሶላትን ለሚሰግዱት ዘካንም ለሚሰጡት እነሱም በመጨረሻይቱ ሕይወት እነሱ የሚያረጋግጡ ለኾኑት፡፡ 27|4|እነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ለእነሱ (ክፉ) ሥራዎቻቸውን ሸለምንላቸው፡፡ ስለዚህ እነርሱ ይዋልላሉ፡፡ 27|5|እነርሱ እነዚያ ክፉ ቅጣት ለእነርሱ ያላቸው ናቸው፡፡ እነርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም እነርሱ በጣም ከሳሪዎቹ ናቸው፡፡ 27|6|አንተም ቁርኣንን ጥበበኛና ዐዋቂ ከኾነው (ጌታህ) ዘንድ በእርግጥ ትስሰጣለህ፡፡ 27|7|ሙሳ ለቤተሰቦቹ «እኔ እሳትን አየሁ፡፡ ከእርሷ ወሬን አመጣላችኋለሁ፡፡ ወይም ትሞቁ ዘንድ የተለኮሰ ችቦን አመጣላችኋለሁ» ባለ ጊዜ (የኾነውን አውሳላቸው)፡፡ 27|8|በመጣትም ጊዜ እንዲህ በማለት ተጠራ፤ «በእሳቲቱ ያለው ሰውና በዙሪያዋ ያሉም ሁሉ ተባረኩ፡፡ የዐለማትም ጌታ አላህ ጥራት ይገባው፡፡» 27|9|«ሙሳ ሆይ! እነሆ እኔ አሸናፊው ጥበበኛው አላህ ነኝ፡፡ 27|10|«በትርህንም ጣል» (ተባለ ጣለም)፡፡ እርሷ እንደ ትንሽ እባብ በፍጥነት ስትስለከለክ ባያትም ጊዜ፤ ወደ ኋላ ዞሮ ሸሸ፡፡ አልተመለሰምም፡፡ «ሙሳ ሆይ! አትፈራ፤ እኔ መልክተኞቹ እኔ ዘንድ አይፈሩምና፡፡ 27|11|«ግን የበደለ ሰው ከዚያም ከመጥፎ ሥራው በኋላ መልካምን የለወጠ እኔ መሓሪ አዛኝ ነኝ፡፡ 27|12|«እጅህንም በአንገትጌህ ውስጥ አግባ፡፡ ያለነውር (ያለ ለምጽ) ነጭ ኾና ትወጣለችና፡፡ በዘጠኝ ተዓምራት ወደ ፈርዖንና ወደ ሕዝቦቹ (ኺድ)፡፡ እነርሱ አመጸኞች ሕዝቦች ናቸውና፡፡ 27|13|ተዓምራታችንም ግልጽ ኾና በመጣቻቸው ጊዜ «ይህ ግልጽ ድግምት ነው» አሉ፡፡ 27|14|ነፍሶቻቸውም ያረጋገጧት ሲኾኑ ለበደልና ለኩራት በእርሷ ካዱ፡፡ የአመጸኞችም ፍጻሜ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከት፡፡ 27|15|ለዳውድና ለሱለይማንም ዕውቀትን በእርግጥ ሰጠናቸው፡፡ አሉም፡- «ምስጋና ለአላህ ለእዚያ ከምእምናን ባሮቹ በብዙዎቹ ላይ ላበለጠን ይገባው፡፡» 27|16|ሱለይማንም ዳውድን ወረሰ፡፡ አለም «ሰዎች ሆይ! የበራሪን ንግግር (የወፍን ቋንቋ) ተስተማርን፡፡ ከነገሩም ሁሉ ተሰጠን፡፡ ይህ እርሱ በእርግጥ ግልጽ የኾነ ችሮታ ነው፡፡» 27|17|ለሱለይማንም ሰራዊቶቹ ከጋኔን፣ ከሰውም፣ ከበራሪም የኾኑት ተሰበሰቡ፡፡ እነሱም ይከመከማሉ፡፡ 27|18|በጉንዳንም ሸለቆ በመጡ ጊዜ አንዲት ጉንዳን «እናንተ ጉንዳኖች ሆይ! ወደ መኖሪያዎቻችሁ ግቡ፡፡ ሱለይማንና ሰራዊቱ እነርሱ የማያውቁ ሲኾኑ አይሰባብሩዋችሁ» አለች፡፡ 27|19|ከንግግርዋም እየሳቀ ጥርሱን ፈገግ አደረገ፡፡ «ጌታዬ ሆይ! ያቺን በእኔና በወላጆቼ ላይ የለገስካትን ጸጋህን እንዳመሰግን የምትወደውንም በጎ ሥራ እንድሠራ ምራኝ፡፡ በችሮታህም በመልካሞቹ ባሮችህ ውስጥ አግባኝ» አለ፡፡ 27|20|በራሪዎቹንም ተመለከተ፤ አለም «ሁድሁድን ለምን አላየውም! በእውነቱ ከራቁት ነበርን፡፡ 27|21|«ብርቱን ቅጣት በእርግጥ እቀጣዋለሁ፡፡ ወይም በእርግጥ ዐርደዋለሁ፤ ወይም ግልጽ በኾነ አስረጅ ይመጣኛል» (አለ) 27|22|(ወፉ) ዕሩቅ ያልኾነንም ጊዜ ቆዬ፡፡ አለም «ያላወቅከውን ነገር አወቅኩ፡፡ ከሰበእም እርግጠኛን ወሬ አመጣሁልህ፡፡ 27|23|«እኔ የምትገዛቸው የኾኑችን ሴት ከነገሩም ሁሉ የተሰጠችኝ አገኘሁ፡፡ ለእርሷም ታላቅ ዙፋን አልላት፡፡ 27|24|«እርስዋንም ሕዝቦችዋንም ከአላህ ሌላ ለፀሐይ ሲሰግዱ አገኘኋቸው፡፡ ሰይጣንም ለእነሱ ሥራዎቻቸውን ሸልሞላቸዋል፡፡ ከእውነተኛውም መንገድ አግዷቸዋል፡፡ ስለዚህ እነሱ (ወደ እውነት) አይምመሩም፡፡» 27|25|ለዚያ በሰማያትና በምድር የተደበቀውን ለሚያወጣው፣ የምትሸሽጉትንና የምትገ ልጹትንም ሁሉ ለሚያውቀው አላህ እንዳይሰግዱ (ሰይጣን አግዷቸዋል)፡፡ 27|26|አላህ ከርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ የታላቁ ዐርሽ (ዙፋን) ጌታ ነው፡፡ 27|27|(ሱለይማንም) አለ «እውነት እንደ ተናገርክ ወይም ከውሸታሞቹ እንደ ኾንክ ወደፊት እናያለን፡፡ 27|28|«ይህንን ደብዳቤዬን ይዘህ ኺድ፡፡ ወደእነርሱም ጣለው፡፡ ከዚያም ከእነሱ ዘወር በል፡፡ ምን አንደሚመልሱም ተመልከት፡፡» 27|29|(እርሷም በደረሳት ጊዜ) አለች «እናንተ መማክርቶች ሆይ! እኔ ክብር ያለው ጽሑፍ ወደኔ ተጣለ፡፡ 27|30|«እርሱ ከሱለይማን ነው፡፡ እርሱም በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩኅ በጣም አዛኝ በኾነው፡፡ 27|31|«በእኔ ላይ አትኩሩ፡፡ ታዛዦችም ኾናችሁ ወደኔ ኑ፤ (የሚል ነው)፡፡ 27|32|«እናንተ መማክርቶች ሆይ! በነገሬ (የሚበጀውን) ንገሩኝ፡፡ እስከምትገኙልኝ ድረስ አንድንም ነገር ቆራጭ አይደለሁምና» አለች፡፡ 27|33|«እኛ የኀይል ባለቤቶች የብርቱ ጦርም ባለቤቶች ነን፡፡ ግን ትዕዛዙ ወደ አንቺ ነው፡፡ ምን እንደምታዢም አስተውዪ፤» አሏት፡፡ 27|34|(እርሷም) አለች «ንጉሦች ከተማን (በኀይል) በገቡባት ጊዜ ያበላሹዋታል፡፡ የተከበሩ ሰዎችዋንም ወራዶች ያደርጋሉ፡፡ እንደዚሁም (እነዚህ) ይሠራሉ፡፡ 27|35|«እኔም ወደእነርሱ ገጸ በረከትን የምልክና መልክተኞቹ በምን እንደሚመለሱ የምጠባበቅ ነኝ፡፡» 27|36|(መልክተኛው) ሱለይማንንም በመጣው ጊዜ አለ «በገንዘብ ትረዱኛላችሁን አላህም የሰጠኝ ከሰጣችሁ የበለጠ ነው፡፡ ይልቁንም እናንተ በገጸ በረከታችሁ ትደሰታላችሁ፡፡» 27|37|«ወደእነሱ ተመለስ፡፡ ለእነርሱም በእርሷ ችሎታ በሌላቸው ሰራዊት እንመጣባቸዋለን፡፡ ከእርሷም እነርሱ የተዋረዱ ኾነው በእርግጥ እናወጣቸዋለን» (አለ)፡፡ 27|38|«እናንተ መኳንንቶች ሆይ! ሙስሊሞች ኾነው ሳይመጡኝ በፊት ዙፋንዋን የሚያመጣልኝ ማንኛችሁ ነው» አለ፡፡ 27|39|ከጋኔን ኀይለኛው «ከችሎትህ ከመነሳትህ በፊት እኔ እርሱን አመጣልሃለሁ፡፡ እኔም በእርሱ ላይ ብርቱ ታማኝ ነኝ» አለ፡፡ 27|40|ያ እርሱ ዘንድ ከመጽሐፉ ዕውቀት ያለው ሰው (የተገለጸው) «ዓይንህ ወደ አንተ ከመመለሱ በፊት እኔ እርሱን አመጣልሃለሁ» አለ፤ (እንደዚሁም አደረገ)፡፡ እርሱ ዘንድ ረግቶ ባየውም ጊዜ «ይህ ከጌታዬ ችሮታ ነው፡፡ የማመሰግን ወይም የምክድ መኾኔን ሊሞክረኝ (ቸረልኝ)፡፡ ያመሰገነም ሰው የሚያመሰግነው ለራሱ ነው፡፡ የካደም ሰው ጌታዬ ከእርሱ ተብቃቂ ቸር ነው» አለ፡፡ 27|41|«ዙፋንዋን ለእርሷ አሳስቱ፡፡ ታውቀው እንደኾነ ወይም ከእነዚያ ከማያወቁት ትኾን እንደሆነ፤ እናያለን፤» አላቸው፡፡ 27|42|በመጣች ጊዜ፡- «ዙፋንሽ እንደዚህ ነውን» ተባለች፡፡ «እርሱ ልክ እርሱ ነው መሰለኝ» አለች፡፡ (ሱለይማን) «ከእርሷ በፊትም ዕውቀትን ተሰጠን ሙስሊሞችም ነበርን፤» (አለ)፡፡ 27|43|ከአላህ ሌላ ትግገዛው የነበረችውንም ከለከላት፡፡ እርሷ ከከሓዲዎች ሕዝቦች ነበረችና፡፡ 27|44|ሕንጻውን ግቢ ተባለች፡፡ ባየቺውም ጊዜ ባሕር ነው ብላ ጠረጠረችው፡፡ ከባቶችዋም ገለጠች፡፡ «እርሱ ከመስተዋት የተለሰለሰ ሕንጻ ነው» አላት፡፡ «ጌታዬ ሆይ! እኔ ነፍሴን በደልኩ፡፡ ከሱለይማንም ጋር ሆኜ ለዓለማት ጌታ ለአላህ ታዘዝኩ» አለች፡፡ 27|45|ወደ ሰሙድም ወንድማቸውን ሷሊሕን አላህን ተገዙ በማለት በእርግጥ ላክነው፡፡ ወዲያውም እነሱ የሚነታረኩ ሁለት ጭፍሮች ኾኑ፡፡ 27|46|«ሕዝቦቼ ሆይ! ከመልካሙ በፊት በክፉው (ቅጣትን አምጣብን በማለት) ለምን ታስቸኩላላችሀ ይታዘንላችሁ ዘንድ አላህን ምሕረትን አትለምኑምን» አላቸው፡፡ 27|47|«ባንተና ከአንተም ጋር ባሉት ሰዎች ምክንያት ገደቢሶች ኾን» አሉት፡፡ «ገደቢስነታችሁ አላህ ዘንድ ነው፤ ይልቁንም እናንተ የምትፈተኑ ሕዝቦች ናችሁ» አላቸው፡፡ 27|48|በከተማይቱም ውስጥ በምድር ውስጥ የሚያበላሹና የማያሳምሩ ዘጠኝ ሰዎች ነበሩ፡፡ 27|49|«እርሱንና ቤተሰቦቹን ሌሊት ልንገድል ከዚያም ለዘመዱ የቤተሰቦቹን ጥፋት (መገደላቸውን) አላየንም፤ እኛም እውነተኞች ነን ልንል በአላህ ተማማሉ» አሉ፡፡ 27|50|ተንኮልንም መከሩ፡፡ እነርሱም የማያወቁ ሲኾኑ በተንኮላቸው አጠፋናቸው፡፡ 27|51|የተንኮላቸውም መጨረሻ እንዴት እንደነበረ እኛ እነርሱንም ሕዝቦቻቸውንም በሙሉ እንዴት እንዳጠፋናቸው ተመልከት፡፡ 27|52|እኚህም በበደላቸው ምክንያት ባዶዎች ሲሆኑ ቤቶቻቸው ናቸው፡፡ በዚህም ውስጥ ለሚያወቁ ሕዝቦች አስደናቂ ተዓምር አለበት፡፡ 27|53|እነዚያንም ያመኑትንና ከክሕደት ይጠነቀቁ የነበሩትን አዳን፡፡ 27|54|ሉጥንም ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፤ «እናንተ የምታዩ ስትኾኑ ፀያፍን ነገር ትሠራላችሁን 27|55|«እናንተ ከሴቶች አልፋችሁ ወንዶችን ለመከጀል ትመጣላችሁን በእውነቱ እናንተ የምትሳሳቱ ሕዝቦች ናቸሁ፡፡» 27|56|የሕዝቦቹም መልስ የሉጥን ቤተሰቦች «ከከተማችሁ አውጡ፡፡ እነርሱ የሚጥራሩ ሰዎች ናቸውና» ማለት እንጅ ሌላ አልነበረም፡፡ 27|57|እርሱንና ቤተሰቦቹንም አዳን፡፡ ሚስቱ፤ ብቻ ስትቀር፡፡ (በጥፋቱ ውስጥ) ከቀሪዎቹ አደረግናት፡፡ 27|58|በእነርሱም ላይ (የድንጋይ) ዝናብን አዘነብንባቸው፡፡ የተስፈራሪዎቹም ዝናብ ከፋ፡፡ 27|59|(ሙሐመድ ሆይ) በል «ምስጋና ለአላህ ይግባው፡፡ በእነዚያም በመረጣቸው ባሮቹ ላይ ሰላም ይውረድ፡፡ አላህ በላጭ ነውን ወይስ ያ የሚያጋሩት (ጣዖት)፡፡ 27|60|ወይም ያ ሰማያትንና ምድርን የፈጠረና ከሰማይም ለእናንተ ውሃን ያወረደው (ይበልጣል ወይስ የሚያጋሩት) በእርሱም ባለውበት የኾኑትን የታጠሩ አትክልቶችን ዛፍዋን ልታበቅሉ ለናንተ ችሎታ ያልነበራችሁን አበቀልን፡፡ ከአላህ ጋር ሌላ አምላክ አለን (የለም)፡፡ ግን እነርሱ (ከእውነት) የሚያዘነብሉ ሕዝቦች ናቸው፡፡ 27|61|ወይም ያ ምድርን መርጊያ ያደረገና በመካከሏም ወንዞችን ያደረገ፣ ለእርሷም ጋራዎችን ያደረገ፣ በሁለቱ ባሕሮችም (በጣፋጩና በጨው ባሕር) መካከል ግርዶን ያደረገ (ይበልጣልን ወይስ የሚያጋሩት) ከአላህ ጋር ሌላ አምላክ አለን ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 27|62|ወይም ያ ችግረኛን በለመነው ጊዜ የሚቀበል፣ መከራንም የሚያስወግድ፣ በምድርም ላይ ምትኮች የሚያደረጋችሁ፤ (ይበልጣልን ወይስ የሚያጋሩት) ከአላህ ጋር ሌላ አምላክ አለን ጥቂትንም አትገሠጹም፡፡ 27|63|ወይም ያ በየብስና በባሕር ጨለማዎች ውስጥ የሚመራችሁ ነፋሶችንም ከዝናሙ በፊት አብሳሪ ኾነው የሚልክ (ይበልጣልን ወይስ የሚያጋሩት) ከአላህ ጋር ሌላ አምላክ አለን አላህ (በእርሱ) ከሚያጋሩዋቸው ሁሉ ላቀ፡፡ 27|64|ወይም ያ መፍጠርን የሚጀምር ከዚያም የሚመልሰው ከሰማይና ከምድርም ሲሳይን የሚሰጣችሁ አምላክ (ይበልጣልን ወይስ የሚያጋሩት) ከአላህ ጋር ሌላ አምላክ አለን «እውነተኞች እንደኾናችሁ፤ አስረጃችሁን አምጡ» በላቸው፡፡ 27|65|«በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ ሩቅን ምስጢር አያውቅም፡፡ ግን አላህ (ያውቀዋል)፡፡ መቼ እንደሚቀሰቀሱም አያውቁም» በላቸው፡፡ 27|66|በእውነት የመጨረሻይቱን ዓለም (ኹኔታ) ማወቃቸው ተሟላን አይደለም እነርሱ ከእርሷ በመጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ በእውነትም እነርሱ ከእርሷ ዕውሮች ናቸው፡፡ 27|67|እነዚያም የካዱት አሉ «እኛም አባቶቻችንም ዐፈር በኾን ጊዜ እኛ (ከመቃብር) የምንወጣ ነን 27|68|«ይህንን እኛም ከፊት የነበሩት አባቶቻችንም በእርግጥ ተቀጥረንበታል፡፡ ይህ የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ተረቶች እንጅ ሌላ አይደለም» (አሉ)፡፡ 27|69|«በምድር ላይ ኺዱ፡፡ የአመጸኞችም መጨረሻ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከቱ» በላቸው፡፡ 27|70|በእነሱም ላይ አትዘን፡፡ ከሚመክሩብህም ነገር በጭንቀት ውስጥ አትኹን፡፡ 27|71|«እውነተኞችም እንደ ኾናችሁ ይህ ቀጠሮ መቼ ነው» ይላሉ፡፡ 27|72|«የዚያ የምትቻኮሉበት ከፊሉ ለእናንተ የቀረበ መኾኑ ተረጋግጧል» በላቸው፡፡ 27|73|ጌታህም በሰዎች ላይ በእርግጥ የችሮታ ባለቤት ነው፡፡ ግን አብዛኛዎቻቸው አያመሰግኑም፡፡ 27|74|ጌታህም ልቦቻቸው የሚደብቁትንና የሚገልጹትን ያውቃል፡፡ 27|75|በሰማይና በምድር ውስጥ ምንም የተደበቀ ነገር የለም ገላጭ በኾነው መጽሐፍ ውስጥ ያለ ቢኾን እንጅ፡፡ 27|76|ይህ ቁርኣን በእስራኤል ልጆች ላይ የእነዚያን እነርሱ በእርሱ የሚለያዩበትን አብዛኛውን ይነግራል፡፡ 27|77|እርሱም ለምእምናን መምሪያና እዝነት ነው፡፡ 27|78|ጌታህ በመካከላቸው በትክክል ፍርዱ ይፈርዳል፡፡ እርሱም አሸናፊው ዐዋቂው ነው፡፡ 27|79|በአላህም ላይ ተጠጋ፡፡ አንተ ግልጽ በኾነው እውነት ላይ ነህና፡፡ 27|80|አንተ ሙታንን አታሰማም፡፡ ደንቆሮዎችንም የሚተው ኾነው በዞሩ ጊዜ ጥሪን አታሰማም፡፡ 27|81|አንተም (ልበ) ዕውሮችን ከጥመታቸው አቅኚ አይደለህም፡፡ በአንቀጾቻችን የሚያምኑትን በስተቀር አታሰማም፡፡ እነርሱ ፍጹም ታዛዦች ናቸውና፡፡ 27|82|በእነርሱም ላይ (የቅጣት) ቃሉ በተረጋገጠ ጊዜ ሰዎቹ በአንቀጾቻችን የማያረጋግጡ እንደነበሩ የምትነግራቸውን እንስሳ ለእነርሱ ከምድር እናወጣለን፡፡ 27|83|ከሕዝቦቹም ሁሉ ባንቀፆቻችን የሚያስተባብሉትን ጭፍሮች የምንሰበስብበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ እነሱም ይከመከማሉ፡፡ 27|84|በመጡም ጊዜ (አላህ) ይላቸዋል «በአንቀጾቼ እርሷን በማወቅ ያላዳረሳችሁ ስትሆኑ አስተባበላችሁን ወይስ ምንን ትሠሩ ነበራችሁ» 27|85|በመበደላቸውም በእነርሱ ላይ ቃሉ ይፈጸምባቸዋል፡፡ እነርሱም አይናገሩም፡፡ 27|86|እኛ ሌሊትን በእርሱ ውስጥ እንዲያርፉበት ቀንንም የሚያሳይ እንዳደረግን አያዩምን ለሚያምኑ ሕዝቦች በዚህ ውስጥ ተዓምራቶች አሉበት፡፡ 27|87|በቀንዱም በሚነፋ ቀን በሰማያት ውስጥ ያሉትና በምድርም ውስጥ ያሉት ሁሉ አላህ የሻው ነገር ብቻ ሲቀር በሚደነግጡ ጊዜ (የሚኾነውን አስታውስ)፡፡ ሁሉም የተናነሱ ኾነውም ወደርሱ ይመጣሉ፡፡ 27|88|ጋራዎችንም እርሷ እንደ ደመና አስተላለፍ የምታልፍ ስትኾን የቆመች ናት ብለህ የምታስባት ሆና ታያታለህ፡፡ የዚያን ነገሩን ሁሉ ያጠነከረውን የአላህን ጥበብ (ተመልከት)፡፡ እርሱ በምትሠሩት ሁሉ ውስጥ ዐዋቂ ነው፡፡ 27|89|በመልካም ሥራ የመጣ ሰው ለእርሱ ከእርስዋ የበለጠ ምንዳ አልለው፡፡ እነርሱም በዚያ ቀን ከድንጋጤ ጸጥተኞች ናቸው፡፡ 27|90|በመጥፎም የመጡ ሰዎች ፊቶቻቸው በእሳት ውስጥ ይደፋሉ፡፡ «ትሠሩት የነበራችሁትን እንጅ አትመነዱም» (ይባላሉ)፡፡ 27|91|የታዘዝኩት የዚህችን አገር ጌታ ያንን ክልል ያደረጋትን እንድግገዛ ብቻ ነው፡፡ ነገሩንም ሁሉ የእርሱ ነው፡፡ ከሙስሊሞችም እንድኾን ታዝዣለሁ (በላቸው)፡፡ 27|92|ቁርኣንንም እንዳነብ (ታዝዣለሁ)፡፡ የተመራም ሰው የሚመራው ለእራሱ ብቻ ነው፡፡ የተሳሳተም ሰው «እኔ ከአስጠንቃቂዎች ነኝ እንጅ ሌላ አይደለሁም» በለው፡፡ 27|93|ምስጋናም ለአላህ ነው፡፡ ተዓምራቶቹን ወደፊት ያሳያችኋል፡፡ «ታውቋትምአላችሁ» በላቸው፡፡ ጌታህም ከምትሠሩት ሁሉ ዘንጊ አይደለም፡፡ 28|1|ጠ.ሰ.መ (ጣ ሲን ሚም)፡፡ 28|2|ይህቺ ገላጭ ከሆነው መጽሐፍ አንቀጾች ናት፡፡ 28|3|ከሙሳና ከፈርዖን ዜና እውነተኞች ስንኾን ለሚያምኑ ሕዝቦች ባንተ ላይ እናነባለን፡፡ 28|4|ፈርዖን በምድር ላይ ተንበጣረረ፡፡ ነዋሪዎቿንም የተከፋፈሉ ጓዶች አደረጋቸው፡፡ ከእነርሱ ጭፍሮችን ያዳክማል፡፡ ወንዶች ልጆቻቸውን በብዛት ያርዳል፡፡ ሴቶቻቸውንም ይተዋል፤ እርሱ ከሚያበላሹት ሰዎች ነበርና፡፡ 28|5|በእነዚያም በምድር ውስጥ በተጨቆኑ ላይ ልንለግስ፣ መሪዎችም ልናደርጋቸው ወራሾችም ልናደርጋቸው እንሻለን፡፡ 28|6|ለእነርሱም በምድር ላይ ልናስመች ፈርዖንንና ሃማንንም ሰራዊቶቻቸውንም ከእነሱ ይፈሩት የነበሩትን ነገር ልናሳያቸው (እንሻለን)፡፡ 28|7|ወደ ሙሳም እናት «አጥቢው፣ በርሱም ላይ በፈራሽ ጊዜ በባሕሩ ውስጥ ጣይው አትፈሪም፣ አትዘኝም፣ እኛ ወዳንቺ መላሾቹና ከመልክተኞቹም አድራጊዎቹ ነንና» ማለትን አመለከትን፡፡ 28|8|የፈርዖን ቤተሰቦችም (መጨረሻው) ለእነርሱ ጠላት ሐዘንም ይሆን ዘንድ አነሱት፡፡ ፈርዖንና ሃማንም ሰራዊቶቻቸውም ሀጢአተኞች ነበሩ፡፡ 28|9|የፈርዖንም ሚስት «ለእኔ የዓይኔ መርጊያ ነው፡፡ ለአንተም፡፡ አትግደሉት፡፡ ሊጠቅመን ወይም ልጅ አድርገን ልንይዘው ይከጀላልና» አለች፡፡ እነርሱም (ፍጻሜውን) የማያውቁ ሆነው (አነሱት)፡፡ 28|10|የሙሳም እናት ልብ ባዶ ሆነ፡፡ ከምእምናን ትሆን ዘንድ በልቧ ላይ ባላጠነከርን ኖሮ ልትገልጸው ቀርባ ነበር፡፡ 28|11|ለእኅቱም ተከታተይው አለቻት፡፡ እርሱንም እነሱ የማያውቁ ሲሆኑ በሩቅ ሆና አየችው፡፡ 28|12|(ወደናቱ ከመመለሱ) በፊትም አጥቢዎችን (መጥባትን) በእርሱ ላይ እርም አደረግን፡፡ (እኅቱ) «ለእናንተ የሚያሳድጉላችሁን እነርሱም ለእርሱ ቅን አገልጋዮች የሆኑን ቤተሰቦች ላመልክታችሁን» አለችም፡፡ 28|13|ወደእናቱም ዓይንዋ እንድትረጋ፣ እንዳታዝንም፣ የአላህም የተስፋ ቃል እርግጥ መሆኑን እንድታውቅ መለስነው፡፡ ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 28|14|ብርታቱንም በደረሰና በተስተካከለ ጊዜ ጥበብንና ዕውቀትን ሰጠነው፡፡ እንዲሁም መልካም ሠሪዎችን እንመነዳለን፡፡ 28|15|ከተማይቱንም ሰዎቿ በዝንጋቴ ጊዜ ላይ ሆነው ሳሉ ገባ፡፡ በእርሷም ውስጥ የሚጋደሉን ሁለት ሰዎችን አገኘ፡፡ ይህ ከወገኑ ነው፤ ይህም ከጠላቱ ነው፡፡ ያም ከወገኑ የሆነው ሰው በዚያ ከጠላቱ በሆነው ሰው ላይ እርዳታን ጠየቀው፡፡ ሙሳም በጡጫ መታው፡፡ ገደለውም፡፡ ይህ ከሰይጣን ሥራ ነው፡፡ እርሱ ግልጽ አሳሳች ጠላት ነውና አለ፡፡ 28|16|«ጌታዬ ሆይ! እኔ ነፍሴን በደልኩ፡፡ ለእኔም ማር አለ፡፡» ለእርሱም ምሕረት አደረገለት እርሱ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 28|17|«ጌታዬ ሆይ! በእኔ ላይ በመለገስህ ይሁንብኝ (ከስህተቴ እጸጸታለሁ)፤ ለአመጸኞችም ፈጽሞ ረዳት አልሆንም አለ፡፡ 28|18|በከተማይቱም ውስጥ ፈሪ የሚጠባበቅ ሆኖ አደረ፡፡ በድንገትም ያ ትላንት እርዳታን የጠየቀው ሰው በጩኸት እርዳታን ይጠይቀዋል፡፡ ሙሳ ለርሱ «አንተ በእርግጥ ግልጽ ጠማማ ነህ» አለው፡፡ 28|19|(ሙሳ) ያንን እርሱ ለሁለቱም ጠላት የሆነውን ሰው በኃይል ሊይዘው በፈለገም ጊዜ «ሙሳ ሆይ! በትላንትናው ቀን ነፍስን እንደ ገደልክ ልትገድለኝ ትፈልጋለህን በምድር ለይ ጨካኝ መሆንን እንጅ ሌላ አትፈልግም፡፡ ከመልካም ሠሪዎችም መሆንን አትፈልግም» አለው፡፡ 28|20|ከከተማይቱም ዳርቻ አንድ ሰው እየሮጠ መጣ፡፡ «ሙሳ ሆይ! ሹማምንቶቹ ሊገድሉህ ባንተ ይመካከራሉና ውጣ፡፡ እኔ ላንተ ከመካሪዎች ነኝና» አለው፡፡ 28|21|የፈራና የሚጠባበቅ ሆኖም ከእርሷ ወጣ፡፡ «ጌታዬ ሆይ! ከበደለኞቹ ሕዝቦች አድነኝ» አለ፡፡ 28|22|ወደ መድየን አቅጣጫ ፊቱን ባዞረ ጊዜም «ጌታዬ ቀጥተኛውን መንገድ ሊመራኝ እከጅላለሁ» አለ፡፡ 28|23|ወደ መድየንም ውሃ በመጣ ጊዜ በእርሱ ላይ ከሰዎች ጭፍሮችን (መንጋዎቻቸውን) የሚያጠጡ ሆነው አገኘ፡፡ ከእነርሱ በታችም (ከውሃው መንጎቻቸውን) የሚከለክሉን ሁለት ሴቶች አገኘ፡፡ «ነገራችሁ ምንድን ነው» አላቸው፡፡ «እረኞቹ ሁሉ (መንጋዎቻቸውን) እስከሚመልሱ አናጠጣም፡፡ አባታችንም ትልቅ ሽማግሌ ነው» አሉት፡፡ 28|24|ለሁለቱም አጠጣላቸው፡፡ ከዚያም ወደ ጥላው ዘወር አለ፡፡ «ጌታዬ ሆይ! እኔ ከመልካም ነገር ወደኔ ለምታወርደው ፈላጊ ነኝ» አለ፡፡ 28|25|ከሁለቱ አንደኛይቱም ከሐፍረት ጋር የምትኼድ ሆና መጣችው፡፡ «አባቴ ለእኛ ያጠጣህልንን ዋጋ ሊሰጥህ ይጠራሃል» አለችው፡፡ ወደእርሱ በመጣና ወሬውን በእርሱ ላይ በተረከለትም ጊዜ «አትፍራ ከበደለኞቹ ሕዝቦች ድነሃል» አለው፡፡ 28|26|ከሁለቱ አንደኛይቱም «አባቴ ሆይ ቅጠረው፡፡ ከቀጠርከው ሰው ሁሉ በላጩ ብርቱው ታማኙ ነውና» አለችው፡፡ 28|27|«ስምንትን ዓመታት ልታገለግለኝ እኔ ከእነዚህ ሁለት ሴቶቸ ልጆቼ አንዲቱን ላጋባህ እሻለሁ፡፡ ዐስርን ብትሞላም ከአንተ ነው፡፡ ባንተ ላይ ማስቸገርንም አልሻም፡፡ አላህ የሻ እንደ ኾነ ከመልካሞቹ ሰዎች ኾኜ ታገኘኛለህ» አለው፡፡ 28|28|(ሙሳም) «ይህ (ውለታ) በእኔና ባንተ መካከል (ረጊ) ነው፡፡ ከሁለቱ ጊዜያቶች ማንኛውንም ብፈጽም በእኔ ላይ ወሰን ማለፍ የለም፡፡ አላህም በምንለነው ላይ ምስክር» ነው አለ፡፡ 28|29|ሙሳም ጊዜውን በጨረሰና ከቤተሰቦቹ ጋር በኼደ ጊዜ ከጡር ተራራ ጎን እሳትን አየ፡፡ ለቤተሰቡ (እዚህ) «ቆዩ፡፡ እኔ እሳትን አየሁ፡፡ ከእርሷ ወሬን ወይም ትሞቁ ዘንድ ከእሳት ትንታግን አመጣላችኋለሁ» አለ፡፡ 28|30|በመጣትም ጊዜ ከሸለቆው ቀኝ ዳርቻ ከዛፊቱ በኩል በተባረከችው ስፍራ ውስጥ «ሙሳ ሆይ! እኔ የዓለማት ጌታ አላህ እኔ ነኝ» በማለት ተጠራ፡፡ 28|31|«በትርህንም ጣል» (ተባለ)፡፡ እንደ ትንሽ እባብ ስትስለከለክ ባያትም ጊዜ ወደ ኋላ ዞሮ ሸሸ፤ አልተመለሰምም፡፡ «ሙሳ ሆይ! ተመለስ አትፍራም፤ አንተ ከጥብቆቹ ነህና» (ተባለም)፡፡ 28|32|«እጅህን በአንገትጌህ ውስጥ አግባ፡፡ ያለ ነውር ነጭ ሆና ትወጣለችና፡፡ ክንፍህንም ከፍርሃት (ለመዳን) ወዳንተ አጣብቅ፡፡ እነዚህም ከጌታህ የሆኑ ወደ ፈርዖንና ወደ መኳንንቶቹ የሚደርሱ ሁለት አስረጅዎች ናቸው፡፡ እነርሱ አመጸኞች ሕዝቦች ነበሩና፡፡» 28|33|(ሙሳ) አለ «ጌታዬ ሆይ! እኔ ከእነርሱ ነፍስን ገድያለሁ፡፡ ስለዚህ እንዳይገድሉኝ እፈራለሁ፡፡ 28|34|«ወንድሜም ሃሩን እርሱ ምላሱ ከእኔ የተባ ነው፡፡ እውነተኛነቴንም የሚያረጋግጥልኝ ረዳት ኾኖ ከእኔ ጋር ላከው፡፡ እኔ ሊያስተባብሉኝ እፈራለሁና፡፡» 28|35|(አላህም) «ጡንቻህን በወንድምህ በእርግጥ እናበረታለን፡፡ ለሁለታችሁም ስልጣንን እናደርጋለን፡፡ ወደእናንተም (በመጥፎ) አይደርሱም፡፡ በተዓምራቶቻችን (ኺዱ)፡፡ እናንተና የተከተላችሁም ሁሉ አሸናፊዎች ናችሁ» አላቸው፡፡ 28|36|ሙሳም በታምራቶቻችን ግልጽ ኾነው በመጣባቸው ጊዜ «ይህ የተቀጠፈ ድግምት እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ ይህንንም በመጀመሪያዎቹ አባቶቻችን ውስጥ አልሰማንም» አሉ፡፡ 28|37|ሙሳም «ጌታዬ ከእርሱ ዘንድ በቀጥታው መንገድ የመጣውን ሰው ምስጉኒቱም አገር ለእርሱ የምትኾንለትን ሰው ዐዋቂ ነው፡፡ እነሆ በደለኞቹ አይድኑም» አለ፡፡ 28|38|ፈርዖንም «እናንተ ጭፍሮች ሆይ! ከእኔ ሌላ ለእናንተ አምላክን ምንም አላወቅሁም፡፡ ሃማንም ሆይ! ጭቃን ለእኔ አቃጥልልኝ፤ (ጡብ ሥራልኝ)፡፡ ለእኔም ከፍተኛ ሕንጻን ሥራልኝ፡፡ ወደ ሙሳ አምላክ ልወጣ እከጅላለሁና፡፡ እኔም ከውሸታሞቹ መኾኑን እጠረጥረዋለሁ» አለ፡፡ 28|39|እርሱም ሰራዊቶቹም በምድር ላይ ያለ አግባብ ኮሩ፡፡ እነርሱም ወደእኛ የማይመለሱ መኾናቸውን ጠረጠሩ፡፡ 28|40|እርሱንም ሰራዊቱንም በጥብቅ ያዝናቸው፡፡ በባሕርም ውስጥ ጣልናቸው፡፡ የበደለኞች መጨረሻም፤ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከት፡፡ 28|41|ወደ እሳት የሚጠሩ መሪዎችም አደረግናቸው፡፡ በትንሣኤም ቀን አይርረዱም፡፡ 28|42|በይህችም በቅርቢቱም ዓለም ውስጥ እርግማንን አስከተልናቸው፡፡ በትንሣኤም ቀን እነሱ ከሚባረሩት ናቸው፡፡ 28|43|የፊተኞቹን የክፍለ ዘመናት ሕዝቦችም ከአጠፋን በኋላ ለሰዎች የልብ ብርሃን መሪም እዝነትም ሲኾን ይገሰጹ ዘንድ ለሙሳ መጽሐፉን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ 28|44|ወደ ሙሳም ትዕዛዝን ባወረድንለት ጊዜ (ከተራራው) በምዕራባዊው ጎን አልነበርክም ከተጣዱትም አልነበርክም፡፡ 28|45|ግን እኛ (ከእርሱ በኋላ) የክፍለ ዘመናትን ሰዎች አስገኘን፡፡ በእነሱም ላይ ዕድሜዎች ተራዘሙ፡፡ በመድየንም ሰዎች ውስጥ ተቀማጭ በእነሱ ላይ አንቀጾቻችን የምታነብ አልነበርክም፡፡ ግን እኛ ላኪዎችህ ኾንን፡፡ 28|46|በጠራነውም ጊዜ በጡር ጎን አልነበርክም፡፡ ግን ከአንተ በፊት ምንም አስፈራሪ ያልመጣቸውን ሕዝቦች ታስፈራራ ዘንድ ከጌታህ በኾነ ችሮታ (ላክንህ) ሊገሰጹ ይከጀላልና፡፡ 28|47|እጆቻቸውም ባሳለፉት ምክንያት መከራ የምትነካቸውና «ጌታችን ሆይ! አንቀጾችህን እንድንከተል ከምእምናንም እንድንኾን ወደኛ መልክተኛን አትልክም ኖሯልን» የሚሉ ባልኾኑ ኖሮ (አንልክም ነበር)፡፡ 28|48|እውነቱም ከእኛ ዘንድ በመጣላቸው ጊዜ «ለሙሳ የተሰጠው ብጤ አይስሰጠውም ኖሯልን» አሉ፡፡ «ከዚህ በፊት ሙሳ በተሰጠው አልካዱምን የተረዳዱ ሁለት ድግምቶች ናቸው» አሉ፡፡ «እኛ በሁሉም ከሓዲዎች ነንም» አሉ፡፡ 28|49|«ከአላህ ዘንድ የኾነን መጽሐፍ እርሱ ከሁለቱም ይበልጥ ቅን የኾነን አምጡ፡፡ እውነተኞች እንደ ኾናችሁ (ብታመጡት) እከተለዋለሁ» በላቸው፡፡ 28|50|እሺ ባይሉህም፤ የሚከተሉት፤ ዝንባሌዎቻቸውን ብቻ መኾኑን ዕወቅ፡፡ ከአላህም የኾነ መመሪያ ሳይኖረው ዝንባሌውን ከተከተለ ሰው ይበልጥ የጠመመ አንድም የለም፡፡ አላህ በደለኞች ሕዝቦችን አይመራምና፡፡ 28|51|ይገሰጹም ዘንድ ቃልን (ቁርኣንን በያይነቱ) ለእነርሱ በእርግጥ አስከታተልን፡፡ 28|52|እነዚያ ከእርሱ በፊት መጽሐፍን የሰጠናቸው እነርሱ በእርሱ ያምናሉ፡፡ 28|53|በእነሱ ላይ በሚነበብላቸውም ጊዜ «በእርሱ አምነናል፡፡ እርሱ ከጌታችን የኾነ እውነት ነው፡፡ እኛ ከርሱ በፊት ሙስሊሞች ነበርን» ይላሉ፡፡ 28|54|እነዚያ በመታገሳቸው ዋጋቸውን ሁለት ጊዜ ይስሰጣሉ፡፡ ክፉውንም ነገር በበጎ ምግባር ይገፈትራሉ፡፡ ከሰጠናቸውም ሲሳይ ይለግሳሉ፡፡ 28|55|ውድቅንም ቃል በሰሙ ጊዜ ከእርሱ ይርቃሉ፡፡ «ለእኛ ሥራዎቻችን አሉን፡፡ ለናንተም ሥራዎቻችሁ አሏችሁ፡፡ ሰላም በእናንተ ላይ (ይኹን) ባለጌዎችን አንፈልግም» ይላሉ፡፡ 28|56|አንተ የወደድከውን ሰው ፈጽሞ አታቀናም፡፡ ግን አላህ የሚሻውን ሰው ያቀናል እርሱም ቅኖቹን ዐዋቂ ነው፡፡ 28|57|«ከአንተ ጋር ቅንን መንገድ ብንከተል ከምድራችን እንባረራለን» አሉም፡፡ ከእኛ ዘንድ (የተሰጠ) ሲሳይ ሲሆን የነገሩ ሁሉ ፍሬዎች ወደእርሱ የሚነዱበትን ጸጥተኛ ክልል (መካን) ለእነሱ አላስመቸናቸውምን ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 28|58|ከከተማም ኑሮዋን (ምቾቷን) የካደችን (ከተማ) ያጠፋናት ብዙ ናት፡፡ እነዚህም ከእነሱ በኋላ ጥቂት ጊዜ እንጅ ያልተኖረባቸው ሲኾኑ መኖሪያዎቻቸው ናቸው፡፡ እኛም (ከእነርሱ) ወራሾች ነበርን፡፡ 28|59|ጌታህም ከተሞችን በዋናዋ (ከተማ) ውስጥ አንቀጾቻችንን በእነሱ ላይ የሚያነብ መልክተኛን እስከሚልክ ድረስ አጥፊ አልነበረም፡፡ ከተሞችንም ባለቤቶቿ በዳዮች ሆነው እንጅ አጥፊዎች አልነበርንም፡፡ 28|60|ከማንኛውም ነገር የተሰጣችሁት፤ የቅርቢቱ ሕይወት ጥቅምና ጌጧ ነው፡፡ አላህ ዘንድ ያለውም (ምንዳ) በጣም በላጭና ዘውታሪ ነው አታውቁምን 28|61|መልካምን ተስፋ ቃል የገባንለትና እርሱም አግኚው የሆነ ሰው የቅርቢቱን ሕይወት ጥቅም እንዳስመቸነውና ከዚያም እርሱ በትንሣኤ ቀን (ለእሳት) ከሚቀረቡት እንደ ኾነው ሰው ነውን 28|62|(አላህ) የሚጠራባቸውንና እነዚያ ተጋሪዎቼ ትሏቸው የነበራችሁት የት ናቸው የሚልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 28|63|እነዚያ በእነርሱ ላይ ቃሉ የተረጋገጠባቸው ይላሉ «ጌታችን ሆይ! እነዚህ እነዚያ ያጠመምናቸው ናቸው፡፡ እንደጠመምን አጠመምናቸው፡፡ (ከእነሱ) ወዳንተ ተጥራራን፡፡ እኛን ይግገዙ አልነበሩም፡፡ 28|64|«(ለአላህ) የምታጋሯቸውንም ጥሩ» ይባላሉ፤ ይጠሯቸዋልም፡፡ ግን ለእነርሱ አይመልሱላቸውም፡፡ ቅጣቱንም ያያሉ፡፡ እነርሱ ይመሩ በነበሩ ኖሮ (አያዩትም ነበር)፡፡ 28|65|«የሚጠራባቸውንና ለመልክተኞቹም ምንን መለሳችሁ» የሚልበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 28|66|በዚያም ቀን ወሬዎቹ ሁሉ በእነርሱ ላይ ይሰውሩባቸዋል፡፡ እነርሱም አይጠያየቁም፡፡ 28|67|የተጸጸተና ያመነ ሰውማ መልካምንም የሠራ ከሚድኑት ሊኾን ይከጀላል፡፡ 28|68|ጌታህም የሚሻውን ይፈጥራል፤ ይመርጣልም፡፡ ለእነርሱ (ለሰዎቹ) ምርጫ የላቸውም፡፡ አላህ ከማይግገባው ሁሉ ጠራ፡፡ ከሚያጋሯቸውም ላቀ፡፡ 28|69|ጌታህም ልቦቻቸው የሚደብቁትንና የሚገልጹትን ሁሉ ያውቃል፡፡ 28|70|እርሱም አላህ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ ምስጋና በመጀመሪያይቱም በመጨረሻይቱም ዓለም ለእርሱ ብቻ ነው፡፡ ፍርዱም የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ወደእርሱም ትመለሳላችሁ፡፡ 28|71|አያችሁን (ንገሩኝ) «አላህ በእናንተ ላይ ሌሊትን እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ ዘውታሪ ቢያደርገው ከአላህ ሌላ ብርሃንን የሚያመጣላችሁ አምላክ ማነው አትሰሙምን» በላቸው፡፡ 28|72|አያችሁን «አላህ በእናንተ ላይ ቀንን እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ ዘውታሪ ቢያደርገው ከአላህ ሌላ በውስጡ የምታርፉበትን ሌሊት የሚያመጣላችሁ አምላክ ማን ነው (ንገሩኝ) አታስተውሉምን» በላቸው፡፡ 28|73|ከችሮታውም ለእናንተ ሌሊትንና ቀንን በውስጡ ልታርፉበት፣ ከትሩፋቱም ልትፈልጉበት፣ አመስገኞችም ልትኾኑ አደረገላችሁ፡፡ 28|74|የሚጠራባቸውንም ቀንና «እነዚያ ተጋሪዎቼ ትሏቸው የነበራችሁት የት ናቸው» የሚልበትን (አስታውስ)፡፡ 28|75|ከሕዝቦችም ሁሉ መስካሪን እናወጣለን፡፡ (ያን ጊዜ) እውነተኛውም አምላክነት ለአላህ ብቻ መኾኑን ያውቃሉ፡፡ ይቀጣጥፉት የነበሩትም ከእነርሱ ይጠፋቸዋል፡፡ 28|76|ቃሩን ከሙሳ ነገዶች ነበር፡፡ በእነርሱም ላይ አመጸ፡፡ ከድልቦችም ያንን መከፈቻዎቹ ብቻ የኃይል ባለቤቶች የኾኑ ጭፍሮችን (ሸክሙ) የሚከብድን ሰጠነው፡፡ ወገኖቹ ለእርሱ አትኩራ፤ አላህ ኩራተኞችን አይወድምና ባሉት ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 28|77|«አላህም በሰጠህ ሀብት የመጨረሻይቱን አገር ፈልግ፡፡ ከቅርቢቱም ዓለም ፋንታህን አትርሳ፡፡ አላህም ወደ አንተ መልካምን እንዳደረገልህ (ለሰዎች) መልካምን አድርግ፡፡ በምድርም ውስጥ ማጥፋትን አትፈልግ፡፡ አላህ አጥፊዎችን አይወድምና» (አሉት)፡፡ 28|78|(ሀብቱን) «የተሰጠሁት እኔ ዘንድ ባለው እውቀት ብቻ ነው አለ፡፡ አላህ ከእርሱ በፊት ከክፍለ ዘመናት ሰዎች በኀይል ከእርሱ ይበልጥ የበረቱትን (ሀብትን) በመሰብሰብም ይበልጥ የበዙትን በእርግጥ ያጠፋ መኾኑን አያውቅምን አመጸኞችም ከኀጢኣቶቻቸው (ምሕረት የሚከተለውን ጥያቄ) አይጠየቁም፡፡ 28|79|በሕዝቦቹም ላይ በጌጡ ውስጥ ኾኖ ወጣ፡፡ እነዚያ ቅርቢቱን ሕይወት የሚፈልጉት «ወይ ምኞታችን! ቃሩን የተሰጠው ብጤ ምነው ለእኛ በኖረን፤ እርሱ የታላቅ ዕድል ባለቤት ነውና» አሉ፡፡ 28|80|እነዚያም ዕውቀትን የተሰጡት «ወዮላችሁ! የአላህ ምንዳ ለአመነ ሰው መልካምንም ለሠራ በላጭ ነው፡፡ ታጋሾችም እንጅ ሌላው አያገኛትም» አሉ፡፡ 28|81|በእርሱም በቤቱም ምድርን ደረባን፡፡ ለእርሱም ከአላህ ሌላ የሚረዱት ጭፍሮች ምንም አልነበሩትም፡፡ ከሚርረዱትም አልነበረም፡፡ 28|82|እነዚያም በትላንትናው ቀን ስፍራውን ይመኙ የነበሩት «ወይ ጉድ! ለካ አላህ ከባሮቹ ለሚሻው ሰው ሲሳይን ያሰፋል፤ ያጠባልም፡፡ አላህ በእኛ ላይ (በእምነት) ባልለገሰልን ኖሮ ምድርን በእኛ ላይ በገለበጠብን ነበር፡፡ ወይ ጉድ! ከሓዲዎች አይድኑም» የሚሉ ኾነው አነጉ፡፡ 28|83|ይህች የመጨረሻይቱ አገር ለእነዚያ በምድር ውስጥ ኩራትንና ማመፅን ለማይፈልጉት እናደርጋታለን፡፡ ምስጉኒቱም መጨረሻ ለጥንቁቆቹ ናት፡፡ 28|84|በደግ ሥራ የመጣ ሰው ለእርሱ ከእርሷ በላጭ ምንዳ አልለው፡፡ በክፉም ሥራ የመጡ ሰዎች እነዚህ መጥፎዎችን የሠሩ ይሠሩት የነበሩትን እንጅ አይመነዱም፡፡ 28|85|ያ ቁርኣንን የተከፋፈለ ኾኖ ባንተ ላይ ያወረደው (አምላክ) ወደ መመለሻ (ወደመካ) በእርግጥ መላሽህ ነው፡፡ «ጌታዬ በቅን መንገድ የመጣውን ሰውና እርሱም በግልጽ ስሕተት ውስጥ የኾነውን ሰው ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 28|86|መጽሐፉ ወዳንተ መወረዱን ተስፋ የምታደርግ አልነበርክም፡፡ ግን ከጌታህ ችሮታ (ተወረደልህ)፡፡ ለከሓዲዎችም በፍጹም ረዳት አትኹን፡፡ 28|87|ከአላህም አንቀጾች ወዳንተ ከተወረዱ ጊዜ በኋላ አያግዱህ፡፡ ወደ ጌታህም (ሰዎችን) ጥራ፡፡ ከአጋሪዎቹም አትኹን፤ 28|88|ከአላህም ጋር ሌላን አምላክ አትግገዛ፡፡ ከእርሱ በቀር አምላክ የለም፡፡ ነገሩ ሁሉ ከአላህ በቀር ጠፊ ነው፡፡ ፍርዱ የርሱ፤ ብቻ ነው፡፡ ወደእርሱም ትመለሳላችሁ፡፡ 29|1|አ.ለ.መ (አሊፍ ላም ሚም) 29|2|ሰዎቹ አምነናል በማለታቸው ብቻ እነሱ ሳይፈተኑ የሚተው መኾናቸውን ጠረጠሩን 29|3|እነዚያንም ከእነሱ በፊት የነበሩትን በእርግጥ ፈትነናል፡፡ እነዚያንም እውነት የተናገሩትን አላህ በእርግጥ ያውቃል፡፡ ውሸታሞቹንም ያውቃል፡፡ 29|4|ይልቁንም እነዚያ መጥፎዎችን ሥራዎች የሚሠሩት ሊያመልጡን ይጠረጥራሉን ያ የሚፈርዱት (ፍርድ) ከፋ፡፡ 29|5|የአላህን መገናኘት ተስፋ የሚያደርግ ሰው (ይዘጋጅ)፡፡ የአላህ ቀጠሮ በእርግጥ መጪ ነውና፡፡ እርሱም ሰሚው ዐዋቂው ነው፡፡ 29|6|የታገለ ሰውም የሚታገለው ለነፍሱ ነው፡፡ አላህ ከዓለማት በእርግጥ ተብቃቂ ነውና፡፡ 29|7|እነዚያም ያመኑ፤ መልካሞችንም የሠሩ መጥፎዎቹን ሥራዎቻቸውን ከእነሱ ላይ እናብስላቸዋለን፡፡ በዚያም ይሠሩት በነበሩት መልካም ሥራ በእርግጥ እንመነዳቸዋለን፡፡ 29|8|ሰውንም በወላጆቹ መልካም አድራጎትን አዘዝነው፡፡ ላንተም በእርሱ ዕውቀት የሌለህን (ጣዖት) በእኔ እንድታጋራ ቢታገሉህ አትታዘዛቸው፡፡ መመለሻችሁ ወደኔ ነው፡፡ ትሠሩት የነበራችሁትንም ሁሉ እነግራችኋለሁ፡፡ 29|9|እነዚያንም ያመኑ፤ መልካም ሥራዎችንም የሠሩ በደጋጎቹ ውስጥ በእርግጥ እናገባቸዋለን፡፡ 29|10|ከሰዎችም በአላህ አመንን የሚል ሰው አልለ፡፡ በአላህም (በማመኑ) በተሰቃየ ጊዜ የሰዎችን ማሰቃየት እንደ አላህ ቅጣት ያደርጋል፡፡ ከጌታህም እርዳታ ቢመጣ እኛ በእርግጥ ከእናንተ ጋር ነበርን ይላሉ፡፡ አላህ በዓለማት ሕዝብ ልቦች ውስጥ ያለውን ሁሉ ዐዋቂ አይደለምን 29|11|አላህም እነዚያን ያመኑትን በእርግጥ ያውቃል፡፡ መናፍቆቹንም ያውቃል፡፡ 29|12|እነዚያም የካዱት ሰዎች ለእነዚያ ላመኑት «መንገዳችንን ተከተሉ፤ ኀጢአቶቻችሁንም እንሸከማለን» አሉ፡፡ እነርሱም ከኀጢአቶቻቸው ምንንም ተሸካሚዎች አይደሉም፡፡ እነርሱ በእርግጥ ውሸታሞች ናቸው፡፡ 29|13|ሸክሞቻቸውንና ከሸክሞቻቸው ጋር (ሌሎች) ሸክሞችንም በእርግጥ ይሸከማሉ፡፡ በትንሣኤም ቀን ይቀጥፉት ከነበሩት በእርግጥ ይጠየቃሉ፡፡ 29|14|ኑሕንም ወደ ሕዝቦቹ በእርግጥ ላክነው፡፡ በውስጣቸውም ሺህ ዓመትን አምሳ ዓመት ሲቀር ተቀመጠ፡፡ እነርሱ በዳዮች ኾነውም የውሃው ማጥለቅለቅ ያዛቸው፡፡ 29|15|ኑሕንና የመርከቢቱንም ጓዶች አዳናቸው፡፡ እርሷንም ለዓለማት ተዓምር አደረግናት፡፡ 29|16|ኢብራሂምንም ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «አላህን ተገዙ ፍሩትም፡፡ ይህ የምታውቁ ብትሆኑ ለእናንተ በላጭ ነው፡፡ 29|17|«ከአላህ ሌላ የምትገዝዙት ጣዖታትን ብቻ ነው፡፡ ውሸትንም ትቀጣጥፋላችሁ፡፡ እነዚያ ከአላህ ሌላ የምትግገዙዋቸው ለእናንተ ሲሳይን ሊሰጧችሁ አይችሉም፡፡ ስለዚህ ሲሳይን ከአላህ ዘንድ ብቻ ፈልጉ፡፡ ተገዙትም፡፡ ለእርሱም አመሰግኑ፡፡ ወደእርሱ ትመለሳላችሁ፡፡ 29|18|«ብታስተባብሉም ከፊታችሁ የነበሩት ሕዝቦች በእርግጥ አስተባብለዋል፡፡ በመልክተኛውም ላይ ግልጽ ማድረስ እንጂ ሌላ የለበትም፡፡» 29|19|አላህ መፍጠርን እንዴት እንደሚጀመር ከዚያም እንዴት እንደሚመልሰው አይመለከቱምን ይህ በአላህ ላይ ቀላል ነው፡፡ 29|20|«፡--በምድር ላይ ኺዱ፤ መፍጠርንም እንዴት እንደ ጀመረ ተመልከቱ፡፡ ከዚያም፤ አላህ የመጨረሻይቱን መነሳት ያስነሳል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና» በላቸው፡፡ 29|21|የሚሻውን ሰው ይቀጣል፡፡ የሚሻውንም ሰው ያዝንለታል፡፡ ወደእርሱም ትመለሳላችሁ፡፡ 29|22|እናንተም በምድርም ኾነ በሰማይ የምታቅቱ አይደላችሁም፡፡ ከአላህም ሌላ ረዳትም ተከላካይም ምንም የላችሁም፡፡ 29|23|እነዚያም በአላህ አንቀጾችና በመገናኘቱ የካዱ እነዚያ ከእዝነቴ ተስፋን ቆረጡ፡፡ እነዚያም ለእነሱ አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 29|24|የሕዝቦቹም መልስ፡- «ግደሉት፤ ወይም አቃጥሉት» ማለት እንጂ ሌላ አልነበረም፡፡ ከእሳቲቱም አላህ አዳነው፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚያምኑ ሕዝቦች ተዓምራቶች አሉበት፡፡ 29|25|(ኢብራሂም) አለም «ከአላህ ሌላ ጣዖታትን (አማልክት) የያዛችሁት በቅርቢቱ ሕይወት በመካከላችሁ ለመዋደድ ብቻ ነው፡፡ ከዚያም በትንሣኤ ቀን ከፊላቸሁ በከፊሉ ይክዳል፡፡ ከፊላችሁም ከፊሉን ይረግማል፡፡ መኖሪያችሁም እሳት ናት፡፡ ለእናንተም ከረዳቶች ምንም የላችሁም፡፡» 29|26|ሉጥም ለእርሱ አመነ፤ (ኢብራሂም) «እኔ ወደ ጌታዬ ተሰዳጅ ነኝ፡፡ እነሆ እርሱ አሸናፊው ጥበበኛው ነውና» አለም፡፡ 29|27|ለእርሱም ኢስሐቅንና ያዕቆብን ሰጠነው፡፡ በዘሩም ውስጥ ነብይነትንና መጽሐፍን አደረግን፡፡ ምንዳውንም በቅርቢቱ ዓለም ሰጠነው፡፡ እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከደጋጎቹ ነው፡፡ 29|28|ሉጥንም ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ) «እናንተ ጠያፍን ስራ ትሠራላችሁን በእርሷ ከዓለማት አንድም አልቀደማችሁም፡፡ 29|29|«እናንተ በእርግጥ ወንዶችን ትመጣላችሁን መንገድንም ትቆርጣላችሁን በሸንጓችሁም የሚነወርን ነገር ትሠራላችሁን» (አላቸው)፡፡ የሕዝቦቹም መልስ «ከእውነተኞቹ እንደ ሆንክ የአላህን ቅጣት አምጣብን» ማለት እንጂ ሌላ አልነበረም፡፡ 29|30|«ጌታዬ ሆይ! በአመጸኞች ሕዝቦች ላይ እርዳኝ» አለ፡፡ 29|31|መልክተኞቻችንም ኢብራሂምን በብስራት በመጡት ጊዜ «እኛ የዚህችን ከተማ ሰዎች አጥፊዎች ነን፡፡ ሰዎቿ በዳዮች ነበሩና» አሉት፡፡ 29|32|«በእርሷ ውስጥ ሉጥ አለ እኮ» አላቸው፡፡ «እኛ በውስጧ ያለውን ይበልጥ ዐዋቂ ነን፡፡ (እርሱን) በእርግጥ እናድነዋለን፡፡ ቤተሰቦቹንም ጭምር፡፡ ሚስቱ ብቻ ስትቀር፡፡ እርሷ በጥፋቱ ውስጥ ከሚቀሩት ናት» አሉት፡፡ 29|33|መልክተኞቻችንም ሉጥን በመጡት ጊዜ በእነሱ ምክንያት አዘነ፡፡ በእነርሱም ልቡ ተጨነቀ፡፡ «አትፍራ፤ አትዘንም፡፡ እኛ አዳኞችህ ነን፡፡ ቤተሰቦችህንም፤ ሚስትህ ብቻ ስትቀር፡፡ እርሷ በጥፋቱ ውስጥ ከቀሪዎቹ ናት» አሉትም፡፡ 29|34|«እኛ በዚህች ከተማ ሰዎች ላይ ያምጹ በነበሩት ምክንያት ከሰማይ ቅጣትን አውራጆች ነን፡፡» 29|35|በእርግጥም ለሚያስቡ ሰዎች ከእርሷ ግልጽ ምልክትን ተውን (አስቀረን)፡፡ 29|36|ወደ መድየንም ወንድማቸውን ሹዐይብን (ላክን)፡፡ «ሕዝቦቼ ሆይ! አላህን ተገዙ፣ የመጨረሻውንም ቀን ፍሩ፣ በምድርም ውስጥ የምታጠፉ ሆናችሁ አታበላሹ አላቸውም፡፡ 29|37|አስተባባሉትም፡፡ የምድር መንቀጥቀጥ ያዘቻቸው፡፡ በሃገራቸውም ውስጥ ተንከፍርረው አነጉ፡፡ 29|38|ዓድንና ሰሙድንም (አጠፋን)፡፡ ከመኖሪያዎቻቸውም (ፍርስራሾች በኩል መጥፋታቸው) ለእናንተ በእውነት ተገለጠላችሁ፡፡ ሰይጣንም ሥራዎቻቸውን ለእነርሱ ሸለመላቸው፡፡ ከመንገድም አገዳቸው፡፡ የማስተዋልም ባለቤቶች ነበሩ፤ (ግን አላስተዋሉም)፡፡ 29|39|ቃሩንንም ፈርዖንንም ሃማንንም (አጠፋን)፡፡ ሙሳም በተዓምራቶች በእርግጥ መጣባቸው፡፡ በምድርም ላይ ኮሩ፡፡ አምላጪዎችም አልነበሩም፡፡ 29|40|ሁሉንም በኅጢኣቱ ያዝነው፡፡ ከእነሱም ውስጥ ጠጠርን ያዘለ ነፋስን የላክንበት አልለ፡፡ ከእነሱም ውስጥ ጩኸት የያዘችው አልለ፡፡ ከእነርሱም ውስጥ በእርሱ ምድርን የደረባንበት አልለ፡፡ ከእነሱም ውስጥ ያሰጠምንው አልለ፡፡ አላህም የሚበድላቸው አልነበረም፡፡ ግን ነፍሶቻቸውን የሚበድሉ ነበሩ፡፡ 29|41|የእነዚያ ከአላህ ሌላ ረዳቶችን (ጣዖታትን) የያዙ ሰዎች ምሳሌ ቤትን እንደ ሠራች ሸረሪት ብጤ ነው፡፡ ከቤቶችም ሁሉ በጣም ደካማው የሸረሪት ቤት ነው፡፡ ቢያውቁ ኖሮ (አማልክት አድርገው አይግገዟቸውም ነበር)፡፡ 29|42|አላህ ያንን ከእርሱ ሌላ የሚግገዙትን ማንኛውንም ያውቃል፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 29|43|እነዚህንም ምሳሌዎች ለሰዎች እንገልጻቸዋለን፡፡ ከሊቃውንቶቹም በስተቀር ሌሎቹ አያውቋትም፡፡ 29|44|«አላህ ሰማያትንና ምድርን እውነተኛ ሆኖ ፈጠረ፡፡» በዚህ ውስጥ ለምእምናን ተዓምር አለበት፡፡ 29|45|ከመጽሐፍ ወደ አንተ የተወረደውን አንብብ፡፡ ሶላትንም ደንቡን ጠብቀህ ስገድ፡፡ ሶላት ከመጥፎና ከሚጠላ ነገር ሁሉ ትከለክላለችና፡፡ አላህንም ማውሳት ከሁሉ ነገር በላጭ ነው፤ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ያውቃል፡፡ 29|46|የመጽሐፉን ባለቤቶችም በዚያች እርሷ መልካም በኾነችው ክርክር እንጂ አትከራከሩ፡፡ ከእነርሱ እነዚያን የበደሉትን ሲቀር፡፡ በሉም «በዚያ ወደኛ በተወረደው ወደናንተም በተወረደው አመንን፡፡ አምላካችንም አምላካችሁም አንድ ነው፡፡ እኛም ለእርሱ ታዛዦች ነን፡፡» 29|47|እንደዚሁም ወዳንተ መጽሐፍን አወረድን፡፡ እነዚያም መጽሐፍን የሰጠናቸው፤ በእርሱ ያምናሉ፡፡ ከእነዚህም (ከመካ ሰዎች) በእርሱ የሚያምኑ አልሉ፡፡ በተዓምራቶቻችንም ከሓዲዎቹ እንጂ ማንም አይክድም፡፡ 29|48|ከእርሱ በፊትም መጽሐፍን የምታነብ በቀኝህም የምትጽፈው አልነበርክም፡፡ ያን ጊዜ አጥፊዎቹ በእርግጥ በተጠራጠሩ ነበር፡፡ 29|49|አይደለም እርሱ (ቁርኣን) በእነዚያ ዕውቀትን በተሰጡት ሰዎች ልቦች ውስጥ (የጠለቀ) ግልጾች አንቀጾች ነው፡፡ በአንቀጾቻችንም በዳዮቹ እንጂ ሌላው አይክድም፡፡ 29|50|«በእርሱ ላይም ከጌታህ ዘንድ ተዓምራቶች ለምን አልተወረዱም» አሉ፡፡ «ተዓምራቶች አላህ ዘንድ ብቻ ናቸው፡፡ እኔም ግልጽ አስፈራሪ ብቻ ነኝ» በላቸው፡፡ 29|51|እኛ መጽሐፉን በእነሱ ላይ የሚነበብ ኾኖ ባንተ ላይ ማውረዳችን አይበቃቸውምን በዚህ ውስጥ ለሚያምኑ ሕዝቦች ችሮታና ግሳጼ አለበት፡፡ 29|52|«በእኔና በእናንተ መካከል መስካሪ በአላህ በቃ፡፡ በሰማያትና በምድርም ያለውን ሁሉ ያውቃል» በላቸው፡፡ እነዚያም በብላሽ ነገር ያመኑ በአላህም የካዱ እነዚያ እነሱ ከሳሪዎች ናቸው፡፡ 29|53|በቅጣትም ያስቸኩሉሃል፡፡ የተወሰነም ጊዜ ባልነበረ ኖሮ ቅጣቱ በመጣባቸው ነበር፡፡ እነርሱ የማያውቁ ሲኾኑም በድንገት በእርግጥ ይመጣባቸዋል፡፡ 29|54|በቅጣት ያስቸኩሉሃል፡፡ ገሀነምም ከሓዲዎችን በእርግጥ ከባቢ ናት፡፡ 29|55|ቅጣቱ ከበላያቸው፣ ከእግሮቻቸውም ሥር በሚሸፍናቸው ቀን ትሠሩት የነበራችሁትን ቅመሱ በሚላቸውም (ቀን ትከባቸዋለች)፡፡ 29|56|እናንተ ያመናችሁ ባሮቼ ሆይ! ምድሬ በእርግጥ ሰፊ ናት፤ (ብትቸገሩ ተሰደዱ)፡፡ እኔንም ብቻ ተገዙኝ፡፡ 29|57|ነፍስ ሁሉ ሞትን ቀማሽ ናት፡፡ ከዚያም ወደኛ ትመለሳላችሁ፡፡ 29|58|እነዚያም ያመኑና መልካም ሥራዎችን የሠሩ ከገነት በሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ሰገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ በእርግጥ እናሰፍራቸዋለን፡፡ የሠራተኞች ምንዳ ምንኛ አማረ! 29|59|(እነሱ) እነዚያ የታገሱ በጌታቸውም ላይ የሚመኩ ናቸው፡፡ 29|60|ከተንቀሳቃሽም ምግቧን ለመሸከም የማትችለው ብዙ ናት፡፡ አላህ ይመግባታል፡፡ እናንተንም (ይመግባል)፡፡ እርሱ ሰሚው ዐዋቂው ነውና፡፡ 29|61|ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ ፀሐይንና ጨረቃንም የገራ ማን እንደኾነ ብትጠይቃቸው «በእርግጥ አላህ ነው» ይሉሃል፡፡ ታድያ እንዴት ይመለሳሉ፡፡ 29|62|አላህ ከባሮቹ ለሚሻው ሲሳይን ያሰፋል፡፡ ለእርሱም ያጠብባል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 29|63|ከሰማይም ውሃን ያወረደና በእርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው ያደረጋት ማን እንደኾነ ብትጠይቃቸው «አላህ ነው» ይሉሃል፡፡ «ምስጋና ለአላህ ነው» በላቸው፡፡ ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 29|64|ይህችም የቅርቢቱ ሕይወት መታለያና ጨዋታ እንጂ ሌላ አይደለችም፡፡ የመጨረሻይቱም አገር እርሷ በእርግጥ የዘላለም ሕይወት አገር ናት፡፡ የሚያውቁ ቢኾኑ ኖሮ፤ (ጠፊይቱን ሕይወት አይመርጡም ነበር)፡፡ 29|65|በመርከቦች ውስጥ በተሳፈሩ ጊዜም አላህን መገዛትን ለእርሱ ብቻ ያጠሩ ኾነው ይጠሩታል፡፡ ወደ የብስ (በማውጣት) ባዳናቸው ጊዜም ወዲያውኑ እነርሱ (ጣዖትን) ያጋራሉ፡፡ 29|66|በሰጠናቸው ጸጋ ሊክዱና ሊጠቃቀሙ (ያጋራሉ)፡፡ ወደፊትም (የሚጠብቃቸውን) ያውቃሉ፡፡ 29|67|ሰዎቹ ከዙሪያቸው ሲነጠቁ እኛ (አገራቸውን ) ጸጥተኛ ክልል ማድረጋችንን አያዩምን በውድቅ ነገር ያምናሉን በአላህም ጸጋ ይክዳሉን 29|68|በአላህ ላይም ውሸትን ከቀጣጠፈ ሰው ወይም እውነቱ በመጣለት ጊዜ ከአስዋሸ ይበልጥ በዳይ ማነው በገሀነም ውስጥ ለከሓዲዎች መኖሪያ የለምን 29|69|እነዚያም በእኛ መንገድ የታገሉ መንገዳችንን በእርግጥ እንመራቸዋለን፡፡ አላህም በእርግጥ ከበጎ ሠሪዎች ጋር ነው፡፡ 30|1|አ.ለ.መ (አሊፍ ላም ሚም)፡፡ 30|2|ሩም ተሸነፈች፡፡ 30|3|በጣም ቅርብ በሆነችው ምድር፡፡ እነርሱም ከመሸነፋቸው በኋላ በእርግጥ ያሸንፋሉ፡፡ 30|4|በጥቂት ዓመታት ውስጥ (ያሸንፋሉ)፡፡ ትዕዛዙ በፊትም በኋላም የአላህ ነው፡፡ በዚያ ቀንም ምእመናን ይደሰታሉ፡፡ 30|5|በአላህ እርዳታ (ይደሰታሉ)፡፡ የሚሻውን ሰው ይረዳል፤ እርሱም አሸናፊው አዛኙ ነው፡፡ 30|6|አላህ እርዳታን ቀጠረ፡፡ አላህ ቀጠሮውን አያፈርስም፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 30|7|ከቅርቢቱ ህይወት ግልጹን ብቻ ያውቃሉ፡፡ እነርሱም ከኋለኛይቱ ዓለም እነርሱ ዘንጊዎች ናቸው፡፡ 30|8|በነፍሶቻቸው (ሁኔታ) አያስተውሉምን? ሰማያትንና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ አላህ በእውነትና በተወሰነ ጊዜ እንጂ አልፈጠራቸውም፡፡ ከሰዎቹም ብዙዎቹ በጌታቸው መገናኘት ከሓዲዎች ናቸው፡፡ 30|9|በምድር ላይ አይኼዱምና የእነዚያን ከበፊታቸው የነበሩትን ሰዎች ፍጻሜ እንዴት እንደነበረ አይመለከቱምን? በኀይል ከእነርሱም ይበልጥ የጠነከሩ ነበሩ፡፡ ምድርንም አረሱ፡፡ (እነዚህ) ከአለሟትም የበዛ አለሟት፡፡ መልዕክተ ኞቻቸውም በተዓምራቶች መጡባቸው፤ (አስተባበሉምና ጠፉ)፡፡ አላህም የሚበድላቸው አልነበረም፤ ግን ነፍሶቻቸውን ይበድሉ ነበሩ፡፡ 30|10|ከዚያም የእነዚያ ያጠፉት ሰዎች መጨረሻ በአላህ አንቀጾች በማስተባበላቸውና በእርሷ የሚሳለቁ በመኾናቸው ምክንያት መጥፎ ቅጣት ሆነች፡፡ 30|11|አላህ መፍጠርን ይጀምራል፡፡ ከዚያም ይመልሰዋል፤ ከዚያም ወደርሱ ትመለሳላችሁ፡፡ 30|12|ሰዓቲቱም በምትቆምበት ቀን አመጸኞች ጭጭ ይላሉ፡፡ 30|13|ለእነርሱም ከሚያጋሩዋቸው (ጣዖታት) አማላጆች አይኖሯቸውም፤ በሚያጋሯቸውም (ጣዖታት) ከሓዲዎች ይኾናሉ፡፡ 30|14|ሰዓቲቱ በምትቆምበት ቀንም በዚያ ቀን ይለያያሉ፡፡ 30|15|እነዚያ ያመኑትና መልካሞችን ሥራዎች የሠሩትማ እነርሱ በገነት ጨፌ ውስጥ ይደሰታሉ፡፡ 30|16|እነዚያም የካዱትማ በአንቀጾቻችንና በኋለኛይቱም ዓለም መገናኘት ያስተባበሉት እነዚያ በቅጣቱ ውስጥ የሚጣዱ ናቸው፡፡ 30|17|አላህንም በምታመሹ ጊዜ በምታነጉም ጊዜ አጥሩት፤ (ስገዱለት)፡፡ 30|18|ምስጋናም በሰማያትና በምድር ውስጥ ለርሱ ብቻ (የተገባው) ነው፡፡ በሰርክም፤ በቀትር ውስጥ በምትገቡም ጊዜ፤ (አጥሩት)፡፡ 30|19|ሕያውን ከሙት ያወጣል፡፡ ሙታንም ከሕያው ያወጣል፡፡ ምድርንም ከሞተች በኋላ ህያው ያደርጋታል፡፡ እንደዚሁም (ከመቃብር) ትወጣላችሁ፡፡ 30|20|እናንተንም ከዐፈር መፍጠሩ ከዚያም እናንተ ወዲያውኑ የምትበታተኑ ሰዎች መኾናችሁ ከአስደናቂ ምልክቶቹ ነው፡፡ 30|21|ለእናንተም ከነፍሶቻችሁ (ከጎሶቻችሁ) ሚስቶችን ወደእነርሱ ትረኩ ዘንድ መፍጠሩ፣ በመካከላችሁም ፍቅርንና እዝነትን ማድረጉ ከአስደናቂ ምልክቶቹ ነው፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚያስተውሉ ሕዝቦች ተዓምራቶች አልሉ፡፡ 30|22|ሰማያትንና ምድርንም መፍጠሩ፣ የቋንቋዎቻችሁና የመልኮቻችሁም መለያየት፣ ከአስደናቂ ምልክቶቹ ነው፡፡ በዚህ ውስጥ ለዐዋቂዎች ተዓምራቶች አልሉበት፡፡ 30|23|በሌሊትና በቀንም መተኛታችሁ፣ ከችሮታውም መፈለጋችሁ ከምልክቶቹ ነው፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚሰሙ ሕዝቦች ተዓምራቶች አልሉበት፡፡ 30|24|ብልጭታንም ፈሪዎችና ከጃዮች ስትሆኑ ለእናንተ ማሳየቱ፣ ከሰማይም ውሃን ማውረዱ፣ በእርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው ማድረጉ ከአስደናቂ ምልክቶቹ ነው፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚያስቡ ሕዝቦች ተዓምራቶች አልሉበት፡፡ 30|25|ሰማይና ምድርም (ያለምሰሶ) በትዕዛዙ መቆማቸው፣ ከዚያም (መልአኩ ለትንሣኤ) ከምድር ጥሪን በጠራችሁ ጊዜ እናንተ ወዲያውኑ የምትወጡ መሆናችሁ ከአስደናቂ ምልክቶቹ ነው፡፡ 30|26|በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ሁሉም ለእርሱ ታዛዦች ናቸው፡፡ 30|27|እርሱም ያ መፍጠርን የሚጀምር ከዚያም የሚመልሰው ነው፡፡ እርሱም (መመለሱ) በእርሱ ላይ በጣም ገር ነው፡፡ ለእርሱም በሰማያትም በምድርም ከፍተኛ ባሕርይ (አንድነትና ለእርሱ ብጤ የሌለው መኾን) አልለው፡፡ እርሱም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 30|28|ለእናንተ ከነፍሶቻችሁ የሆነን ምሳሌ አደረገላችሁ፡፡ (እርሱም) እጆቻችሁ ከያዟቸው (ባሮች) ውስጥ በሰጠናችሁ ጸጋ ለእናንተ ተጋሪዎች አሏችሁን? ታዲያ እናንተና እነርሱ በእርሱ ትክክል ናችሁን? ነፍሶቻችሁን (ብጤዎቻችሁን) እንደምትፈሩ ትፈሯቸዋላችሁን? እንደዚሁ ለሚያስተውሉ ሕዝቦች፤ አንቀጾችን እንገልጻለን፡፡ 30|29|ይልቁንም እነዚያ የበደሉ ሰዎች ያለ ዕውቀት ዝንባሌዎቻቸውን ተከተሉ፡፡ አላህም ያጠመመውን ሰው የሚያቀናው ማነው? ለእነርሱም ከረዳቶች ምንም የላቸውም፡፡ 30|30|ወደ እውነት ተዘንባይ ኾነህም ፊትህን ለሃይማኖት ቀጥ አድርግ፡፡ የአላህን ፍጥረት ያችን አላህ ሰዎችን በእርስዋ ላይ የፈጠረባትን (ሃይማኖት ያዟት)፡፡ የአላህን ፍጥረት መለወጥ የለም፡፡ ይህ ቀጥተኛ ሃይማኖት ነው፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 30|31|ወደእርሱ ተመላሾች ሆናቸሁ (የአላህን ሃይማኖት ያዙ)፡፡ ፍሩትም፡፡ ሶላትንም አስተካክላችሁ ስገዱ፡፡ ከአጋሪዎቹም አትሁኑ፡፡ 30|32|ከእነዚያ ሃይማኖታቸውን ከለያዩትና ክፍልፍሎችም ከሆኑት (አትሁኑ)፡፡ ሕዝብ ሁሉ እነሱ ዘንድ ባለው ነገር ተደሳቾች ናቸው፡፡ 30|33|ሰዎችንም ችግር ባገኛቸው ጊዜ ጌታቸውን ወደርሱ ተመላሾች ሆነው ይጠሩታል፡፡ ከዚያም ከእርሱ ችሮታን ባቀመሳቸው ጊዜ ከእነርሱ ከፊሎቹ ወዲያውኑ በጌታቸው (ጣዖትን) ያጋራሉ፡፡ 30|34|በሰጠናቸው ጸጋ ሊክዱ (ያጋራሉ)፡፡ ተጣቀሙም፤ በእርግጥም (መጨረሻችሁን) ወደፊት ታውቃላችሁ፡፡ 30|35|በእነርሱ ላይ አስረጅ አወረድን? ታዲያ እርሱ በዚያ በእርሱ ያጋሩ በነበሩት ነገር ይናገራልን;(የለም)፡፡ 30|36|ሰዎችንም ችሮታን ባቀመስናቸው ገዜ በእርሷ ይደሰታሉ፡፡ እጆቻቸውም ባሳለፉት ምክንያት መከራ ብታገኛቸው ወዲያውኑ እነርሱ ተስፋ ይቆርጣሉ፡፡ 30|37|አላህ ለሚሻው ሰው ሲሳይን የሚያሰፋ የሚያጠብም መሆኑን አያዩምን በዚህ ውስጥ ለሚያምኑ ሕዝቦች አስደናቂ ምልክቶች አልሉበት፡፡ 30|38|የዝምድናን ባለቤት ተገቢውን ስጠው፡፡ ለድኻም ለመንገደኛም (እርዳ)፡፡ ይህ ለእነዚያ የአላህን ፊት (ውዴታውን) ለሚሹ መልካም ነው፡፡ እነዚያም እነርሱ የፈለጉትን የሚያገኙ ናቸው፡፡ 30|39|ከበረከትም በሰዎች ገንዘቦች ውስጥ ይጨመር ዘንድ የምትሰጡት አላህ ዘንድ አይጨምርም፡፡ ከምጽዋትም የአላህን ፊት የምትሹ ሆናችሁ የምትሰጡት እነዚያ (ሰጪዎች) አበርካቾች እነርሱ ናቸው፡፡ 30|40|አላህ ያ የፈጠራችሁ፣ ከዚያም ሲሳይን የሰጣችሁ፣ ከዚያም የሚገድላችሁ ከዚያም ሕያው የሚያደርጋችሁ ነው፡፡ ከምታጋሯቸው (ጣዖታት) ውስጥ ከዚህ ነገር አንዳችን የሚሠራ አለን ለአላህ ጥራት ይገባው፡፡ (በእርሱ) ከሚያጋሩትም ሁሉ ላቀ፡፡ 30|41|የሰዎች እጆች በሠሩት ኃጢኣት ምክንያት የዚያን የሠሩትን ከፊሉን ያቀምሳቸው ዘንድ መከራው በየብስና በባሕር ተገለጠ፤ (ተሰራጨ)፡፡ እነርሱ ሊመለሱ ይከጀላልና፡፡ 30|42|«በምድር ላይ ኺዱ የእነዚያንም በፊት የነበሩትን ሰዎች መጨረሻ እንዴት እንደነበረ ተመልከቱ» በላቸው፡፡ አብዛኞቻቸው አጋሪዎች ነበሩ፡፡ 30|43|ለርሱ መመለስ የሌለው ቀን (የትንሣኤ ቀን) ከአላህ ሳይመጣ በፊት ፊትህን ወደ ቀጥተኛው ሃይማኖት ቀጥ አድርግ፡፡ በዚያ ቀን (ወደ ገነትና ወደ እሳት) ይለያያሉ፡፡ 30|44|የካደ ሰው ክህደቱ (ጠንቁ) በእርሱው ላይ ነው፡፡ መልካምም የሠሩ ለነፍሶቻቸው (ማረፊያዎችን) ያዘጋጃሉ፡፡ 30|45|እነዚያን ያመኑትንና መልካሞችንም የሠሩትን ከችሮታው ይመነዳ ዘንድ (ይለያያሉ)፡፡ እርሱ ከሓዲዎችን አይወድምና፡፡ 30|46|ነፋሶችንም (በዝናብ) ልታበስራችሁ፣ ከችሮታውም (በእርሷ) ሊያቀምሳችሁ፣ መርከቦችም በትዕዛዙ እንዲንሻለሉ፣ ከችሮታውም እንድትፈልጉ፣ ታመሰግኑትም ዘንድ መላኩ ከአስደናቂ ምልክቶቹ ነው፡፡ 30|47|ከአንተ በፊትም መልክተኞችን ወደየሕዝቦቻቸው በእርግጥ ላክን፡፡ በግልጽ ማስረጃዎችም መጡባቸው፡፡ ከእነዚያ ካመጹትም ተበቀልን፡፡ ምእመኖቹንም መርዳት በእኛ ላይ ተገቢ ሆነ፡፡ 30|48|አላህ ያ ነፋሶችን የሚልክ ነው፡፡ ደመናንም ይቀሰቅሳሉ፡፡ በሰማይ ላይም እንደሚሻ ይዘረጋዋል፡፡ ቁርጥራጮችም ያደርገዋል፡፡ ዝናቡንም ከደመናው መካከል ሲወጣ ታያለህ፡፡ በእርሱም ከባሮቹ የሚሻውን በለየ ጊዜ ወዲያውኑ እነሱ ይደሰታሉ፡፡ 30|49|በእነርሱም ላይ ከመወረዱ በፊት ከእርሱ በፊት በእርግጥ ተስፋ ቆራጮች ነበሩ፡፡ 30|50|ምድርንም ከሞተች በኋላ እንዴት ሕያው እንደሚያደርጋት ወደ አላህ ችሮታ ፈለጎች ተመልከት፡፡ ይህ (አድራጊ) ሙታንንም በእርግጥ ሕያው አድራጊ ነው፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 30|51|ነፋስንም (በአዝመራዎች ላይ) ብንልክና ገርጥቶ ቢያዩት ከእርሱ በኋላ በእርግጥ (ችሮታውን) የሚክዱ ይሆናሉ፡፡ 30|52|አንተም ሙታንን አታሰማም፡፡ ደንቆሮዎችንም ዟሪዎች ሆነው በሸሹ ጊዜ ጥሪን አታሰማም፡፡ 30|53|አንተ ዕውሮችንም ከጥመታቸው የምታቀና አይደለህም፡፡ በአንቀጾቻችን የሚያምኑትን ሰዎች እንጂ ሌላን አታሰማም፡፡ እነርሱም ታዛዦች ናቸው፡፡ 30|54|አላህ ያ ከደካማ (ፍትወት ጠብታ) የፈጠራችሁ ነው፡፡ ከዚያም ከደካማነት በኋላ ኀይልን አደረገ፡፡ ከዚያም ከብርቱነት በኋላ ደካማነትንና ሽበትን አደረገ፡፡ የሚሻውን ይፈጥራል፡፡ እርሱም ዐዋቂው ቻዩ ነው፡፡ 30|55|ሰዓቲቱ በምትሆንበት ቀን ከሓዲዎች «ከአንዲት ሰዓት በስተቀር (በመቃብር) አልቆየንም» ብለው ይምላሉ፡፡ እንደዚሁ (ከእውነት) ይመለሱ ነበሩ፡፡ 30|56|እነዚያንም ዕውቀትንና እምነትን የተሰጡት «በአላህ መጽሐፍ (ፍርድ) እስከ ትንሣኤ ቀን በእርግጥ ቆያችሁ፡፡ ይህም (የካዳችሁት) የትንሣኤ ቀን ነው፡፡ ግን እናንተ የማታውቁ ነበራችሁ» ይሏቸዋል፡፡ 30|57|በዚያም ቀን እነዚያን የበደሉትን ማመካኘታቸው አይጠቅማቸውም፡፡ እነርሱም በወቀሳ አይታለፉም፡፡ 30|58|በዚያም ቁርኣን ውስጥ ከምሳሌ ሁሉ ለሰዎች በእርግጥ ገለጽን፡፡ በተዓምርም ብትመጣባቸው እነዚያ የካዱት ሰዎች «እናንተ አበላሺዎች እንጂ ሌላ አይደላችሁም» ይላሉ፡፡ 30|59|እንደዚሁ አላህ በእነዚያ በማያውቁት ሰዎች ልቦች ላይ ያትማል፡፡ 30|60|ስለዚህ ታገስ፡፡ የአላህ ቀጠሮ እውነት ነውና፡፡ እነዚያም በትንሣኤ የሚያረጋግጡት አያቅልሉህ፡፡ 31|1|አ.ለ.መ. (አሊፍ ላም ሚም)፡፡ 31|2|ይህች ጥበብ ከተመላው መጽሐፍ አንቀጾች ናት፡፡ 31|3|ለበጎ አድራጊዎች መሪና እዝነት ስትኾን፡፡ 31|4|ለእነዚያ ሶላትን አስተካክለው ለሚያደርሱት፣ ዘካንም ለሚሰጡት፣ እነርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም እነርሱ የሚያረጋግጡ ለሆኑት፡፡ 31|5|እነዚያ ከጌታቸው በሆነ ቅን መንገድ ላይ ናቸው፡፡ እነዚያም እነርሱ ምኞታቸውን ያገኙ ናቸው፡፡ 31|6|ከሰዎችም ያለ ዕውቀት ሆኖ ከአላህ መንገድ ሊያሳስትና ማላገጫ አድርጎ ሊይዛት አታላይ ወሬን የሚገዛ አልለ፡፡ እነዚያ ለእነርሱ አዋራጅ ቅጣት አላቸው፡፡ 31|7|አንቀጾቻችንም በእርሱ ላይ በሚነበቡ ጊዜ እንዳልሰማትና በጆሮቹ ድንቁርና እንዳለበት የኮራ ሆኖ ይዞራል፡፡ በአሳማሚ ቅጣትም አብስረው፡፡ 31|8|እነዚያ ያመኑና መልካሞችንም የሠሩ ለእነርሱ የጸጋ ገነቶች አሏቸው፡፡ 31|9|በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ሲሆኑ፤ አላህም እውነተኛን ተስፋ ቃል ገባላቸው፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 31|10|ሰማያትን ያለምታዩዋት አዕማድ (ምሰሶዎች) ፈጠረ፡፡ በምድርም ውስጥ በእናንተ እንዳታረገርግ ተራራዎችን ጣለ፡፡ በእርሷም ላይ ከተንቀሳቃሽ ሁሉ በተነ፡፡ ከሰማይም ውሃን አወረድን፡፡ በእርሷም ውስጥ ከመልካም ዓይነት ሁሉ አበቀልን፡፡ 31|11|ይህ የአላህ ፍጡር ነው፡፡ እነዚያ ከእርሱ ሌላ ያሉት ምንን እንደፈጠሩ እስኪ አሳዩኝ፡፡ በእውነቱ በዳዮቹ በግልጽ ጥመት ውስጥ ናቸው፡፡ 31|12|ለሉቅማንም ጥበብን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ (አልነውም)፡- «አላህን አመስግን፡፡» ያመሰገነም ሰው የሚያመሰግነው ለራሱ ብቻ ነው፡፡ የካደም ሰው (በራሱ ላይ ነው)፡፡ አላህ ተብቃቂ ምስጉን ነውና፡፡ 31|13|ሉቅማንም ለልጁ እርሱ የሚገሥጸው ሲኾን «ልጄ ሆይ! በአላህ (ጣዖትን) አታጋራ፡፡ ማጋራት ታላቅ በደል ነውና» ያለውን (አስታውስ)፡፡ 31|14|ሰውንም በወላጆቹ (በጎ እንዲያደርግ) በጥብቅ አዘዝነው፡፡ እናቱ ከድካም በላይ በሆነ ድካም አረገዘችው፡፡ ጡት መጣያውም በሁለት ዓመት ውስጥ ነው፡፡ ለእኔም ለወላጆችህም አመስግን በማለት (አዘዝነው)፡፡ መመለሻው ወደኔ ነው፡፡ 31|15|ለአንተ በእርሱ ዕውቀት የሌለህን ነገር በእኔ እንድታጋራ ቢታገሉህም አትታዘዛቸው፡፡ በቅርቢቱም ዓለም፤ በመልካም ሥራ ተወዳጃቸው፡፡ ወደእኔም የተመለሰን ሰው መንገድ ተከተል፡፡ ከዚያም መመለሻችሁ ወደእኔ ነው፡፡ ትሠሩት የነበራችሁትንም ሁሉ እነግራችኋለሁ፤ (አልነው)፡፡ 31|16|(ሉቅማንም አለ) «ልጄ ሆይ! እርሷ የሰናፍጭ ቅንጣት ክብደት ያህል ብትሆንና በቋጥኝ ውስጥ ወይም በሰማያት ውስጥ ወይም በምድር ውስጥ ብትሆን አላህ ያመጣታል፡፡ አላህ ሩኅሩኅ ውስጥ ዐዋቂ ነውና፡፡ 31|17|«ልጄ ሆይ! ሶላትን አስተካክለህ ስገድ፡፡ በበጎ ነገርም እዘዝ፡፡ ከሚጠላም ሁሉ ከልክል፡፡ በሚያገኝህም መከራ ላይ ታገስ፡፡ ይህ በምር ከሚያዙ ነገሮች ነው፡፡ 31|18|«ጉንጭህንም (በኩራት) ከሰዎች አታዙር፡፡ በምድርም ላይ ተንበጥርረህ አትሂድ፡፡ አላህ ተንበጥራሪን ጉረኛን ሁሉ አይወድምና፡፡ 31|19|«በአካኼድህም መካከለኛ ኹን፡፡ ከድምጽህም ዝቅ አድርግ፡፡ ከድምጾች ሁሉ አስከፊው የአህዮች ድምጽ ነውና፡፡» 31|20|አላህ በሰማያት ያለውንና በምድርም ያለውን ሁሉ ለእናንተ ያገራላችሁ ጸጋዎቹንም ግልጽም ድብቅም ሲኾኑ የሞላላችሁ መኾኑን አታዩምን? ከሰዎችም ያለ ዕውቀትና ያለ መሪ፣ ያለግልጽ መጽሐፍም በአላህ የሚከራከር አልለ፡፡ 31|21|ለእነርሱም አላህ ያወረደውን ተከተሉ በተባሉ ጊዜ አይደለም በእርሱ ላይ አባቶቻችንን ያገኘንበትን እንከተላለን ይላሉ፡፡ ሰይጣን ወደ እሳት ቅጣት የሚጠራቸው ቢሆንም (ይከተሉዋቸዋልን?) 31|22|እርሱ መልካም ሠሪ ሆኖ ፊቱን ወደ አላህ የሚሰጥም ሰው ጠንካራን ገመድ በእርግጥ ጨበጠ፡፡ የነገሩም ሁሉ ፍጻሜ ወደ አላህ ነው፡፡ 31|23|የካደም ሰው ክህደቱ አያሳዝንህ፡፡ መመለሻቸው ወደኛ ነው፤ የሠሩትንም ሁሉ እንነግራቸዋለን፡፡ አላህ በልቦች ውስጥ ያለን ሁሉ ያውቃልና፡፡ 31|24|ጥቂትን እናጣቅማቸዋለን፡፡ ከዚያም ወደ ብርቱ ቅጣት እናስገድዳቸዋለን፡፡ 31|25|ሰማያትንና ምድርንም የፈጠረ ማን እንደሆነ ብትጠይቃቸው በእርግጥ አላህ ነው ይላሉ፡፡ ምስጋና ለአላህ ይገባው በላቸው፡፡ ይልቁንም አብዛኛዎቹ አያውቁም፡፡ 31|26|በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ አላህ እርሱ ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡ 31|27|ከዛፍም በምድር ያለው ሁሉ ብእሮች ቢሆኑ ኖሮ ባሕሩም ከእርሱ (ማለቅ) በኋላ ሰባት ባህሮች የሚጨመሩለት ሆኖ (ቀለም ቢሆንና ቢጻፍባቸው) የአላህ ቃላት ባላለቀች ነበር፡፡ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና፡፡ 31|28|እናንተን መፍጠርና እናንተን መቀስቀስ እንደ አንዲት ነፍስ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ አላህ ሰሚ ተመልካች ነውና፡፡ 31|29|አላህ ሌሊትን በቀን ውስጥ የሚያስገባ፣ ቀንንም በሌሊት ውስጥ የሚያስገባ፣ ፀሐይንና ጨረቃንም የገራ መሆኑን አታይምን? ሁሉም እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ ይሮጣሉ፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 31|30|ይህ አላህ እርሱ እውነት ከእርሱም ሌላ የሚግገዙት (ጣዖት) ውሸት በመሆኑና አላህም እርሱ የበላይ ታላቅ በመሆኑ ነው፡፡ 31|31|ከአስደናቂ ምልክቶቹ ሊያሳያችሁ መርከቦች በአላህ ችሮታ በባህር ውስጥ የሚንሻለሉ መሆናቸውን አታይምን? በዚህ ውስጥ በጣም ታጋሽ አመስጋኝ ለሆኑ ሁሉ ተዓምራቶች አሉበት፡፡ 31|32|እንደ ጥላዎችም የሆነ ማዕበል በሸፈናቸው ጊዜ አላህን ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ ያጠሩ ሆነው ይጠሩታል፡፡ ወደ የብስም ባዳናቸው ጊዜ ከእነሱ ትክክለኛም አልለ፡፡ (ከእነርሱም የሚክድ አለ)፡፡ በአንቀጾቻችንም አታላይ ከዳተኛ ሁሉ እንጂ ሌላው አይክድም፡፡ 31|33|እናንተ ሰዎች ሆይ! ጌታችሁን ፍሩ፡፡ ወላጅም ከልጁ (በምንም) የማይጠቅምበትን፤ ተወላጅም እርሱ ወላጅን በምንም ጠቃሚ የማይሆንበትን ቀን ፍሩ፡፡ የአላህ ቀጠሮ እውነት ነውና፡፡ ቅርቢቱም ሕይወት አትሸንግላችሁ፡፡ በአላህም (መታገስ) አታላዩ (ሰይጣን) አያታልላችሁ፡፡ 31|34|አላህ የሰዓቲቱ ዕውቀት እርሱ ዘንድ ብቻ ነው፡፡ ዝናብንም ያወርዳል፡፡ በማሕፀኖችም ውስጥ ያለን ሁሉ ያውቃል፡፡ ማንኛይቱ ነፍስም ነገ የምትሠራውን አታውቅም፡፡ ማንኛይቱ ነፍስም በየትኛው ምድር እንደምትሞት አታውቅም፡፡ አላህ ዐዋቂ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 32|1|አ.ለ.መ (አሊፍ ላም ሚም)፡፡ 32|2|የመጽሐፉ መወረድ ጥርጥር የለበትም፡፡ ከዓለማት ጌታ ነው፡፡ 32|3|ይልቁንም «ቀጠፈው» ይላሉን? አይደለም፡፡ እርሱ ከጌታህ ዘንድ የሆነ እውነት ነው፡፡ በእርሱ ከአንተ በፊት ከአስፈራሪ (ነቢይ) ያልመጣባቸውን ሕዝቦች ልታስፈራራበት (ያወረደልህ ነው)፡፡ እነርሱ ሊምመሩ ይከጀላልና፡፡ 32|4|አላህ ያ ሰማያትንና ምድርን በመካከላቸውም ያለውን ሁሉ በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ ከዚያም በዐርሹ ላይ (ስልጣኑ) የተደላደለ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ ለእናንተ ረዳትም አማላጅም ምንም የላችሁም፤ አትገሰጹምን? 32|5|ነገሩን ሁሉ ከሰማይ ወደ ምድር ያዘጋጃል፡፡ ከዚያም ከምትቆጥሩት (ዘመን) ልኩ ሺህ ዓመት በሆነ ቀን ውስጥ ወደርሱ ይወጣል (ይመለሳል)፡፡ 32|6|ይህ (ይህንን የሠራው) ሩቁንም ቅርቡንም ሁሉ ዐዋቂው አሸናፊው፣ አዛኙ (ጌታ) ነው፡፡ 32|7|ያ የፈጠረውን ነገር ሁሉ ያሳመረው የሰውንም ፍጥረት ከጭቃ የጀመረው ነው፡፡ 32|8|ከዚያም ዘሮቹን ከተንጣለለ፣ ከደካማ ውሃ ያደረገ ነው፡፡ 32|9|ከዚያም (ቅርጹን) አስተካከለው፡፡ በእርሱ ውስጥም ከመንፈሱ ነፋበት፤ (ነፍስ ዘራበት)፡፡ ለእናንተም ጆሮዎችን፣ ዓይኖችንና ልቦችንም አደረገላችሁ፡፡ በጣም ጥቂትን ብቻ ታመሰግናላችሁ፡፡ 32|10|«በምድርም ውስጥ (በስብሰን) በጠፋን ጊዜ እኛ በአዲስ መፈጠር ውስጥ እንሆናለን?» አሉ፡፡ በእውነቱ እነርሱ በጌታቸው መገናኘት ከሓዲዎች ናቸው፡፡ 32|11|«በእናንተ የተወከለው መልአከ ሞት ይገድላችኋል፡፡ ከዚያም ወደ ጌታችሁ ትመለሳላችሁ» በላቸው፡፡ 32|12|አመጸኞችም በጌታቸው ዘንድ ራሶቻቸውን ያቀረቀሩ ሆነው «ጌታችን ሆይ! አየን፣ ሰማንም፡፡ መልካምን እንሠራለንና (ወደ ምድረ ዓለም) መልሰን፡፡ እኛ አረጋጋጮች ነን፡፡» (የሚሉ ሲሆኑ) ብታይ ኖሮ (አስደንጋጭን ነገር ታይ ነበር)፡፡ 32|13|በሻንም ኖሮ ነፍስን ሁሉ ቅንነቷን (እምነቷን) በሰጠናት ነበር፡፡ ግን ገሀነምን ከአጋንንትና ከሰዎች የተሰበሰቡ ሆነው በእርግጥ እሞላለሁ ማለት ቃሉ ከእኔ ተረጋግጧል፡፡ 32|14|ይህንንም ቀናችሁን መገናኘትን በመርሳታችሁ ምክንያት (ቅጣትን) ቅመሱ! እኛ ተውናችሁ፡፡ ትሠሩት በነበራችሁትም ጥፋት ዘውታሪን ቅጣት ቅመሱ (ይባላሉ)፡፡ 32|15|በአንቀጾቻችን የሚያምኑት እነዚያ በእርሷ በተገሰጹ ጊዜ ሰጋጆች ሆነው የሚወድቁትና እነርሱም የማይኮሩ ሆነው በጌታቸው ምስጋና (ተጎናጽፈው) የሚያወድሱት ብቻ ናቸው፡፡ 32|16|ጌታቸውን ለመፍራትና ለመከጀል የሚጠሩት ሆነው ጎኖቻቸው ከመጋደሚያ ስፍራዎች ይራራቃሉ፡፡ ከሰጠናቸውም (ጸጋ) ይለገሳሉ፡፡ 32|17|ይሠሩትም በነበሩት ለመመንዳት ከዓይኖች መርጊያ ለእነርሱ የተደበቀላቸውን (ጸጋ) ማንኛይቱም ነፍስ አታውቅም፡፡ 32|18|አማኝ የሆነ ሰው አመጸኛ እንደ ሆነ ሰው ነውን? አይስተካከሉም፡፡ 32|19|እነዚያ ያመኑና መልካሞችን የሰሩማ ለእነርሱ ይሠሩት በነበሩት ምክንያት መስተንግዶ ሲሆኑ መኖሪያ ገነቶች አሏቸው፡፡ 32|20|እነዚያ ያመጹትማ፤ መኖሪያቸው እሳት ናት፡፡ ከእርሷ መውጣትን በፈለጉ ቁጥር በእርሷ ውስጥ ይመለሳሉ፡፡ ለእነርሱም «ያንን በእርሱ ታስተባብሉበት የነበራችሁትን የእሳት ቅጣት ቅመሱ» ይባላሉ፡፡ 32|21|ይመለሱ ዘንድም ከትልቁ ቅጣት በፊት (በዚህ ዓለም) ከትንሹ ቅጣት በእርግጥ እናቀምሳቸዋለን፡፡ 32|22|በጌታውም አንቀጾች ከተገሰጸና ከዚያም ከተዋት ሰው ይበልጥ በደለኛ ማነው? (የለም)፤ እኛ ከተንኮለኞቹ ተበቃዮች ነን፡፡ 32|23|ሙሳንም መጽሐፍን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ እርሱን ከመገናኘትህም በመጠራጠር ውስጥ አትሁን፡፡ ለእስራኤል ልጆችም መሪ አደረግነው፡፡ 32|24|በታገሱና በተዓምራቶቻችን የሚያረጋግጡ በሆኑም ጊዜ ከእነርሱ በትዕዛዛችን የሚመሩ መሪዎች አደረግን፡፡ 32|25|ጌታህ እርሱ በዚያ በእርሱ ይለያዩበት በነበሩት ነገር በትንሣኤ ቀን በመካከላቸው (በፍርድ) ይለያል፡፡ 32|26|ከክፍለ ዘመናት ሰዎች ብዙዎችን ያጠፋን መሆናችን በመኖሪያዎቻቸው የሚሄዱ ሲሆኑ ለእነርሱ አልተገለፀላቸውምን? በዚህ ውስጥ ምልክቶች አሉት፤ አይሰሙምን? 32|27|እኛ ውሃን ወደ ደረቅ ምድር የምንነዳ እንስሶቻቸውና ነፍሶቻቸው ከእርሱ የሚበሉለትንም አዝመራ በእርሱ የምናወጣ መኾናችንን አያዩምን? አይመለከቱምን? 32|28|«ከእውነተኞችም እንደሆናችሁ ይህ ፍርድ መቼ ነው?» ይላሉ፡፡ 32|29|«በፍርድ ቀን እነዚያን የካዱትን ሰዎች እምነታቸው አይጠቅማቸውም፡፡ እነርሱም ጊዜን አይሰጡም፤» በላቸው፡፡ 32|30|እነርሱንም ተዋቸው፡፡ ተጠባበቅም፤ እነርሱ ተጠባባቂዎች ናቸውና፡፡ 33|1|አንተ ነቢዩ ሆይ! አላህን ፍራ፡፡ ከሓዲዎችንና መናፍቃንንም አትታዘዝ፡፡ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡ 33|2|ከጌታህም ወደ አንተ የሚወረደውን ተከተል፡፡ አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውሰጠ አዋቂ ነውና፡፡ 33|3|በአላህም ላይ ተመካ፡፡ መመኪያም በአላህ በቃ፡፡ 33|4|አላህ ለአንድ ሰው በሆዱ ውስጥ ሁለትን ልቦች አላደረገም፡፡ ሚስቶቻችሁንም እነዚያን ከእነርሱ እንደናቶቻችሁ ጀርባዎች ይሁኑብን የምትሏቸውን እናቶቻችሁ አላደረገም፡፡ ልጅ በማድረግ የምታስጠጓቸውንም ልጆቻችሁ አላደረገም፡፡ ይህ በአፎቻችሁ የምትሉት ነው፡፡ አላህም እውነቱን ይናገራል፡፡ እርሱም ትክክለኛውን መንገድ ይመራል፡፡ 33|5|ለአባቶቻቸው (በማስጠጋት) ጥሯቸው፡፡ እርሱ አላህ ዘንድ ትክክለኛ ነው፡፡ አባቶቻቸውንም ባታውቁ በሃይማኖት ወንድሞቻችሁና ዘመዶቻችሁ ናቸው፡፡ በእርሱ በተሳሳታችሁበት ነገርም በእናንተ ላይ ኀጢአት የለባችሁም፡፡ ግን ልቦቻችሁ ዐውቀው በሠሩት (ኀጢአት አለባችሁ)፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 33|6|ነቢዩ በምእምናን ከነፍሶቻቸው ይበልጥ ተገቢ ነው፡፡ ሚስቶቹም እናቶቻቸው ናቸው፡፡ የዝምድና ባለቤቶችም ከፊላቸው በከፊሉ (ውርስ) በአላህ መጽሐፍ ውስጥ ከምእምናንና ከስደተኞቹ ይልቅ የተገባቸው ናቸው፡፡ግን ወደ ወዳጆቻችሁ (በኑዛዜ) መልካምን ብትሰሩ (ይፈቀዳል)፡፡ ይህ በመጽሐፉ ውሰጥ የተመዘገበ ነው፡፡ 33|7|ከነቢዮችም የጠበቀ ኪዳናቸውን ከአንተም፣ ከኑሕም፣ ከኢብራሒምም፣ ከሙሳም ከመርየም ልጅ ዒሳም በያዝን ጊዜ (አስታወስ)፡፡ ከእነርሱም የከበደን ቃል ኪዳን ያዝን፡፡ 33|8|(አላህ) እውነተኞችን ከውነታቸው ሊጠይቅ (ይህንን ሠራ)፡፡ ለከሓዲዎችም አሳማሚን ቅጣት አዘጋጀ፡፡ 33|9|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ብዙ ሰራዊት በመጣችባችሁና በእነርሱ ላይ ነፋስንና ያላያችኋትን ሰራዊት በላክን ጊዜ በእናንተ ላይ (ያደረገላችሁን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 33|10|ከበላያችሁም ከናንተ በታችም በመጡባችሁ ጊዜ፣ ዓይኖችም በቃበዙ፣ ልቦችም ላንቃዎች በደረሱና በአላህም ጥርጣሬዎችን በጠረጠራችሁ ጊዜ (ያደረገላችሁን አስታውሱ)፡፡ 33|11|እዚያ ዘንድ ምእምናን ተሞከሩ፡፡ ብርቱን መንቀጥቀጥም ተንቀጠቀጡ፡፡ 33|12|መናፍቆችና እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ያለባቸውም «አላህና መልክተኛው ማታለልን እንጂ ሌላን አልቀጠሩንም» በሚሉ ጊዜ (ያደረገላችሁን አስታውሱ)፡፡ 33|13|ከእነርሱም የሆኑ ጭፍሮች «የየስሪብ ሰዎች ሆይ! ለእናንተ ስፍራ የላችሁምና ተመለሱ» ባሉ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡ ከእነርሱም «ከፊሎቹ እርሷ ነውረኛ ሳትሆን ቤቶቻችን ነውረኛ ናቸው» የሚሉ ሆነው ነቢዩን (ከጦሩ ለመመለስ) ፈቃድን ይጠይቃሉ፡፡ መሸሽን እንጂ ሌላ አይፈልጉም፡፡ 33|14|በእነርሱም ላይ (ቤቶቻቸው) ከየቀበሌዋ በተገባባት ከዚያም ከኢስላም መመለስን በተጠየቁ ኖሮ በሠሯት ነበር፡፡ በእርሷም ጥቂትን ጊዜ እንጂ አይቆዩም ነበር፡፡ 33|15|ጀርባዎችንም ላያዞሩ ከዚያ በፊት በእርግጥ አላህን ቃል ኪዳን የተጋቡ ነበሩ፡፡ የአላህም ቃል ኪዳን የሚጠየቁበት ነው፡፡ 33|16|ከሞት ወይም ከመገደል ብትሸሹ መሸሻችሁ ፈጽሞ አይጠቅማችሁም፡፡ ያን ጊዜም ጥቂትን እንጂ የምትጣቀሙ አትደረጉም በላቸው፡፡ 33|17|«(አላህ) በእናንተ ክፉን ነገር ቢሻ ያ ከአላህ የሚጠብቃችሁ ማነው? ወይም ለእናንተ ችሮታን ቢሻ፤ (በክፉ የሚነካችሁ ማነው?)» በላቸው፤ ከአላህም ሌላ ለእነርሱ ወዳጅም ረዳትም አያገኙም፡፡ 33|18|ከእናንተ ውስጥ የሚያሳንፉትን፣ ለወንድሞቻቸውም «ወደኛ ኑ» የሚሉትን፣ ውጊያንም ጥቂትን እንጂ የማይመጡትን በእርግጥ አላህ ያውቃቸዋል፡፡ 33|19|በእናንተ ላይ (እርዳታን) የነፈጉ ሆነው እንጅ (የማይመጡትን)፣ ሽብሩም በመጣ ጊዜ እንደዚያ ከሞት (መከራ) በርሱ ላይ የሚሸፍን ዐደጋ እንደወደቀበት ዓይኖቻቸው ወዲያና ወዲህ የምትዞር ኾና ወዳንተ ሲመለከቱ ታያቸዋለህ፡፡ ሽብሩም በኼደ ጊዜ በገንዘብ ላይ የሚሳሱ ኾነው በተቡ ምላሶች ይነድፏችኋል፡፡ እነዚያ አላመኑም፡፡ ስለዚህ አላህ ሥራዎቻቸውን አበላሸ፡፡ ይህም በአላህ ላይ ገርነው፡፡ 33|20|(መናፍቆች) አሕዛብን አልኼዱም ብለው ያስባሉ፡፡ አሕዛቦቹም ቢመጡ እነርሱ በዘላኖች ውስጥ በገጠር (የራቁ) ሊሆኑ ይመኛሉ፡፡ ከወሬዎቻችሁ ይጠይቃሉ፡፡ በእናንተ ውስጥ በነበሩም ኖሮ ጥቂትን እንጂ አይዋጉም ነበር፡ 33|21|ለእናንተ አላህንና የመጨረሻውን ቀን የሚከጅል ለሆነ ሰው፣ አላህንም በብዙ ለሚያወሳ በአላህ መልዕክተኛ መልካም መከተል አልላችሁ፡፡ 33|22|አማኞቹም አሕዛብን ባዩ ጊዜ «ይህ አላህና መልክተኛው የቀጠሩን ነው፡፡ አላህና መልክተኛውም እውነትን ተናገሩ» አሉ፡፡ (ይህ) እምነትንና መታዘዝንም እንጂ ሌላን አልጨመረላቸውም፡፡ 33|23|ከአማኞቹ በእርሱ ላይ ለአላህ ቃል ኪዳን የገቡበትን በእውነት የፈጸሙ ወንዶች አልሉ፡፡ ከነርሱም ስለቱን የፈጸመ (ለሃይማኖቱ የተገደለ) አልለ፤ ከነርሱም ገና የሚጠባበቅ አልለ፡፡ (የገቡበትን ቃል) መለወጥንም አልለወጡም፡፡ 33|24|አላህ እውነተኞችን በውነተኛነታቸው ሊመነዳ መናፍቃንንም ቢሻ ሊቀጣ ወይም (ቢመለሱ) በእነርሱ ላይ ጸጸታቸውን ሊቀበል (ይህን አደረገ)፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 33|25|እነዚያንም የካዱትን በቁጭታቸው የተመሉ መልካምን ነገር ያላገኙ ሆነው አላህ መለሳቸው፡፡ አማኞቹንም አላህ መጋደልን በቃቸው፡፡ አላህም ብርቱ አሸናፊ ነው፡፡ 33|26|እነዚያንም ከመጽሐፉ ባለቤቶች (አሕዛቦችን) የረዷቸውን (ቁረይዟን) ከምሽጎቻቸው አወረዳቸው፡፡ በልቦቻቸውም ውስጥ መባባትን ጣለባቸው፡፡ ከፊሉን ትገድላላችሁ፡፡ ከፊሉንም ትማርካላችሁ፡፡ 33|27|ምድራቸውንም፣ ቤቶቻቸውንም፣ ገንዘቦቻቸውንም ገና ያልረገጣችኋትንም ምድር አወረሳችሁ፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 33|28|አንተ ነቢይ ሆይ! ለሚስቶችህ (እንዲህ) በላቸው «ቅርቢቱን ሕይወትና ጌጧን የምትፈልጉ እንደ ሆናችሁ ኑ፤ አጣቅማችኋለሁና፡፡ መልካምንም ማሰማራት (በመፍታት) አሰማራችኋለሁና፡፡ 33|29|«አላህንና መልክተኛውን የመጨረሻይቱን አገርም የምትፈልጉ ብትሆኑም፤ እነሆ አላህ ከእናንተ ለመልካም ሠሪዎቹ ትልቅን ምንዳ አዘጋጅቷል፡፡» 33|30|የነቢዩ ሴቶች ሆይ! ከእናንተ ውስጥ ግልጽ የሆነን መጥፎ ሥራ የምትሠራ ለእርሷ ቅጣቱ ሁለት እጥፍ ሆኖ ይነባበርባታል፡፡ ይህም በአላህ ላይ ገር ነው፡፡ 33|31|ከእናንተም ለአላህና ለመልክተኛው የምትታዘዝ መልካም ሥራንም የምትሠራ ምንዳዋን ሁለት ጊዜ እንሰጣታለን፡፡ ለእርሷም የከበረን ሲሳይ አዘጋጅተንላታል፡፡ 33|32|የነቢዩ ሴቶች ሆይ! ከሴቶች እንደማናቸው አይደላችሁም፡፡ አላህን ብትፈሩ (ትበልጣላችሁ)፡፡ ያ በልቡ ውስጥ በሽታ ያለበት እንዳይከጅል በንግግር አትለስልሱም፡፡ መልካምንም ንግግር ተናገሩ፡፡ 33|33|በቤቶቻችሁም ውስጥ እርጉ፡፡ እንደ ፊተኛይቱ መሃይምነት ጊዜ መገለጥም በማጌጥ አትገለጡ፡፡ ሶላትንም በደንቡ ስገዱ፡፡ ዘካንም ስጡ፡፡ አላህንና መልክተኛውንም ታዘዙ፡፡ የነቢዩ ቤተሰቦች ሆይ! አላህ የሚሻው ከእናንተ ላይ እርክሰትን ሊያስወግድና ማጥራትንም ሊያጠራችሁ ብቻ ነው፡፡ 33|34|ከአላህ አንቀጾችና ከጥበቡም በቤቶቻችሁ የሚነበበውን አስታውሱ፡፡ አላህ እዝነቱ ረቂቅ ውስጠ ዐዋቂ ነውና፡፡ 33|35|ሙስሊሞች ወንዶችና ሙስሊሞች ሴቶች፣ ምእምናንና ምእምናትም፣ ታዛዦች ወንዶችና ታዛዦች ሴቶችም፣ እውነተኞች ወንዶችና እውነተኞች ሴቶችም፣ ታጋሾች ወንዶችና ታጋሾች ሴቶችም፣ አላህን ፈሪዎች ወንዶችና አላህን ፈሪዎች ሴቶችም፣ መጽዋቾች ወንዶችና መጽዋቾች ሴቶችም፣ ጿሚዎች ወንዶችና ጿሚዎች ሴቶችም፣ (ካልተፈቀደ ሥራ) ብልቶቻቸውን ጠባቂዎች ወንዶችና ጠባቂ ሴቶችም፣ አላህን በብዙ አውሺዎች ወንዶችና አውሺዎች ሴቶችም፣ አላህ ለእነርሱ ምሕረትንና ታላቅን ምንዳ አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ 33|36|አላህና መልክተኛውም ነገርን በፈረዱ ጊዜ ለምእምናንና ለምእምናት ከነገራቸው ለእነርሱ ምርጫ ሊኖራቸው አይገባም! የአላህንና የመልክተኛውንም ትእዛዝ የጣሰ ሰው ግልጽ የሆነን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ፡፡ 33|37|ለእዚያም አላህ በእርሱ ላይ ለለገሰለትና (አንተም ነጻ በማውጣት) በእርሱ ላይ ለለገስክለት ሰው (ለዘይድ) አላህ ገላጩ የሆነን ነገር በነፍስህ ውስጥ የምትደብቅና አላህ ልትፈራው ይልቅ የተገባው ሲሆን ሰዎችን የምትፈራ ሆነህ «ሚስትህን ባንተ ዘንድ ያዝ፤ (ከመፍታት) አላህንም ፍራ» በምትል ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ዘይድም ከእርሷ ጉዳይን በፈጸመ ጊዜ በምእምናኖች ላይ ልጅ አድርገው ባስጠጉዋቸው (ሰዎች) ሚስቶች ከእነርሱ ጉዳይን በፈጸሙ ጊዜ (በማግባት) ችግር እንዳይኖርባቸው እርሷን አጋባንህ፡፡ የአላህም ትእዛዝ ተፈጻሚ ነው፡፡ 33|38|በነቢዩ ላይ አላህ ለእርሱ በፈረደው ነገር ምንም ችግር ሊኖርበት አይገባም፡፡ በእነዚያ ከዚያ በፊት ባለፉት (ነቢያት) አላህ ደነገገው፡፡ የአላህም ትእዛዝ የተፈረደ ፍርድ ነው፡፡ 33|39|ለእነዚያ የአላህን መልእክቶች ለሚያደርሱና ለሚፈሩት ከአላህ በስተቀርም አንድንም ለማይፈሩት (ተደነገገ)፡፡ ተቆጣጣሪም በአላህ በቃ፡፡ 33|40|ሙሐመድ ከወንዶቻችሁ የአንድም ሰው አባት አይደለም፡፡ ግን የአላህ መልክተኛና የነቢዮች መደምደሚያ ነው፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 33|41|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ብዙ ማውሳትን አውሱት፡፡ 33|42|በቀኑ መጀመሪያና መጨረሻም አጥሩት፡፡ 33|43|እርሱ ያ በእናንተ ላይ እዝነትን የሚያወርድ ነው፡፡ መላእክቶቹም (እንደዚሁ ምሕረትን የሚለምኑላችሁ ናቸው)፡፡ ከጨለማዎች ወደ ብርሃን ያወጣችሁ ዘንድ (ያዝንላችኋል)፡፡ ለአማኞችም በጣም አዛኝ ነው፡፡ 33|44|በሚገናኙት ቀን መከባበሪያቸው ሰላም መባባል ነው፡፡ ለእነርሱም የከበረን ምንዳ አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ 33|45|አንተ ነቢዩ ሆይ! እኛ መስካሪ፣ አብሳሪና አስፈራሪም አድርገን ላክንህ፡፡ 33|46|ወደ አላህም በፈቃዱ ጠሪ፣ አብሪ ብርሃንም (አድርገን ላክንህ)፡፡ 33|47|አማኞችንም ከአላህ ዘንድ ለእነርሱ ታላቅ ችሮታ ያላቸው መኾኑን አብስራቸው፡፡ 33|48|ከሓዲዎችንና መናፍቃንንም አትታዘዛቸው፡፡ ማሰቃየታቸውንም (ለአላህ) ተው፡፡ በአላህም ላይ ተጠጋ፡፡ መጠጊያም በአላህ በቃ፡፡ 33|49|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ምእምናትን ባገባችሁና ከዚያም ሳትነኩዋቸው በፊት በፈታችኋቸው ጊዜ ለእናንተ በእነርሱ ላይ የምትቆጥሩዋት ዒዳ ምንም የላችሁም፡፡ አጣቅሟቸውም፤ (ጉርሻ ስጧቸው)፡፡ መልካም ማሰናበትንም አሰናብቷቸው፡፡ 33|50|አንተ ነቢዩ ሆይ! እኛ እነዚያን መህሮቻቸውን የሰጠሃቸውን ሚስቶችህን፣ አላህ ባንተ ላይ ከመለሰልህም እነዚያን እጅህ የጨበጠቻቸውን ምርኮኞች፣ እነዚያንም ከአንተ ጋር የተሰደዱትን የአጎትህን ሴቶች ልጆች፣ የአክስቶችህንም ሴቶች ልጆች፣ የየሹማህንም ሴቶች ልጆች፣ የየሹሜዎችህንም ሴቶች ልጆች (ማግባትን) ለአንተ ፈቅደንልሃል፡፡ የአመነችንም ሴት ነፍሷን (ራሷን) ለነቢዩ ብትሰጥ ነቢዩ ሊያገባት የፈለገ እንደ ኾነ ከምእምናን ሌላ ላንተ ብቻ የጠራች ስትኾን (ፈቀድንልህ)፡፡ በእነርሱ (በምእምናን) ላይ በሚስቶቻቸውና እጆቻቸው በጨበጧቸው (ባሮች ነገር) ግዴታ ያደረግንባቸውን በእርግጥ ዐውቀናል፡፡ ባንተ ላይ ችግር እንዳይኖር (ያለፉትን ፈቀድንልህ)፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 33|51|ከእነርሱ የምትሻትን ታቆያለህ፡፡ የምትሻውንም ወደ አንተ ታስጠጋለህ፡፡ (በመፍታት) ከአራቅሃትም የፈለግሃትን (በመመለስ ብታስጠጋ) በአንተ ላይ ኀጢአት የለብህም፡፡ ይህ ዓይኖቻቸው ወደ መርጋት፣ ወደ አለማዘናቸውም፣ ለሁሉም በሰጠሃቸው ነገር ወደ መውደዳቸውም በጣም የቀረበ ነው፡፡ አላህም በልቦቻችሁ ውስጥ ያለውን ሁሉ ያውቃል፡፡ አላህም ዐዋቂ ታጋሽ ነው፡፡ 33|52|ከእነዚህ በኋላ እጅህ ከጨበጠቻቸው (ባሮች) በስተቀር ሴቶች ለአንተ አይፈቀዱልህም፡፡ ከሚስቶችም መልካቸው ቢደንቅህም እንኳ በእነርሱ ልታላውጥ (አይፈቀደልህም)፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ተጠባባቂ ነው፡፡ 33|53|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! መድረሱን የማትጠባበቁ ስትኾኑ ወደ ምግብ ካልተፈቀደላችሁ በስተቀር የነቢዩን ቤቶች (በምንም ጊዜ) አትግቡ፡፡ ግን በተጠራችሁ ጊዜ ግቡ፡፡ በተመገባችሁም ጊዜ ወዲያውኑ ተበተኑ፡፡ ለወግ የምትጫወቱ ኾናችሁም (አትቆዩ)፡፡ ይህ ነቢዩን በእርግጥ ያስቸግራል፡፡ ከእናንተም ያፍራል፡፡ ግን አላህ ከእውነት አያፍርም፡፡ ዕቃንም (ለመዋስ) በጠየቃችኋቸው ጊዜ ከመጋረጃ ኋላ ኾናችሁ ጠይቋቸው፡፡ ይህ ለልቦቻችሁ፤ ለልቦቻቸውም የበለጠ ንጽሕና ነው፡፡ የአላህንም መልክተኛ ልታስቸግሩ ሚስቶቹንም ከእርሱ በኋላ ምንጊዜም ልታገቡ ለእናንተ አይገባችሁም፡፡ ይህ አላህ ዘንድ ከባድ (ኀጢአት) ነው፡፡ 33|54|ማንኛውንም ነገር ብትገልጹ ወይም ብትደብቁት (በርሱ ይመነዳችኋል)፡፡ አላህ ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 33|55|(የነቢዩ ሚስቶች) በአባቶቻቸው፣ በወንዶች ልጆቻቸውም፣ በወንድሞቻቸውም፣ ወንድሞቻቸው ወንዶች ልጆችም፣ በእኅቶቻቸው ወንዶች ልጆችም፣ (ምእምናት በኾኑት) በሴቶቻቸውም፣ እጆቻቸው በጨበጧቸውም ባሮች (አጠገብ በመገለጥ) በእነርሱ ላይ ኃጢአት የለባቸውም፡፡ (ሴቶች ሆይ! ታዘዙ) አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ መስካሪ ነውና፡፡ 33|56|አላህና መላእክቱ በነቢዩ ላይ የአክብሮት እዝነትን ያወርዳሉ፡፡ እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በእርሱ ላይ የአክብሮት እዝነትን አውርዱ፡፡ የማክበርንም ሰላምታ ሰላም በሉ፡፡ 33|57|እነዚያ አላህንና መልክተኛውን የሚያስከፉ በቅርቢቱ ዓለም በመጨረሻይቱም አላህ ረግሟቸዋል፡፡ ለእነርሱም አዋራጅን ቅጣት ደግሶላቸዋል፡፡ 33|58|እነዚያንም ምእምናንንና ምእምናነትን ባልሰሩት ነገር (በመዝለፍ) የሚያሰቃዩ ዕብለትንና ግልጽ ኃጢአትን በእርግጥ ተሸከሙ፡፡ 33|59|አንተ ነቢዩ ሆይ! ለሚስቶቸህ፣ ለሴቶች ልጆችህም፣ ለምእምናን ሚስቶችም ከመከናነቢያዎቻቸው በላያቸው ላይ እንዲለቁ ንገራቸው፡፡ ይህ እንዲታወቁና (በባለጌዎች) እንዳይደፈሩ ለመኾን በጣም የቀረበ ነው፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 33|60|መናፍቃንና እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ (የአመንዝራነት) በሽታ ያለባቸው በመዲናም ውሰጥ (በወሬ) አሸባሪዎቹ (ከዚህ ሥራቸው) ባይከለከሉ በእነርሱ ላይ በእርግጥ እንቀሰቅስሃለን፡፡ ከዚያም በእርሷ ውስጥ ጥቂትን እንጂ አይጎራበቱህም፡፡ 33|61|የተረገሙ ኾነው እንጂ (አይጎራበቱህም)፡፡ በየትም ስፍራ ቢገኙ ይያዛሉ፡፡ መገደልንም ይገደላሉ፡፡ 33|62|(ይህቺ) በእነዚያ በፊት ባለፉት (ላይ የደነገጋት) የአላህ ድንጋጌ ናት፡፡ ለአላህም ድንጋጌ ፈጽሞ መለወጥን አታገኝም፡፡ 33|63|ሰዎች ከሰዓቲቱ ይጠይቁሃል፡፡ «ዕውቀትዋ አላህ ዘንደ ብቻ ነው፤» በላቸው፡፡ የሚያሳወቅህም ምንድን ነው! ሰዓቲቱ በቅርብ ጊዜ ልትኾን ይከጀላል፡፡ 33|64|አላህ ከሓዲዎችን በእርግጥ ረግሟቸዋል፡፡ ለእነርሱም የተጋጋመችን እሳት አዘጋጅቷል፡፡ 33|65|በእርሷ ውስጥ ዘለዓለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ፤ ወዳጅም ረዳትም አያገኙም፡፡ 33|66|ፊቶቻቸው በእሳት ውሰጥ በሚገለባበጡ ቀን «ዋ ምኞታችን! አላህን በተገዛን መልክተኛውንም በታዘዝን ኖሮ» እያሉ ይጸጸታሉ፡፡ 33|67|ይላሉም «ጌታችን ሆይ! እኛ ጌቶቻችንንና ታላላቆቻችንን ታዘዝን፡፡ መንገዱንም አሳሳቱን፡፡ 33|68|«ጌታችን ሆይ! ከቅጣቱ እጥፍን ስጣቸው፡፡ ታላቅን እርግማንም እርገማቸው፡፡» 33|69|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እንደእነዚያ ሙሳን እንዳሰቃዩት ሰዎች አትኹኑ፡፡ ካሉትም ነገር ሁሉ አላህ አጠራው፡፡ አላህም ዘንድ ባለሞገስ ነበር፡፡ 33|70|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ፡፡ ትክክለኛንም ንግግር ተናገሩ፡፡ 33|71|ሥራዎቻችሁን ለእናንተ ያበጅላችኋልና፡፡ ኀጢአቶቻችሁንም ለእናንተ ይምርላችኋል፡፡ አላህንና መልክተኛውን የሚታዘዝም ሰው በእርግጥ ታላቅን እድል አገኘ፡፡ 33|72|እኛ አደራን በሰማያትና በምድር፣ በተራራዎችም ላይ አቀረብናት፡፡ መሸከሟንም እንቢ አሉ፡፡ ከእርሷም ፈሩ፡፡ ሰውም ተሸከማት፡፡ እርሱ በጣም በደለኛ ተሳሳች ነውና፡፡ 33|73|መናፍቃንንና መናፍቃትን፣ ወንዶች አጋሪዎችንና ሴቶች አጋሪዎችንም አላህ ሊቀጣና በምእምናንና በምእምናትም ላይ አላህ ንስሓን ሊቀበል (አደራዋን ሰው ተሸከማት)፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 34|1|ምስጋና ለዚያ በሰማያትም ያለ በምድርም ያለ ሁሉ የርሱ ለኾነው ለአላህ ይገባው፡፡ በመጨረሻይቱም ዓለም ምስጋና ለእርሱ ብቻ ነው፡፡ እርሱም ብልሃተኛው ውስጠ ዐዋቂው ነው፡፡ 34|2|በምድር ውስጥ የሚገባውን ሁሉ ከእርሷም የሚወጣውን ከሰማይም የሚወርደውን በእርሷም ውስጥ የሚያርገውን ሁሉ ያውቃል፡፡ እርሱም አዛኙ መሓሪው ነው፡፡ 34|3|እነዚያ የካዱትም «ሰዓቲቱ አትመጣብንም» አሉ፡፡ በላቸው «አይደለም፤ ሩቁን ሁሉ ዐዋቂ በኾነው ጌታዬ እምላለሁ፡፡ በእርግጥ ትመጣባችኋለች፡፡ የብናኝ ክብደት ያክል እንኳ በሰማያትና በምድር ውስጥ ከእርሱ አይርቅም፡፡ ከዚህ ያነሰም ኾነ የበለጠ የለም በግልጹ መጽሐፍ ውስጥ የተመዘገበ ቢኾን እንጅ፡፡» 34|4|እነዚያን ያመኑትንና መልካሞችን የሠሩትን ሊመነዳ (ሰዓቲቱ ትመጣባችኋለች)፤ እነዚያ ለእነርሱ ምህረትና የከበረ ሲሳይ አላቸው፡፡ 34|5|እነዚያም የሚያመልጡ መስሏቸው አንቀጾቻችንን ለማፍረስ የጣሩ እነዚያ ለእነርሱ ከመጥፎ ቅጣት የኾነ አሳማሚ ስቃይ አላቸው፡፡ 34|6|እነዚያም ዕውቀትን የተሰጡት ያንን ከጌታህ ወዳንተ የተወረደውን እርሱ እውነትና አሸናፊ ምስጉን ወደ ኾነው አላህ መንገድ የሚመራ መኾኑን ያውቃሉ፡፡ 34|7|እነዚያም የካዱት «(ሙታችሁ) መበጣጠስን ሁሉ በተበጣጠሳችሁ ጊዜ እናንተ በአዲስ መፈጠር ውስጥ ትኾናላችሁ ብሎ የሚነግራችሁን ሰው እናሳያችሁን?» አሉ፡፡ 34|8|በአላህ ላይ ውሸትን ቀጠፈን? ወይስ በእርሱ ዕብደት አለበትን? (አሉ)፡፡ እንዳሉት አይደለም፡፡ እነዚያ በመጨረሻይቱ (ዓለም) የሚያምኑት (በእርሷ) በቅጣት ውስጥ (አሁን) በራቀ ስህተትም ውስጥ ናቸው፡፡ 34|9|ከሰማይና ከምድር በፊታቸውና በኋላቸው ወዳለው ሁሉ አይመለከቱምን? ብንሻ በእነርሱ ምድርን እንደረባባቸዋለን፡፡ ወይም በእነርሱ ላይ ከሰማይ ቁራጭን እንጥልባቸዋለን፤ በዚህ ውስጥ (ወደ ጌታው) ተመላሽ ለኾነ ባሪያ ሁሉ ምልክት አለበት፡፡ 34|10|ለዳውድም ከእኛ የኾነን ችሮታ በእርግጥ ሰጠነው፡፡ (አልንም)፡-«ተራራዎች ሆይ! ከእርሱ ጋር ውዳሴን መላልሱ፡፡ በራሪዎችንም (ገራንለት)፡፡ ብረትንም ለእርሱ አለዘብንለት፡፡» 34|11|ሰፋፊዎችን ጥሩሮች ሥራ፡፡ በአሠራርዋም መጥን፡፡ መልካምንም ሥራ ሥሩ፡፡ እኔ የምትሠሩትን ነገር ሁሉ ተመልካች ነኝና (አልነው)፡፡ 34|12|ለሱለይማንም ነፋስን የቀትር በፊት ጉዞዋ የወር መንገድ የቀትር በኋላ ጉዞዋም የወር መንገድ ሲኾን ገራንለት፡፡ የነሐስንም ምንጭ ለእርሱ አፈሰስንለት፡፡ ከጋኔኖችም በጌታው ፈቃድ በፊቱ የሚሠሩን (አደረግንለት)፡፡ ከነርሱም ውስጥ ከትእዛዛችን ዝንፍ የሚል ከነዲድ እሳት ቅጣት እናቀምሰዋለን፡፡ 34|13|ከምኩራቦች፣ ከምስሎችም እንደ ገንዳ ከኾኑ ገበታዎችም፣ ከተደላደሉ ታላላቅ ድስቶችም የሚሻውን ሁሉ ይሠሩለታል፡፡ (አልናቸውም) «የዳውድ ቤተሰቦች ሆይ! አመስጋኞች ኾናችሁ (ለጌታችሁ) ሥሩ፡፡» ከባሮቼ በጣም አመስጋኞቹም ጥቂቶች ናቸው፡፡ 34|14|በእርሱም ላይ ሞትን በፈጸምንበት ጊዜ መሞቱን በትሩን የምትበላ ተንቀሳቃሽ ምስጥ እንጂ ሌላ አላመለከታቸውም፡፡ በወደቀ ጊዜም ጋኔኖች ሩቅን ምስጢር የሚያወቁ በኾኑ ኖሮ በአዋራጅ ስቃይ ውስጥ የማይቆይ እንደነበሩ ተረዱ፡፡ 34|15|ለሰበእ በመኖሪያቸው በእውነት አስደናቂ ምልክት ነበራቸው፡፡ ከግራና ከቀኝ ሁለት አትክልቶች (ነበሯቸው)፡፡ «ከጌታችሁ ሲሳይ ብሉ፡፡ ለእርሱም አመስግኑ፡፡ (አገራችሁ) ውብ አገር ናት፡፡ (ጌታችሁ) መሓሪ ጌታም ነው» (ተባሉ)፡፡ 34|16|(ከማመስገን) ዞሩም፡፡ በእነርሱም ላይ የግድቡን ጎርፍ ለቀቅንባቸው፡፡ በአትክልቶቻቸውም ሁለት አትክልቶች፣ ባለመርጋጋ ፍሬዎችን፣ ባለጠደቻና ከቁርቁራም ባለጥቂት ዛፎችን ለወጥናቸው፡፡ 34|17|በመካዳቸው ይህንን መነዳናቸው፤ (እንዲህ ያለውን ቅጣት) በጣም ከሓዲን እንጂ ሌላውን እንቀጣለን? 34|18|በእነርሱና በዚያች በውስጧ በረከትን ባደረግንባት አገር (በሻም) መካከልም ቅጥልጥል ከተሞችን አደረግን፡፡ በእርሷም ጉዞን ወሰንን፡፡ «ጸጥተኞች ኾናችሁ በሌሊቶችም በቀኖችም ተጓዙ፤» (አልን)፡፡ 34|19|«ጌታችን ሆይ! በጉዞዎቻችን መካከል አራርቅልን» አሉም፡፡ ነፍሶቻቸውንም በደሉ፡፡ (መገረሚያ) ወሬዎችም አደረግናቸው፡፡ መበታተንንም ሁሉ በታተንናቸው፡፡ በዚህ ውስጥ በጣም ታጋሽና አመስጋኝ ለሆነ ሁሉ መገሰጫዎች አሉበት፡፡ 34|20|ኢብሊስም በእነርሱ ላይ ምኞቱን በእርግጥ ፈጸመ፤ ከአመኑትም የሆኑት ጭፍሮች በስተቀር ተከተሉት፡፡ 34|21|በመጨረሻይቱም ዓለም የሚያምነውን ከዚያ እርሱ ከእርሷ በመጠራጠር ውስጥ ከሆነው ሰው ለይተን እንድናውቅ እንጅ በእነርሱ ላይ ለእርሱ ምንም ስልጣን አልነበረውም፡፡ ጌታህም በነገሩ ሁሉ ላይ ተጠባባቂ ነው፡፡ 34|22|«እነዚያን ከአላህ ሌላ (አማልክት ብላችሁ) የምታስቧቸውን ጥሩ፡፡ በሰማያትም በምድርም ውስጥ የብናኝ ክብደት ያክል ምንንም አይችሉም፡፡ ለእነርሱም በሁለቱም ውስጥ ምንም ሽርክና የላቸውም፡፡ ከእነርሱም ለእርሱ ምንም አጋዥ የለውም፤» በላቸው፡፡ 34|23|ምልጃም እርሱ ለፈቀደለት ሰው ብቻ ቢሆን እንጂ እርሱ ዘንድ ምንም አትጠቅምም፡፡ ከልቦቻቸው ላይ ድንጋጤው በተገለጸም ጊዜ (ተማላጆቹ) «ጌታችሁ ምን አለ?» ይላሉ፡፡ (አማላጆቹ) «እውነትን አለ፤ እርሱም ከፍተኛው ታላቁ ጌታ ነው» ይላሉ፡፡ 34|24|«ከሰማያትና ከምድር (ዝናብንና በቃይን) የሚሰጣችሁ ማነው?» በላቸው፡፡ «አላህ ነው፡፡ እኛ ወይም እናንተ በትክክለኛው መንገድ ላይ ወይም በግልጽ መሳሳት ውስጥ ነን» በላቸው፡፡ 34|25|«ከአጠፋነው ጥፋት አትጠየቁም፡፡ ከምትሠሩትም ሥራ አንጠየቅም» በላቸው፡፡ 34|26|«ጌታችን በመካከላችን ይሰበስባል፡፡ ከዚያም በመካከላችን በእውነት ይፈርዳል፡፡ እርሱም በትክክል ፈራጁ ዐዋቂው ነው» በላቸው፡፡ 34|27|«እነዚያን ተጋሪዎች አድርጋችሁ በእርሱ ያስጠጋችኋቸውን (ጣዖታት) አሳዩኝ፡፡ ተዉ (አታጋሩ)፤ በእውነቱ እርሱ አሸናፊው ብልሃተኛው አላህ ነው» በላቸው፡፡ 34|28|አንተንም ለሰዎች ሁሉ በመላ አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን ቢሆን እንጂ አላክንህም፡፡ ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 34|29|«እውነተኞችም እንደ ሆናችሁ ይህ ቀጠሮ መቼ ነው?» ይላሉ፡፡ 34|30|«ለእናንተ ከእርሱ አንዲትንም ሰዓት የማትዘገዩበት የማትቀድሙበትም የቀጠሮ ቀን አላችሁ» በላቸው፡፡ 34|31|እነዚያ የካዱትም በዚህ ቁርኣን በዚያ ከበፊቱ ባለውም (መጽሐፍ) በጭራሽ አናምንም አሉ፡፡ በዳዮችም ከፊላቸው ወደ ከፊሉ ንግግርን የሚመላለሱ ሆነው በጌታቸው ዘንድ በሚቆሙ ጊዜ ብታይ ኖሮ፤ (አስደናቂን ነገር ታይ ነበር)፡፡ እነዚያ የተዋረዱት ለእነዚያ ለኮሩት «እናንተ ባልነበራችሁ ኖሮ አማኞች በኾን ነበር» ይላሉ፡፡ 34|32|እነዚያ የኮሩት ለእነዚያ ለተዋረዱት «ከትክክለኛው እምነት ከመጣላችሁ በኋላ እኛ ከለከልናችሁን? አይደለም (እናንተው) ከሓዲዎች ነበራችሁ» ይሏቸዋል፡፡ 34|33|እነዚያም የተዋረዱት ለእነዚያ ለኮሩት «አይደለም፤ በአላህ እንድንክድና ለእርሱ ባላንጣዎችን እንድናደርግ ስታዙን (የከለከለን) የሌሊትና የቀን ዱለታችሁ ነው» ይላሉ፡፡ ቅጣቱንም ባዩ ጊዜ ጸጸትን ይገልጻሉ፡፡ በእነዚያም በካዱት አንገቶች ላይ እንዛዝሎችን እናደርጋለን፡፡ ይሠሩት የነበሩትን እንጂ ሌላን ይመነዳሉን? 34|34|በከተማም አስፈራሪን አልላክንም፡፡ ነዋሪዎችዋ «እኛ በዚያ በርሱ በተላካችሁበት ከሓዲዎች ነን» ያሉ ቢኾኑ እንጂ፡፡ 34|35|«እኛም በገንዘቦችና በልጆች ይበልጥ የበዛን ነን፡፡ እኛም የምንቀጣ አይደለንም» አሉ፡፡ 34|36|በላቸው «ጌታዬ ሲሳይን ለሚሻው ሰው ያሰፋል፤ ያጠባልም፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም፡፡» 34|37|ገንዘቦቻችሁና ልጆቻችሁም ያች እኛ ዘንድ መቅረብን የምታቀርባችሁ አይደለችም፡፡ ያመነና መልካምን የሠራ ብቻ ሲቀር፡፡ እነዚያ ለእነርሱ በሠሩት መልካም ሥራ እጥፍ ምንዳ አልላቸው፡፡ እነርሱም በገነት ሰገነቶች ውስጥ ጸጥተኞች ናቸው፡፡ 34|38|እነዚያም የሚያቅቱ መስሏቸው አንቀጾቻችንን ለማበላሸት የሚጥሩት እነዚያ በቅጣቱ ውስጥ የሚጣዱ ናቸው፡፡ 34|39|«ጌታዬ ሲሳይን ከባሮቹ ለሚሻው ሰው ያሰፋል፡፡ ለእርሱም ያጠብባል፡፡ ከማንኛውም ነገር የምትለግሱትን እርሱ ይተካዋል፡፡ እርሱም ከሲሳይ ሰጪዎች ሁሉ በላጭ ነው» በላቸው፡፡ 34|40|ሁሉንም በሚሰበስባቸውና ከዚያም ለመላእክቶቹ «እነዚህ እናንተን ይግገዙ ነበሩን?» በሚላቸው ቀን (የሚኾነውን አስታውስ)፡፡ 34|41|(መላእክቶቹም) «ጥራት ይገባህ ከእነርሱ ሌላ ረዳታችን አንተ ብቻ ነህ፡፡ (እንደሚሉት) አይደለም ይልቁንም ጋኔንን ይግገዙ ነበሩ፡፡ አብዛኞቻቸው በእነርሱ አማኞች ናቸው» ይላሉ፡፡ 34|42|ዛሬም ከፊላችሁ ለከፊሉ መጥቀምንም ኾነ መጉዳትን አይችሉም፡፡ ለእነዚያም ለበደሉት «ያችን በእርሷ ታስተባብሉባት የነበራችሁትን የእሳት ቅጣት ቅመሱ» እንላቸዋለን፡፡ 34|43|በእነርሱም ላይ አንቀጾቻችን ግልጽ ኾነው በተነበቡላቸው ጊዜ «ይህ አባቶቻችሁ ይግገዙት ከነበሩት ነገር ሊከለክላችሁ የሚፈልግ ሰው እንጂ ሌላ አይደለም» አሉ፡፡ «ይህም (ቁርኣን) የተቀጣጠፈ ውሸት ነው እንጂ ሌላ አይደለም» አሉ፡፡ እነዚያም የካዱት እውነቱ በመጣላቸው ጊዜ «ይህ ግልጽ ድግምት ነው እንጂ ሌላ አይደለም» አሉ፡፡ 34|44|የሚያጠኑዋቸው የኾኑ መጽሐፍቶችንም ምንም አልሰጠናቸውም፡፡ ከአንተ በፊትም አስፈራሪ ነቢይን ወደእነርሱ አልላክንም፡፡ 34|45|እነዚያም ከእነርሱ በፊት የነበሩት አስተባብለዋል፡፡ የሰጠናቸውንም ከዐስር አንዱን (እነዚህ) አልደረሱም፡፡ መልክተኞቼንም አስተባበሉ፤ (ነቀፍኳቸውም)፡፡ መንቀፌም እንዴት ነበር! 34|46|«የምገስጻችሁ ባንዲት ነገር ብቻ ነው፡፡ (እርሷም) ሁለት ሁለት አንድ አንድም ኾናችሁ ለአላህ እንድትነሱ ከዚያም በጓደኛችሁ (በሙሐመድ) ምንም ዕብደት የሌለበት መኾኑን መርምራችሁ እንድትርረዱ ነው፡፡ እርሱ ለእናንተ ከብርቱ ቅጣት በስተፊት አስጠንቃቂ ነው እንጂ ሌላ አይደለም» በላቸው፡፡ 34|47|«ከዋጋ ማንኛውም የጠየቅኋችሁ ቢኖር እርሱ ለእናንተው ነው፤ ዋጋዬ በአላህ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 34|48|«ጌታዬ እውነትን ያወርዳል፡፡ ሩቅ የኾኑትን ምስጢሮች ሁሉ ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 34|49|«እውነቱ መጣ፡፡ ውሸትም መነሻም መድረሻም የለውም (ተወገደ)» በላቸው፡፡ 34|50|«ብሳሳት የምሳሳተው በራሴ ላይ ብቻ ነው፡፡ ብመራም ጌታዬ ወደኔ በሚያወርደው ነው፡፡ እርሱ ሰሚ ቅርብ ነውና» በላቸው፡፡ 34|51|በደነገጡና ማምለጫ በሌላቸው ጊዜ ከቅርብ ስፍራም በተያዙ ጊዜ (ኹኔታቸውን) ብታይ ኖሮ (አስደናቂን ነገር ባየህ ነበር)፡፡ 34|52|«በእርሱም (አሁን) አመንን» ይላሉ፡፡ ለእነርሱም ከሩቅ ስፍራ (እምነትን) በቀላል ማግኘት ከየታቸው? 34|53|በፊትም በእርሱ በእርግጥ ክደዋል፡፡ ከሩቅ ስፍራም በግምት ንግግርን ይጥላሉ፡፡ 34|54|ከዚህ ቀደም በመሰሎቻቸው እንደ ተሠራውም ብጤ በእነርሱና በሚፈልጉት መካከል ተጋረደ፡፡ እነርሱ በእርግጥ በአወላዋይ ጥርጣሬ ውስጥ ነበሩና፡፡ 35|1|ምስጋና ሰማያትንና ምድርን ፈጣሪ፣ መላእክትን ባለ ሁለት ሁለት፣ ባለ ሶስት ሶስትም፣ ባለ አራት አራትም ክንፎች የኾኑ መልክተኞች አድራጊ ለኾነው አላህ ይገባው፡፡ በፍጥረቱ ውስጥ የሚሻውን ይጨምራል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና፡፡ 35|2|አላህ ለሰዎች ከችሮታ የሚከፍታት ለእርሷ ምንም አጋጅ የላትም፡፡ የሚያግደውም ከእርሱ በኋላ ለእርሱ ምንም ለቃቂ የለውም፡፡ እርሱም አሸነፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 35|3|እናንተ ሰዎች ሆይ! በእናንተ ላይ (ያለውን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ፡፡ ከአላህ ሌላ ፈጣሪ አለን? ከሰማይና ከምድርም ሲሳይን የሚሰጣችሁ አለን? ከእርሱ በስተቀር አምላክ (ሰጪም) የለም፡፡ ታዲያ ወዴት ትዞራላችሁ፡፡ 35|4|ቢያስተባብሉህም ከአንተ በፊት የነበሩ መልክተኞች በእርግጥ ተስተባብለዋል፡፡ ወደ አላህም ነገሮች ሁሉ ይመለሳሉ፡፡ 35|5|እናንተ ሰዎች ሆይ! የአላህ ቀጠሮ እውነት ነው፡፡ የቅርቢቱም ሕይወት አታታላችሁ፡፡ አታላዩም (ሰይጣን) በአላህ (መታገስ) አያታላችሁ፡፡ 35|6|ሰይጣን ለናንተ ጠላት ነው፡፡ ስለዚህ ጠላት አድርጋችሁ ያዙት፡፡ ተከታዮቹን የሚጠራው ከእሳት ጓዶች እንዲኾኑ ብቻ ነው፡፡ 35|7|እነዚያ የካዱት ለእነርሱ ብርቱ ቅጣት አልላቸው፡፡ እነዚያም ያመኑትና በጎ ስራዎችን የሠሩት ለእነርሱ ምሕረትና ታላቅ ምንዳ አልላቸው፡፡ 35|8|መጥፎ ሥራው የተሸለመለትና መልካም አድርጎ ያየው ሰው (አላህ እንዳቀናው ሰው ነውን?) አላህም የሚሻውን ሰው ያጠምማል፡፡ የሚሻውንም ያቀናል፡፡ ስለዚህ በእነርሱ ላይ (ባለመቅናታቸው) ስለመቆላጨት ነፍስህ አትጥፋ፡፡ አላህ የሚሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 35|9|አላህም ያ ነፋሶችን የላከ ነው፡፡ ደመናዎችንም ትቀሰቅሳለች፤ ወደ ሙት (ድርቅ) አገርም እንነዳዋለን፡፡ በእርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው እናደርጋታለን፡፡ ሙታንንም መቀስቀስ እንደዚሁ ነው፡፡ 35|10|ማሸነፍን የሚፈልግ የኾነ ሰው አሸናፊነት ለአላህ ብቻ ነው፤ (እርሱን በመግገዛት ይፈልገው)፡፡ መልካም ንግግር ወደርሱ ይወጣል፡፡ በጎ ሥራም ከፍ ያደርገዋል፡፡ እነዚያም መጥፎ ሥራዎችን የሚዶልቱ ለእነሱ ብርቱ ቅጣት አልላቸው፡፡ የእነዚያም ተንኮል እርሱ ይጠፋል፡፡ 35|11|አላህም ከዐፈር፣ ከዚያም ከፍትወት ጠብታ ፈጠራችሁ፡፡ ከዚያም ጎሳዎች አደረጋችሁ፡፡ ሴትም አታረግዝም አትወልድምም በዕውቀቱ ቢኾን እንጂ፡፡ ዕድሜው ከሚረዘምም አንድም አይረዘምም ከዕድሜውም አይጎደልም በመጽሐፉ ውስጥ ያለ ቢኾን እንጂ፡፡ ይህ በአላህ ላይ ገር ነው፡፡ 35|12|ሁለቱ ባሕሮችም አይተካከሉም! ይህ ጣፋጭ፣ ጥምን ቆራጭ፣ መጠጡ በገር ተዋጭ ነው፡፡ ይህኛውም ጨው መርጋጋ ነው፡፡ እርጥብ ስጋንም ከሁሉም ትበላላችሁ፡፡ (ከጨው ባሕር) የምትለብሷትንም ጌጥ ታወጣላችሁ፡፡ ከችሮታው ልትፈልጉና ልታመሰግኑም መርከቦችን በእርሱ ውስጥ ውሃውን ቀዳጆች ኾነው (ሲንሻለሉ) ታያለህ፡፡ 35|13|ሌሊትን በቀን ውስጥ ያስገባል፡፡ ቀንንም በሌሊት ውሰጥ ያስገባል፤ ፀሐይንና ጨረቃንም ገራ፡፡ ሁሉም እተወሰነ ጊዜ ድረስ ይሮጣሉ፡፡ ይህ ጌታችሁ አላህ ነው፡፡ ንግሥናው የእርሱ ብቻ ነው፡፡ እነዚያም ከእርሱ ሌላ የምትግገዟቸው የተምር ፍሬ ሽፋን እንኳ አይኖራቸውም፡፡ 35|14|ብትጠሩዋቸው ጥሪያችሁን አይሰሙም፡፡ ቢሰሙም ኖሮ ለእናንተ አይመልሱላችሁም፡፡ በትንሣኤም ቀን (እነርሱን በአላህ) ማጋራታችሁን ይክዳሉ፡፡ እንደ ውስጠ ዐዋቂው ማንም አይነግርህም፡፡ 35|15|እናንተ ሰዎች ሆይ! እናንተ (ሁል ጊዜ) ወደ አላህ ከጃዮች ናችሁ፡፡ አላህም እርሱ ተብቃቂው ምስጉኑ ነው፡፡ 35|16|ቢሻ ያስወግዳችኋል፡፡ አዲስንም ፍጡር ያመጣል፡፡ 35|17|ይህም በአላህ ላይ ምንም አስቸጋሪ አይደለም፡፡ 35|18|ኀጢአትን ተሸካሚም (ነፍስ) የሌላዋን ሸክም አትሸከምም፡፡ የተከበደችም (ነፍስ) ወደ ሸክሟ ብትጣራ (ተጠሪው) የቅርብ ዝምድና ባለቤት ቢኾንም እንኳ ከእርሷ አንዳችን የሚሸከምላት አታገኝም፡፡ የምታስጠነቅቀው እነዚያን ጌታቸውን በሩቅ የሚፈሩትን፣ ሶላትንም አስተካክለው ያደረሱትን ብቻ ነው፡፡ የተጥራራም ሰው የሚጥራራው ለራሱ ብቻ ነው፡፡ መመለሻም ወደ አላህ ብቻ ነው፡፡ 35|19|ዕውሩና የሚያየውም አይስተካከሉም፡፡ 35|20|ጨለማዎችና ብርሃንም፤ (እንደዚሁ)፡፡ 35|21|ጥላና ሐሩርም፡፡ 35|22|ሕያዋንና ሙታንም አይስተካከሉም፡፡ አላህ የሚሻውን ሰው ያሰማል፡፡ አንተም በመቃብር ውስጥ ያሉትን አሰሚ አይደለህም፡፡ 35|23|አንተ አስጠንቃቂ እንጂ ሌላ አይደለህም፡፡ 35|24|እኛ አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን በእውነቱ (መምሪያ) ላክንህ፡፡ ማንኛይቱም ሕዝብ በውስጧ አስፈራሪ ያላለፈባት የለችም፡፡ 35|25|ቢያስተባብሉህም እነዚያ ከበፊታቸው የነበሩት በእርግጥ አስተባብለዋል፡፡ መልክተኞቻቸው በግልጽ ማስረጃዎችን፣ በጽሑፎችም፣ አብራሪ በኾነ መጽሐፍም መጥተዋቸዋል፡፡ 35|26|ከዚያም እነዚያን የካዱትን ያዝኳቸው፡፡ ቅጣቴም እንዴት ነበር! (በስፍራው ነው)፡፡ 35|27|አላህ ከሰማይ ውሃን ማውረዱን አላየህምን? በእርሱም ዓይነቶቻቸው የተለያዩ ፍሬዎችን አወጣን፡፡ ከጋራዎችም መልኮቻቸው የተለያዩ ነጮች፣ ቀዮችም፣ በጣም ጥቁሮችም የኾኑ መንገዶች አልሉ፡፡ 35|28|ከሰዎችም፣ ከተንቀሳቃሾችም፣ ከቤት እንሰሳዎችም እንደዚሁ መልኮቻቸው የተለያዩ አልሉ፡፡ አላህን ከባሮቹ ውስጥ የሚፈሩት ዐዋቂዎቹ ብቻ ናቸው፡፡ አላህ አሸናፊ መሓሪ ነው፡፡ 35|29|እነዚያ የአላህን መጽሐፍ የሚያነቡ፣ ሶላትንም አስተካክለው ያደረሱ፣ ከሰጠናቸውም ሲሳይ በምስጢርም ኾነ በግልጽ የለገሱ፣ በፍጹም የማትከስርን ንግድ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ 35|30|ምንዳዎቻቸውን ሊሞላላቸው፣ ከችሮታውም ሊጨምርላቸው (ተስፋ ያደርጋሉ)፡፡ እርሱ በጣም መሓሪ አመስጋኝ ነውና፡፡ 35|31|ያም ከመጽሐፉ ወዳንተ ያወረድንልህ ከበፊቱ ላለው አረጋጋጭ ሲኾን እርሱ እውነት ነው፡፡ አላህ በርግጥ በባሮቹ ውስጥ ዐዋቂ ተመልካች ነው፡፡ 35|32|ከዚያም እነዚያን ከባሮቻችን የመረጥናቸውን መጽሐፉን አወረስናቸው፡፡ ከእነርሱም ነፍሱን በዳይ አልለ፡፡ ከእነርሱም መካከለኛ አልለ፡፡ ከእነሱም በአላህ ፈቃድ በበጎ ሥራዎች ቀዳሚ አልለ፡፡ ያ (ማውረስ)፤ እርሱ ታላቅ ችሮታ ነው፡፡ 35|33|የመኖሪያ ገነቶችን በውስጧ የወርቅ አንባሮችን፣ ሉልንም የሚሸለሙ ኾነው ይገቡባታል፡፡ በእርሷ ውስጥ አልባሳታቸውም ሐር ነው፡፡ 35|34|ይላሉም «ምስጋና ለእዚያ ከእኛ ላይ ሐዘንን ላስወገደልን አላህ ይገባው፡፡ ጌታችን በጣም መሓሪ አመስጋኝ ነውና፡፡ 35|35|(እርሱም) ያ ከችሮታው የዘላለም መኖሪያን አገር ያሰፈረን ነው፡፡ በእርሷ ውስጥ መከራ አይነካንም፡፡ በእርሷም ውስጥ ድካም አይነካንም፡፡» 35|36|እነዚያ የካዱትም ለእነርሱ የገሀነም እሳት አልላቸው፡፡ ይሞቱ ዘንድ በእነርሱ ላይ (በሞት) አይፈረድም፡፡ ከቅጣቷም ከእነርሱ አይቀለልላቸውም፡፡ እንደዚሁ ከሓዲን ሁሉ እንመነዳለን፡፡ 35|37|እነርሱም በርሷ ውስጥ እርዳታን በመፈለግ በኀይል ይጮሃሉ፡፡ «ጌታችን ሆይ! ከእዚያ እንሠራው ከነበርነው ሌላ በጎ ሥራን እንሠራ ዘንድ አውጣን» (ይላሉ)፡፡ «በእርሱ ውስጥ ያስታወሰ ሰው የሚገሰጽበትን ዕድሜ አላቆየናችሁምን? አስጠንቃቂውም መጥቶላችኋል (አስተባብላችኋልም)፡፡ ስለዚህ ቅመሱ፡፡ ለበደለኞችም ምንም ረዳት የላቸውም» (ይባላሉ)፡፡ 35|38|አላህ የሰማያትንና የምድርን ምስጢር በእርግጥ ዐዋቂ ነው፡፡ እርሱ በልቦች ውስጥ ያለን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 35|39|እርሱ ያ በምድር ውስጥ ምትኮች ያደረጋችሁ ነው፡፡ የካደም ሰው ክህደቱ በእርሱው ላይ ብቻ ነው፡፡ ከሓዲዎችንም ክሕደታቸው ከጌታቸው ዘንድ መጠላትን እንጂ ሌላ አይጨመርላቸውም፡፡ ከሓዲዎችንም ክሕደታቸው ከሳራን እንጂ አይጨምርላቸውም፡፡ 35|40|በላቸው «እነዚያን ከአላህ ሌላ የምትግገዟቸውን ተጋሪዎቻችሁን አያችሁን? ከምድር ምንን እንደ ፈጠሩ አሳዩኝ፡፡ ወይስ ለእነርሱ በሰማያት ውስጥ ሽርክና አላቸውን? ወይስ መጽሐፍን ሰጠናቸውና እነርሱ ከርሱ በግልጽ አስረጅ ላይ ናቸውን? አይደለም በደለኞች ከፊላቸው ከፊሉን ማታለልን እንጂ አይቀጥሩም፡፡» 35|41|አላህ ሰማያትንና ምድርን እንዳይወገዱ ይይዛቸዋል፡፡ ቢወገዱም ከእርሱ ሌላ አንድም የሚይዛቸው የለም፡፡ እነሆ እርሱ ታጋሽ መሓሪ ነውና፡፡ 35|42|አስፈራሪም ቢመጣላቸው ከሕዝቦቹ ሁሉ ከአንደኛዋ ይበልጥ የተመሩ ሊኾኑ የመሓላቸውን ድካ አድርሰው በአላህ ማሉ፡፡ አስፈራሪም በመጣላቸው ጊዜ መበርገግን እንጂ ሌላ አልጨመረላቸውም፡፡ 35|43|በምድር ላይ ኩራትንና በክፉ (ተንኮል) መዶለትንም (እንጂ አልጨመረላቸውም፡፡ ክፉ ተንኮልም በባለቤቱ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይሰፍርም፡፡ የቀድሞዎቹን ደንብ እንጂ ይጠባበቃሉን? ለአላህ ደንብም መልለወጥን አታገኝም፡፡ ለአላህ ደንብም መዛወርን አታገኝም፡፡ 35|44|በምድር ላይ አይኼዱምና የእነዚያን ከእነርሱ በፊት የነበሩትን ሰዎች መጨረሻ እንዴት እንደ ነበረ አይመለከቱምን? ከእነርሱም በኀይል የበረቱ ነበሩ፡፡ አላህም በሰማያትም ኾነ በምድር ውስጥ ምንም ነገር የሚያቅተው አይደለም፡፡ እርሱ ዐዋቂ ቻይ ነውና፡፡ 35|45|አላህም ሰዎችን በሠሩት ኀጢአት ቢይዝ ኖሮ በወለሏ (በምድር) ላይ ምንም ተንቀሳቃሽ ባልተወ ነበር፡፡ ግን እተወሰነ ጊዜ ድረስ ያቆያቸዋል፡፡ ጊዜያቸውም በመጣ ወቅት (በኀጢአታቸው ይቀጣቸዋል)፡፡ አላህ በባሮቹ (ኹኔታ) ተመልካች ነውና፡፡ 36|1|የ.ሰ.(ያ ሲን) 36|2|ጥበብ በተመላበት ቁርኣን እምላለሁ፡፡ 36|3|አንተ በእርግጥ ከመልክተኞቹ ነህ፡፡ 36|4|በቀጥታም መንገድ ላይ ነህ፡፡ 36|5|አሸናፊ አዛኝ ከሆነው አምላክ መወረድን ተወረደ፡፡ 36|6|አባቶቻቸው ያልተስፈራሩትን ሕዝቦች ልታስጠነቅቅበት (ተወረደ)፡፡ እነርሱ ዘንጊዎች ናቸውና፡፡ 36|7|በአብዛኞቻቸው ላይ ቃሉ በእውነት ተረጋገጠ፡፡ ስለዚህ እነርሱ አያምኑም፡፡ 36|8|እኛ በአንገቶቻቸው ላይ እንዛዝላዎችን አደረግን፡፡ እርሷም (እንዛዝላይቱ) ወደ አገጮቻቸው ደራሽ ናት፡፡ እነርሱም ራሶቻቸውን ያንጋጠጡ ናቸው፡፡ 36|9|ከስተፊታቸውም ግርዶን ከስተኋላቸውም ግርዶን አደረግን፡፡ ሸፈንናቸውም፡፡ ስለዚህ እነሱ አያዩም፡፡ 36|10|ብታሰጠነቅቃቸውም ባታስጠነቅቃቸውም በእነርሱ ላይ እኩል ነው፡፡ አያምኑም፡፡ 36|11|የምታስጠነቅቀው ግሳጼን የተከተለንና አልረሕማንን በሩቅ የፈራን ሰው ብቻ ነው፡፡ በምሕረትና በመልካም ምንዳም አብስረው፡፡ 36|12|እኛ ሙታንን እኛ በእርግጥ ሕያው እናደርጋለን፡፡ ያስቀደሙትንም ሥራ ፈለጎቻቸውንም እንጽፋለን፡፡ ነገሩንም ሁሉ ገላጭ መሪ በኾነ መጽሐፍ ውስጥ አጠቃለልነው፡፡ 36|13|ለእነርሱም የከተማይቱን (የአንጾኪያን) ሰዎች ምሳሌ መልክተኞቹ በመጧት ጊዜ (የኾነውን) ግለጽላቸው፡፡ 36|14|ወደእነርሱ ሁለትን ሰዎች በላክንና ባስተባበሉዋቸው ጊዜ በሶስተኛም በአበረታንና እኛ ወደ እናንተ መልክተኞች ነን ባሏቸው ጊዜ (የኾነውን ምሳሌ ግለጽላቸው)፡፡ 36|15|እናንተ መሰላችን ሰዎች እንጂ ሌላ አይደላችሁም፡፡ አልረሕማንም ምንም ነገር አላወረደም፡፡ እናንተ የምትዋሹ እንጂ ሌላ አይደላችሁም አሉዋቸው፡፡ 36|16|(መልክተኞቹም) አሉ «ጌታችን ያውቃል፡፡ እኛ ወደእናንተ በእርግጥ መልክተኞች ነን፡፡ 36|17|«በእኛ ላይም ግልጽ የኾነ ማድረስ እንጂ ሌላ የለብንም፡፡» 36|18|(ሕዝቦቹም) «እኛ በእናንተ ገደ ቢሶች ኾን፡፡ ባትከለከሉ በእርግጥ እንወግራችኋለን፡፡ ከእኛም አሳማሚ ቅጣት በእርግጥ ያገኛችኋል» አሉ፡፡ 36|19|«ገደ ቢስነታችሁ ከእናንተው ጋር ነው፡፡ ብትገሰጹ (ትዝታላችሁን?) በእውነቱ እናንተ ወሰን አላፊዎች ሕዝቦች ናችሁ» አሏቸው፡፡ 36|20|ከከተማይቱም ሩቅ ዳርቻ የሚሮጥ ሰው መጣ፡፡ «ወገኖቼ ሆይ! መልክተኞቹን ተከተሉ» አለ፡፡ 36|21|«እነርሱ ቅኑን መንገድ የተመሩ ሲኾኑ ዋጋን የማየጠይቁዋችሁን ሰዎች ተከተሉ» (አላቸው)፡፡ 36|22|«ያንንም የፈጠረኝን፤ ወደርሱም የምትመለሱበትን (ጌታ) የማልገዛ ለእኔ ምን አለኝ?» (አለ)፡፡ 36|23|«ከእርሱ ሌላ አማልክትን እይዛለሁን? አልረህማን በጉዳት ቢሻኝ ምልጃቸው ከእኔ (ለመመለስ) ምንም አትጠቅመኝም፤ አያድኑኝምም፡፡ 36|24|«እኔ ያን ጊዜ በግልጽ ስህተት ውስጥ ነኝ፡፡ 36|25|«እኔ በጌታችሁ አመንኩ፤ ስሙኝም፤» (አለ)፡፡ 36|26|«ገነትን ግባ» ተባለ፡፡ (እርሱም) አለ፡- «ወገኖቼ ቢያውቁ እመኛለሁ፡፡ 36|27|«ጌታዬ ለእኔ ምሕረት ያደረገልኝና ከተከበሩትም ያደረገኝ መኾኑን፡፡» 36|28|ከእርሱም በኋላ በሕዝቦቹ ላይ (ልናጠፋቸው) ሰራዊትን ከሰማይ አላወረድንም፡፡ (በማንም ላይ) አወራጆችም አልነበርንም፡፡ 36|29|(ቅጣታቸው) አንዲት ጩኸት እንጂ ሌላ አልነበረችም፡፡ ወዲያውኑም እነርሱ ጠፊዎች ኾኑ፡፡ 36|30|በባሮቹ ላይ ዋ ቁልጭት! ከመልክተኛ አንድም አይመጣቸውም በእርሱ የሚሳለቁበት ቢኾኑ እንጅ፡፡ 36|31|ከእነርሱ በፊት ከክፍለ ዘመናት ሕዝቦች ብዙዎችን ማጥፋታችንንና እነርሱ ወደነርሱ የማይመለሱ መኾናቸውን አላወቁምን? 36|32|ሁሉም እኛ ዘንድ የሚሰበሰቡ የሚቀረቡ እንጂ ሌላ አይደሉም፡፡ 36|33|የሞተችውም ምድር ለእነርሱ ምልክት ናት! ሕያው አደረግናት፡፡ ከእርሷም ፍሬን አወጣን፤ ከርሱም ይበላሉ፡፡ 36|34|በእርሷም ውሰጥ ከዘምበባዎችና ከወይኖች የኾኑ አትክልቶችን አደረግን፡፡ በእርሷም ውስጥ ምንጮችን አፈለቅን፡፡ 36|35|ከፍሬውና እጆቻቸው ከሠሩትም ይበሉ ዘንድ (ይህን አደረግን)፤ አያመሰግኑምን? 36|36|ያ ምድር ከምታበቅለው ከነፍሶቻቸውም ከማያውቁትም ነገር ዓይነቶችን ሁሏንም የፈጠረ (አምላክ) ጥራት ይገባው፡፡ 36|37|ሌሊቱም ለእነርሱ ምልክት ነው፡፡ ከእርሱ ላይ ቀንን እንገፍፋለን፡፡ ወዲያውኑም እነርሱ በጨለማ ውስጥ ይገባሉ፡፡ 36|38|ፀሐይም ለእርሷ ወደ ሆነው መርጊያ ትሮጣለች፡፡ ይህ የአሸናፊው የዐዋቂው አምላክ ውሳኔ ነው፡፡ 36|39|ጨረቃንም የመስፈሪያዎች ባለቤት ሲኾን እንደ ዘንባባ አሮጌ ቀንዘል እስኪኾን ድረስ (መኼዱን) ለካነው፡፡ 36|40|ፀሐይ ጨረቃን ልትደርስበት አይገባትም፡፡ ሌሊትም ቀንን (ያለ ጊዜው) ቀዳሚ አይኾንም፡፡ ሁሉም በመዞሪያቸው ውስጥ ይዋኛሉ፡፡ 36|41|እኛም (የቀድሞ) ትውልዳቸውን በተሞላች መርከብ ውስጥ የጫን መኾናችን ለእነርሱ ምልክት ነው፡፡ 36|42|ከመሰሉም በእርሱ የሚሳፈሩበትን ለእነርሱ ፈጠርንላቸው፡፡ 36|43|ብንሻም እናሰጥማቸዋለን፡፡ ለእነርሱም ረዳት የላቸውም፡፡ እነርሱም የሚድዳኑ አይደሉም፡፡ 36|44|ግን ከእኛ ለኾነው ችሮታና እስከ ጊዜ ሞታቸው ለማጣቀም (አዳንናቸው)፡፡ 36|45|ለእነርሱም «በስተፊታችሁና በኋለችሁ ያለውን ነገር ተጠንቀቁ ይታዘንላችኋልና» በተባሉ ጊዜ (ፊታቸውን ያዞራሉ)፡፡ 36|46|ከጌታቸውም ተዓምራት ማንኛይቱም ተዓምር አትመጣላቸውም፤ ከእርሷ የሚሸሹ ቢኾኑ እንጅ፡፡ 36|47|ለእነርሱም «አላህ ከሰጣችሁ ሲሳይ ለግሱ» በተባሉ ጊዜ እነዚያ የካዱት ለእነዚያ ላመኑት «አላህ ቢሻ ኖሮ የሚያበላውን ሰው እናበላለን? እናንተ በግልጽ ስህተት ውስጥ እንጂ በሌላ ላይ አይደላችሁም» ይላሉ፡፡ 36|48|«እውነተኞችም እንደኾናችሁ ይህ ቀጠሮ መቼ ነው?» ይላሉ፡፡ 36|49|እነርሱ የሚከራከሩ ሲኾኑ በድንገት የምትይዛቸው የኾነችን አንዲትን ጩኸት እንጂ ሌላን አይጠባበቁም፡፡ 36|50|(ያን ጊዜ) መናዘዝንም አይችሉም፡፡ ወደ ቤተሰቦቻቸወም አይመለሱም፡፡ 36|51|በቀንዱም ይነፋል፡፡ ወዲያውኑም እነርሱ ከመቃብሮቻቸው ወደ ጌታቸው በፍጥነት ይገሰግሳሉ፡፡ 36|52|«ወይ ጥፋታችን! ከመኝታችን ማን ቀሰቀሰን? ይህ ያ አዛኙ ጌታ (በእርሱ) የቀጠረን መልክተኞቹም እውነትን የነገሩን ነው» ይላሉ፡፡ 36|53|(እርሷ) አንዲት ጩኸት እንጂ አይደለችም፡፡ ወዲያውኑም እነርሱ እኛ ዘንድ የሚሰበሰቡ የሚቀርቡ ናቸው፡፡ 36|54|«ዛሬም ማንኛይቱም ነፍስ ምንም አትበደልም፡፡ ትሠሩትም የነበራችሁትን እንጂ ሌላን አትመነዱም» (ይባላሉ)፡፡ 36|55|የገነት ሰዎች ዛሬ በእርግጥ በሥራዎች ውስጥ ተደሳቾች ናቸው፡፡ 36|56|እነርሱም ሚስቶቻቸውም በጥላዎች ውስጥ ናቸው፡፡ ባለ አጎበር አልጋዎች ላይ ተደጋፊዎች ናቸው፡፡ 36|57|በውስጧ ለእነርሱ ፍራፍሬዎች አሏቸው፡፡ ለእነርሱም የሚፈልጉት ሁሉ አልላቸው፡፡ 36|58|(ለእነርሱም) አዛኝ ከሆነው ጌታ በቃል ሰላምታ አላቸው። 36|59|(ይላልም) «እናንተ አመጸኞች ሆይ! ዛሬ (ከምእምናን) ተለዩ፡፡» 36|60|የአደም ልጆች ሆይ! ሰይጣንን አትገዙ፤ እርሱ ለእናንተ ግልጽ ጠላት ነውና በማለት ወደእናንተ አላዘዝኩምን? 36|61|ተገዙኝም፤ ይህ ቀጥተኘ መንገድ ነው፤ (በማለትም)፡፡ 36|62|ከእናንተም ብዙን ፍጡር በእርግጥ አሳስቷል፡፡ የምታውቁም አልነበራችሁምን? 36|63|ይህቺ ያቺ ትቀጠሩዋት የነበረችው ገሀነም ናት፡፡ 36|64|ትክዱ በነበራችሁት ምክንያት ዛሬ ግቧት (ይባላሉ)፡፡ 36|65|ዛሬ በአፎቻቸው ላይ እናትምና እጆቻቸው ያነጋግሩናል፡፡ እግሮቻቸውም ይሠሩት በነበሩት ሁሉ ይመሰክራሉ፡፡ 36|66|ብንሻም ኖሮ በዐይኖቻቸው ላይ በአበስን ነበር፡፡ መንገድንም (እንደ ልመዳቸው) በተሽቀዳደሙ ነበር፡፡ እንዴትም ያያሉ? 36|67|ብንሻም ኖሮ በስፍራቸው ላይ እንዳሉ ወደ ሌላ ፍጥረት በለወጠናቸው ነበር፡፡ መኼድንም መመለስንም ባልቻሉም ነበር፡፡ 36|68|ዕድሜውንም የምናረዝመውን ሰው በፍጥረቱ (ወደ ደካማነት) እንመልሰዋለን፤ አያውቁምን? 36|69|(ሙሐመድን) ቅኔንም አላስተማርነውም፡፡ ለእርሱም አይግገባውም፡፡ እርሱ (መጽሐፉ) መገሰጫና ገላጭ ቁርኣን እንጅ (ቅኔ) አይደለም፡፡ 36|70|(ግሣጼነቱም ልቡ) ሕያው የኾነን ሰው ሊያስፈራራበትና ቃሉም በከሓዲዎች ላይ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ 36|71|እኛ እጆቻችን (ኃይሎቻችን) ከሠሩት ለእነርሱ እንስሳዎችን መፍጠራችንን አያውቁምን? እነርሱም ለእርሷ ባለ መብቶች ናቸው፡፡ 36|72|ለእነርሱም ገራናት፡፡ ስለዚህ ከእርሷ ውስጥ የሚጋልቡት አልለ፡፡ ከእርሷም ይበላሉ፡፡ 36|73|ለእነርሱም በእርሷ ውስጥ (ሌሎች) ጥቅሞች መጠጦችም አሉዋቸው፡፡ ታዲያ አያመሰግኑምን; 36|74|መረዳትንም በመከጀል ከአላህ ሌላ አማልክትን ያዙ፡፡ 36|75|መርዳታቸውን አይችሉም፡፡ እነርሱም ለእርሳቸው (ወደ እሳት) የተቀረቡ ሰራዊት ናቸው፡፡ 36|76|ንግግራቸውም አያሳዝንህ፡፡ እኛ የሚደብቁትንም የሚገልጹትንም እናውቃለንና፡፡ 36|77|ሰውየው እኛ ከፍቶት ጠብታ የፈጠርነው መኾናችን አላወቀምን? ወዲያውም እርሱ (ትንሣኤን በመካድ) ግልጽ ተከራካሪ ይኾናልን? 36|78|ለእኛም ምሳሌን አደረገልን፡፡ መፈጠሩንም ረሳ፡፡ «አጥንቶችን እነርሱ የበሰበሱ ሲኾኑ ሕያው የሚያደርጋቸው ማነው?» አለ፡፡ 36|79|«ያ በመጀመሪያ ጊዜ (ከኢምንት) ያስገኛት ሕያው ያደርጋታል፡፡ እርሱም በፍጡሩ ሁሉ (ኹኔታ) ዐዋቂ ነው» በለው፡፡ 36|80|ያ ለእናንተ በእርጥብ ዛፍ እሳትን ያደረገላችሁ ነው፡፡ ወዲያውኑም እናንተ ከእርሱ ታቀጣጥላላችሁ፡፡ 36|81|ያ ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ ብጤያቸውን በመፍጠር ላይ ቻይ አይደለምን? ነው እንጅ፡፡ እርሱም በብዙ ፈጣሪው ዐዋቂው ነው፡፡ 36|82|ነገሩም አንዳችን በሻ ጊዜ ኹን ማለት ነው፡፡ ወዲያው ይኾናልም፡፡ 36|83|ያ የነገሩ ሁሉ ስልጣን በእጁ የኾነው ጌታ ጥራት ይገባው፡፡ ወደእርሱም ትመለሳላችሁ፡፡ 37|1|መሰለፍን በሚሰለፉት፡፡ 37|2|መገሠጽንም በሚገሥጹት፤ 37|3|ቁርኣንንም በሚያነቡት እምላለሁ፡፡ 37|4|አምላካችሁ በእርግጥ አንድ ነው፡፡ 37|5|የሰማያትና የምድር በመካከላቸው ያለውም ፍጡር ሁሉ ጌታ ነው፡፡ የምሥራቆችም ጌታ ነው፡፡ 37|6|እኛ ቅርቢቱን ሰማይ በከዋክብት ጌጥ አጌጥናት፡፡ 37|7|አመጸኛም ከሆነ ሰይጣን ሁሉ መጠበቅን ጠበቅናት፡፡ 37|8|ወደላይኛው ሰራዊት አያዳምጡም፡፡ ከየወገኑም ሁሉ ችቦ ይጣልባቸዋል፡፡ 37|9|የሚባረሩ ሲሆኑ (ይጣልባቸዋል)፡፡ ለእነሱም ዘውታሪ ቅጣት አላቸው፡፡ 37|10|ንጥቂያን የነጠቀ ወዲያውም አብሪ ኮከብ የተከተለው ሲቀር፤ (እርሱ ይሰማዋል)፡፡ 37|11|ጠይቃቸውም፤ እነርሱ በአፈጣጠር ይበልጥ የበረቱ ናቸውን? ወይስ እኛ (ከእነርሱ በፊት) የፈጠርነው? (ፍጡር) እኛ ከሚጣበቅ ጭቃ ፈጠርናቸው፡፡ 37|12|ይልቁንም (በማስተባበላቸው) ተደነቅህ፤(ከመደነቅህ) ይሳለቃሉም፡፡ 37|13|በተገሠጹም ጊዜ አይመለሱም፡፡ 37|14|ተዓምርን ባዩም ጊዜ ለመሳለቅ ይጠራራሉ፡፡ 37|15|ይላሉም «ይህ ግልጽ ድግምት እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ 37|16|«በሞትንና ዐፈርና አጥንቶችም በኾን ጊዜ እኛ የምንቀሰቀስ ነን? 37|17|«የቀድሞዎቹ አባቶችንም? (ይላሉ)፡፡ 37|18|«አዎን እናንተ ወራዶች ሆናችሁ (ትነሳላችሁ)» በላቸው፡፡ 37|19|እርሷም አንዲት ጩኸት ብቻ ናት፡፡ እነርሱም ወዲያውኑ (ምን እንደሚፈጸምባቸው) ያያሉ፡፡ 37|20|«ዋ ጥፋታችን! ይህ የፍርዱ ቀን ነው» ይላሉም፡፡ 37|21|«ይህ ያ በእርሱ ታስተባብሉ የነበራችሁት መለያው ቀን ነው» (ይባላሉ)፡፡ 37|22|(ለመላእክቶችም) «እነዚያን ነፍሶቻቸውን የበደሉትን ሰዎች ጓደኞቻቸውንም ይግገዟቸው የነበሩትንም (ጣዖታት) ሰብስቡ፡፡ 37|23|«ከአላህ ሌላ (የሚገዙዋቸውን ሰብስቧቸው) ወደ እሳት መንገድም ምሩዋቸው፡፡ 37|24|«አቁሟቸውም፡፡ እነርሱ ተጠያቂዎች ናቸውና» (ይባላል)፡፡ 37|25|(ለእነርሱም) «የማትረዳዱት ለእናንተ ምን አላችሁ? (ይባላሉ)፡፡ 37|26|በእርግጥ እነርሱ ዛሬ እጃቸውን የሰጡ ወራዳዎች ናቸው፡፡ 37|27|የሚወቃቀሱም ሆነው ከፊላቸው በከፊሉ ላይ ይመጣሉ፡፡ 37|28|(ለአስከታዮቹ) እናንተ ከስተቀኝ ትመጡብን ነበር ይላሉ፡፡ 37|29|(አስከታዮቹም) ይላሉ «አይደለም ፈጽሞ ምእምናን አልነበራችሁም፡፡ 37|30|«ለእኛም በእናንተ ላይ ምንም ስልጣን አልነበረንም፡፡ በእርግጥ እናንተ ጠማሞች ሕዝቦች ነበራችሁ፡፡ 37|31|«በእኛም ላይ የጌታችን ቃል ተረጋገጠብን፤ እኛ (ሁላችንም ቅጣቱን) ቀማሾች ነን፡፡ 37|32|«ወደ ጥምመት ጠራናችሁም፡፡ እኛ ጠማሞች ነበርንና» (ይላሉ)፡፡ 37|33|ስለዚህ እነርሱ በዚያ ቀን በቅጣቱ ነጋሪዎች ናቸው፡፡ 37|34|እኛ በአመጸኞች ሁሉ እንደዚሁ እንሠራለን፡፡ 37|35|እነርሱ ከአላህ ሌላ አምላክ የለም በተባሉ ጊዜ ይኮሩ ነበሩ፡፡ 37|36|እኛ ለዕብድ ባለቅኔ ብለን አማልክቶቻችንን የምንተው ነን? ይሉም ነበር፡፡ 37|37|አይደለም እውነቱን (ሃይማኖት) አመጣ፡፡ መልክተኞቹንም እውነተኛነታቸውን አረጋገጠ፡፡ 37|38|እናንተ አሳማሚውን ቅጣት በእርግጥ ቀማሾች ናችሁ፡፡ 37|39|ትሠሩትም የነበራችሁትን እንጂ ሌላን አትመነዱም፡፡ 37|40|ግን ምርጥ የሆኑት የአላህ ባሮች (ቅጣትን አይቀምሱም)፡፡ 37|41|እነዚያ ለእነርሱ የታወቀ ሲሳይ አላቸው፡፡ 37|42|ፍራፍሬዎች (አሏቸው) እነርሱም የተከበሩ ናቸው፤ 37|43|በድሎት ገነቶች ውስጥ፡፡ 37|44|ፊት ለፊት የሚታያዩ ሲሆኑ በአልጋዎች ላይ (ይንፈላሰሳሉ)፡፡ 37|45|ከሚመነጭ ወይን ጠጅ በያዘ ብርጭቆ በእነርሱ ላይ ይዞርባቸዋል፡፡ 37|46|ነጭ ለጠጪዎች ጣፋጭ ከኾነች፡፡ 37|47|በእርሷ ውስጥም ምታት የለባትም፡፡ እነርሱም ከእርሷ የሚሰክሩ አይደሉም፡፡ 37|48|እነርሱም ዘንድ ዓይናቸውን (በባሎቻቸው ላይ) አሳጣሪዎች የኾኑ ዓይናማዎች አልሉ፡፡ 37|49|እነርሱ ልክ የተሸፈነ (የሰጎን) ዕንቁላል ይመስላሉ፡፡ 37|50|የሚጠያየቁም ሆነው ከፊላቸው ወደ ከፊሉ ይመጣሉ፡፡ 37|51|ከእነርሱ የሆነ ተናጋሪ ይላል «እኔ ጓደኛ ነበረኝ፡፡ 37|52|«በእርግጥ አንተ ከሚያምኑት ነህን? የሚል፡፡ 37|53|«በሞትንና ዐፈር አጥንቶችም በሆን ጊዜ እኛ በእርግጥ እንመረመራለን?» (የሚል)፡፡ 37|54|እናንተ ተመልካቾች ናችሁን? ይላል፡፡ 37|55|ይመለከታልም፤ በገሀነም መካከልም (ጓደኛውን) ያየዋል፡፡ 37|56|ይላል «በአላህ እምላለሁ፤ በእርግጥ ልታጠፋኝ ቀርበህ ነበር፡፡ 37|57|«የጌታየም ጸጋ ባልነበረ ኖሮ ወደ እሳት ከሚቀርቡት እሆን ነበር፡፡» 37|58|(የገነት ሰዎች ይላሉ) «እኛ የምንሞት አይደለንምን? 37|59|«የመጀመሪያይቱ መሞታችን ብቻ ስትቀር፡፡ እኛም የምንቅቀጣ አይደለንምን?» (ይላሉ)፡፡ 37|60|ይህ (ለገነት ሰዎች የተወሳው) እርሱ በእርግጥ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ 37|61|ለዚህ ብጤ ሠሪዎች ይሥሩ፡፡ 37|62|በመስተንግዶነት ይህ ይበልጣልን? ወይስ የዘቁም ዛፍ? 37|63|እኛ ለበዳዮች ፈተና አድርገናታል፡፡ 37|64|እርሷ በገሀነም አዘቅት ውስጥ የምትወጣ ዛፍ ናት፡፡ 37|65|እንቡጧ ልክ የሰይጣናት ራሶች ይመስላል፡፡ 37|66|እነርሱም ከእርሷ በይዎች ናቸው፤ ሆዶችንም ከእርሷ ሞይዎች ናቸው፡፡ 37|67|ከዚያም ለእነርሱ በእርሷ ላይ ከተኳሳ ውሃ ቅልቅል (መጠጥ) አልላቸው፡፡ 37|68|ከዚያም መመለሻቸው ወደ ተጋጋመች እሳት ነው፡፡ 37|69|እነሱ አባቶቻቸውን የተሳሳቱ ሆነው አግኝተዋልና፡፡ 37|70|እነሱም በፈለጎቻቸው ላይ ይገሰግሳሉና፡፡ 37|71|ከእነርሱ በፊትም የቀድሞዎቹ (ሕዝቦች) አብዛኞቻቸው በእርግጥ ተሳስተዋል፡፡ 37|72|በውስጣቸውም አስፈራሪዎችን በእርግጥ ልከናል፡፡ 37|73|የተስፈራሪዎቹም መጨረሻ እንዴት እንደነበረ ተመልከት፡፡ 37|74|ምርጥ የሆኑት የአላህ ባሮች ብቻ ሲቀሩ፡፡ 37|75|ኑሕም በእርግጥ ጠራን፡፡ ጥሪውን ተቀባዮቹም ምንኛ አማርን! 37|76|እርሱንም ቤተሰቦቹንም ከከባድ ጭንቅ አዳንን፡፡ 37|77|ዘሮቹንም እነርሱን ብቻ ቀሪዎች አደረግን፤ 37|78|በርሱም ላይ በኋለኞቹ ሕዝቦች ውስጥ (መልካም ዝናን) ተውን፡፡ 37|79|«በዓለማት ውስጥ ሰላም በኑሕ ላይ ይኹን፡፡» 37|80|እኛ እንደዚሁ መልካም ሠሪዎችን እንመነዳለን፡፡ 37|81|እርሱ ከምእምናን ባሮቻችን ነውና፡፡ 37|82|ከዚያም ሌሎቹን አሰጠምን፡፡ 37|83|ኢብራሂምም በእርግጥ ከተከታዮቹ ነው፡፡ 37|84|ወደ ጌታው በቅን ልብ በመጣ ጊዜ (የኾነውን አስታውስ)፡፡፡ 37|85|«ለአባቱና ለሕዝቦቹ ምንን ትግገዛላችሁ?» ባለ ጊዜ፡፡ 37|86|«ለቅጥፈት ብላችሁ ከአላህ ሌላ አማልክትን ትሻላችሁን? 37|87|«በዓለማትም ጌታ ሃሳባችሁ ምንድን ነው?» አለ፡፡ 37|88|በከዋክብትም መመልከትን ተመለከተ፡፡ 37|89|«እኔ በሽተኛ ነኝም» አለ፡፡ 37|90|ከእርሱም የሸሹ ሆነው ኼዱ፡፡ 37|91|ወደ አማልክቶቻቸውም ተዘነበለ፡፡ አለም፡- «አትበሉምን?» 37|92|«የማትናገሩት ለናንተ ምን አላችሁ?» 37|93|በኀይል የሚመታቸውም ሆኖ በእነርሱ ላይ በድብቅ ተዘነበለ፡፡ 37|94|ወደእርሱም (ሰዎቹ) እየሮጡ መጡ፡፡ 37|95|አላቸው «የምትጠርቡትን ትግገዛላችሁን?» 37|96|«አላህ እናንተንም የምትሠሩትንም የፈጠረ ሲኾን፡፡» 37|97|«ለእርሱም ግንብን ገንቡ በእሳት ነበልባል ውስጥ ጣሉትም» አሉ፡፡ 37|98|በእርሱም ተንኮልን አሰቡ፡፡ ዝቅተኞችም አደረግናቸው፡፡ 37|99|አለም «እኔ ወደ ጌታዬ ኼያጅ ነኝ፡፡ በእርግጥ ይመራኛልና፡፡» 37|100|ጌታዬ ሆይ! ከመልካሞቹ የሆነን (ልጅ) ስጠኝ፡፡ 37|101|ታጋሽ በሆነ ወጣት ልጅም አበሰርነው፡፡ 37|102|ከእርሱ ጋርም ለሥራ በደረሰ ጊዜ «ልጄ ሆይ! እኔ በሕልሜ እኔ የማርድህ ሆኜ አያለሁ፡፡ ተመልከትም፤ ምን ታያለህ?» አለው፡፡ «አባቴ ሆይ! የታዘዝከውን ሥራ፡፡ አላህ ቢሻ ከታጋሾቹ ሆኜ ታገኘኛለህ» አለ፡፡ 37|103|ሁለቱም ትዕዛዙን በተቀበሉና በግንባሩም ጎን ላይ በጣለው ጊዜ (የሆነው ሆነ)፡፡ 37|104|ጠራነውም፤ (አልነው) «ኢብራሂም ሆይ! 37|105|ራእይቱን በእውነት አረጋገጥክ፡፡» እኛ እንደዚሁ መልካም ሠሪዎችን እንመነዳለን፡፡ 37|106|ይህ እርሱ በእውነት ግልጽ ፈተና ነው፡፡ 37|107|በታላቅ ዕርድም (መስዋዕት) ተቤዠነው፡፡ 37|108|በእርሱም ላይ በኋለኞቹ ሕዝቦች ውስጥ መልካም ዝናን አስቀረንለት፡፡ 37|109|ሰላም በኢብራሂም ላይ ይሁን፡፡ 37|110|እንደዚሁ መልካም ሠሪዎችን ሁሉ እንመነዳለን፡፡ 37|111|እርሱ በእርግጥ ካመኑት ባሮቻችን ነው፡፡ 37|112|በኢስሐቅም አበሰርነው፡፡ ከመልካሞቹ የሆነ ነቢይ ሲሆን፡፡ 37|113|በእርሱና በኢስሐቅ ላይም ባረክን፡፡ ከሁለቱም ዘሮች በጎ ሠሪ አልለ፡፡ ለነፍሱ ግልጽ በዳይም አለ፡፡ 37|114|በሙሳና በሃሩን ላይም በእርግጥ ለገስን፡፡ 37|115|እነርሱንም ሕዝቦቻቸውንም ከታላቅ ጭንቅ አዳንን፡፡ 37|116|ረዳናቸውም፡፡ እነርሱም አሸናፊዎች ነበሩ፡፡ 37|117|በጣም የተብራራውንም መጽሐፍ ሰጠናቸው፡፡ 37|118|ቀጥተኛውንም መንገድ መራናቸው፡፡ 37|119|በሁለቱም ላይ በኋለኞቹ ሕዝቦች ውስጥ መልካም ዝናን ተውንላቸው፡፡ 37|120|ሰላም በሙሳና በሃሩን ላይ ይሁን፡፡ 37|121|እኛ እንደዚሁ በጎ አድራጊዎችን ሁሉ እንመነዳለን፡፡ 37|122|ሁለቱም በእርግጥ ከአመኑት ባሮቻችን ናቸው፡፡ 37|123|ኢልያስም በእርግጥ ከመልክተኞቹ ነው፡፡ 37|124|ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፤ አላህን አትፈሩምን? 37|125|በዕልን ትገዛላችሁን? ከሰዓሊዎቹ ሁሉ ይበልጥ በጣም አሳማሪ የሆነውንም አምላክ ትተዋላችሁን? 37|126|አላህን ጌታችሁንና የቀድሞዎቹ አባቶቻችሁን ጌታ (ትተዋላችሁን)? 37|127|አስተባበሉትም፡፡ ስለዚህ እነርሱ (ለቅጣት) የሚጣዱ ናቸው፡፡ 37|128|ንጹሕ የተደረጉት የአላህ ባሮች ብቻ ሲቀሩ፡፡ 37|129|በእርሱ ላይም በኋለኞቹ ሕዝቦች ውስጥ መልካም ዝናን ተውንለት፡፡ 37|130|ሰላም በኢልያሲን ላይ ይሁን፡፡ 37|131|እኛ እንደዚሁ መልካም ሠሪዎችን እንመነዳለን፡፡ 37|132|እርሱ በእርግጥ ከምእመናን ባሮቻችን ነው፡፡ 37|133|ሉጥም በእርግጥ ከመልክተኞቹ ነው፡፡ 37|134|እርሱንና ቤተሰቦቹን ሁሉንም በአዳንናቸው ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 37|135|(በቅጣቱ ውስጥ) ከቀሪዎቹ የሆነችው አሮጊት ብቻ ስትቀር፡፡ 37|136|ከዚያም ሌሎቹን አጠፋን፡፡ 37|137|እናንተም ያነጋችሁ ስትሆኑ በእነርሱ (መኖሪያዎች) ላይ (በቀን) ታልፋላችሁ፡፡ 37|138|በሌሊትም (ታልፋላችሁ)፤ ልብም አታደርጉምን? 37|139|ዩኑስም በእርግጥ ከመልክተኞቹ ነው፡፡ 37|140|ወደ ተመላው መርከብ በኮበለለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 37|141|ዕጣም ተጣጣለ፡፡ ከተሸነፉትም ሆነ፡፡ 37|142|እርሱም ተወቃሽ ሲሆን ዐሳው ዋጠው፡፡ 37|143|እርሱ ለጌታው ከአወዳሾቹ ባልሆነም ኖሮ፤ 37|144|እስከሚቀሰቀሱበት ቀን ድረስ በሆዱ ውስጥ በቆየ ነበር፡፡ 37|145|እርሱ በሽተኛ ሆኖ በቃይ በሌለው (በባሕር) ዳርቻ ላይ ጣልነውም፡፡ 37|146|በእርሱም ላይ (በአጠገቡ) ከቅል የሆነችን ዛፍ አበቀልን፡፡ 37|147|ወደ መቶ ሺሕ ሰዎችም (ዳግመኛ) ላክነው፡፡ ከቶውንም ይጨምራሉ፡፡ 37|148|አመኑም፡፡ እስከ ጊዜ ድረስም አጣቀምናቸው፡፡ 37|149|(የመካን ሰዎች) ጠይቃቸውም፡፡ «ለጌታህ ሴቶች ልጆች ለእነርሱም ወንዶች ልጆች ይኖራልን?» 37|150|ወይስ እኛ እነርሱ የተጣዱ ሆነው መላእክትን ሴቶች አድርገን ፈጠርን? 37|151|ንቁ! እነርሱ ከቅጥፈታቸው (የተነሳ) ይላሉ፡- 37|152|«አላህ (መላእክትን) ወለደ፡፡» እነርሱም በእርግጥ ውሸታሞች ናቸው፡፡ 37|153|በወንዶች ልጆች ላይ ይልቅ ሴቶችን ልጆች መረጥን? 37|154|ለእናንተ ምን (አስረጅ) አላችሁ? እንዴት ትፈርዳላችሁ! 37|155|አትገነዘቡምን? 37|156|ወይስ ለእናንተ ግልጽ አስረጅ አላችሁን? 37|157|«እውነተኞች እንደ ሆናችሁ መጽሐፋችሁን አምጡ» (በላቸው)፡፡ 37|158|በአላህና በአጋንንት መካከልም ዝምድናን አደረጉ፡፡ አጋንንትም እነርሱ (ይህን ባዮች በእሳት) የሚጣዱ መሆናቸውን በእርግጥ ዐውቀዋል፡፡ 37|159|አላህ ከሚመጥኑት ሁሉ ጠራ፡፡ 37|160|ግን የተመረጡት የአላህ ባሮች (በአላህ ላይ አይዋሹም)፡፡ 37|161|እናንተም የምትገዟቸውም ሁሉ፤ 37|162|በእርሱ (በአላህ) ላይ አንድንም አጥማሚዎች አይደላችሁም፡፡ 37|163|ያንን እርሱ ገሀነምን ገቢ የሆነውን ሰው ቢሆን እንጅ፡፡ 37|164|(ጂብሪል አለ) ከእኛም አንድም የለም፤ ለእርሱ የታወቀ ደረጃ ያለው ቢሆን እንጅ፡፡ 37|165|እኛም (ጌታን ለመግገዛት) ተሰላፊዎቹ እኛ ነን፡፡ 37|166|እኛም (አላህን) አጥሪዎቹ እኛ ነን፡፡ 37|167|እነርሱም (ከሓዲዎቹ) በእርግጥ ይሉ ነበሩ፡- 37|168|«ከቀድሞዎቹ (መጻሕፍት) ገሳጭ መጽሐፍ እኛ ዘንድ በነበረን ኖሮ፤ 37|169|«የአላህ ምርጦች ባሮች በሆን ነበር፡፡» 37|170|ግን (ቁርኣኑ በመጣላቸው ጊዜ) በእርሱ ካዱ፡፡ ወደፊትም በእርግጥ ያውቃሉ፡፡ 37|171|(የእርዳታ) ቃላችንም መልክተኞች ለሆኑት ባሮቻችን በእውነት አልፋለች፡፡ 37|172|እነርሱ ተረጂዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 37|173|ሰራዊቶቻችንም በእርግጥ አሸናፊዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 37|174|ከእነርሱም (ከመካ ከሓዲዎች) እስከ ጥቂት ጊዜ ድረስ ዙር (ተዋቸው)፡፡ 37|175|እያቸውም ወደፊትም (የሚደርስባቸውን) ያያሉ፡፡ 37|176|በቅጣታችንም ያቻኩላሉን? 37|177|በቀያቸውም በወረደ ጊዜ የተስፈራሪዎቹ ንጋት ከፋ! 37|178|እነርሱንም እስከ (ጥቂት) ጊዜ ድረስ ተዋቸው፡፡ 37|179|ተመልከትም በእርግጥም ያያሉ፡፡ 37|180|የማሸነፍ ጌታ የሆነው ጌታህ ከሚሉት ሁሉ ጠራ፡፡ 37|181|በመልክተኞቹም ላይ ሰላም ይኹኑ፤ 37|182|ምስጋናም ለዓለማት ጌታ ለአላህ ይሁን፡፡ 38|1|ጸ. (ሷድ) የክብር ባለቤት በሆነው ቁርኣን እምላለሁ (ብዙ አማልክት አሉ እንደሚሉት አይደለም)፡፡ 38|2|ይልቁንም እነዚያ የካዱት ሰዎች በትዕቢትና በክርክር ውስጥ ናቸው፡፡ 38|3|ከእነርሱ በፊት ከክፍለ ዘመናት ሕዝቦች ብዙን አጥፍተናል፡፡ (ጊዜው) የመሸሻና የማምለጫ ጊዜ ሳይሆንም (ለእርዳታ) ተጣሩ፡፡ 38|4|ከእነርሱ የሆነ አስፈራሪም ስለ መጣላቸው ተደነቁ፡፡ ከሓዲዎቹም «ይህ ድግምተኛ (ጠንቋይ) ውሸታም ነው» አሉ፡፡ 38|5|«አማልክቶቹን አንድ አምላክ አደረጋቸውን? ይህ አስደናቂ ነገር ነው» (አሉ)፡፡ 38|6|ከእነርሱም መኳንንቶቹ «ሂዱ፤ በአማልክቶቻችሁም (መግገዛት) ላይ ታገሱ፡፡ ይህ (ከእኛ) የሚፈለግ ነገር ነውና» እያሉ አዘገሙ፡፡ 38|7|«ይህንንም በኋለኛይቱ ሃይማኖት አልሰማንም፡፡ ይህ ውሸትን መፍጠር እንጅ ሌላ አይደለም» (እያሉም)፡፡ 38|8|«ከመካከላችን በእርሱ ላይ ቁርኣን ተወረደን?» (አሉ)፡፡ በእውነት እነርሱ ከግሳጼዬ (ከቁርኣን) በመጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ በእርግጥም ቅጣቴን ገና አልቀመሱም፡፡ 38|9|ይልቁንም የአሸናፊውና የለጋሱ ጌታህ የችሮታው መጋዘኖች እነርሱ ዘንድ ናቸውን? 38|10|ወይስ የሰማያትና የምድር የመካከላቸውም ንግሥና የእነርሱ ነውን? (ነው ቢሉ) በመሰላሎችም ይውጡ፡፡ 38|11|እዚያ ዘንድ ከአሕዛብ የሆኑ ተሸናፊ ሰራዊት ናቸው፡፡ 38|12|ከእነርሱ በፊት የኑሕ ሕዝቦች፣ ዓድም፣ የችካሎች ባለቤት የሆነው ፈርዖንም አስተባበሉ፡፡ 38|13|ሰሙድም፣ የሉጥ ሰዎችም፣ የአይከት ሰዎችም (አስተባበሉ)፡፡ እነዚህ አሕዛቦቹ ናቸው፡፡ 38|14|ሁሉም መልክተኞቹን ያስዋሹ እንጅ ሌላ አይደሉም፡፡ ቅጣቴም ተረጋገጠባቸው፡፡ 38|15|እነዚህም ለእርሷ መመለስ የሌላትን አንዲትን ጩኸት እንጅ ሌላን አይጠባበቁም፡፡ 38|16|«ጌታችን ሆይ! ከምርመራው ቀን በፊት መጽሐፋችንን አስቸኩልልን» አሉም፡፡ 38|17|በሚሉት ነገር ላይ ታገስ፡፡ የኀይል ባለቤት የሆነውን ባሪያችንንም ዳውድን አውሳላቸው፡፡ እርሱ በጣም መላሳ ነውና፡፡ 38|18|እኛ ተራራዎችን ከቀትር በኋላና በረፋድም ከእርሱ ጋር የሚያወድሱ ሲሆኑ ገራንለት፡፡ 38|19|በራሪዎችንም (አእዋፍን) የሚሰበሰቡ ሆነው (ገራንለት)፡፡ ሁሉም ለእርሱ (ማወደስ) የሚመላለስ ነው፡፡ 38|20|መንግሥቱንም አበረታንለት፡፡ ጥበብንም ንግግርን መለየትንም ሰጠነው፡፡ 38|21|የተከራካሪዎቹም ወሬ መጥቶልሃልን? ምኩራቡን በተንጠላጠሉ ጊዜ፡፡ 38|22|በዳውድ ላይም በገቡ ጊዜ ከእነርሱም በደነገጠ ጊዜ «አትፍራ፤ (እኛ) ከፊላችን በከፊሉ ላይ ወሰን ያለፈ ሁለት ተከራካሪዎች ነን፡፡ በመካከላችንም በእውነት ፍረድ፡፡ አታዳላም፡፡ ወደ መካከለኛውም መንገድ ምራን፤» አሉት፡፡ 38|23|«ይህ ወንድሜ ነው፤ ለእርሱ ዘጠና ዘጠኝ ሴቶች በጎች አሉት፡፡ ለኔም አንዲት ሴት በግ አለችኝ፡፡ እርሷንም ዕድሌ አድርጋት አለኝ፡፡ በንግግርም አሸነፈኝ» አለው፡፡ 38|24|«ሴት በግህን ወደ በጎቹ (ለመቀላቀል) በመጠየቁ በእርግጥ በደለህ፡፡ ከተጋሪዎችም ብዙዎቹ ከፊላቸው በከፊሉ ላይ ወሰን ያልፋሉ፡፡ እነዚያ ያመኑትና መልካሞችን የሠሩት ብቻ ሲቀሩ፡፡ እነርሱም በጣም ጥቂቶች ናቸው» አለ፡፡ ዳውድም የፈተንነው መኾኑን ዐወቀ፡፡ ጌታውንም ምሕረትን ለመነ፡፡ ሰጋጅ ኾኖ ወደቀም፡፡ በመጸጸት ተመለሰም፡፡ 38|25|ለእርሱም እኛ ዘንድ መቅረብ (ክብር) መልካም መመለሻም አለው፡፡ 38|26|ዳውድ ሆይ! እኛ በምድር ላይ ምትክ አድርገንሃልና በሰዎች መካከል በእውነት ፍረድ፡፡ ዝንባሌሀንም አትከተል፤ከአላህ መንገድ ያሳሳትሃልና፡፡ እነዚያ ከአላህ መንገድ የሚሳሳቱ የምርመራውን ቀን በመርሳታቸው ለእነርሱ ብርቱ ቅጣት አላቸው፡፡ 38|27|ሰማይንና ምድርን በመካከላቸውም ያለውን ሁሉ ለከንቱ አልፈጠርንም፡፡ ይህ የእነዚያ የካዱት ሰዎች ጥርጣሬ ነው፡፡ ለእነዚያም ለካዱት ሰዎች ከእሳት ወዮላቸው! 38|28|በእውነቱ እነዚያን ያመኑትንና መልካሞችን የሠሩትን በምድር ውስጥ እንደሚያጠፉት እናደርጋለን? ወይስ አላህን ፊረዎቹን እንደ ከሓዲዎቹ እናደርጋለን? 38|29|(ይህ) ወዳንተ ያወረድነው ብሩክ መጽሐፍ ነው፡፡ አንቀጾቹን እንዲያስተነትኑና የአእምሮዎች ባለቤቶችም እንዲገሰጹ (አወረድነው)፡፡ 38|30|ለዳውድም ሱለይማንን ሰጠነው፡፡ ምን ያምር ባሪያ! (ሱለይማን)፣ እርሱ መላሳ ነው፡፡ 38|31|በእርሱ ላይ ከቀትር በኋላ በሦስት እግሮችና በአራተኛዋ ኮቴ ጫፍ የሚቆሙ ጮሌዎች ፈረሶች በተቀረቡለት ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 38|32|አለም «እኔ (ፀሐይ) በግርዶ እስከ ተደበቀች ድረስ ከጌታዬ ማስታወስ ፋንታ ፈረስን መውደድን መረጥኩ፡፡» 38|33|«በእኔ ላይ መልሷት» (አለ) አጋዶችዋንና አንገቶችዋንም ማበስ ያዘ፡፡ 38|34|ሱለይማንንም በእርግጥ ፈተንነው፡፡ በመንበሩም ላይ አካልን ጣልን፡፡ ከዚያም በመጸጸት ተመለሰ፡፡ 38|35|«ጌታዬ ሆይ! ለእኔ ማር፡፡ ከእኔ በኋላ ለአንድም የማይገባንም ንግሥና ስጠኝ፡፡ አንተ ለጋሱ አንተ ብቻ ነህና» አለ፡፡ 38|36|ነፋስንም በትእዛዙ ወደፈለገበት ስፍራ ልዝብ ኾና የምትፈስ ስትኾን ገራንለት፡፡ 38|37|ሰይጣናትንም ገንቢዎችንና ሰጣሚዎችን ሁሉ (ገራንለት)፡፡ 38|38|ሌሎችንም በፍንጆች ተቆራኞችን (ገራንለት)፡፡ 38|39|«ይህ ስጦታችን ነው፡፡ ያለግምት ለግስ፤ ወይም ጨብጥ» (አልነው)፡፡ 38|40|ለእርሱም እኛ ዘንድ መቅረብ፤ መልካም መመለሻም በእርግጥ አልለው፡፡ 38|41|ባሪያችንን አዩብንም አውሳላቸው፡፡ «እኔ ሰይጣን በጉዳትና በስቃይ ነካኝ» ሲል ጌታውን በተጣራ ጊዜ፡፡ 38|42|«በእግርህ (ምድርን) ምታ፡፡ ይህ ቀዝቃዛ መታጠቢያ መጠጥም ነው» (ተባለ)፡፡ 38|43|ለእርሱም ከእኛ ዘንድ ለችሮታ ባለአእምሮዎችንም ለመገሠጽ ቤተሰቦቹን ከእነርሱም ጋር መሰላቸውን ሰጠነው፡፡ 38|44|«በእጅህም ጭብጥ አርጩሜን ያዝ፡፡ በእርሱም (ሚስትህን) ምታ፡፡ ማላህንም አታፍርስ» (አልነው)፡፡ እኛ ታጋሸ ኾኖ አገኘነው፡፡ ምን ያምር ባሪያ እርሱ በጣም መላሳ ነው፡፡ 38|45|ባሮቻችንንም ኢብራሂምን፣ ኢስሐቅንና ያዕቆበንም፣ የኅይልና የማስተዋል ባለቤቶች የኾኑን አውሳላቸው፡፡ 38|46|እኛ ጥሩ በኾነች ጠባይ መረጥናቸው፡፡ (እርሷም) የመጨረሻይቱን አገር ማስታወስ ናት፡፡ 38|47|እነርሱም እኛ ዘንድ ከመልካሞቹ ምርጦች ናቸው፡፡ 38|48|ኢስማዒልንም፣ አልየሰዕንም፣ ዙልኪፍልንም አውሳ፡፡ ሁሉም ከበላጮቹ ናቸው፡፡ 38|49|ይህ መልካም ዝና ነው፡፡ ለአላህ ፈሪዎችም በእርግጥ ውብ የኾነ መመለሻ አላቸው፡፡ 38|50|በሮቻቸው ለእነርሱ የተከፈቱ ሲኾኑ የመኖሪያ ገነቶች አሏቸው፡፡ 38|51|በእርሷ ውስጥ የተደገፉ ኾነው በውስጧ በብዙ እሸቶችና በመጠጥም ያዝዛሉ፡፡ 38|52|እነርሱ ዘንድም ዓይኖቻቸውን (በባሎቻቸው ላይ) አሳጣሪዎች እኩያዎች (ሴቶች) አልሉ፡፡ 38|53|ይህ ለምርመራው ቀን የምትቀጠሩት ተሰፋ ነው፡፡ 38|54|ይህ ሲሳያችን ነው፡፡ ለእርሱ ምንም ማለቅ የለውም፡፡ 38|55|ይህ (ለአማኞች ነው)፡፡ ለጠማሞችም በጣም የከፋ መመለሻ አላቸው፡፡ 38|56|የሚገቧት ስትኾን ገሀነም (አለቻቸው)፡፡ ምንጣፊቱም ምንኛ ከፋች፡፡ 38|57|ይህ (ለከሓዲዎች ነው)፡፡ ይቅመሱትም፡፡ የፈላ ውሃና እዥ ነው፡፡ 38|58|ሌላም ከመሰሉ ዓይነቶች አልሉ፡፡ 38|59|ይህ ከእናንተ ጋር በመጋፈጥ ገቢ ጭፍራ ነው፤ (ይባላሉ)፡፡ ለእነርሱ አይስፋቸው፡፡ እነርሱ እሳትን ገቢዎች ናቸውና (ይላሉ)፡፡ 38|60|(ተከታዮቹ) ይላሉ «ይልቁን እናንተ አይስፋችሁ፡፡ እናንተ (ክህደቱን) ለእኛ አቀረባችሁት፡፡ መርጊያይቱም (ገሀነም) ከፋች፡፡» 38|61|«ጌታችን ሆይ! ይህንን ያቀረበልንን ሰው በእሳት ውስጥ እጥፍን ቅጣት ጨምርለት» ይላሉ፡፡ 38|62|ይላሉም «ለእኛ ምን አለን? ከመጥፎዎች እንቆጥራቸው የነበሩትን ሰዎች (እዚህ) አናይምሳ፡፡» 38|63|«መቀለጃ አድርገን ያዝናቸውን? ወይስ ዓይኖቻችን ከእነሱ ዋለሉ?» 38|64|ይህ በእርግጥ እምነት ነው፡፡ (እርሱም) የእሳት ሰዎች (የእርስ በእርስ) መካሰስ ነው፡፡ 38|65|«እኔ አስፈራሪ ብቻ ነኝ፡፡ ኀያል አንድ ከኾነው አላህ በቀር ምንም አምላክ የለም» በላቸው፡፡ 38|66|«የሰማያትና የምድር በመካከላቸውም ያለው ሁሉ ጌታ አሸናፊው መሓሪው ነው፡፡» 38|67|በላቸው «እርሱ (ቁርኣን) ታላቅ ዜና ነው፡፡ 38|68|«እናንተ ከእርሱ ዘንጊዎች ናችሁ፡፡ 38|69|(በአደም ነገር) «በሚከራከሩ ጊዜ በላይኛው ሰራዊት ለእኔ ምንም ዕውቀት አልነበረኝም፡፡ 38|70|«ወደእኔም አስፈራሪ ገላጭ መኾኔ እንጂ ሌላ አይወረድልኝም» (በል)፡፡ 38|71|ጌታህ «ለመላእክት እኔ ሰውን ከጭቃ ፈጣሪ ነኝ ባለ ጊዜ» (አስታውስ)፡፡ 38|72|«ፍጥረቱንም ባስተካከልኩና ከመንፈሴ በነፋሁበት ጊዜ ለእርሱ ሰጋጆች ኾናችሁ ውደቁ» (አልኩ)፡፡ 38|73|መላእክትም መላውም ባንድነት ሰገዱ፡፡ 38|74|ኢብሊስ ብቻ ሲቀር፡፡ ኮራ፤ ከከሓዲዎቹም ነበር፡፡ 38|75|(አላህም) «ኢብሊስ ሆይ! በሁለት እጆቼ (በኃይሌ) ለፈጠርኩት ከመስገድ ምን ከለከለህ? (አሁን) ኮራህን? ወይስ (ፊቱኑ) ከትዕቢተኞቹ ነበርክ?» አለው፡፡ 38|76|«እኔ ከእርሱ በላጭ ነኝ፡፡ ከእሳት ፈጠርከኝ፤ ከጭቃም ፈጠርከው» አለ፡፡ 38|77|(አላህ) አለው «ከእርሷ ውጣ፤ አንተ የተባረርክ ነህና፡፡» 38|78|«እርግማኔም እስከ ፍርዱ ቀን ድረስ ባንተ ላይ ይኹን፡፡» 38|79|«ጌታዬ ሆይ! እስከሚቀሰቀሱበት ቀን ድረስ አቆየኝም» አለ፡፡ 38|80|(አላህም) አለው «አንተ ከሚቆዩት ነህ፡፡» 38|81|«እስከ ታወቀው ወቅት ቀን ድረስ፡፡» 38|82|(እርሱም) አለ «በአሸናፊነትህ ይኹንብኝ፤ በመላ አሳስታቸዋለሁ፡፡» 38|83|«ከእነርሱ ምርጥ የኾኑት ባሮችህ ብቻ ሲቀሩ፡፡» 38|84|(አላህ) አለው «እውነቱም (ከኔ ነው)፡፡ እውነትንም እላለሁ፡፡ 38|85|ከአንተና ከእነርሱ ውስጥ ከተከተሉህ ባንድ ላይ ገሀነምን በእርግጥ እሞላታለሁ፡፡» 38|86|በላቸው «በእርሱ ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም፤ እኔም ከተግደርዳሪዎቹ አይደለሁም፡፡ 38|87|«እርሱ (ቁርኣን) ለዓለማት መገሠጫ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ 38|88|«ትንቢቱንም (እውነት መኾኑን) ከጊዜ በኋላ በእርግጥ ታውቁታላችሁ፡፡» 39|1|የመጽሐፉ መወረድ አሸናፊው ጥበበኛው ከኾነው አላህ ነው፡፡ 39|2|እኛ ወደ አንተ መጽሐፉን በእውነት (የተመላ) ሲኾን አወረድነው፡፡ አላህንም ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ ያጠራህ ኾነህ ተገዛው፡፡ 39|3|ንቁ! ፍጹም ጥሩ የኾነው ሃይማኖት የአላህ ብቻ ነው፡፡ እነዚያም ከእርሱ ሌላ (ጣዖታትን) ረዳቶች የያዙት «ወደ አላህ ማቃረብን እንዲያቀርቡን እንጅ ለሌላ አንገዛቸውም» (ይላሉ)፡፡ አላህ በዚያ እነርሱ በእርሱ በሚለያዩበት ነገር በመካከላቸው ይፈርዳል፡፡ አላህ እርሱ ውሸታም ከሓዲ የኾነን ሰው አያቀናም፡፡ 39|4|አላህ ልጅን መያዝ በፈለገ ኖሮ ከሚፈጥረው ውስጥ የሚሻውን ይመርጥ ነበር፡፡ ጥራት ተገባው፡፡ እርሱ አሸናፊው አንዱ አላህ ነው፡፡ 39|5|ሰማያትንና ምድርን በእወነት ፈጠረ፡፡ ሌሊትን በቀን ላይ ይጠቀልላል፡፡ ቀንንም በሌሊት ላይ ይጠቀልላል፤ ፀሐይንና ጨረቃንም ገራ፡፡ ሁሉም ለተወሰነ ጊዜ ይሮጣሉ፡፡ ንቁ! እርሱ አሸናፊው መሓሪው ነው፡፡ 39|6|ከአንዲት ነፍስ ፈጠራችሁ፡፡ ከዚያም ከእርሷ መቀናጆዋን አደረገ፡፡ ለእናንተም ከግመልና ከከብት፣ ከፍየል፣ ከበግ ስምንት ዓይነቶችን (ወንድና ሴት) አወረደ፡፡ በእናቶቻችሁ ሆዶች ውስጥ በሦስት ጨለማዎች ውስጥ ከመፍጠር በኋላ (ሙሉ) መፍጠርን ይፈጠራችኋል፡፡ ይህ ጌታችሁ አላህ ነው፡፡ ስልጣኑ የርሱ ብቻ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ ታዲያ ወዴት ትዞራላችሁ፡፡ 39|7|ብትክዱ አላህ ከእናንተ የተብቃቃ ነው፡፡ ለባሪያዎቹም ከህደትን አይወድም፡፡ ብታመሰግኑም፤ እርሱን ይወድላችኋል፡፡ ማንኛይቱም ኃጢኣትን ተሸካሚ ነፍስ የሌላይቱን ኃጢኣት አትሸከምም፡፡ ከዚያም መመለሻችሁ ወደ ጌታችሁ ነው፡፡ ትሠሩት የነበራችሁትንም ይነግራችኋል፡፡ እርሱ በልቦች ውስጥ ያሉትን ዐዋቂ ነውና፡፡ 39|8|ሰውንም ጉዳት ባገኘው ጊዜ ጌታውን ወደርሱ ተመላሽ ኾኖ ይጠራል፡፡ ከዚያም ከእርሱ ዘንድ ጸጋን በሰጠው ጊዜ ያንን ከዚያ በፊት ወደርሱ ይጸልይበት የነበረውን (መከራ) ይረሳል፡፡ ከመንገዱ ለማሳሳትም ለአላህ ባላንጣዎችን ያደርጋል፡፡ «በክህደትህ ጥቂትን ተጣቀም፡፡ አንተ በእርግጥ ከእሳት ጓዶች ነህ» በለው፡፡ 39|9|እርሱ የመጨረሻይቱን ዓለም (ቅጣት) የሚፈራ የጌታውንም ችሮታ የሚከጅል ሲኾን በሌሊት ሰዓቶች ሰጋጅና ቋሚ ኾኖ ለጌታው የሚግገዛ ሰው (እንደ ተስፋ ቢሱ ከሓዲ ነውን? በለው)፡፡ «እነዚያ የሚያውቁና እነዚያ የማያውቁ ይስተካከላሉን?» በላቸው፡፡ የሚገነዘቡት ባለ አእምሮዎቹ ብቻ ናቸው፡፡ 39|10|(ጌታችሁ) «እናንተ ያመናችሁ ባሮቼ ሆይ! ጌታችሁን ፍሩ፡፡ ለነዚያ በዚህች በቅርቢቱ ዓለም መልካም ለሠሩት መልካም ምንዳ አላቸው፡፡ የአላህ ምድርም ሰፊ ናት፤ (ብትቸገሩ ተሰደዱ)፡፡ ታጋሾቹ ምንዳቸውን የሚሰጡት ያለግምት ነው» (ይላል) በላቸው፡፡ 39|11|በል «እኔ አላህን ሃይማኖትን ለርሱ ያጠራሁ ኾኜ እንድግገዛው ታዘዝኩ፡፡ 39|12|«የሙስሊሞችም መጀመሪያ እንድኾን ታዘዝኩ፡፡» 39|13|«እኔ ከጌታዬ ባምጽ የታላቁን ቀን ቅጣት እፈራለሁ» በል፡፡ 39|14|አላህን «ሃይማኖቴን ለእርሱ ያጠራሁ ኾኜ እግገዛዋለሁ» በል፡፡ 39|15|«ከእርሱ ሌላ የሻችሁትን ተገዙ፡፡ ከሳሪዎች ማለት እነዚያ በትንሣኤ ቀን ነፍሶቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ያከሰሩ ናቸው፡፡ ንቁ! ይህ እርሱ ግልጽ ከሳራ ነው» በላቸው፡፡ 39|16|ለእነርሱ ከበላያቸው ከእሳት የኾኑ (ድርብርብ) ጥላዎች አልሏቸው፡፡ ከበታቻቸውም ጥላዎች አልሏቸው። ይህ አላህ ባሮቹን (እንዲጠነቀቁ) በእርሱ ያስፈራራበታል፡፡ «ባሮቼ ሆይ! ስለዚህ ፍሩኝ፡፡» 39|17|እነዚያም ጣዖታትን የሚግገዟት ከመኾን የራቁ ወደ አላህም የዞሩ ለእነርሱ ብስራት አልላቸው፡፡ ስለዚህ ባሮቼን አብስር፡፡ 39|18|እነዚያን ንግግርን የሚያዳምጡትንና መልካሙን የሚከተሉትን (አብስር)፡፡ እነዚያ እነርሱ አላህ የመራቸው ናቸው፡፡ እነዚያም እነርሱ ባለአእምሮዎቹ ናቸው፡፡ 39|19|በእርሱ ላይ የቅጣት ቃል የተረጋገጠችበትን ሰው (ትመራዋለህን?) አንተ በእሳት ውስጥ ያለን ሰው ታድናለህን? 39|20|ግን እነዚያ ጌታቸውን የፈሩ ለእነርሱ ከበላያቸው የታነጹ ሰገነቶች ያሏቸው ሰገነቶች ከስሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው የኾኑ አልሏቸው፡፡ (ይህንን) አላህ ቃል ገባላቸው፡፡ አላህ ቃሉን አያፈርስም፡፡ 39|21|አላህ ከሰማይ ውሃን እንዳወረደና በምድርም ውስጥ ምንጮች አድርጎ እንዳስገባው አላየህምን? ከዚያም በእርሱ ዓይነቶቹ የተለያዩን አዝመራ ያወጣል፡፡ ከዚያም ይደርቃል፡፡ ገርጥቶም ታየዋለህ፡፡ ከዚያም ስብርብር ያደርገዋል፡፡ በዚህ ውስጥ ለባለ አእምሮዎች ግሣጼ አለበት፡፡ 39|22|አላህ ደረቱን ለእስልምና ያስፋለትና እርሱም ከጌታው ዘንድ በብርሃን ላይ የኾነ ሰው (ልቡ እንደ ደረቀ ሰው ነውን?) ልቦቻቸውም ከአላህ መወሳት ለደረቁ ሰዎች ወዮላቸው፡፡ እነዚያ በግልጽ መሳሳት ውስጥ ናቸው፡፡ 39|23|አላህ ከዜና ሁሉ መልካምን፣ ተመሳሳይ፣ ተደጋጋሚ የኾነን መጽሐፍ አወረደ፡፡ ከእርሱ (ግሣጼ) የእነዚያ ጌታቸውን የሚፈሩት ሰዎች ቆዳዎች ይኮማተራሉ፡፡ ከዚያም ቆዳዎቻቸውና ልቦቻቸው ወደ አላህ (ተስፋ) ማስታወስ ይለዝባሉ፡፡ ይህ የአላህ መምሪያ ነው፡፡ በእርሱ የሚሻውን ሰው ይመራበታል፡፡ አላህም የሚያጠመው ሰው ለእርሱ ምንም አቅኚ የለውም፡፡ 39|24|በትንሣኤ ቀን ክፉን ቅጣት በፊቱ የሚመክት ሰው (ከቅጣት እንደሚድን ነውን?) ለበዳዮችም «ትሠሩት የነበራችሁትን (ቅጣቱን) ቅመሱ» ይባላሉ፡፡ 39|25|ከእነሱ በፊት የነበሩት አስተባበሉ፡፡ ቅጣቱም ከማያውቁት በኩል መጣባቸው፡፡ 39|26|አላህም በቅርቢቱ ሕይወት ውርደትን አቀመሳቸው፡፡ የመጨረሻይቱም ዓለም ቅጣት በጣም ትልቅ ነው፡፡ የሚያውቁ ቢኾኑ ኖሮ (አያስተባብሉም ነበር)፡፡ 39|27|በዚህም ቁርኣን ውስጥ ለሰዎች ይገሠጹ ዘንድ ከየምሳሌው ሁሉ በእርግጥ አብራራን፡፡ 39|28|መዛባት የሌለበት ዐረብኛ ቁርኣን ሲኾን (አብራራነው)፡፡ ሊጠነቀቁ ይከጀላልና፡፡ 39|29|አላህ በእርሱ ተጨቃጫቂዎች የኾኑ ተጋሪዎች ያሉትን ባሪያና ለአንድ ሰው ብቻ ንጹሕ የኾነን ባሪያ (ለሚያጋራና ባንድነቱ ለሚያምን ሰው) ምሳሌ አደረገ፡፡ በምሳሌ ይስተካከላሉን? ምስጋና ለአላህ ይገባው፡፡ በእውነቱ አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 39|30|አንተ ሟች ነህ፤ እነርሱም ሟቾች ናቸው፡፡ 39|31|ከዚያም እናንተ በትንሣኤ ቀን እጌታችሁ ዘንድ ትከራከራላችሁ፡፡ 39|32|በአላህም ላይ ከዋሸ እውነቱንም በመጣለት ጊዜ ከአስተባበለ ሰው ይበልጥ በዳይ ማን ነው? በገሀነም ውስጥ ለከሓዲዎች መኖሪያ የለምን? (አለ እንጅ)፡፡ 39|33|ያም በእውነት የመጣው በእርሱ ያመነውም እነዚያ እነርሱ አላህን ፊሪዎች ናቸው፡፡ 39|34|ለእነርሱ በጌታቸው ዘንድ የሚሹት ሁሉ አልላቸው፡፡ ይህ የበጎ አድራጊዎች ምንዳ ነው፡፡ 39|35|አላህ ያንን (በስሕተት) የሠሩትን መጥፎ ሥራ ከእነርሱ ሊሰርይላቸው በዚያም ይሠሩት በነበሩት በመልካሙ ሥራ ምንዳቸውን ሊመነዳቸው (ይህንን አደረገ)፡፡ 39|36|አላህ ባሪያውን በቂ አይደለምን? በእነዚያ ከእርሱ ሌላ በኾኑትም (ጣዖታት) ያስፈራሩሃል፡፡ አላህ የሚያጠመውም ሰው ለርሱ ምንም አቅኚ የለውም፡፡ 39|37|አላህ የሚያቀናውም ሰው ለእርሱ ምንም አጥማሚ የለውም፡፡ አላህ አሸናፊ የመበቀል ባለቤት አይደለምን? 39|38|ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ ማን እንደ ኾነ ብትጠይቃቸው «አላህ ነው» ይሉሃል፡፡ «ከአላህ ሌላ የምትግገዟቸውን (ጣዖታት) አያችሁን? (ንገሩኝ) አላህ በጉዳት ቢፈልገኝ እነርሱ ጉዳቱን ገላጮች ናቸውን? ወይስ በችሮታው ቢፈቅደኝ እነርሱ ችሮታውን አጋጆች ናቸውን?» በላቸው፡፡ «አላህ በቂዬ ነው፡፡ በእርሱ ላይ ተመኪዎች ይመካሉ» በል፡፡ 39|39|(ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው «ሕዝቦቼ ሆይ! ባላችሁበት ኹኔታ ላይ ሥሩ፡፡ እኔ ሠሪ ነኝና፡፡ ወደፊትም ታውቃላችሁ፡፡» 39|40|ያንን የሚያሳፍረው ቅጣት የሚመጠበትንና በእርሱ ላይ ዘውታሪ ቅጣት የሚሰፍርበትን (ታውቃላችሁ) 39|41|እኛ መጽሐፉን ባንተ ላይ ለሰዎች (ጥቅም) በእውነት አወረድነው፡፡ የተመራም ሰው ለነፍሱ ነው፡፡ የጠመመም ሰው የሚጠምመው (ጉዳቱ) በእርሷ ላይ ነው፡፡ አንተም (ታስገድዳቸው ዘንድ) በእነርሱ ላይ ጠባቂ አይደለህም፡፡ 39|42|አላህ ነፍሶችን በሞታቸው ጊዜ ይወስዳል፡፡ ያችንም ያልሞተችውን በእንቅልፏ ጊዜ (ይወስዳታል)፡፡ ታዲያ ያችን ሞትን የፈረደባትን ይይዛታል፡፡ ሌላይቱንም እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ ይለቅቃታል፡፡ በዚህ ውስጥ ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች ምልክቶች አልሉበት፡፡ 39|43|ይልቁንም (ቁረይሾች) ከአላህ ሌላ አማላጆችን ያዙ፡፡ «እነርሱ ምንንም የማይችሉና የማያውቁ ቢኾኑም?» በላቸው፡፡ 39|44|«ምልጃ መላውም የአላህ ብቻ ነው፡፡ የሰማያትና የምድር ሥልጣን የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ከዚያም ወደእርሱ ትመለሳላችሁ» በላቸው፡፡ 39|45|አላህም ብቻውን በተወሳ ጊዜ የእነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ሰዎች ልቦች ይሸማቀቃሉ፤ (ይደነብራሉ)፡፡ እነዚያም ከእርሱ ሌላ የኾኑት (ጣዖታት) በተወሱ ጊዜ እነርሱ ወዲያውኑ ይደሰታሉ፡፡ 39|46|«ሰማያትንና ምድርን የፈጠርክ ሩቁንም ቅርቡንም ዐዋቂ የኾንክ አላህ ሆይ! አንተ በባሮችህ መካከል በእዚያ በእርሱ ይለያዩበት በነበሩት ነገር ትፈርዳለህ» በል፡፡ 39|47|ለእነዚያም ለበደሉት በምድር ያለው ሁሉ መላውም ከእርሱ ጋር መሰሉም ቢኖራቸው ኖሮ በትንሣኤ ቀን ከቅጣቱ ክፋት የተነሳ በእርሱ ነፍሶቻቸውን በተበዡበት ነበር፡፡ ለእነርሱም ከአላህ ዘንድ ያስቡት ያልነበሩት ሁሉ ይገለጽላቸዋል፡፡ 39|48|ለእነርሱም የሠሩዋቸው መጥፎዎቹ ይገለጹላቸዋል፡፡ በእነርሱም ላይ በእርሱ ያላግጡበት የነበሩት ቅጣት ይሰፍርባቸዋል፡፡ 39|49|ሰውም ጉዳት ባገኘው ጊዜ ይጠራናል፡፡ ከዚያም ከእኛ የኾነውን ጸጋ በሰጠነው ጊዜ «እርሱን የተሰጠሁት፤ በዕውቀት ብቻ ነው» ይላል፡፡ ይልቁንም እርሷ (ጸጋይቱ) መፈተኛ ናት፡፡ ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 39|50|እነዚያ ከእነርሱ በፊት የነበሩት ሕዝቦች በእርግጥ ብለዋታል፡፡ ይሠሩት የነበሩትም ነገር ከእነርሱ አልጠቀማቸውም፡፡ 39|51|የሠሩዋቸውም መጥፎዎች (ቅጣት) አገኛቸው፡፡ ከእነዚህም እነዚያ የበደሉት የሠሩዋቸው መጥፎዎች (ፍዳ) በእርግጥ ይነካቸዋል፡፡ እነርሱም አምላጮች አይደሉም፡፡ 39|52|አላህ ሲሳዩን ለሚሻው ሰው የሚያሰፋ የሚያጠብም መኾኑን አያውቁምን? በዚህ ውስጥ ለሚያምኑት ሕዝቦች ግሣጼዎች አሉበት፡፡ 39|53|በላቸው «እናንተ በነፍሶቻችሁ ላይ ድንበር ያለፋችሁ ባሮቼ ሆይ! ከአላህ እዝነት ተስፋ አትቁረጡ፡፡ አላህ ኃጢኣቶችን በመላ ይምራልና፡፡ እነሆ እርሱ መሓሪው አዛኙ ነውና፡፡ 39|54|«ቅጣቱም ወደእናንተ ከመምጣቱና ከዚያም የማትርረዱ ከመኾናችሁ በፊት ወደ ጌታችሁ (በመጸጸት) ተመለሱ፡፡ ለእርሱም ታዘዙ፡፡ 39|55|«እናንተ የማታውቁ ስትኾኑም ቅጣቱ በድንገት ሳይመጣባችሁ በፊት ከጌታችሁ ወደናንተ የተወረደውን መልካሙን (መጽሐፍ) ተከተሉ፡፡» 39|56|(የካደች) ነፍስ «እኔ ከሚሳለቁት የነበርኩ ስኾን በአላህ በኩል ባጓደልኩት ዋ ጸጸቴ» ማለቷን (ለመፍራት)፤ 39|57|ወይም «አላህ በመራኝ ኖሮ ከሚጠነቀቁት እኾን ነበር» ማለቷን (ለመፍራት)፡፡ 39|58|ወይም ቅጣቱን በምታይ ጊዜ «ለእኔ (ወደ ምድረ ዓለም) አንድ ጊዜ መመለስ በኖረኝና ከበጎ አድራጊዎቹ በኾንኩ» ማለቷን (ለመፍራት መልካሙን ተከተሉ)፡፡ 39|59|የለም ተመርተሃል፡፡ አንቀጾቼ በእርግጥ መጥተውልሃል፡፡ በእነርሱም አስተባብለሃል፡፡ ኮርተሃልም፡፡ ከከሓዲዎቹም ኾነሃል፤ (ይባላል)፡፡ 39|60|በትንሣኤ ቀንም እነዚያን በአላህ ላይ የዋሹትን ፊቶቻቸው የጠቆሩ ኾነው ታያቸዋለህ፡፡ በገሀነም ውስጥ ለትዕቢተኞች መኖሪያ የለምን? 39|61|እነዚያንም የተጠነቀቁትን በማግኛቸው ስፍራ ኾነው አላህ ያድናቸዋል፡፡ ክፉ ነገር አይነካቸውም፡፡ እነርሱም አያዝኑም፡፡ 39|62|አላህ የነገሩ ሁሉ ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ አስተናባሪ ነው፡፡ 39|63|የሰማያትና የምድር (ድልብ) መክፈቻዎች የእርሱ ብቻ ናቸው፡፡ እነዚያም በአላህ አንቀጾች የካዱት እነዚያ እነሱ ከሳሪዎቹ ናቸው፡፡ 39|64|«እናንተ መሃይማን ሆይ! ከአላህ ሌላን እንድግገዛ ታዙኛላችሁን?» በላቸው፡፡ 39|65|ብታጋራ ሥራህ በእርግጥ ይታበሳል፡፡ በእርግጥም ከከሓዲዎቹ ትኾናለህ ማለት ወደ አንተም ወደእነዚያም ካንተ በፊት ወደነበሩት በእርግጥ ተወርዷል፡፡ 39|66|ይልቅ አላህን ብቻ ተገዛም፡፡ ከአመስጋኞቹም ኹን፡፡ 39|67|አላህንም በትንሣኤ ቀን ምድር በመላ ጭብጡ ስትኾን፤ ሰማያትም በኀይሉ የሚጠቀለሉ ሲኾኑ (ከርሱ ጋር ሌላን በማጋራታቸው) ተገቢ ክብሩን አላከበሩትም፡፡ ከሚያጋሩት ጠራ፤ ላቀም፡፡ 39|68|በቀንዱም ይንነፋል፡፡ በሰማያት ውስጥ ያለው ፍጡርና በምድርም ውስጥ ያለው ፍጡር ሁሉ አላህ የሻው ሲቀር በድንጋጤ ይሞታል፡፡ ከዚያም በእርሱ ሌላ (መንነፋት) ይንነፋል፡፡ ወዲያውም እነርሱ (የሚሠራባቸውን) የሚጠባበቁ ኾነው ቋሚዎች ይኾናሉ፡፡ 39|69|ምድርም በጌታዋ ብርሃን ታበራለች፡፡ መጽሐፉም ይቅቀረባል፡፡ ነቢያቱና ምስክሮቹም ይመጣሉ፡፡ በመካከላቸውም በእውነት ይፈረዳል፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 39|70|ነፍስም ሁሉ የሠራችውን ሥራ ትሞላለች፤ (ትሰፈራለች)፡፡ እርሱም የሚሠሩትን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 39|71|እነዚያ የካዱትም የተከፋፈሉ ጭፍሮች ኾነው ወደ ገሀነም ይንነዳሉ፡፡ በመጧትም ጊዜ ደጃፎችዋ ይከፈታሉ፡፡ ዘበኞችዋም «ከእናንተ የኾኑ መልክተኞች የጌታችሁን አንቀጾች በናንተ ላይ የሚያነቡላችሁ የዚህንም ቀን መገናኘት የሚያስጠነቅቋችሁ አልመጡዋ ችሁምን?» ይሏቸዋል፡፡ «የለም መጥተውናል፤ ግን የቅጣቲቱ ቃል በከሓዲዎች ላይ ተረጋገጠች» ይላሉ፡፡ 39|72|«የገሀነምን ደጃፎች በውስጧ ዘውታሪዎች ስትኾኑ ግቡ፡፡ የትዕቢተኞችም መኖሪያ ምን ትከፋ!» ይባላሉ፡፡ 39|73|እነዚያም ጌታቸውን የፈሩት የተከፋፈሉ ጭፍሮች ኾነው ወደ ገነት ይንነዳሉ፡፡ በመጧትም ጊዜ ደጃፎችዋ የተከፈቱ ሲኾኑ ዘበኞችዋም ለእነርሱ «ሰላም በናንተ ላይ ይኹን፡፡ ተዋባችሁ፡፡ ዘውታሪዎች ኾናችሁ ግቧት» በሏቸው ጊዜ (ይገቧታል)፡፡ 39|74|«ምስጋና ለአላህ ለዚያ ተስፋ ቃሉን ለሞላልን፡፡ የገነትን ምድር በምንሻው ስፍራ የምንሰፍር ስንኾን ላወረሰን ይገባው» ይላሉም፡፡ የሠሪዎችም ምንዳ ምን ያምር! 39|75|መላእክትንም በጌታቸው ምስጋና ቀላቅለው የሚያጠሩ ሲኾኑ በዐርሹ ዙሪያ ከባቢዎች ኾነው ታያለህ፡፡ በመካከላቸው በእውነት ይፈረዳል፡፡ ይባላልም፤ «ምስጋና ለአላህ ለዓለማት ጌታ ይገባው፡፡» 40|1|ሐ.መ (ሓ.ሚም)፤ 40|2|የመጽሐፉ መወረድ አሸናፊ ዐዋቂ ከሆነው አላህ ነው፡፡ 40|3|ኀጢአትን መሓሪ፣ ጸጸትንም ተቀባይ፣ ቅጣተ ብርቱ፣ የልግስና ባለቤት ከኾነው (አላህ የወረደ ነው)፡፡ ከእርሱ በቀር አምላክ የለም፡፡ መመለሻው ወደርሱ ብቻ ነው፡፡ 40|4|በአላህ አንቀጾች እነዚያ የካዱት ቢኾኑ እንጅ ማንም (በመዝለፍ) አይከራከርም፡፡ በያገሮችም ውስጥ መዘዋወራቸው አይሸንግልህ፡፡ 40|5|ከእነርሱ በፊት የኑሕ ሕዝቦች ከኋላቸውም አሕዛቦቹ አስተባባሉ፡፡ ሕዝቦችም ሁሉ መልክተኛቸውን ሊይዙ አሰቡ፡፡ በውሸትም በእርሱ እውነትን ሊያጠፉበት ተከራከሩ፡፡ ያዝኳቸውም፡፡ ታዲያ ቅጣቴ እንዴት ነበር? 40|6|እንደዚሁም የጌታህ ቃል በእነዚያ በካዱት ላይ እነርሱ የእሳት ጓዶች ናቸው ማለት ተረጋገጠች፡፡ 40|7|እነዚያ ዐርሹን የሚሸከሙት እነዚያም በዙሪያው ያሉት በጌታቸው ምስጋና ያወድሳሉ፡፡ በእርሱም ያምናሉ፡፡ «ጌታችን ሆይ! ነገሩን ሁሉ በእዝነትና በዕውቀት ከበሃል፡፡ ስለዚህ ለእነዚያ ለተጸጸቱት መንገድህንም ለተከተሉት ምሕረት አድርግላቸው፡፡ የእሳትንም ቅጣት ጠብቃቸው፡፡» እያሉ ለእነዚያ ላመኑት ምሕረትን ይለምናሉ፡፡ 40|8|«ጌታችን ሆይ! እነርሱንም፣ ከአባቶቻቸውና ከሚስቶቻቸውም፣ ከዝርዮቻቸውም፣ የበጀውን ሁሉ እነዚያን ቃል የገባህላቸውን የመኖሪያ ገነቶች አግባቸው፡፡ አንተ አሸናፊው ጥበበኛው አንተ ነህና፡፡ 40|9|«ከቅጣቶችም ጠብቃቸው፡፡ በዚያ ቀንም የምትጠብቃውን ሰው በእርግጥ አዘንክለት፡፡» ይህም እርሱ ታላቅ ማግኘት ነው፡፡ 40|10|እነዚያ የካዱት ሰዎች «ወደ እምነት በምትጠሩና በምትክዱ ጊዜ አላህ (እናንተን) መጥላቱ ነፍሶቻችሁን (ዛሬ) ከመጥላታችሁ የበለጠ ነው» በማለት ይጥጠራሉ፡፡ 40|11|«ጌታችን ሆይ! ሁለትን ሞት አሞትከን፡፡ ሁለትንም ሕይወት ሕያው አደረግከን፡፡ በኃጢኣቶቻችንም መሰከርን፡፡ ታዲያ (ከእሳት) ወደ መውጣት መንገድ አለን?» ይላሉ፡፡ 40|12|«ይህ እነሆ አላህ ብቻውን በተጠራ ጊዜ ስለ ካዳችሁ በእርሱም ተጋሪ ቢደረግ የምታምኑ ስለ ኾናችሁ ነው፡፡ ስለዚህ ፍርዱ ከፍተኛ ታላቅ ለኾነው አላህ ብቻ ነው፡፡» 40|13|እርሱ ያ (ለአምላክነቱ) ምልክቶቹን የሚያሳያችሁ ለእናንተም ከሰማይ ሲሳይን የሚያወርድላችሁ ነው፡፡ ወደእርሱም የሚመለስ ሰው ቢኾን እንጂ ሌላው አይገሰጽም፡፡ 40|14|አላህንም ከሓዲዎች ቢጠሉም ሃይማኖትን ለእርሱ አጥሪዎች ኾናችሁ ተገዙት፡፡ 40|15|(እርሱ) ደረጃዎችን ከፍ አድራጊ የዐርሹ ባለቤት ነው፡፡ የመገናኛውን ቀን ያስፈራራ ዘንድ ከባሮቹ በሚሻው ሰው ላይ ከትዕዛዙ መንፈስን (ራእይን) ያወርዳል፡፡ 40|16|እነርሱ (ከመቃብር) በሚወጡበት ቀን በአላህ ላይ ከእነርሱ ምንም ነገር አይደበቅም፡፡ «ንግሥናው ዛሬ ለማን ነው?» (ይባላል፤)፡፡ «ለአሸናፊው ለአንዱ አላህ ብቻ ነው» (ይባላል)፡፡ 40|17|«ዛሬ ነፍስ ሁሉ በሠራችው ሥራ ትምመነዳለች፡፡ ዛሬ በደል የለም፡፡ አላህ በእርግጥ ምርመራው ፈጣን ነው» (ይባላል)፡፡ 40|18|ቅርቢቱንም (የትንሣኤን) ቀን ልቦች ጭንቀትን የተመሉ ኾነው ላንቃዎች ዘንድ የሚደርሱበትን ጊዜ አስጠንቅቃቸው፡፡ ለበዳዮች ምንም ወዳጅና ተሰሚ አማላጅ የላቸውም፡፡ 40|19|(አላህ) የዓይኖችን ክዳት ልቦችም የሚደብቁትን ሁሉ ያውቃል፡፡ 40|20|አላህም በእውነት ይፈርዳል፡፡ እነዚያም ከእርሱ ሌላ የሚግገዟቸው በምንም አይፈርዱም፡፡ አላህ እርሱ ሰሚው ተመልካቹ ነው፡፡ 40|21|የእነዚያን ከእነርሱ በፊት የነበሩትን ሕዝቦች ፍጻሜ እንዴት እንደነበረ ይመለከቱ ዘንድ በምድር ላይ አይኼዱምን? በኀይልና በምድር ላይ በተዋቸው ምልክቶች፤ ከእነርሱ ይበልጥ የበረቱ ነበሩ፡፡ አላህም በኀጢአቶቻቸው ያዛቸው፡፡ ለእነርሱም ከአላህ (ቅጣት) ምንም ጠባቂ አልነበራቸውም፡፡ 40|22|ይህ (መያዝ) እነርሱ መልክተኞቻቸው በተዓምራቶች ይመጡባቸው ስለነበሩና ስለ ካዱ ነው፡፡ አላህም ያዛቸው፡፡ እርሱ ኀያል ቅጣተ ብርቱ ነውና፡፡ 40|23|ሙሳንም በተዓምራቶቻችንና በግልጽ ማስረጃ በእርግጥ ላክነው፡፡ 40|24|ወደ ፈርዖንና ወደ ሃማን፤ ወደ ቃሩንም (ላክነው)፡፡ «ድግምተኛ ውሸታም ነው» አሉም፡፡ 40|25|ከእኛ ዘንድ እውነትን ይዞ በመጣላቸውም ጊዜ «የእነዚያን ከእርሱ ጋር ያመኑትን ሰዎች ወንዶች ልጆች ግደሉ፤ ሴቶቻቸውንም አስቀሩ» አሉ፡፡ የከሓዲዎችም ተንኮል በጥፋት ውስጥ እንጅ አይደለም፡፡ 40|26|ፈርዖንም «ተዉኝ፤ ሙሳን ልግደል፡፡ ጌታውንም ይጥራ፡፡ ያድነው እንደኾነ፡፡ እኔ ሃይማኖታችሁን ሊለውጥ፤ ወይም በምድር ውስጥ ጥፋትን ሊያሰራጭ እፈራለሁና» አለ፡፡ 40|27|ሙሳም «እኔ በምርመራው ቀን ከማያምን ትዕቢተኛ ሁሉ በጌታዬና በጌታችሁ ተጠበቅሁ» አለ፡፡ 40|28|ከፈርዖንም ቤተሰቦች አንድ እምነቱን የሚደብቅ ምእመን ሰው አለ፡- «ሰውየውን ከጌታችሁ በተዓምራቶች በእርግጥ የመጣለችሁ ሲኾን ‹ጌታዬ አላህ ነው› ስለሚል ትገድላላችሁን? ውሸታምም ቢኾን ውሸቱ በርሱው ላይ ነው፡፡ እውነተኛ ቢኾን ግን የዚያ የሚያሰፈራራችሁ ከፊሉ ያገኛችኋል፡፡ አላህ ያንን እርሱ ድንበር አላፊ ውሸታም የኾነውን አይመራምና፡፡ 40|29|«ወገኖቼ ሆይ! በምድር ላይ አሸናፊዎች ስትኾኑ ዛሬ መንግስቱ የእናንተ ነው፡፡ ታዲያ ከአላህ ቅጣት ቢመጣብን የሚያድነን ማን ነው?» (አለ)፡፡ ፈርዖን «የማየውን ነገር እንጅ፤ አላመለክታችሁም፡፡ ቅኑንም መንገድ እንጅ አልመራችሁም» አላቸው፡፡ 40|30|ያም ያመነው ሰው አለ «እኔ በናንተ ላይ የአሕዛቦቹን ቀን ብጤ እፈራላችኋለሁ፡፡ 40|31|«የኑሕን ሕዝቦች፣ የዓድንና የሰሙድንም፣ የእነዚያንም ከኋላቸው የነበሩትን ልማድ ብጤ (እፈራላችኋለሁ)፡፡ አላህም ለባሮቹ መበደልን የሚሻ አይደለም፡፡ 40|32|«ወገኖቼ ሆይ! እኔ በእናንተ ላይ የመጠራሪያን ቀን እፈራለሁ፡፡» 40|33|ወደ ኋላ ዞራችሁ በምትሸሹበት ቀን፤ ለናንተ ከአላህ (ቅጣት) ምንም ጠባቂ የላችሁም፡፡ አላህም የሚያጠመው ሰው ለርሱ ምንም አቅኚ የለውም፡፡ 40|34|ዩሱፍም ከዚህ በፊት ግልጽ ማስረጃዎችን በእርግጥ አመጣላቸሁ፡፡ ከዚያም እርሱ ካመጣላችሁ ነገር ከመጠራጠር አልተወገዳችሁም፡፡ በጠፋም ጊዜ «አላህ ከእርሱ ኋላ መልክተኛን በጭራሽ አይልክም» አላችሁ፡፡ አላህ እንደዚሁ ድንበር አላፊ ተጠራጣሪ የኾነን ሰው ያሳስታል፡፡ 40|35|እነዚያ፤ የመጣላቸው አስረጅ ሳይኖር በአላህ ተዓምራቶች የሚከራከሩ (ክርክራቸው) አላህ ዘንድና እነዚያም አመኑት ዘንድ መጠላቱ በጣም ተለቀ፡፡ እንደዚሁ አላህ በኩሩ ጨካኝ (ሰው) ልብ ሁሉ ላይ ያትማል፡፡ 40|36|ፈርዖንም አለ «ሃማን ሆይ! መንገዶችን እደርስ ዘንድ ረዢም ሕንጻን ለእኔ ካብልኝ፡፡ 40|37|«የሰማያትን መንገዶች (እደርስ ዘንድ)፣ ወደ ሙሳም አምላክ እመለከት ዘንድ፡፡ እኔም ውሸታም ነው ብዬ በእርግጥ እጠረጥረዋለሁ» (አለ)፡፡ እንደዚሁም ለፈርዖን መጥፎ ሥራው ተሸለመለት፡፡ ከቅን መንገድም ታገደ፡፡ የፈርዖንም ተንኮል በከሳራ ውስጥ እንጅ አይደለም፡፡ 40|38|ያም ያመነው አለ «ወገኖቼ ሆይ! ተከተሉኝ፡፡ ቀጥታውን መንገድ እመራችኋለሁና፡፡ 40|39|«ወገኖቼ ሆይ! ይህቺ ቅርቢቱ ሕይወት (ጥቂት) መጣቀሚያ ብቻ ናት፡፡ መጨረሻይቱም ዓለም እርሷ መርጊያ አገር ናት፡፡» 40|40|«መጥፎን የሠራ ሰው ብጤዋን እንጅ አይምመነዳም፡፡ እርሱ ምእመን ኾኖ ከወንድ ወይም ከሴት በጎን የሠራም ሰው እነዚያ ገነትን ይገባሉ፡፡ በእርሷ ውስጥ ያለ ቁጥጥር ይመገባሉ፡፡ 40|41|«ወገኖቼም ሆይ! ወደ መዳን የምጠራችሁ ስኾን ወደ እሳትም የምትጠሩኝ ስትኾኑ ለኔ ምን አለኝ! 40|42|«በአላህ ልክድና በእርሱም ለእኔ ዕውቀት የሌለኝን ነገር በእርሱ እንዳጋራ ትጠሩኛላችሁ፡፡ እኔም ወደ አሸናፊው፤ መሓሪው (አላህ) እጠራችኋለሁ፡፡ 40|43|«በእርግጥ ወደእርሱ የምትጠሩብኝ (ጣዖት) ለእርሱ በቅርቢቱም ኾነ በመጨረሻይቱ ዓለም (ተሰሚ) ጥሪ የለውም፡፡ መመለሻችንም በእርግጥ ወደ አላህ ነው፡፡ ወሰን አላፊዎቹም እነሱ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ 40|44|«ወደ ፊትም ለእናንተ የምላችሁን ምክር (ቅጣትን በምታዩ ጊዜ) ታስታውሳላችሁ፡፡ ነገሬንም ሁሉ ወደ አላህ አስጠጋለሁ፡፡ አላህ ባሮቹን ተመልካች ነውና፡፡» 40|45|ከመከሩዋቸውም መጥፎዎች አላህ ጠበቀው፡፡ በፈርዖን ቤተሰቦችም ላይ ክፉ ቅጣት ሰፈረባቸው፡፡ 40|46|እሳት በጧትና በማታ በእርሷ ላይ ይቀርባሉ፡፡ ሰዓቲቱም በምትኾንበት ቀን «የፈርዖንን ቤተሰቦች ብርቱን ቅጣት (ገሀነምን) አግቡዋቸው» (ይባላል)፡፡ 40|47|በእሳትም ውስጥ የሚከራከሩበትን ጊዜ (አስታውስ)፡፡ ደካማዎቹም ለእነዚያ ለኮሩት «እኛ ለእናንተ ተከታዮች ነበርንና እናንተ (አሁን) ከእሳት ከፊሉን ከእኛ ላይ ገፍታሪዎች ናችሁን?» ይላሉ፡፡ 40|48|እነዚያም የኮሩት «እኛ ሁላችንም በውስጧ ነን፡፡ አላህ በባሮቹ መካከል በእርግጥ ፈረደ» ይላሉ፡፡ 40|49|እነዚያም በእሳት ውሰጥ ያሉት ለገሀነም ዘበኞች «ጌታችሁን ለምኑልን፤ ከእኛ ላይ ከቅጣቱ አንድን ቀን ያቃልልን» ይላሉ፡፡ 40|50|(ዘበኞቹም) «መልእክተኞቻችሁ በተዓምራቶች ይመጡላችሁ አልነበሩምን?» ይላሉ፡፡ (ከሓዲዎቹም) «እንዴታ መጥተውናል እንጅ፤ (ግን አስተባበልናቸው)» ይላሉ፡፡ «እንግዲያውስ ጸልዩ፡፡ የከሓዲዎችም ጸሎት በከንቱ እንጅ አይደለም» ይሏቸዋል፡፡ 40|51|እኛ መልክተኞቻችንን፣ እነዚያንም ያመኑትን በቅርቢቱ ሕይወት ምስክሮችም በሚቆሙበት ቀን በእርግጥ እንረዳለን፡፡ 40|52|በደለኞችን ምክንያታቸው በማይጠቅማቸው ቀን (እንረዳለን)፡፡ ለእነርሱም ርግማን አልላቸው፡፡ ለእነርሱም መጥፎ አገር አልላቸው፡፡ 40|53|ሙሳንም መምሪያን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ የእስራኤልንም ልጆች መጽሐፉን አወረስናቸው፡፡ 40|54|ለባለ አእምሮዎች መሪና ገሳጭ ሲኾን፡፡ 40|55|(ሙሐመድ ሆይ!) ታገስም የአላህ ተስፋ እውነት ነውና፡፡ ለስህተትህም ምሕረትን ለምን፡፡ ከቀትር በኋላም በማለዳም ጌታሀን ከማመስገን ጋር አጥራው፡፡ 40|56|እነዚያ የመጣላቸው አስረጅ ሳይኖር በአላህ አንቀጾች የሚከራከሩ በልቦቻቸው ውስጥ እነርሱ ደራሾቹ ያልኾኑት ኩራት ብቻ እንጅ ምንም የለም፡፡ በአላህም ተጠበቅ፡፡ እነሆ እርሱ ሰሚው ተመልካቹ ነውና፡፡ 40|57|ሰማያትንና ምድርን መፍጠር ሰዎችን ከመፍጠር ይልቅ ታላቅ ነው፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም፡፡ 40|58|ዕውርና የሚያይ እነዚያም አምነው መልካሞችን የሠሩና መጥፎ ሠሪው አይስተካከሉም፡፡ በጣም ጥቂትን ብቻ ትገሰጻላችሁ፡፡ 40|59|ሰዓቲቱ በእርግጥ መጪ ናት፡፡ በእርሷ ጥርጥር የለም፡፡ ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያምኑም፡፡ 40|60|ጌታችሁም አለ «ለምኑኝ፤ እቀበላችኋለሁና፡፡ እነዚያ እኔን ከመግገዛት የሚኮሩት ተዋራጆች ኾነው ገሀነምን በእርግጥ ይገባሉ፡፡ 40|61|አላህ ያ ለእናንተ ሌሊትን በውስጡ ልታርፉበት (ጨለማ) ቀንንም (ልትሠሩበት) የሚያሳይ ያደረገላችሁ ነው፡፡ አላህ በሰዎች ላይ በእርግጥ የችሮታ ባለቤት ነውና፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያመሰግኑም፡፡ 40|62|ይሃችሁ ጌታችሁ አላህ ነው፤ የነገሩ ሁሉ ፈጣሪ ነው፤ ከርሱ ሌላ አምላክ የለም፤ ታዲያ (ከእምነት) ወዴት ትመለሳላችሁ፡፡ 40|63|እንደዚሁ እነዚያ በአላህ አንቀጾች ይክዱ የነበሩት (ከእምነት) ይመለሳሉ፡፡ 40|64|አላህ ያ ምድርን መርጊያ ሰማይንም ጣሪያ ያደረገላችሁ ነው፡፡ የቀረጻችኁም ቅርጻችሁንም ያሳመረ ከጣፋጮችም ሲሳዮች የሰጣችሁ ነው፡፡ ይሃችሁ ጌታችሁ አላህ ነው፡፡ የዓለማትም ጌታ አላህ ላቀ፡፡ 40|65|እርሱ ብቻ (ሁል ጊዜ) ሕያው ነው፤ ከርሱ ሌላ አምላክ የለም፤ ሃይማኖትንም ለእርሱ ያጠራችሁ ስትኾኑ «ምስጋና ለዓለማት ጌታ ለአላህ ይኹን» የምትሉ ኾናችሁ ተገዙት፡፡ 40|66|«እኔ ከጌታዬ አስረጂዎች በመጡልኝ ጊዜ እነዚያን ከአላህ ሌላ የምትገዙዋቸውን እንዳልገዛ ተከልክያለሁ፡፡ ለዓለማት ጌታም እንድገዛ ታዝዣለሁ» በላቸው፡፡ 40|67|እርሱ ያ ከዐፈር ከዚያም ከፍትወት ጠብታ ከዚያም ከረጋ ደም የፈጠራችሁ ነው፡፡ ከዚያም ሕጻናት አድርጎ ያወጣችኋል፡፡ ከዚያም ጥንካሬያችሁን ትደርሱ ዘንድ፤ ከዚያም ሽማግሌዎች ትኾኑ ዘንድ (ያቆያችኋል)፡፡ ከእናንተም ውስጥ ከዚህ በፊት የሚሞት አልለ፡፡ (ይህንንም ያደረገው ልትኖሩና) የተወሰነ ጊዜንም ልትደርሱ ታውቁም ዘንድ ነው፡፡ 40|68|እርሱ ያ ሕያው የሚያደርግ የሚገድልም ነው፡፡ አንዳችን ነገር በሻም ጊዜ ለእርሱ የሚለውን «ኹን» ነው፤ ወዲያውም ይኾናል፡፡ 40|69|ወደእነዚያ በአላህ አንቀጾች ወደሚከራከሩት (ከእምነት) እንዴት እንደሚመለሱ አታይምን? 40|70|ወደእነዚያ በመጽሐፉ በዚያም መልክተኞቻችንን በእርሱ በላክንበት ወዳስተባበሉት (አታይምን?) ወደፊትም ያውቃሉ፡፡ 40|71|እንዛዝላዎቹና ሰንሰለቶቹ በአንገቶቻቸው ላይ በተደረጉ ጊዜ (በእርሷ) ይጎተታሉ፡፡ 40|72|በገሀነም ውስጥ (ይጎተታሉ)፤ ከዚያም በእሳት ውስጥ ይማገዳሉ፡፡ 40|73|ከዚያም ለእነርሱ ይባላሉ (በአላህ) «ታጋሯቸው የነበራችሁት የታሉ?» 40|74|«ከአላህ ሌላ (የምታጋሩዋቸው)፤ ከኛ ተሰወሩን?» «ከቶ ከዚህ በፊት ምንንም የምንገዛ አልነበርንም» ይላሉ፤ እንደዚሁ አላህ ከሓዲዎችን ያሳስታል፡፡ 40|75|ይህ (ቅጣት) ያላግባብ በምድር ውሰጥ ትደሰቱ በነበራችሁትና ትንበጣረሩ በነበራችሁት ነው (ይባላሉ)፡፡ 40|76|የገሀነምን በሮች በውስጧ ዘውታሪዎች ስትኾኑ ግቡ (ይባላሉ)፡፡ የትዕቢተኞችም መኖሪያ (ገሀነም) ምን ትከፋ! 40|77|ታገስም የአላህ ቀጠሮ እውነት ነውና፡፡ የዚያንም የምናስፈራራቸውን ከፊሉን (በሕይወትህ) ብናሳይህ (መልካም ነው)፡፡ ወይም ብንገድልህ ወደኛ ይመለሳሉ፡፡ 40|78|ካንተ በፊትም መልክተኞችን በእርግጥ ልከናል፡፡ ከእነርሱ ባንተ ላይ የተረክንልህ አልለ፡፡ ከእነርሱም ባንተ ላይ ያልተረክነው አልለ፡፡ ለማንኛውም መልክተኛ በአላህ ፈቃድ ካልኾነ ተዓምርን ሊያመጣ አይገባውም፡፡ የአላህም ትእዛዝ በመጣ ጊዜ በእውነት ይፈረዳል፡፡ እዚያ ዘንድም አጥፊዎቹ ይከስራሉ፡፡ 40|79|አላህ ያ ለእናንተ ግመልን ከብትንና ፍየልን ከእርሷ (ከፊሏን) ልትጋልቡ የፈጠረላችሁ ነው፡፡ ከእርሷም ትበላላችሁ፡፡ 40|80|ለእናንተም በእርሷ ውስጥ ጥቅሞች አልሏችሁ፡፡ በእርሷም ላይ (እቃን በመጫን) በልቦቻችሁ ያሰባችሁትን ጉዳይ ትደርሱ ዘንድ (ፈጠረላችሁ)፡፡ በእርሷም ላይ በመርከቦችም ላይ ትሳፈራላችሁ፡፡ 40|81|ተዓምራቱንም ያሳያችኋል፡፡ ታዲያ ከአላህ ተዓምራት የትኛውን ትክዳላችሁ? 40|82|የእነዚያን ከእነርሱ በፊት የነበሩትን ሕዝቦች ፍጻሜ እንዴት እንደነበረ ይመለከቱ ዘንድ በምድር ላይ አይኼዱምን? ከእነርሱ ይበልጥ ብዙዎች በኀይልና በምድር ላይ በተዋቸው ምልክቶችም በጣም ብርቱዎች ነበሩ፡፡ ያም ይሠሩት የነበሩት ከእነርሱ ምንም አልጠቀማቸውም፡፡ 40|83|መልክተኞቻቸውም ተዓምራቶችን ባመጡላቸው ጊዜ እነርሱ ዘንድ ባለው ዕውቀት ተደሰቱ፡፡ በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩት ቅጣትም በእነርሱ ላይ ሰፈረባቸው፡፡ 40|84|ብርቱ ቅጣታችንንም ባዩ ጊዜ «በአላህ አንድ ሲኾን አምነናል፤ በእርሱም እናጋራ በነበርነው (ጣዖታት) ክደናል» አሉ፡፡ 40|85|ብርቱ ቅጣታችንን ባዩ ጊዜ ማመናቸውም የሚጠቅማቸው አልነበረም፡፡ የአላህን ደንብ ያችን በባሮቹ ውስጥ ያለፈችውን (ተጠንቀቁ) በዚያ ጊዜም ከሓዲዎች ከሰሩ፡፡ 41|1|ሐ.መ.(ሓ ሚም)፡፡ 41|2|(ይህ ቁርኣን) እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ ከሆነው (አላህ) የተወረደ ነው፡፡ 41|3|አንቀጾቹ የተብራሩ የኾነ መጽሐፍ ነው፡፡ ዐረብኛ ቁርኣን ሲኾን ለሚያውቁ ሕዝቦች (የተብራራ) ነው፡፡ 41|4|አብሳሪና አስፈራሪ ሲኾን (ተወረደ)፡፡ አብዛኛዎቻቸውም ተዉት፡፡ እነርሱም አይሰሙም፡፡ 41|5|አሉም «ልቦቻችን ከእዚያ ወደእርሱ ከምትጠራን እምነት በመሸፈኛዎች ውስጥ ናቸው፡፡ በጆሮዎቻችንም ላይ ድንቁርና አልለ፤ በእኛና ባንተም መካከል ግርዶሽ አልለ፡፡ (በሃይማኖትህ) ሥስራም፤ እኛ ሠሪዎች ነንና፡፡» 41|6|(እንዲህ) በላቸው «እኔ መሰላችሁ ሰው ብቻ ነኝ፡፡ አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው ወደእርሱም ቀጥ በሉ ምሕረትንም ለምኑት ማለት ወደእኔ ይወረድልኛል፡፡ ለአጋሪዎቹም ወዮላቸው፡፡ 41|7|ለእነዚያ ዘካን ለማይሰጡት እነርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም እነርሱ ከሓዲዎች ለኾኑት (ወዮላቸው)፡፡ 41|8|እነዚያ ያመኑትና በጎ ሥራዎችን የሠሩት ለእነርሱ የማይቆረጥ ምንዳ አልላቸው፡፡ 41|9|በላቸው «እናንተ በዚያ ምድርን በሁለት ቀኖች ውስጥ በፈጠረው አምላክ በእርግጥ ትክዳላችሁን? ለእርሱም ባለንጣዎችን ታደርጋላችሁን? ያ (ይህንን የሠራው) የዓለማት ጌታ ነው፡፡ 41|10|በእርሷም ከበላይዋ የረጉ ጋራዎችን አደረገ፡፡ በእርሷም በረከትን አደረገ፡፡ በውስጧም ምግቦችዋን (ካለፉት ሁለት ቀኖች ጋር) በአራት ቀናት ውሰጥ ለጠያቂዎች ትክክል ሲኾኑ ወሰነ፡፡ 41|11|ከዚያም ወደ ሰማይ እርሷ ጭስ ኾና ሳለች አሰበ፡፡ ለእርሷም ለምድርም «ወዳችሁም ኾነ ወይም ጠልታችሁ ኑ» አላቸው፡፡ «ታዛዦች ኾነን መጣን» አሉ፡፡ 41|12|በሁለት ቀኖችም ውስጥ ሰባት ሰማያት አደረጋቸው፡፡ በሰማይቱም ሁሉ ነገሯን አዘጋጀ፡፡ ቅርቢቱንም ሰማይ በመብራቶች አጌጥን፡፡ (ከሰይጣናት) መጠበቅንም ጠበቅናት፡፡ ይህ የአሸናፊው የዐዋቂው (ጌታ) ውሳኔ ነው፡፡ 41|13|(ከእምነት) እንቢ «ቢሉም እንደ ዓድና ሰሙድ መቅሰፍት ብጤ የኾነን መቅሰፍት አስጠነቅቃችኋለሁ» በላቸው፡፡ 41|14|መልክተኞቹ አላህን እንጅ ሌላን አትግገዙ በማለት ከስተፊታቸውም ከስተኋለቸውም በመጡባቸው ጊዜ «ጌታችን በሻ ኖሮ መላእክትን ባወረደ ነበር፡፡ ስለዚህ እኛ በዚያ በእርሱ በተላካችሁበት ከሓዲዎች ነን» አሉ፡፡ 41|15|ዓድም በምድር ላይ ያለ አግባብ ኮሩ፡፡ «ከእኛ ይበልጥ በኀይል ብርቱ ማን ነው?» አሉም፡፡ ያ የፈጠራቸው አላህ እርሱ በኀይል ከእነርሱ ይበልጥ የበረታ መኾኑን አያዩምን? በተዓምራታችንም ይክዱ ነበሩ፡፡ 41|16|በቅርቢቱ ሕይወት የውርደትን ቅጣት ልናቀምሳቸውም በእነርሱ ላይ የሚንሻሻን ብርቱ ነፋስ መናጢዎች በኾኑ ቀናት ውስጥ ላክንባቸው፡፡ የመጨረሻይቱም (ዓለም) ስቃይ በጣም አዋራጅ ነው፡፡ እነርሱም አይረዱም፡፡ 41|17|ሰሙዶችማ መራናቸው ዕውርነትንም በቅንነት ላይ መረጡ፡፡ ይሠሩትም በነበሩት ኃጢኣት አሳናሽ የኾነችው የመብረቅ ቅጣት ያዘቻቸው፡፡ 41|18|እነዚያንም ያመኑትንና ይጠነቀቁ የነበሩትን አዳንናቸው፡፡ 41|19|የአላህም ጠላቶች ወደ እሳት የሚሰበሰቡበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ እነርሱም የሚከመከሙ ኾነው ይነዳሉ፡፡ 41|20|በመጧትም ጊዜ ጆሮዎቻቸው፣ ዓይኖቻቸውና ቆዳዎቻቸውም ይሠሩት በነበሩት ነገር በእነርሱ ላይ ይመሰክሩባቸዋል፡፡ 41|21|ለቆዳዎቻቸውም «በእኛ ላይ ለምን መሰከራችሁብን?» ይላሉ፡፡ «ያ አንዳቹን ነገር ሁሉ ያናገረው አላህ አናገረን፡፡ እርሱም በመጀመሪያ ጊዜ ፈጠራችሁ፡፡ ወደእርሱም ትመለሳላችሁ» ይሏቸዋል፡፡ 41|22|ጆሮዎቻችሁ ዓይኖቻችሁና ቆዳዎቻችሁም በእናንተ ላይ ከመመስከራቸው የምትደበቁ አልነበራችሁም፡፡ ግን አላህ ከምትሠሩት ብዙውን አያውቅም ብላችሁ ጠረጠራችሁ፡፡ 41|23|ይህም ያ በጌታችሁ የጠረጠራችሁት ጥርጣሪያችሁ አጠፋችሁ፡፡ ከከሳሪዎቹም ኾናችሁ (ይባላሉ)፡፡ 41|24|ቢታገሱም እሳት ለእነርሱ መኖሪያቸው ናት፡፡ ወደሚወዱት መመለስንም ቢጠይቁ እነርሱ ተቀባይ የሚያገኙ አይደሉም፡፡ 41|25|ለእነርሱም ቁራኛዎችን አዘጋጀንላቸው፡፡ በፊታቸው ያለውንና በኋላቸው ያለውንም ሁሉ ለእነርሱ ሸለሙላቸው፡፡ ከጋኔንና ከሰውም ከእነርሱ በፊት በእርግጥ ካለፉት ሕዝቦች ጋር ኾነው ቃሉ በእነርሱ ላይ ተረጋገጠባቸው፡፡ እነርሱ በእርግጥ ከሳሪዎች ነበሩና፡፡ 41|26|እነዚያም የካዱት «ይህንን ቁርኣን አታዳምጡ፡፡ ታሸንፉም ዘንድ (ሲነበብ) በእርሱ ውሰጥ ተንጫጩ» አሉ፡፡ 41|27|እነዚያንም የካዱትን ብርቱን ቅጣት እናቀምሳቸዋለን፡፡ የእዚያነም ይሠሩት የነበሩትን መጥፎውን (ፍዳ) በእርግጥ እንመነዳቸዋለን፡፡ 41|28|ይህ የአላህ ጠላቶች ፍዳ ነው፡፡ እሳት በውስጧ ለእነርሱ የዘላለም መኖሪያ አገር አልላቸው፡፡ ከአንቀጾቻችን ይክዱ በነበሩት ምንዳን (ይምመነዳሉ)፡፡ 41|29|እነዚያም የካዱት (በእሳት ውስጥ ኾነው) «ጌታችን ሆይ! እነዚያን ከጋኔንና ከሰው ያሳሳቱንን አሳየን፡፡ ከታችኞቹ ይኾኑ ዘንድ ከጫማዎቻችን ሥር እናደርጋቸዋለንና» ይላሉ፡፡ 41|30|እነዚያ «ጌታችን አላህ ነው» ያሉ ከዚያም ቀጥ ያሉ «አትፍሩ፤ አትዘኑም፤ በዚያችም ተስፋ ቃል ትደረግላችሁ በነበራችሁት ገነት ተበሰሩ» በማለት በነሱ ላይ መላእክት ይወርዳሉ፡፡ 41|31|«እኛ በቅርቢቱም ሕይወት በመጨረሻይቱም ረዳቶቻችሁ ነን! ለእናንተም በእርሷ ውስጥ ነፍሶቻችሁ የሚሹት ሁሉ አልላችሁ፡፡ ለእናንተም በእርሷ ውስጥ የምትፈልጉት ሁሉ አልላችሁ፡፡ 41|32|«መሓሪ አዛኝ ከኾነው አላህ መስተንግዶ ሲኾን» (ይባላሉ)፡፡ 41|33|ወደ አላህ ከጠራና መልካምንም ከሠራ፣ «እኔ ከሙስሊሞች ነኝ» ካለም ሰው ይበልጥ ቃሉ ያማረ ማን ነው? 41|34|መልካሚቱና ክፉይቱም (ጸባይ) አይተካከሉም፡፡ በዚያች እርሷ መልካም በኾነችው ጸባይ (መጥፎይቱን) ገፍትር፡፡ ያን ጊዜ ያ ባንተና በእርሱ መካከል ጠብ ያለው ሰው እርሱ ልክ እንደ አዛኝ ዘመድ ይኾናል፡፡ 41|35|(ይህችንም ጠባይ) እነዚያ የታገሱት እንጅ ሌላው አያገኛትም፡፡ የትልቅም ዕድል ባለቤት እንጅ ማንም አይገጠማትም፡፡ 41|36|ከሰይጣንም ጉትጎታ ቢያገኝህ (ከመልካም ጠባይም ቢመልስህ) በአላህ ተጠበቅ፡፡ እነሆ እርሱ ሰሚው ዐዋቂው ነውና፡፡ 41|37|ሌሊትና ቀንም ፀሐይና ጨረቃም ከምልክቶቹ ናቸው፡፡ ለፀሐይና ለጨረቃ አትስገዱ፡፡ ለእዚያም ለፈጠራቸው አላህ ስገዱ፡፡ እርሱን ብቻ የምትግገዙ እንደ ኾናችሁ (ለሌላ አትስገዱ)፡፡ 41|38|ቢኮሩም እነዚያ በጌታህ ዘንድ ያሉት (መላእክት) በቀንም በሌሊትም ለእርሱ ያወድሳሉ፡፡ እነርሱም አይሰለቹም፡፡ 41|39|አንተ ምድርን ደረቅ ኾና ማየትህም ከምልክቶቹ ነው፡፡ በእርሷም ላይ ውሃን ባወረድን ጊዜ (በቡቃያዎችዋ) ትላወሳለች፡፡ ትነፋለችም፡፡ ያ ሕያው ያደረጋት ጌታ በእርግጥ ሙታንን ሕያው አድራጊ ነው፡፡ እነርሱ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና፡፡ 41|40|እነዚያ አንቀጾቻችንን የሚያጣምሙ በእኛ ላይ አይደበቁም፡፡ (የሚያጣምምና) በእሳት ውስጥ የሚጣለው ሰው ይበልጣልን? ወይስ በትንሣኤ ቀን ጸጥተኛ ኾኖ የሚመጣው ሰው? የሻችሁትን ሥሩ (ዋጋችሁን ታገኛላችሁ)፡፡ እርሱ የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነውና፡፡ 41|41|እነዚያ በቁርኣን እርሱ አሸናፊ መጽሐፍ ሲኾን በመጣላቸው ጊዜ የካዱት (ጠፊዎች ናቸው)፡፡ 41|42|ከኋላውም ከፊቱም ውሸት አይመጣበትም፡፡ ጥበበኛ ምስጉን ከኾነው ጌታ የተወረደ ው፡፡ 41|43|ካንተ በፊት ለነበሩት መልክተኞች የተባለው ብጤ እንጅ ለአንተ ሌላ አይባልም፡፡ ጌታህ የምህረት ባለቤትና የአሳማሚ ቅጣት ባለቤት ነው፡፡ 41|44|በአጀምኛ የኾነ ቁርኣን ባደረግነው ኖሮ አንቀጾቹ «(በምናውቀው ቋንቋ) አይብራሩም ኖሯልን? (ቁርኣኑ) አጀምኛና (መልክተኛው) ዐረባዊ ይኾናልን?» ባሉ ነበር እርሱ ለእነዚያ ለአመኑት መምሪያና መፈወሻ ነው፡፡ እነዚያም የማያምኑት በጆሮዎቻቸው ውስጥ ድንቁርና ነው፡፡ (አይሰሙትም)፡፡ እነርሱም በእነርሱ ላይ እውርነት ነው፡፡ እነዚያ ከሩቅ ስፍራ እንደሚጥጠሩ ናቸው፡፡ 41|45|ሙሳንም መጽሐፉን በእርግጥ ሰጠነው፡፡ በእርሱም ተለያዩበት፡፡ ከጌታህም ያለፈች ቃል ባልነበረች ኖሮ በመካከላቸው በተፈረደ ነበር፡፡ እነርሱም ከእርሱ አወላዋይ በኾነ ጥርጣሬ ውስጥ ናቸው፡፡ 41|46|መልካም የሠራ ሰው ለነፍሱ ነው፡፡ ያጠፋም ሰው በእርሷ ላይ ነው፡፡ ጌታህም ለባሮቹ በዳይ አይደለም፡፡ 41|47|ጊዜይቱን ማወቅ ወደእርሱ ይመለሳል ከፍሬዎችም ከሽፋኖቻቸው አይወጡም፡፡ ከሴትም አንዲትም አታረግዝም፣ አትወልድምም በዕውቀቱ ቢኾን እንጅ፡፡ «ተጋሪዎቼ የት ናቸው?» በማለት በሚጠራቸው ቀንም «ከእኛ ውስጥ (ባላንጣ አልለ ብሎ) ምንም መስካሪ አለመኖሩን አስታወቅንህ» ይላሉ፡፡ 41|48|ያም በፊት ይግገዙት የነበሩት (ጣዖት) ከእነርሱ ይጠፋቸዋል፡፡ ለእነርሱም ምንም መሸሻ የሌላቸው መኾኑን ያረጋግጣሉ፡፡ 41|49|ሰው በጎ ነገርን ከመለመን አይሰለችም፡፡ ክፉም ቢያገኘው ወዲያውኑ በጣም ተስፋ ቆራጭ ተበሳጭ ይኾናል፡፡ 41|50|ካገኘችውም መከራ በኋላ ከእኛ የኾነን እዝነት ብናቀምሰው «ይህ ለእኔ (በሥራዬ የተገባኝ) ነው፡፡ ሰዓቲቱም መጪ ናት ብዬ አላስብም፡፡ ወደ ጌታየም ብመለስ ለእኔ እርሱ ዘንድ መልካሚቱ (ገነት) በእርግጥ አለችኝ» ይላል፡፡ እነዚያንም የካዱትን ሥራዎቻቸውን በእርግጥ እንነግራቸዋለን፡፡ ከብርቱውም ስቃይ በእርግጥ እናቀምሳቸዋለን፡፡ 41|51|በሰውም ላይ ጸጋችንን በለገስን ጊዜ (ከማመስገን) ይዞራል፡፡ በጎኑም ይርቃል፡፡ መከራም ባገኘው ጊዜ የብዙ ልመና ባለቤት ይኾናል፡፡ 41|52|በላቸው «ንገሩኝ (ቁርኣኑ) ከአላህ ዘንድ ቢኾን ከዚያም በእርሱ ብትክዱ (ከውነት) በራቀ ጭቅጭቅ ላይ ከኾነ ሰው ይበልጥ የተሳሳተ ማን ነው?» 41|53|እርሱም (ቁርኣን) እውነት መኾኑ ለእነርሱ እስከሚገለፅላቸው ድረስ በአጽናፎቹ ውስጥና በነፍሶቻቸውም ውስጥ ያሉትን ተዓምራቶቻችንን በእርግጥ እናሳያቸዋለን፡፡ ጌታህም እርሱ በነገሩ ሁሉ ላይ ዐዋቂ መኾኑ አይበቃቸውምን? 41|54|ንቁ! እነርሱ ከጌታቸው መገናኘት በመጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ ንቁ! እርሱ በነገሩ ሁሉ (ዕውቀቱ) ከባቢ ነው፡፡ 42|1|ሐ.መ (ሐ፡ ሚም)፡፡ 42|2|ዐ.ሰ.ቀ (ዓይን ሲን ቃፍ)፤ 42|3|እንደዚሁ (በዚህች ሱራ ውስጥ እንዳለው) አሸናፊው ጥበበኛው አላህ ወዳንተ ያወርዳል፡፡ ወደእነዚያም ከአንተ በፊት ወደ ነበሩት ሕዝቦች (አውርዷል)፡፡ 42|4|በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የእርሱ ነው፡፡ እርሱም የበላዩ ታላቁ ነው፡፡ 42|5|(ከአላህ ፍራቻ) ሰማያት ከበላያቸው ሊቀደዱ ይቀርባሉ፡፡ መላእክትም ጌታቸውን እያመሰገኑ ያወድሳሉ፡፡ በምድርም ላለው ፍጡር ምሕረትን ይለምናሉ፡፡ ንቁ! አላህ እርሱ መሓሪው አዛኙ ነው፡፡ 42|6|እነዚያም ከእርሱ ሌላ (የጣዖታት) ረዳቶችን የያዙ፤ አላህ በእነርሱ ላይ ተጠባባቂ ነው፡፡ አንተም በእነርሱ ላይ ኀላፊ አይደለህም፡፡ 42|7|እንደዚሁም የከተሞች እናት የኾነችውን (የመካን ሰዎች) በአካባቢዋ ያሉትንም ልታስፈራራ የመሰብሰቢያውንም ቀን በእርሱ ጥርጣሬ የሌለበት ሲኾን ልታስጠነቅቅ ዐረብኛ የኾነን ቁርኣን ወደ አንተ አወረድን፡፡ (ከእነርሱም) ከፊሉ በገነት ውሰጥ ከፊሉም በእሳት ውስጥ ነው፡፡ 42|8|አላህም በሻ ኖሮ (ባንድ ሃይማኖት ላይ) አንድ ሕዝብ ባደረጋቸው ነበር፡፡ ግን የሚሻውን ሰው በእዝነቱ ውስጥ ያስገባል፡፡ በዳዮችም ለእነርሱ ወዳጅና ረዳት ምንም የላቸውም፡፡ 42|9|ከእርሱ ሌላ ረዳቶችን ያዙን? (ረዳቶች አይደሉም)፡፡ አላህም ረዳት እርሱ ብቻ ነው፡፡ እርሱም ሙታንን ሕያው ያደርጋል፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 42|10|ከምንም ነገር ያ በእርሱ የተለያዩበት ፍርዱ ወደ አላህ ነው፡፡ «እርሱ አላህ ጌታዬ ነው፡፡ በእርሱ ላይ ተጠጋሁ፣ ወደርሱም እመለሳለሁ» (በላቸው)፡፡ 42|11|ሰማያትንና ምድርን ፈጣሪ ነው፡፡ ከነፍሶቻችሁ ሴቶችን ከቤት እንስሳዎችም ዓይነቶችን (ወንዶችና ሴቶችን) ለእናንተ አደረገላችሁ፡፡ በእርሱ ያበዛችኋል፡፡ የሚመስለው ምንም ነገር የለም፡፡ እርሱም ሰሚው ተመልካቹ ነው፡፡ 42|12|የሰማያትና የምድር (ድልቦች) መከፈቻዎች የእርሱ ናቸው፡፡ ሲሳይን ለሚሻው ሰው ያሰፋል፤ ያጠባልም፡፡ እርሱ ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 42|13|ለእናንተ ከሃይማኖት ያንን በእርሱ ኑሕን ያዘዘበትን ደነገገላችሁ፡፡ ያንንም ወዳንተ ያወረድነውን ያንንም በእርሱ ኢብራሂምን ሙሳንና ዒሳንም ያዘዝንበትን ሃይማኖትን በትክክል አቋቁሙ በእርሱም አትለያዩ ማለትን (ደነገግን)፡፡ በአጋሪዎቹ ላይ ያ ወደርሱ የምትጠራቸው ነገር ከበዳቸው፡፡ አላህ የሚሻውን ሰው ወደእርሱ (እምነት) ይመርጣል፡፡ የሚመለስንም ሰው ወደርሱ ይመራል፡፡ 42|14|(የሃይማኖት ሰዎች) ዕውቀቱም ከመጣላቸው በኋላ በመካከላቸው ለምቀኝነት እንጅ ለሌላ አልተለያዩም፡፡ እስከ ተወሰነም ጊዜ (በማቆየት) ከጌታህ ያለፈች ቃል ባልነበረች ኖሮ በእነርሱ መካከል (አሁን) በተፈረደ ነበር፡፡ እነዚያም ከኋላቸው መጽሐፉን እንዲወርሱ የተደረጉት ከእርሱ በእርግጥ በአወላዋይ ጥርጣሬ ውስጥ ናቸው፡፡ 42|15|ለዚህም (ድንጋጌ ሰዎችን) ጥራ፡፡ እንደታዘዝከውም ቀጥ በል፡፡ ዝንባሌዎቻቸውንም አትከተል፡፡ «በላቸውም ከመጽሐፍ አላህ ባወረደው ሁሉ አመንኩ፡፡ በመካከላችሁም ላስተካክል ታዘዝኩ፡፡ አላህ ጌታችን ጌታችሁም ነው፡፡ ለእኛ ሥራዎቻችን አልሉን፡፡ ለእናንተም ሥራዎቻችሁ አልሏችሁ፡፡ በእኛና በእናንተ መካከል ክርክር የለም፡፡ አላህ በመካከላችን ይሰበስባል፡፡ መመለሻም ወደእርሱ ብቻ ነው፡፡» 42|16|እነዚያም በአላህ (ሃይማኖት) ለእርሱ ተቀባይ ካገኘ በኋላ የሚከራከሩት ማስረጃቸው በጌታቸው ዘንድ ብልሹ ናት፡፡ በእነርሱም ላይ ቁጣ አልለባቸው፡፡ ለእነርሱም ብርቱ ቅጣት አልላቸው፡፡ 42|17|አላህ ያ መጽሐፉን በእውነት ያወረደ ነው፡፡ ሚዛንንም (እንደዚሁ)፡፡ ሰዓቲቱ ምንአልባት ቅርብ መኾንዋን ምን ያሳውቅሃል? 42|18|እነዚያ በእርሷ የማያምኑት በእርሷ ያቻኩላሉ፡፡ እነዚያም ያመኑት ከእርሷ ፈሪዎች ናቸው፡፡ እርሷም እውነት መኾንዋን ያውቃሉ፡፡ ንቁ! እነዚያ በሰዓቲቱ የሚከራከሩት በእርግጥ (ከእውነት) በራቀ ስሕተት ውስጥ ናቸው፡፡ 42|19|አላህ በባሮቹ ሩህሩህ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው (በሰፊው) ሲሳይን ይሰጣል፡፡ እርሱም ብርቱው አሸናፊው ነው፡፡ 42|20|(በሥራው) የኋለኛይቱን ዓለም አዝመራ የሚፈልግ የኾነ ሰው ለእርሱ በአዝመራው ላይ እንጨምርለታለን፡፡ የቅርቢቱንም ዓለም አዝመራ የሚፈልግ የኾነ ሰው ከእርሷ (የተወሰነለትን ብቻ) እንሰጠዋለን፡፡ ለእርሱም በኋለኛይቱ ዓለም ምንም ፋንታ የለውም፡፡ 42|21|ከሃይማኖት አላህ በእርሱ ያልፈቀደውን ለእነርሱ የደነገጉ ተጋሪዎች ለእነርሱ አልሏቸውን? የፍርዱ ቃል ባልነበረ ኖሮ በመካከላቸው (አሁን) በተፈረደ ነበር፡፡ በደለኞችም ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት በእርግጥ አልላቸው፡፡ 42|22|በደለኞችን ከሠሩት ሥራ (ዋጋ በትንሣኤ ቀን) ፈሪዎች ኾነው ታያቸዋለህ፡፡ እርሱም በእነርሱ ላይ ወዳቂ ነው፡፡ እነዚያም ያመኑት መልካሞችንም የሠሩት በገነቶች ጨፌዎች ውስጥ ናቸው፡፡ ለእነርሱ በጌታቸው ዘንድ የሚሹት ሁሉ አልላቸው፡፡ ይህ እርሱ ታላቅ ችሮታ ነው፡፡ 42|23|ይህ (ታላቅ ችሮታ) ያ አላህ እነዚያን ያመኑትንና መልካሞችን የሠሩትን ባሮቹን የሚያበስርበት ነው፡፡ «በእርሱ (መልክቴን በማድረሴ) ላይ በዝምድና ውዴታን እንጅ ዋጋን አልጠይቃችሁም» በላቸው፡፡ መልካሚቱንም ሥራ የሚሠራ ሰው ለእርሱ በእርሷ መልካምን ነገር እንጨምርለታለን፡፡ አላህ መሓሪ አመስጋኝ ነውና፡፡ 42|24|ይልቁንም «በአላህ ላይ ውሸትን ቀጠፈ» ይላሉን? አላህም ቢሻ በልብህ ላይ ያትማል፡፡ አላህም ውሸቱን ያብብሳል፡፡ እውነቱንም በቃላቱ ያረጋግጣል፡፡ እርሱ በልቦች ውስጥ ያለን ሁሉ ዐዋቂ ነውና፡፡ 42|25|እርሱም ያ ከባሮቹ ንስሓን የሚቀበል፣ ከኃጢአቶችም ይቅር የሚል፣ የምትሠሩትንም ሁሉ የሚያውቅ ነው፡፡ 42|26|እነዚያንም ያመኑትንና መልካሞችን የሠሩትን ልመናቸውን ይቀበላል፡፡ ከችሮታውም ይጨምርላቸዋል፡፡ ከሓዲዎቹም ለእነርሱ ብርቱ ቅጣት አልላቸው፡፡ 42|27|አላህም ለባሮቹ (ሁሉ) ሲሳይን በዘረጋ ኖሮ በምድር ውስጥ (ሁሉም) ወሰን ባለፉ ነበር፡፡ ግን የሚሻውን በልክ ያወርዳል፡፡ እርሱ በባሮቹ ውስጥ ዐዋቂ ተመልካች ነውና፡፡ 42|28|እርሱም ያ ተስፋ ከቆረጡ በኋላ ዝናምን የሚያወርድ ችሮታውንም የሚዘረጋ ነው፡፡ እርሱም ረዳቱ ምስጉኑ ነው፡፡ 42|29|ሰማያትንና ምድርንም መፍጠሩ፣ ከተንቀሳቃሽም በሁለቱ ውስጥ የበተነውን (መፍጠሩ) ከአስደናቂ ምልክቶቹ ነው፡፡ እርሱም በሚሻ ጊዜ እነርሱን በመሰብሰብ ላይ ቻይ ነው፡፡ 42|30|ከመከራም ማንኛውም ያገኛችሁ ነገር እጆቻችሁ በሠሩት (ኃጢኣት) ምክንያት ነው፡፡ ከብዙውም ይቅር ይላል፡፡ 42|31|እናንተም በምድር ውስጥ የምታቅቱ አይደላችሁም፡፡ ለእናንተም ከአላህ ሌላ ከዘመድም ከረዳትም ምንም የላችሁም፡፡ 42|32|በባሕር ላይ እንደ ጋራዎች ኾነው ተንሻላዮቹም (መርከቦች) ከአስደናቂ ምልክቶቹ ናቸው፡፡ 42|33|ቢሻ ነፋሱን የረጋ ያደርገዋል፡፡ በባሕሩም ጀርባ ላይ ረጊዎች ይኾናሉ፡፡ በዚህ ውሰጥ በጣም ታጋሽና አመስጋኝ ለኾነ ሁሉ በእርግጥ ምልክቶች አልሉ፡፡ 42|34|ወይም በሠሩት ኃጢኣት ምክንያት (በማስጠም) ያጠፋቸዋል፡፡ ከብዙም ይቅርታ ያደርጋል፡፡ 42|35|(ከእነርሱ ለመበቀል)፤ እነዚያንም በአንቀጾቻችን የሚከራከሩትን ለማወቅ (ያጠፋቸዋል)፡፡ ለእነርሱ ምንም መሸሻ የላቸውም፡፡ 42|36|ከምንም ነገር የተሰጣችሁት የቅርቢቱ ሕይወት መጠቀሚያ ነው፡፡ አላህ ዘንድ ያለውም ምንዳ ለእነዚያ ለአመኑትና በጌታቸው ላይ ለሚጠጉት በላጭና ሁል ጊዜ ነዋሪ ነው፡፡ 42|37|ለእነዚያም የኀጢኣትን ታላላቆችና ጠያፎችን የሚርቁ በተቆጡም ጊዜ እነሱ የሚምሩት ለኾኑት፡፡ 42|38|ለእነዚያም የጌታቸውን ጥሪ ለተቀበሉት፣ ሶላትንም ላዘወተሩት፣ ነገራቸውም በመካከላቸው መመካከር ለኾነው ከሰጠናቸውም ሲሳይ ለሚለግሱት፡፡ 42|39|ለእነዚያም በደል በደረሰባቸው ጊዜ እነርሱ (በመሰሉ) የሚመልሱ ለኾኑት (በላጭና ኗሪ ነው)፡፡ 42|40|የመጥፎም ነገረ ዋጋ ብጤዋ መጥፎ ናት፡፡ ይቅርም ያለና ያሳመረ ሰው ምንዳው በአላህ ላይ ነው፡፡ እርሱ በደለኞችን አይወድም፡፡ 42|41|ከተበደሉም በኋላ (በመሰሉ) የተበቀሉ እነዚያ በነርሱ ላይ ምንም (የወቀሳ) መንገድ የለባቸውም፡፡ 42|42|(የወቀሳ) መንገዱ በእነዚያ ሰዎችን በሚበድሉት፣ በምድርም ውስጥ ያለ ሕግ ወሰን በሚያልፉት፣ ላይ ብቻ ነው፡፡ እነዚያ ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት አልላቸው፡፡ 42|43|የታገስና ምሕረት ያደረገም ሰው ይህ ከምርሮቹ (ከተፈላጊዎቹ) ነገሮች ነው፡፡ 42|44|አላህ የሚያጠመውም ሰው ከእርሱ በኋለ ለእርሱ ምንም ረዳት የለውም፡፡ በደለኞችንም ቅጣቱን ባዩ ጊዜ ወደ መመለስ መንገድ አልለን? የሚሉ ሲኾኑ ታያቸዋለህ፡፡ 42|45|ከውርደት የተነሳ ፈሪዎች ኾነው በዓይን ስርቆት ወደእርሷ (ወደ እሳት) እያስተዋሉ በእርሷ ላይ የሚቀረቡ ሲኾኑ ታያቸዋለህ፡፡ እነዚያም ያመኑት፡- «በእርግጥ ከሳሪዎቹ እነዚያ ነፍሶቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን በትንሣኤ ቀን ያከሰሩት ናቸው» ይላሉ፡፡ 42|46|ንቁ! በደለኞች በእርግጥ በዘውታሪ ስቃይ ውስጥ ናቸው፡፡ ለእነርሱም ከአላህ ሌላ የሚረዷቸው ዘመዶች ምንም አልነበሩዋቸውም፡፡ አላህም የሚያጠመው ሰው ለእርሱ (ወደ እውነት) ምንም መንገድ የለውም፡፡ 42|47|ለእርሱ መመለስ የሌለው ቀን ከአላህ ከመምጣቱ በፊት ለጌታችሁ ታዘዙ፡፡ በዚያ ቀን ለእናንተ ምንም መጠጊያ የላችሁም፡፡ ለእናንተም ምንም መካድ የላችሁም፡፡ 42|48|ቢዞሩም (ወቀሳ የለብህም)፡፡ በእነርሱ ላይ ጠባቂ አድርገን አልላክንህምና፡፡ ባንተ ላይ ማድረስ እንጅ ሌላ የለብህም፡፡ እኛም ሰውን ከእኛ የኾነን ጸጋ ባቀመስነው ጊዜ በርሷ ይደሰታል፡፡ እጆቻቸው ባስቀደሙትም ኀጢአት ምክንያት መከራ ብትደርስባቸው (ተስፋ ይቆርጣሉ)፡፡ ሰው (ውለታን) በጣም ከሐዲ ነውና፡፡ 42|49|የሰማያትና የምድር ንግሥና የአላህ ነው፡፡ የሚሻውን ይፈጥራል፡፡ ለሚሻው ሰው ሴቶችን (ልጆች) ይሰጣል፡፡ ለሚሻውም ሰው ወንዶችን ይሰጣል፡፡ 42|50|ወይም ወንዶችና ሴቶች አድርጎ ያጠናዳቸዋል፡፡ የሚሻውንም ሰው መካን ያደርገዋል፡፡ እርሱ ዐዋቂ ቻይ ነውና፡፡ 42|51|ለሰውም አላህ በራእይ፣ ወይም ከግርዶ ወዲያ፣ ወይም መልክተኛን (መልአክን) የሚልክና በፈቃዱ የሚሻውን ነገር የሚያወርድለት ቢኾን እንጅ (በገሃድ) ሊያናግረው ተገቢው አይደለም፡፡ እርሱ የበላይ ጥበበኛ ነውና፡፡ 42|52|እንደዚሁም ወደ አንተ ከትእዛዛችን ሲኾን መንፈስን (ቁርኣንን) አወረድን፡፡ መጽሐፉም እምነቱም ምን እንደኾነ የምታውቅ አልነበርክም፡፡ ግን (መንፈሱን) ከባሮቻችን የምንሻውን ሰው በእርሱ የምንመራበት ብርሃን አደረግነው፡፡ አንተም ወደ ቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ ትመራለህ፡፡ 42|53|ወደዚያ በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የእርሱ ወደ ኾነው አላህ መንገድ (ትመራለህ)፡፡ ንቁ! ነገሮቹ ሁሉ ወደ አላህ ይመለሳሉ፡፡ 43|1|ሐ.መ (ሓ ሚም)፡፡ 43|2|ገላጭ በኾነው መጽሐፍ እምላለሁ፡፡ 43|3|እኛ ታውቁ ዘንድ ዐረብኛ ቁርኣን አደረግነው፡፡ 43|4|እርሱም በመጽሐፎቹ እናት ውስጥ እኛ ዘንድ በእርግጥ ከፍተኛ ጥበብ የተመላ ነው፡፡ 43|5|ድንበር አላፊዎች ሕዝቦች ለመኾናችሁ ቁርኣኑን ከእናንተ ማገድን እናግዳለን? 43|6|በፊተኞቹም ሕዝቦች ውስጥ ከነቢይ ብዙን ልከናል፡፡ 43|7|ከነቢይም አንድም የሚመጣላቸው አልነበረም በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩ ቢኾኑ እንጅ፡፡ 43|8|ከእነርሱም በኀይል ይበልጥ የበረቱትን አጥፍተናል፡፡ የፊተኞቹም (አጠፋፍ) ምሳሌ አልፏል፡፡ 43|9|«ሰማያትንና ምድርንም ማን ፈጠራቸው» ብለህ ብትጠይቃቸው «አሸናፊው ዐዋቂው (አላህ) በእርግጥ ፈጠራቸው» ይላሉ፡፡ 43|10|(እርሱ) ያ ምድርን ለእናንተ ምንጣፍ ያደረገላችሁ በርሷም ውስጥ ትምመሩ ዘንድ ለእናንተ መንገዶችን ያደረገላችሁ ነው፡፡ 43|11|ያም ከሰማያ ውሃን በልክ ያወረደላችሁ ነው፡፡ በእርሱም የሞተችውን አገር ሕያው አደረግን፡፡ እንደዚሁ (ከመቃብራችሁ) ትውወጣላችሁ፡፡ 43|12|ያም ዓይነቶችን ሁሉ የፈጠረ ለእናንተም ከመርከቦችና ከቤት እንስሳዎች የምትጋልቧቸውን ያደረገላችሁ ነው፡፡ 43|13|በጀርባዎቹ ላይ እንድትደላደሉ ከዚያም በርሱ ላይ የተደላደላችሁ ጊዜ የጌታችሁን ጸጋ እንድታስታውሱ፤ እንድትሉም፡- «ያ ይህንን የማንችለው ስንኾን ለእኛ ያገራለን ጌታ ጥራት ይገባው፡፡ 43|14|እኛም በእርግጥ ወደ ጌታችን ተመላሾች፤ነን» (እንድትሉ)፡፡ 43|15|ከባሮቹም ለእርሱ ቁራጭን (ልጅን) አደረጉለት፡፡ ሰው በእርግጥ ግልጽ ከሓዲ ነው፡፡ 43|16|ከሚፈጥረው ውስጥ ሴቶች ልጆችን ያዘን? በወንዶች ልጆችም (እናንተን) መረጣችሁን? 43|17|አንዳቸውም ለአልረሕማን ምሳሌ ባደረገው ነገር (በሴት ልጅ) በተበሰረ ጊዜ እርሱ በቁጭት የተመላ ኾኖ ፊቱ የጠቆረ ይኾናል፡፡ 43|18|በጌጥ (ተከልሶ) እንዲያድግ የሚደረገውን? እርሱም (ለደካማነቱ) በክርክር የሚያብራራውን ፍጡር (ሴትን) ለአላህ ያደርጋሉን? 43|19|መላእክትንም እነርሱ የአልረሕማን ባሮች የኾኑትን ሴቶች አደረጉ፡፡ ሲፈጠሩ ነበሩን? መመስከራቸው በእርግጥ ትጻፋለች፡፡ ይጠየቃሉም፡፡ 43|20|«አልረሕማንም በሻ ኖሮ ባልተገዛናቸው ነበር» አሉ፡፡ ለእነርሱ በዚህ ምንም ዕውቀት የላቸውም፡፡ እነርሱ የሚዋሹ እንጅ ሌላ አይደሉም፡፡ 43|21|ከእርሱ (ከቁርኣን) በፊት መጽሐፍን ሰጠናቸውን? ስለዚህ እነርሱ እርሱን የጨበጡ ናቸውን? 43|22|ከቶውንም «እኛ አባቶቻችንን በሃይማኖት ላይ አገኘናቸው፡፡ እኛም በፈለጎቻቸው ላይ ተመሪዎች ነን» አሉ፡፡ 43|23|(ነገሩ) እንደዚሁም ነው፡፡ ከበፊትህ በማንኛይቱም ከተማ ውስጥ አስፈራሪን አልላክንም፤ ቅምጥሎችዋ እኛ አባቶቻችንን በሃይማኖት ላይ አገኘን፤ እኛም በፈለጎቻቸው ላይ ተከታዮች ነን ያሉ ቢኾኑ እንጅ፡፡ 43|24|(አስፈራሪው) «አባቶቻችሁን በእርሱ ላይ ከአገኛችሁበት ይበልጥ ቀጥተኛን (ሃይማኖት) ባመጣላችሁም?» አላቸው፡፡ «እኛ በእርሱ በተላካችሁበት ነገር ከሓዲዎች ነን» አሉ፡፡ 43|25|ከእነርሱም ተበቀልን፡፡ ያስተባባዮቹም መጨረሻ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከት፡፡ 43|26|ኢብራሂምም ለአባቱና ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «እኔ ከምትግገዙት ሁሉ ንጹሕ ነኝ፡፡» 43|27|«ከዚያ ከፈጠረኝ በስተቀር (አልግገዛም)፡፡ እርሱ በእርግጥ ይመራኛልና፡፡» 43|28|በዝርዮቹም ውስጥ ይመለሱ ዘንድ (ባንድ አምላክ ማመንን) ቀሪ ቃል አደረጋት፡፡ 43|29|ይልቅ እነዚህን (ቁረይሾችን)፣ አባቶቻቸውንም ቁርኣንና ገላጭ መልክተኛ እስከመጣላቸው ድረስ አጣቀምኳቸው፡፡ 43|30|እውነቱም በመጣላቸው ጊዜ «ይህ ድግምት ነው፡፡ እኛም በእርሱ ከሓዲዎች ነን» አሉ፡፡ 43|31|«ይህም ቁርኣን ከሁለቱ ከተሞች በታላቅ ሰው ላይ አይወረድም ኖሯልን?» አሉ፡፡ 43|32|እነርሱ የጌታህን ችሮታ ያከፈፍላሉን? እኛ በቅርቢቱ ሕይወት ኑሯቸውን በመካከላቸው አከፋፍለናል፡፡ ከፊላቸውም ከፊሉን ሠራተኛ አድርጎ ይይዝ ዘንድ ከፊላቸውን ከከፊሉ በላይ በደረጃዎች (በሀብት) አበለጥን፡፡ የጌታህም ጸጋ (ገነት) ከሚሰበስቡት (ሃብት) በላጨ ናት፡፡ 43|33|ሰዎችም (በክሕደት) አንድ ሕዝብ የሚኾኑ ባልነበሩ ኖሮ በአልረሕማን ፤ለሚክዱት ሰዎች (በዚህች ዓለም) ለቤቶቻቸው ከብር የኾኑን ጣራዎች በእነርሱ ላይ የሚወጡባቸውንም (የብር) መሰላሎች ባደረግንላቸው ነበር፡፡ 43|34|ለቤቶቻቸውም ደጃፎችን በእነርሱ ላይ የሚደገፉባቸውንም አልጋዎች (ከብር ባደረግንላቸው ነበር)፡፡ 43|35|የወርቅ ጌጥንም (ባደረግንላቸው ነበር)፡፡ ይህም ሁሉ የቅርቢቱ ሕይወት መጣቀሚያ እንጅ ሌላ አይደለም፤ (ጠፊ ነው)፡፡ መጨረሻይቱም አገር በጌታህ ዘንድ ለጥንቁቆቹ ናት፡፡ 43|36|ከአልረሕማን ግሣጼ (ከቁርኣን) የሚደናበርም ሰው ለእርሱ ሰይጣንን እናስጠጋለን፡፡ ስለዚህ እርሱ ለእርሱ ቁራኛ ነው፡፡ 43|37|እነርሱም (ተደናባሪዎቹ) ተመሪዎች መኾናቸውን የሚያስቡ ሲኾኑ እነርሱ (ሰይጣናት) ከቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ ያግዷቸዋል፡፡ 43|38|(በትንሣኤ) ወደኛ በመጣም ጊዜ (ቁራኛዬ ሆይ!) «በእኔና ባንተ መካከል የምሥራቅና የምዕራብ ርቀት በኖረ ወይ ምኞቴ! ምን የከፋህ ቁራኛ ነህ» ይላል፡፡ 43|39|ስለ በደላችሁም ዛሬ እናንተ በቅጣት ተጋሪዎች መኾናችሁ አይጠቅማችሁም፤ (ይባላሉ)፡፡ 43|40|አንተ ደንቆሮዎችን ታሰማለህን? ወይስ ዕውሮችንና በግልጽ ጥመት ውስጥ የኾኑን ሰዎች ትመራለህን? 43|41|አንተንም (ቅጣታቸውን ስታይ) ብንወስድህ እኛ ከእነርሱ ተበቃዮች ነን፡፡ 43|42|ወይም ያንን የቀጠርናቸውን ብናሳይህ እኛ በእነርሱ (ቅጣት) ላይ ቻይዎች ነን፡፡ 43|43|ያንንም ወደ አንተ የተወረደልህን አጥብቀህ ያዝ፡፡ አንተ በቀጥተኛው መንገድ ላይ ነህና፡፡ 43|44|እርሱም (ቁርኣን) ለአንተ፣ ለሕዘቦችህም ታላቅ ክብር ነው፡፡ ወደ ፊትም (ከርሱ) ትጠየቃላችሁ፡፡ 43|45|ከመልእክተኞቻችንም ካንተ በፊት የላክናቸውን (ተከታዮቻቸውን) ከአልረሕማን ሌላ የሚገዙዋቸው የኾኑን አማልክት አድርገን እንደ ኾነ ጠይቃቸው፡፡ 43|46|ሙሳንም በተዓምራቶቻችን ወደ ፈርዖንና ወደ ሹማምንቶቹ በእርግጥ ላክን፡፡ «እኔ የዓለማት ጌታ መልክተኛ ነኝ» አላቸውም፡፡ 43|47|በተዓምራታችንም በመጣባቸው ጊዜ ወዲያውኑ እነርሱ በእርሷ ይስቃሉ፡፡ 43|48|ከተዓምርም አንዲትንም አናሳያቸውም እርሷ ከብጤዋ በጣም የበለጠች ብትኾን እንጅ፡፡ (ከክህደታቸው) ይመለሱም ዘንድ በቅጣት ያዝናቸው፡፡ 43|49|«አንተ ድግምተኛ (ዐዋቂ) ሆይ! ጌታህን አንተ ዘንድ ቃል በገባልህ ለእኛ ለምንልን፡፡ እኛ (ቅጣቱን ቢያነሳልን) ተመሪዎች ነን» አሉም፡፡ 43|50|ስቃዩን ከእነርሱ ላይ በገለጥንም ጊዜ ወዲያውኑ ኪዳናቸውን ያፈርሳሉ፡፡ 43|51|ፈርዖንም በሕዝቦቹ ውስጥ ተጣራ፡፡ አለም፤ «ሕዝቦቼ ሆይ! የምስር ግዛት የኔ አይደለምን? እነዚህም ጅረቶች ከስሬ የሚፈሱ ሲኾኑ (የኔ አይደሉምን?) አትመለከቱምን? 43|52|«በውነቱ እኔ ከዚህ ያ እርሱ ወራዳ ንግግሩንም ሊገልጽ የማይቀርብ ከኾነው በላጭ ነኝ፡፡ 43|53|«በእርሱም ላይ የወርቅ አንባሮች ለምን አልተጣሉበትም ወይም መላእክት ከእርሱ ጋር ተቆራኝተው ለምን አልመጡም» (አለ)፡፡ 43|54|ሕዝቦቹንም አቄላቸው፡፡ ታዘዙትም፡፡ እነርሱ አመጸኞች ሕዝቦች ነበሩና፡፡ 43|55|ባስቆጡንም ጊዜ ከእነርሱ በተበቀለን፡፡ ሁሉንም አሰጠምናቸውም፡፡ 43|56|(በጥፋት) ቀዳሚዎችና ለኋለኞቹ (መቀጣጫ) ምሳሌም አደረግናቸው፡፡ 43|57|የመርየም ልጅም ምሳሌ በተደረገ ጊዜ ሕዝቦችህ (ከሓዲዎቹ) ወዲያውኑ ከእርሱ ይስቃሉ፡፡ 43|58|«አማልክቶቻችን ይበልጣሉን ወይስ እርሱ?» አሉም፡፡ ለክርክርም እንጅ ላንተ እርሱን ምሳሌ አላደረጉትም፡፡ በእውነት እነርሱ ክርክረ ብርቱ ሕዝቦች ናቸው፡፡ 43|59|እርሱ በርሱ ላይ የለገስንለት ለእስራኤለም ልጆች ተዓምር ያደረግነው የኾነ ባሪያ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ 43|60|ብንሻም ኖሮ በምድር ላይ ከእናነተ ምትክ መላእክትን ባደረግን ነበር፡፡ 43|61|እርሱም (ዒሳ) ለሰዓቲቱ (ማወቂያ) በእርግጥ ምልክት ነው፡፡ «በእርሷም አትጠራጠሩ፡፡ ተከተሉኝም፤ ይህ ቀጥተኛ መንገድ ነው» (በላቸው)፡፡ 43|62|ሰይጣንም አያግዳችሁ፡፡ እርሱ ለእናንተ ግልጽ ጠላት ነውና፡፡ 43|63|ዒሳ በታምራቶች በመጣ ጊዜም አላቸው «በእርግጥ በጥበብ መጣኋችሁ፡፡ የዚያንም በርሱ የምትለያዩበትን ከፊሉን ለናንተ ላብራራላችሁ (መጣሁ)፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ ታዘዙኝም፡፡ 43|64|«አላህ ጌታዬ ጌታችሁም ነውና ተገዙት፡፡ ይህ ቀጥተኛ መንገድ ነው፡፡» 43|65|ከመካከላቸውም አሕዛቦቹ ተለያዩ፡፡ ለእነዚያም ለበደሉት ከአሳማሚ ቀን ቅጣት ወዮላቸው፡፡ 43|66|ሰዓቲቱን እነርሱ የማያውቁ ኾነው በድንገት ልትመጣባቸው እንጅ ይጠባበቃሉን? 43|67|ወዳጆች በዚያ ቀን ከፊላቸው ለከፊሉ ጠላት ነው፡፡ አላህን ፈሪዎች ብቻ ሲቀሩ፡፡ 43|68|(ለነርሱስ) «ባሮቼ ሆይ! ዛሬ ቀን በእናንተ ላይ ፍርሃት የለባችሁም እናንተም የምታዝኑ አይደላችሁም» (ይባላሉ)፡፡ 43|69|እነዚያ በአንቀጾቻችን ያመኑና ፍጹም ታዛዦች የነበሩ (ባሮቼ ሆይ!) 43|70|«ገነትን ግቡ እናንተም ሚስቶቻችሁም ትደሰታላችሁ ትከበሩም አላችሁ» (ይባላሉ)፡፡ 43|71|ከወርቅ የኾኑ ሰፋፊ ዝርግ ሳሕኖችና ኩባያዎች በእነርሱ ላይ ይዝዞራሉ፡፡ በእርሷም ውስጥ ነፍሶች የሚከጅሉት፣ ዓይኖችም የሚደሰቱበት ሁሉ አልለ፡፡ እናንተም በውስጧ ዘላለም ዘውታሪዎች ናችሁ፡፡ 43|72|ይህችም ያቺ ትሠሩት በነበራችሁት ዋጋ የተሰጣችኋት ገነት ናት፡፡ 43|73|ለእናንተ በውስጧ ብዙ ፍረፍሬዎች በእርግጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 43|74|አመጸኞች በገሀነም ስቃይ ውስጥ በእርግጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 43|75|ከእነርሱ (ቅጣቱ) አይቀለልላቸውም፡፡ እነርሱም በእርሱ ውስጥ ተሰፋ ቆራጮች ናቸው፡፡ 43|76|አልበደልናቸውምም፤ ግን በዳዮቹ እነርሱው ነበሩ፡፡ 43|77|«ማሊክ ሆይ! ጌታህ በኛ ላይ (በሞት) ይፍረድ፡፡» እያሉ ይጣራሉም፡፡ «እናንተ (በቅጣቱ ውስጥ) ዘላለም ነዋሪዎች ናችሁ» ይላቸዋል፡፡ 43|78|እውነተኛውን መንገድ በእርግጥ አመጣንላችሁ፡፡ ግን አብዛኞቻችሁ እውነቱን ጠይዎች ናችሁ፡፡ 43|79|ይልቁንም (በነቢዩ ላይ በማደም) ነገርን አጠነከሩን? እኛም (ተንኮላቸውን ወደእነርሱ በመመለስ) አጠንካሪዎች ነን፡፡ 43|80|ወይም እኛ ምስጢራቸውንና ውይይታቸውን የማንሰማ መኾናችንን ያስባሉን? አይደለም፤ መልክተኞቻችንም እነርሱ ዘንድ ይጽፋሉ፡፡ 43|81|«ለአልረሕማን ልጅ (የለውም እንጅ) ቢኖረው እኔ (ለልጁ) የተገዢዎቹ መጀመሪያ ነኝ» በላቸው፡፡ 43|82|የሰማያትና የምድር ጌታ የዙፋኑ ጌታ ከሚሉት ነገር ሁሉ ጠራ፡፡ 43|83|ተዋቸውም፡፡ ያንን ይስፈራሩበት የነበሩትን ቀናቸውን እስከሚገናኙ ድረስ (በስሕተታቸው ውስጥ) ይዋኙ ይጫዎቱም፡፡ 43|84|እርሱም ያ በሰማይ ውስጥ ሊግገዙት የሚገባው በምድርም ውስጥ ሊግገዙት የሚገባው አምላክ ነው፡፡ እርሱም ብልሃተኛው ዐዋቂው ነው፡፡ 43|85|ያም የሰማያትና የምድር በመካከላቸውም ያለው ሁሉ ንግሥና የእርሱ ብቻ የኾነው አምላክ ላቀ፡፡ የሰዓቲቱም (የመምጫዋ ዘመን) ዕውቀት እርሱ ዘንድ ብቻ ነው፡፡ ወደእርሱም ትመለሳላችሁ፡፡ 43|86|እነዚያም ከአላህ ሌላ የሚግገዟቸው እነርሱ የሚያውቁ ኾነው በእውነት ከመሰከሩት በስተቀር ምልጃን አይችሉም፡፡ 43|87|ማን እንደፈጠራቸውም ብትጠይቃቸው «በእርግጥ አላህ ነው» ይላሉ፡፡ ታዲያ (ከእምነት) ወዴት ይዞራሉ፡፡ 43|88|(ነቢዩ) ጌታዬ ሆይ! እነዚህ የማያምኑ ሕዝቦች ናቸው፤ የማለቱም (ዕውቀት አላህ ዘንድ ነው)፡፡ 43|89|እነርሱንም ተዋቸው፡፡ ነገሬ ሰላም ነው በልም፡፡ ወደፊትም (የሚመጣባቸውን) ያውቃሉ፡፡ 44|1|ሐ.መ (ሓ ሚም)፡፡ 44|2|አብራሪ በኾነው መጽሐፍ እንምላለን፡፡ 44|3|እኛ (ቁርኣኑን) በተባረከች ሌሊት ውስጥ አወረድነው፡፡ እኛ አስፈራሪዎች ነበርንና፡፡ 44|4|በውስጧ የተወሰነው ነገር ሁሉ ይልለያል፡፡ 44|5|ከእኛ ዘንድ የኾነ ትእዛዝ ሲኾን (አወረድነው)፡፡ እኛ (መልክተኞችን) ላኪዎች ነበርን፡፡ 44|6|ከጌታህ በኾነው ችሮታ (ተላኩ)፡፡ እነሆ እርሱ ሰሚው ዐዋቂው ነውና፡፡ 44|7|የሰማያትና የምድር በመካከላቸውም ያለው ነገር ሁሉ ጌታ ከኾነው (ተላኩ)፡፡ የምታረጋግጡ እንደኾናችሁ (ነገሩ እንዳልነው መኾኑን እወቁ)፡፡ 44|8|ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ ሕያው ያደርጋል፡፡ ይገድላልም፡፡ ጌታችሁ የመጀመሪያዎቹ አባቶቻችሁም ጌታ ነው፡፡ 44|9|በእውነቱ እነርሱ የሚጫወቱ ሲኾኑ በመጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ 44|10|ሰማይም በግልጽ ጭስ የምትመጣበትን ቀን ተጠባበቅ፡፡ 44|11|ሰዎችን የሚሸፍን (በኾነ ጭስ) ይህ አሳማሚ ቅጣት ነው፡፡ 44|12|«ጌታችን ሆይ! ከእኛ ላይ ቅጣቱን ግለጥልን፡፡ እኛ አማኞች እንኾናለንና» (ይላሉም)፡፡ 44|13|(ቅጣቱ በወረደ ጊዜ) ለእነርሱ መግገሰጽ እንዴት ይኖራቸዋል? አስረጅ መልክተኛ የመጣቸው ሲኾን (የካዱም ሲኾኑ)፡፡ 44|14|ከዚያም ከእርሱ የዞሩ፤ (ከሰው) «የተሰተማረ ዕብድ ነው» ያሉም ሲኾኑ፡፡ 44|15|እኛ ቅጣቱን ለጥቂት ጊዜ ገላጮች ነን፡፡ እናንተ (ወደ ክህደታችሁ) በእርግጥ ተመላሾች ናችሁ፡፡ 44|16|ታላቂቱን ብርቱ አያያዝ በምንይዝበት ቀን፤ እኛ ተበቃዮች ነን፡፡ 44|17|ከእነርሱም በፊት የፈርዖንን ሕዝቦች በእርግጥ ሞከርን፡፡ ክቡር መልእክተኛም መጣላቸው፡፡ 44|18|«የአላህን ባሮች ወደኔ አድርሱ፡፡ እኔ ለእናንተ ታማኝ መልክተኛ ነኝና፡፡ 44|19|«በአላህም ላይ አትኩሩ፡፡ እኔ ግልጽ የኾነን አስረጅ ያመጣሁላችሁ ነኝና (በማለት መጣላቸው)፡፡ 44|20|«እኔም እንዳትወግሩኝ በጌታየና በጌታችሁ ተጠብቂያለሁ፡፡ 44|21|«በእኔም ባታምኑ ራቁኝ» (ተዉኝ አለ)፡፡ 44|22|ቀጥሎም (ስለ ዛቱበት) «እነዚህ አመጸኞች ሕዝቦች ናቸው» (አጥፋቸው) ሲል ጌታውን ለመነ፡፡ 44|23|(ጌታው) «ባሮቼንም ይዘህ በሌሊት ኺድ፡፡ እናንተ የሚከተሉዋችሁ ናችሁና፡፡ 44|24|«ባሕሩንም የተከፈተ ኾኖ ተወው፡፡ እነርሱ የሚሰጥጠሙ ሰራዊት ናቸውና» (አለው)፡፡ 44|25|ከአትክልቶችና ከምንጮችም ብዙ ነገሮችን ተዉ፡፡ 44|26|ከአዝመራዎችም ከመልካም መቀመጫም፡፡ 44|27|በእርሷ ተደሳቾች ከነበሩባትም ድሎት (ብዙን ነገር ተዉ)፡፡ 44|28|(ነገሩ) እንደዚሁ ኾነ፡፡ ሌሎችንም ሕዝቦች አወረስናት፡፡ 44|29|ሰማይና ምድርም በእነርሱ ላይ አላለቀሱም፡፡ የሚቆዩም አልነበሩም፡፡ 44|30|የእስራኤልንም ልጆች አዋራጅ ከኾነ ስቃይ በእርግጥ አዳንናቸው፡፡ 44|31|ከፈርዖን፤ እርሱ የኮራ ከወሰን አላፊዎቹ ነበርና፡፡ 44|32|ከማወቅም ጋር በዓለማት ላይ በእርግጥ መረጥናቸው፡፡ 44|33|ከታምራቶችም በውስጡ ግልጽ የኾነ ፈተና ያለበትን ሰጠናቸው፡፡ 44|34|እነዚህ (የመካ ከሓዲዎች) በእርግጥ ይላሉ፡- 44|35|እርሷ የፊተኛይቱ ሞታችን እንጅ አይደለችም፡፡ እኛም የምንቀሰቀስ አይደለንም፡፡ 44|36|እውነተኞችም እንደ ኾናችሁ አባቶቻችንን አምጡልን፡፡ 44|37|እነርሱ በላጮች ናቸውን ወይስ የቱብበዕ ሕዝቦችና እነዚያ ከእነርሱ በፊት የነበሩት? አጠፋናቸው፡፡ እነርሱ አመጸኞች ነበሩና፡፡ 44|38|ሰማያትንና ምድርንም በሁለቱ መካከል ያለውንም ሁሉ ቀላጆች ኾነን አልፈጠርንም፡፡ 44|39|ሁለቱንም በምር እንጅ አልፈጠርናቸውም፡፡ ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 44|40|የመለያው ቀን ለሁሉም ቀጠሯቸው ነው፡፡ 44|41|ዘመድ ከዘመዱ ምንንም የማይጠቅምበት እነርሱም የማይርረዱበት ቀን ነው፡፡ 44|42|አላህ ያዘነለት ሰውና ያመነ ብቻ ሲቀር፡፡ (እርሱስ ይርረዳል)፡፡ እርሱ አሸናፊው አዛኙ ነውና፡፡ 44|43|የዘቁመ ዛፍ 44|44|የኀጢኣተኛው ምግብ ነው፡፡ 44|45|እንደ ዘይት አተላ ነው፡፡ በሆዶች ውስጥ የሚፈላ ሲኾን፡፡ 44|46|እንደ ገነፈለ ውሃ አፈላል (የሚፈላ ሲኾን)፡፡ 44|47|ያዙት፤ ወደ ገሀነም መካከልም በኀይል ጎትቱት፡፡ 44|48|ከዚያም «ከራሱ በላይ ከፈላ ውሃ ስቃይ አንቧቡበት፡፡» 44|49|«ቅመስ፤ አንተ አሸናፊው ክብሩ ነህና» (ይባላል)፡፡ 44|50|«ይህ ያ በእርሱ ትጠራጠሩበት የነበራችሁት ነው» (ይባላሉ)፡፡ 44|51|ጥንቁቆቹ በእርግጥ በጸጥተኛ መኖሪያ ውስጥ ናቸው፡፡ 44|52|በአትክልቶችና በምንጮች ውስጥ ናቸው፡፡ 44|53|ፊት ለፊት የተቅጣጩ ኾነው ከስስ ሐርና ከወፍራም ሐር ይለብሳሉ፡፡ 44|54|(ነገሩ) እንደዚሁ ነው፤ ዓይናማዎች የኾኑን ነጫጭ ሴቶችም እናጠናዳቸዋለን፡፡ 44|55|በእርሷም ውስጥ የተማመኑ ኾነው፤ ከፍራፍሬ ሁሉ ያዝዛሉ፡፡ 44|56|የፊተኛይቱን ሞት እንጅ (ዳግመኛ) በእርሷ ውስጥ ሞትን አይቀምሱም፡፡ የገሀነምንም ቅጣት (አላህ) ጠበቃቸው፡፡ 44|57|ከጌታህ በኾነ ችሮታ (ጠበቃቸው)፡፡ ይህ እርሱ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ 44|58|(ቁርኣኑን) በቋንቋህም ያገራነው (ሕዝቦችህ) ይገነዘቡ ዘንድ ብቻ ነው፡፡ 44|59|ተጠባበቅም እነርሱ ተጠባባቂዎች ናቸውና፡፡ 45|1|ሐ.መ (ሓ ሚም)፡፡ 45|2|የመጽሐፉ መወረድ አሸናፊ ጥበበኛ ከኾነው አላህ ነው፡፡ 45|3|በሰማያትና በምድር ውስጥ ለምእምናን ሁሉ (ለችሎታው) እርገጠኛ ምልክቶች አልሉ፡፡ 45|4|እናንተንም በመፍጠር ከተንቀሳቃሽም (በምድር ላይ) የሚበትነውን ሁሉ (በመፍጠሩ) ለሚያረጋግጡ ሕዝቦች ተዓምራቶች አልሉ፡፡ 45|5|በሌሊትና መዓልት መተካካትም፣ ከሲሳይም (ከዝናም) አላህ ከሰማይ ባወረደው በርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው በማድረጉ፣ ነፋሶችንም (በያቅጣጫቸው) በማዘዋወሩ ለሚያውቁ ሕዝቦች ማስረጃዎች አልሉ፡፡ 45|6|እነዚህ ባንተ ላይ በውነት የምናነባቸው ሲኾኑ የአላህ ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ከአላህና ከማስረጃዎቹም ወዲያ በየትኛው ንግግር ያምናሉ? 45|7|ውሸታም ኀጢአተኛ ለኾነ ሁሉ ወዮለት፡፡ (ጥፋት ተገባው)፡፡ 45|8|የአላህን አንቀጾች በእርሱ ላይ የሚነበቡለት ሲኾኑ ይሰማል፡፡ ከዚያም የኮራ ሲኾን እንዳልሰማት ኾኖ (በክሕደቱ ላይ) ይዘወትራል፡፡ በአሳማሚም ቅጣት አብስረው፡፡ 45|9|ከአንቀጾቻችንም አንዳችን ባወቀ ጊዜ መሳለቂያ አድርጎ ይይዛታል፡፡ እነዚያ ለእነርሱ አዋራጅ ቅጣት አልላቸው፡፡ 45|10|ከፊታቸውም ገሀነም አልለች፡፡ የሰበሰቡትም ሀብት ከእነርሱ ላይ ምንንም አይመልስላቸውም፡፡ ከአላህ ሌላም ረዳቶች አድርገው የያዙዋቸው (አይጠቅሟቸውም)፡፡ ለእነርሱም ታላቅ ቅጣት አልላቸው፡፡ 45|11|ይህ (ቁርኣን) መሪ ነው፡፡ እነዚያም በጌታቸው አንቀጾች የካዱት ለእነርሱ ከብርቱ ቅጣት የኾነ አሳማሚ ስቃይ አልላቸው፡፡ 45|12|አላህ ያ ባሕርን በውስጡ ታንኳዎች በፈቃዱ እንዲንሻለሉበት ከችሮታውም እንድትፈልጉበት እንድታመሰግኑትም ለእናነተ የገራላችሁ ነው፡፡ 45|13|ለናንተም በሰማያት ያለውንና በምድርም ያለውን ሁሉ በመላ ከእርሱ ሲኾን የገራላችሁ ነው፡፡ በዚህ ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች ተዓምራት አልለበት፡፡ 45|14|ለእነዚያ ለአመኑት ሰዎች (ምሕረት አድርጉ) በላቸው፡፡ ለእነዚያ የአላህን ቀኖች ለማይፈሩት ይምራሉና፡፡ ሕዝቦችን ይሠሩት በነበሩት ነገር ይመነዳ ዘንድ (ምሕረት አድርጉ በላቸው)፡፡ 45|15|መልካምን የሠራ ሰው ለነፍሱ ነው፡፡ ያከፋም ሰው በእርሷ ላይ ነው፡፡ ከዚያም ወደ ጌታችሁ ትመለሳላችሁ፡፡ 45|16|ለእስራኤል ልጆችም መጽሐፍንና ሕግን፣ ነቢይነትንም በእርግጥ ሰጠናቸው፡፡ ከመልካም ሲሳዮችም ለገስንላቸው፡፡ በዓለማት ላይም አበለጥናቸው፡፡ 45|17|ከትዕዛዝም ግልጾችን ሰጠናቸው፡፡ ዕውቀቱም ከመጣላቸው በኋላ በመካከላቸው ለምቀኝነት እንጅ ለሌላ አልተለያዩም፡፡ ጌታህ በትንሣኤ ቀን በዚያ በእርሱ ይለያዩበት በነበሩት ነገር በመካከላቸው በእርግጥ ይፈርዳል፡፡ 45|18|ከዚያም ከነገሩ (ከሃይማኖት) በትክክለኛይቱ ሕግ ላይ አደረግንህ፡፡ ስለዚህ ተከተላት፡፡ የእነዚያንም የማያውቁትን ሕዝቦች ዝንባሌዎች አትከተል፡፡ 45|19|እነርሱ ከአላህ (ቅጣት) ምንንም ከአንተ አይገፈትሩልህምና፡፡ በደለኞም ከፊላቸው የከፊሉ ረዳቶች ናቸው፡፡ አላህም የጥንቁቆቹ ረዳት ነው፡፡ 45|20|ይሀ (ቁርኣን) ለሰዎች የልብ ብርሃኖች ነው፡፡ ለሚያረጋግጡም ሕዝቦች መሪና እዝነት ነው፡፡ 45|21|እነዚያ ኀጢአቶችን የሠሩ ሕይወታቸውም ሞታቸውም ትክክል ሲኾን እንደእነዚያ እንደ አመኑትና መልካሞችን እንደሠሩት ልናደርጋቸው ይጠረጥራሉን? (አይጠርጥሩ)፡፡ የሚፈርዱት ምንኛ ከፋ! 45|22|አላህም ሰማያትንና ምድርን (ለችሎታው እንደሚያመለክትባቸውና) ነፍስም ሁሉ በሠራችው ሥራ ትምመነዳ ዘንድ በትክክል ፈጠረ፡፡ እነርሱም አይበደሉም፡፡ 45|23|ዝንባሌውን አምላኩ አድርጎ የያዘውን፣ አላህም ከዕውቀት ጋር ያጠመመውን፣ በጆሮውና በልቡ ላይም ያተመበትን፣ በዓይኑም ላይ ሺፋን ያደረገበትን ሰው አየህን! ታዲያ ከአላህ በኋላ የሚያቀናው ማነው? አትገሠጹምን? 45|24|እርሷም (ሕይወት) የቅርቢቱ ሕይወታችን እንጅ ሌላ አይደለችም፡፡ «እንሞታለን፤ ሕያውም እንኾናለን፡፡ ከጊዜም (ማለፍ) በስተቀር ሌላ አያጠፋንም» አሉ፡፡ ለእነርሱም በዚህ (በሚሉት) ምንም ዕውቀት የላቸውም፡፡ እነርሱ የሚጠራጠሩ እንጅ ሌላ አይደሉም፡፡ 45|25|አንቀጾቻችንም ግልጾች ኾነው በእነርሱ ላይ በተነበቡላቸው ጊዜ ክርክራቸው «እውነተኞች እንደ ኾናችሁ አባቶቻችንን አምጡ» ማለት እንጅ ሌላ አልነበረም፡፡ 45|26|«አላህ ሕያው ያደርጋችኋል፤ ከዚያም ይገድላችኋል፣ ከዚያም ወደ ትንሣኤ ቀን ይሰበስባችኋል፡፡ በእርሱ ጥርጥር የለበትም፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም» በላቸው፡፡ 45|27|የሰማያትና የምድር ግዛት የአላህ ብቻ ነው፡፡ ሰዓቲቱም በምትቆምበት ቀን ያን ጊዜ አጥፊዎች ሁሉ ይከስራሉ፡፡ 45|28|ሕዝብንም ሁሉ ተንበርካኪ ኾና ታያታለህ፡፡ ሕዝብ ሁሉ ወደ መጽሐፏ ትጥጠራለች፡፡ «ዛሬ ትሠሩት የነበራችሁትን ነገር ትመነዳላችሁ» (ይባላሉ)፡፡ 45|29|ይህ መጽሐፋችን ነው፡፡ በእናንተ ላይ በእውነት ይናገራል፡፡ እኛ ያንን ትሠሩት የነበራችሁትን እናስገለብጥ ነበርን (ይባላሉ)፡፡ 45|30|እነዚያ ያመኑትና መልካሞችን የሠሩትማ ጌታቸው በእዝነቱ ውስጥ ያገባቸዋል፡፡ ይህ እርሱ ግልጽ የኾነ ማግኘት ነው፡፡ 45|31|እነዚያም የካዱትማ (ለእነርሱ ይባላሉ) «አንቀጾቼ በእናንተ ላይ ይነበቡ አልነበሩምን? ኮራችሁም፡፡ ከሓዲዎች ሕዝቦችም ነበራችሁ፡፡» 45|32|«የአላህ ቀጠሮ እውነት ነው፡፡ ሰዓቲቱም በእርሷ (መምጣት) ጥርጥር የለም፡፡» በተባለ ጊዜም «ሰዓቲቱ ምን እንደ ኾነች አናውቅም፡፡ መጠራጠርን የምንጠራጠር እንጅ ሌላ አይደለንም፡፡ እኛም አረጋጋጮች አይደለንም» አላችሁ፡፡ 45|33|የሠሩዋቸውም ኀጢአቶች ለእነርሱ ይገለጹላቸዋል፡፡ ያም በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩት ቅጣት በእነርሱ ላይ ይወርድባቸዋል፡፡ 45|34|«ይህንንም ቀናችሁን መገናኘትን እንደ ረሳችሁ ዛሬ እንረሳችኋለን፡፡ (እንተዋችኋለን)፡፡ መኖሪያችሁም እሳት ናት፡፡ ለእናንተም ከረዳቶች ምንም የላችሁም» ይባላል፡፡ 45|35|ይህ እናንተ የአላህን አንቀጾች መቀለጃ አድርጋችሁ በመያዛችሁና ቅርቢቱም ሕይወት ስለአታለለቻችሁ ነው፤ (ይባላሉ)፡፡ ዛሬ ከእርሷ አይወጥጡም፤ እነርሱም በወቀሳ አይታለፉም፡፡ 45|36|ምስጋናም ለአላህ ለሰማያት ጌታ ለምድርም ጌታ ለዓለማት ጌታ የተገባው ነው፡፡ 45|37|ኩራትም በሰማያትም በምድርም ለእርሱ ብቻ ነው፡፡ እርሱም አሸነፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 46|1|ሐ.መ (ሓ ሚም)፡፡ 46|2|የመጽሐፉ መወረድ አሸናፊ ጥበበኛ ከኾነው አላህ ነው፡፡ 46|3|ሰማያትንና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ በምርና የተወሰነ ጊዜንም በመለካት እንጅ (ለቀልድ) አልፈጠርናቸውም፡፡ እነዚያ የካዱትም ከተስፈራሩት ነገር (ትተው) ዘዋሪዎች ናቸው፡፡ 46|4|«ከአላህ ሌላ የምትግገዟቸውን አያችሁን? ከምድር ምንን እንደ ፈጠሩ አሳዩኝ፡፡ ወይም በሰማያት ለእነርሱ (ከአላህ ጋር) መጋራት አላቸውን? (ያማልዱናል በማለታችሁ) እውነተኞች እንደ ኾናችሁ ከዚህ (ቁርኣን) በፊት የኾነን መጽሐፍ ወይም ከዕውቀት የኾነ ቅርስን አምጡልኝ» በላቸው፡፡ 46|5|እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስም ለእርሱ የማይመልስለትን (ጣዖት) ከአላህ ሌላ ከሚጠራ ሰው ይበልጥ የተሳሳተ ማነው? እነርሱም ከጥሪያቸው ዘንጊዎች ናቸው፡፡ 46|6|ሰዎችም በተሰበሰቡ ጊዜ (ጣዖቶቹ) ለእነርሱ ጠላቶች ይኾናሉ፡፡ (እነሱን) መገዛታቸውንም ከሓዲዎች ይኾናሉ፡፡ 46|7|በእነርሱም ላይ አንቀጾቻችን ግልጾች ኾነው በተነበቡ ጊዜ እነዚያ እውነቱን በመጣላቸው ጊዜ የካዱትን «ይህ ግልጽ ድግምት ነው» አሉ፡፡ 46|8|ይልቁንም ቀጠፈው ይላሉን? «ብቀጥፈው ለእኔ ከአላህ (ቅጣት ለማዳን) ምንንም አትችሉም፡፡ እርሱ ያንን በእርሱ የምትቀባዥሩበትን ዐዋቂ ነው፡፡ በእኔና በእናንተ መካከል መስካሪ በእርሱ በቃ፡፡ እርሱም መሓሪው አዛኙ ነው» በላቸው፡፡ 46|9|«ከመልክተኞች ብጤ የሌለኝ አይደለሁም፡፡ በእኔም በእናንተም ምን እንደሚሥሠራም አላውቅም፡፡ ወደእኔ የሚወረደውን እንጅ ሌላን አልከተልም፡፡ እኔም ግልጽ አስፈራሪ እንጅ ሌላ አይደለሁም» በላቸው፡፡ 46|10|(ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው «እስቲ ንገሩኝ፤ (ቁርኣኑ) ከአላህ ዘንድ ቢኾን፡፡ በእርሱም ብትክዱ፣ ከእስራኤል ልጆችም መስካሪ በብጤው (በእርሱ) ላይ ቢመሰክር፣ ቢያምንም፣ (ከእምነት) ብትኮሩም፣ (በዳይ አትኾኑምን?)» አላህ በእርግጥ በደለኞችን ሕዝቦች አያቀናም፡፡ 46|11|እነዚያንም የካዱት ሰዎች ስለእነዚያ ስለ አመኑት ሰዎች (እምነቱ) «መልካም ነገር በኾነ ኖሮ ወደርሱ ባልቀደሙን ነበር» አሉ፡፡ በእርሱም ባልተመሩ ጊዜ «ይህ (ቁርኣን) ጥንታዊ ቅጥፈት ነው» ይላሉ፡፡ 46|12|ከበፊቱም የሙሳ መጽሐፍ መሪና ጸጋ ሲኾን አልለ፡፡ ይህም እነዚያን የበደሉትን ሊያስፈራራ በዐረብኛ ቋንቋ ሲኾን (የፊቶቹን መጻሕፍት) አረጋጋጭ መጽሐፍ ነው፡፡ ለበጎ አድራጊዎችም ብስራት ነው፡፡ 46|13|እነዚያ «ጌታችን አላህ ነው» ያሉ፣ ከዚያም ቀጥ ያሉ በነርሱ ላይ ፍርሃት የለባቸውም፡፡ እነርሱም አያዝኑም፡፡ 46|14|እነዚያ የገነት ጓዶች ናቸው፡፡ በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ሲኾኑ፡፡ በዚያ ይሠሩት በነበሩት ምክንያት ታላቅን ምንዳ (ይምመነዳሉ)፡፡ 46|15|ሰውንም በወላጆቹ በጎ መዋልን በጥብቅ አዘዝነው፡፡ እናቱ በችግር ላይ ኾና አረገዘችው፡፡ በችግርም ወለደችው፡፡ እርግዝናውና ከጡት መለያውም ሰላሳ ወር ነው፡፡ ጥንካሬውንም ወቅት በደረሰ ጊዜ (ከዚያ አልፎ) አርባ ዓመትንም በደረሰ ጊዜ «ጌታዬ ሆይ! ያችን በእኔ ላይና በወላጆቼ ላይ የለገስካትን ጸጋህን እንዳመሰግን የምትወደውንም መልካም ሥራ እንድሠራ ምራኝ፡፡ ዘሮቼንም ለእኔ አብጅልኝ፡፡ እኔ ወዳንተ ተመለስኩ፡፡ እኔም ከሙስሊሞ ነኝ» አለ፡፡ 46|16|እነዚህ (ይህንን ባዮች) በገነት ጓዶች ውስጥ ሲኾኑ እነዚያ ከሠሩት ሥራ መልካሙን ከነሱ የምንቀበላቸውና ከኀጢአቶቻቸውም የምናልፋቸው ናቸው፡፡ ያንን ተስፋ ይስሰጡት የነበሩትን እውነተኛ ቀጠሮ (እንሞላላቸዋለን)፡፡ 46|17|ያንንም ለወላጆቹ «ፎህ ለእናንተ ከእኔ በፊት የክፍል ዘመናት ሰዎች (ሳይወጡ) በእርግጥ ያለፉ ሲኾኑ (ከመቃብር) እንድወጥጣ ታስፈራሩኛላችሁን?» ያለውን ሁለቱም (ወላጆቹ) አላህን የሚለምኑ ሲኾኑ (ባታምን) «ወዮልህ፡፡ እመን፡፡ የአላህ ቀጠሮ እርግጠኛ ነው፡፡» (ሲሉት) «ይህ የፊተኞቹ ሰዎች ጽሑፍ ተረቶች እንጅ ሌላ አይደለም» የሚለውንም ሰው (አስታውስ)፡፡ 46|18|እነዚህ እነዚያ ከጋኔንም ከሰውም ከእነርሱ በፊት ካለፉት ሕዝቦች ጋር ቃሉ በእነርሱ ላይ የተረጋገጠባቸው ናቸው፡፡ እነርሱ ከሳሪዎች ነበሩና፡፡ 46|19|ለሁሉም ከሠሩት ሥራ ደረጃዎች አልሏቸው፡፡ ሥራዎቻቸውንም ይሞላላቸው ዘንድ (ይህንን መነዳቸው) እነርሱም አይበደሉም፡፡ 46|20|እነዚያም የካዱት በእሳት ላይ በሚጋፈጡ ቀን «ጣፋጮቻችሁን በአነስተኛይቱ ሕይወታችሁ አሳለፋችሁ፡፡ በእርሷም ተጣቀማችሁ፡፡ ስለዚህ በምድር ላይ ያለ አግባብ ትኮሩ በነበራችሁትና ታምጹ በነበራችሁት ዛሬ የውርደትን ቅጣት ትምመነዳላችሁ» (ይባላሉ)፡፡ 46|21|የዓድንም ወንድም (ሁድን) ሕዝቦቹን በአሕቃፍ ባስጠነቀቀ ጊዜ አውሳለቸው፡፡ በስተፊቱና በስተኋላውም ብዙ አስፈራሪዎች በእርግጥ አልፈዋል፡፡ «ከአላህ በስተቀር አትግገዙ እኔ በእናነተ ላይ የከባድ ቀንን ቅጣት እፈራላችኋለሁና» በማለት (ባሰጠነቀቀ ጊዜ)፡፡ 46|22|«ከአማልክቶቻችን ልታዞረን መጣህብን? ከውነተኞቹም እንደኾንክ የምትዝትብንን (ቅጣት) አምጣው» አሉ፡፡ 46|23|«ዕውቀቱ አላህ ዘንድ ብቻ ነው፡፡ ያን በእርሱ የተላክሁበትንም አደርስላችኋለሁ፡፡ ግን እኔ የምትሳሳቱ ሕዝቦች ኾናችሁ አያችኋለሁ» አላቸው፡፡ 46|24|ሸለቆዎቻቸውን ተቅጣጪ አግዳሚ ደመና ኾኖ ባዩትም ጊዜ «ይህ አዝናቢያችን የኾነ ደመና ነው» አሉ፡፡ (ሁድም) «አይደለም፤ እርሱ ያ በእርሱ የተቻኮላችሁበት መዐት ነው፡፡ በውስጧ አሳማሚ ስቃይ ያለባት ነፋስ ናት፡፡ 46|25|በጌታዋ ትዕዛዝ አንዳቹን ሁሉ ታጠፋለች» (አላቸው)፡፡ ከመኖሪያዎቻቸውም በስተቀር ምንም የማይታዩ ኾኑ፡፡ እንደዚሁ አመጸኞችን ሕዝቦች ሁሉ እንቀጣለን፡፡ 46|26|በዚያም እናንተን በእርሱ ባላስመቸንበት (ድሎት) በእርግጥ አስመቸናቸው፡፡ ለእነርሱም መስሚያንና ማያዎችን፣ ልቦችንም አደረግንላቸው፡፡ ግን መስሚያቸውና ማያዎቻቸው፣ ልቦቻቸውም ከእነሱ ምንም አልጠቀሟቸውም፡፡ በአላህ አንቀጾች ይክዱ ነበሩና፡፡ በእነርሱም ላይ ያ በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩት ቅጣት ወረደባቸው፡፡ 46|27|ከከተሞችም እነዚያን በአካባቢያችሁ የነበሩትን በእርግጥ አጠፋን (ከክሕደታቸው) ይመለሱም ዘንድ አስረጂዎችን መላለስን፡፡ 46|28|እነዚያም መቃረቢያ ይኾኑ ዘንድ ከአላህ ሌላ አማልክት አድርገው የያዙዋቸው አይረዷቸውም ኖሯልን? በእርግጥ ከነሱ ራቁ፡፡ ይህም ውሸታቸውና (በልማድ) ይቀጥፉት የነበሩት ነው፡፡ 46|29|ከጋኔን የኾኑን ጭፍሮች ቁርኣንን የሚያዳምጡ ሲኾኑ ወዳንተ ባዞርን ጊዜም (አስታውስ)፡፡ በተጣዱትም ጊዜ ዝም ብላችሁ አዳምጡ ተባባሉ፡፡ በተጨረሰም ጊዜ አስጠንቃቂዎች ኾነው ወደ ሕዝቦቻቸው ተመለሱ፡፡ 46|30|አሉም «ሕዝቦቻችን ሆይ! እኛ ከሙሳ በኋላ የተወረደን መጽሐፍ በፊቱ ያለውን (መጽሐፍ) የሚያረጋግጥ ወደ እውነትና ወደ ቀጥተኛ መንገድ የሚመራ የኾነን ሰማን፡፡ 46|31|ወገኖቻችን ሆይ! የአላህን ጠሪ ተቀበሉ፡፡ በእርሱም እመኑ፡፡ (አላህ) ከኀጢአቶቻችሁ ለእናንተ ይምራልና፡፡ ከአሳማሚ ቅጣትም ያድናችኋልና፡፡ 46|32|የአላህንም ጠሪ የማይቀበል ሰው በምድር ውስጥ የሚያመልጥ አይደለም፡፡ ከእርሱም ሌላ ለእርሱ ረዳቶች የሉትም፡፡ እነዚያ በግልጽ ስሕተት ውስጥ ናቸው» (አሉ)፡፡ 46|33|ያ ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ እነርሱንም በመፍጠሩ ያልደከመው አላህ ሙታንን ሕያው በማድረግ ላይ ቻይ መኾኑን አላስተዋሉምን? (በማስነሳት) ቻይ ነው፡፡ እርሱ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና፡፡ 46|34|እነዚያም የካዱት ሰዎች በእሳት ላይ በሚቀረቡ ቀን «ይህ እውነት አይደለምን?» (ይባላሉ)፡፡ «እውነት ነው፤ በጌታችን ይኹንብን» ይላሉ፡፡ (አላህም) «ትክዱ በነበራችሁት ምክንያት ቅጣቱን ቅመሱ» ይላቸዋል፡፡ 46|35|ከመልክተኞችም የቆራጥነት ባለቤቶች የኾኑት እንደ ታገሱ ሁሉ ታገስ፡፡ ለእነርሱም (ለሕዝቦችህ ቅጣት) አትቻኮል፡፡ ያንን የሚስፈራሩበትን ቅጣት በሚያዩ ቀን እነርሱ ከቀን አንዲትን ሰዓት አንጅ እንዳልቆዩ ይኾናሉ፡፡ (ይህ ቁርኣን) በቂ ግሳጼ ነው አመጸኞችም ሕዝቦች እንጅ (ሌሎች) ይጥጠፋሉን? 47|1|እነዚያ የካዱ ከአላህ መንገድም የከለከሉ (አላህ) ሥራዎቻቸውን አጠፋባቸው፡፡ 47|2|እነዚያም ያመኑ፣ በጎዎችንም የሠሩ፣ በሙሐመድ ላይም የወረደው እርሱ ከጌታቸው ሲኾን እውነት ስለ ኾነ ያመኑ ከእነርሱ ላይ ኃጢአቶቻቸውን ያባብሳል፡፡ ኹኔታቸውንም ሁሉ ያበጃል፡፡ 47|3|ይህ እነዚያ የካዱት ውሸትን የተከተሉ በመኾናቸውና እነዚያም ያመኑት ከጌታቸው የኾነን እውነት ስለተከተሉ ነው፡፡ እንደዚሁ አላህ ለሰዎች ምሳሌዎቻቸውን ያብራራል፡፡ 47|4|እነዚያንም የካዱትን (በጦር ላይ) ባገኛችሁ ጊዜ ጫንቃዎችን በኀይል ምቱ፡፡ ባደካማችኋቸውም ጊዜ (አትግደሏቸው ማርኳቸው)፡፡ ማሰሪያውንም አጥብቁ፡፡ በኋላም ወይም በነጻ ትለቋቸዋላችሁ፤ ወይም ትበዧቸዋላችሁ፡፡ (ይህም) ጦሪቱ መሳሪያዋን እስከምትጥል ድረስ ነው፡፡ (ነገሩ) ይህ ነው፡፡ አላህም ቢሻ ከእነርሱ (ያለጦር) በተበቀለ ነበር፡፡ ግን ከፊላችሁን በከፊሉ ሊሞክር (በዚህ አዘዛችሁ)፡፡ እነዚያንም በአላህ መንገድ ላይ የተገደሉትን ሥራዎቻቸውን ፈጽሞ አያጠፋባቸውም፡፡ 47|5|በእርግጥ ይመራቸዋል፡፡ ኹኔታቸውንም ሁሉ ያበጃል፡፡ 47|6|ገነትንም ያገባቸዋል፡፡ ለእነርሱ አስታውቋታል፡፡ 47|7|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን (ሃይማኖቱን) ብትረዱ፤ ይረዳችኋል፡፡ ጫማዎቻችሁንም ያደላድላል፡፡ 47|8|እነዚያም የካዱት ለእነርሱ ጥፋት ተገባቸው፡፡ ሥራዎቻቸውንም አጠፋባቸው፡፡ 47|9|ይህ እነርሱ አላህ ያወረደውን ስለጠሉ ነው፡፡ ስለዚህ ሥራዎቻቸውን አበላሸባቸው፡፡ 47|10|የእነዚያ ከእነርሱ በፊት የነበሩት (ከሓዲዎች) መጨረሻ እንዴት እንደ ነበረ ያዩ ዘንድ በምድር ለይ አልኼዱምን? አላህ በእነርሱ ላይ (ያላቸውን ሁሉ) አጠፋባቸው፡፡ ለከሐዲዎችም ሁሉ ብጤዎችዋ አልሏቸው፡፡ 47|11|ይህ አላህ የእነዚያ ያመኑት ሰዎች ረዳት ስለኾነና ከሓዲዎችም ለእነርሱ ረዳት ስለሌላቸው ነው፡፡ 47|12|አላህ እነዚያን ያመኑትንና መልካሞችን የሠሩትን ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች ያገባቸዋል፡፡ እነዚያም የካዱት (በቅርቢቱ ዓለም) ይጣቀማሉ፡፡ እንስሳዎችም እንደሚበሉ ይበላሉ፡፡ እሳትም ለእነርሱ መኖሪያቸው ናት፡፡ 47|13|ከከተማም እርሷ ከዚያች ካወጣችህ ከተማህ ይበልጥ በኀይል ጠንካራ የኾነች (ባለቤቶችዋን) ያጠፋናቸው ብዙ ናት፡፡ ለእነርሱም ረዳት አልነበራቸውም፡፡ 47|14|ከጌታው በኾነች አስረጅ ላይ የኾነ ምእመን ክፉ ሥራቸው ለእነርሱ እንደ ተሸለመላቸውና ዝንባሌዎቻቸውን እንደ ተከተሉት ነውን? 47|15|የዚያች ጥንቁቆቹ ተስፋ የተሰጧት ገነት ምስል በውስጧ ሺታው ከማይለውጥ ውሃ ወንዞች፣ ጣዕሙ ከማይለወጥ ወተትም ወንዞች፣ ለጠጪዎች ሁሉ ጣፋጭ ከኾነች የወይን ጠጅም ወንዞች ከተነጠረ ማርም ወንዞች አልሉባት፡፡ ለእነርሱም በውስጧ ከፍሬዎች ሁሉ (በያይነቱ) ከጌታቸው ምሕረትም አልላቸው፡፡ (በዚች ገነት ውስጥ ዘውታሪ የኾነ ሰው) እርሱ በእሳት ውስጥ ዘውታሪ እንደኾነ ሰው፣ ሞቃትንም ውሃ እንደተጋቱ፣ አንጀቶቻቸውንም ወዲያውኑ እንደቆራረጠው ነውን? (አይደለም)፡፡ 47|16|ከእነርሱም ወዳንተ የሚያዳምጡ አልሉ፡፡ ከአንተም ዘንድ በወጡ ጊዜ ለእነዚያ ዕውቀት ለተሰጡት «አሁን ምን አለ?» ይላሉ፡፡ እነዚህ እነዚያ በልቦቻቸው ላይ አላህ ያተመባቸው ዝንባሌዎቻቸውንም የተከተሉ ናቸው፡፡ 47|17|እነዚያም የተመሩት (አላህ) መመራትን ጨመረላቸው፡፡ (ከእሳት) መጥጠበቂያቸውንም ሰጣቸው፡፡ 47|18|ሰዓቲቱንም ድንገት የምትመጣባቸው መኾንዋን እንጅ ይጠባበቃሉን? ምልክቶችዋም በእርግጥ መጥተወል፡፡ በመጣቻቸውም ጊዜ ማስታወሳቸው ለእነርሱ እንዴት ይጠቅማቸዋል? 47|19|እነሆ ከአላህ ሌላ አምላክ አለመኖሩንም ዕወቅ፡፡ ስለ ስህተትህም ለምእመናንም ምሕረትን ለምን፡፡ አላህም መዘዋወሪያችሁን፣ መርጊያችሁንም ያውቃል፡፡ 47|20|እነዚያም ያመኑት ሰዎች (መታገል ያለባት) «ሱራ አትወርድም ኖሮአልን?» ይላሉ፡፡ የጠነከረችም ሱራ በተወረደችና በውስጧም መጋደል በተወሳ ጊዜ እነዚያን በልቦቻቸው ውስጥ (የንፍቅና) በሺታ ያለባቸውን ሰዎች ከሞት የኾነ መከራ በርሱ ላይ እንደ ወደቀበት ሰው አስተያየት ወዳንተ ሲመለከቱ ታያቸዋለህ፡፡ ለእነሱም ወዮላቸው፡፡ 47|21|ታዛዥነትና መልካም ንግግር (ይሻላቸዋል) ትዕዛዙም ቁርጥ በኾነ ጊዜ ለአላህ (ትዕዛዝ) እውነተኞች በኾኑ ኖሮ ለእነርሱ የተሻለ በኾነ ነበር፡፡ 47|22|ብትሽሾሙም በምድር ላይ ማበላሸትን ዝምድናችሁንም መቁረጥን ከጀላችሁን? 47|23|እነዚህ እነዚያ አላህ የረገማቸው፣ ያደነቆራቸውም፣ ዓይኖቻቸውንም ያወራቸው ናቸው፡፡ 47|24|ቁርኣንንም አያስተነትኑምን? በእውነቱ በልቦቻቸው ላይ ቁልፎቿ አልሉባትን? 47|25|እነዚያ ለእነርሱ ቅኑ መንገድ ከተብራራላቸው በኋላ ወደ ኋላቸው የተመለሱት ሰይጣን ለእነርሱ መመለሳቸውን ሸለመላቸው፡፡ ለእነርሱም አዝዘናጋቸው፡፡ 47|26|ይህ እነርሱ ለእነዚያ አላህ ያወረደውን ለጠሉት «በነገሩ ከፊል እንታዘዛችኋለን» ያሉ በመኾናቸው ነው፡፡ አላህም መደበቃቸውን ያውቃል፡፡ 47|27|መላእክትም ፊቶቻቸውንና ጀርባዎቻቸውን የሚመቱ ሲኾኑ በገደሉዋቸው ጊዜ (ኹኔታቸው) እንዴት ይኾናል? 47|28|ይህ እነርሱ አላህን ያስቆጣውን ነገር ስለ ተከተሉ ውዴታውንም ስለ ጠሉ ነው፡፡ ስለዚህ ሥራዎቻቸውን አበላሸባቸው፡፡ 47|29|እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ያለባቸው አላህ ቂሞቻቸውን አለማውጣቱን ጠረጠሩን? 47|30|በሻንም ኖሮ እነርሱን ባሳየንህና በምልክታቸውም በእርግጥ ባወቅሃቸው ነበር፡፡ ንግግርንም በማሸሞራቸው በእርግጥ ታውቃቸዋለህ፡፡ አላህም ሥራዎቻችሁን ያውቃል፡፡ 47|31|ከእናንተም ታጋዮቹንና ታጋሾቹን እስከምናውቅ፣ ወሬዎቻችሁንም እስከምንገልጽ ድረስ በእርግጥ እንሞክራችኋለን፡፡ 47|32|እነዚያ የካዱና ከአላህም መንገድ ያገዱ ለእነርሱም ቅኑ መንገድ ከተገለጸላቸው በኋላ መልክተኛውን የተከራከሩ አላህን በምንም አይጎዱትም፡፡ ሥራዎቻቸውንም በእርግጥ ያበላሻል፡፡ 47|33|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ መልክተኛውንም ታዘዙ፡፡ ሥራዎቻችሁንም አታበላሹ፡፡ 47|34|እነዚያ የካዱ፣ ከአላህም መንገድ ያገዱ፣ ከዚያም እነርሱ ከሓዲዎች ኾነው የሞቱ አላህ ለእነርሱ በፍጹም አይምርም፡፡ 47|35|እናንተም አሸናፊዎቹ ስትኾኑ አላህ ከእናንተ ጋር ሲሆን አትድከሙ፡፡ ወደ ዕርቅም አትጥሩ፡፡ ሥራዎቻችሁንም ፈጽሞ አያጎድልባችሁም፡፡ 47|36|ቅርቢቱ ሕይወት ጫወታና ዛዛታ ብቻ ናት፡፡ ብታምኑም ብትጠነቀቁም ምንዳዎቻችሁን ይሰጣችኋል፡፡ ገንዘቦቻችሁንም (ሁሉ) አይጠይቃችሁም፡፡ 47|37|እርሷን ቢጠይቃችሁና ችክ ቢልባችሁ ትሰስታላችሁ፡፡ ቂሞቻችሁንም ያወጣል፡፡ 47|38|ንቁ! እናንተ እነዚያ በአላህ መንገድ ትለግሱ ዘንድ የምትጥጠሩ ናችሁ፡፡ ከእናንተም ውስጥ የሚሰስት ሰው አልለ፡፡ የሚሰስትም ሰው የሚሰስተው በራሱ ላይ ብቻ ነው፡፡ አላህም ከበርቴ ነው፡፡ እናንተም ድኾች ናችሁ፡፡ ብትሸሹም ሌሎችን ሕዝቦች ይለውጣል፡፡ ከዚያም (ባለመታዘዝ) ብጤዎቻችሁ አይኾኑም፡፡ 48|1|እኛ ላንተ ግልጽ የኾነን መክፈት ከፈትንልህ፡፡ 48|2|አላህ ከኃጢአትህ ያለፈውንና የሚመጣውን ላንተ ሊምር ጸጋውንም ባንተ ላይ ሊሞላ ቀጥተኛውንም መንገድ ሊመራህ (ከፈተልህ)፡፡ 48|3|አላህ ብርቱን እርዳታ ሊረዳህም (ከፈተልህ)፡፡ 48|4|እርሱ ያ በምእምናን ልቦች ውስጥ ከእምነታቸው ጋር እምነትን ይጨምሩ ዘንድ እርጋታን ያወረደ ነው፡፡ ለአላህም የሰማያትና የምድር ሰራዊቶች አልሉት፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 48|5|ምእምናንንና ምእምናትን ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ ሊያገባቸው ከነርሱም ኃጢአቶቻቸውን ሊያብስላቸው (በትግል አዘዛቸው)፡፡ ይህም ከአላህ ዘንድ የኾነ ታላቅ ማግኘት ነው፡፡ 48|6|በአላህም ክፉ ጥርጣሬን ተጠራጣሪዎቹን መናፍቃንና መናፍቃትን፣ ወንዶች አጋሪዎቻችንና ሴቶች አጋሪዎችንም ያሰቃይ ዘንድ (በትግል አዘዘ)፡፡ በእነርሱ ላይ ክፉ ከባቢ አለባቸው፡፡ በእነርሱም ላይ አላህ ተቆጣባቸው፡፡ ረገማቸውም፡፡ ለእነርሱም ገሀነምን አዘጋጀላቸው፡፡ መመለሻነትዋም ከፋች፡፡ 48|7|ለአላህም የሰማያትና የምድር ሰራዊቶች አልሉት፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 48|8|እኛ መስካሪ አብሳሪና አስፈራሪም አድርገን በእርግጥ ላክንህ፡፡ 48|9|በአላህ ልታምኑ፣ በመልክተኛውም (ልታምኑ)፣ ልትረዱትም፣ ልታከብሩትም፣ (አላህን) በጧትና ከቀትር በኋላ ልታወድሱትም (ላክነው)፡፡ 48|10|እነዚያ ቃል ኪዳን የሚጋቡህ ቃል ኪዳን የሚጋቡት አላህን ብቻ ነው፡፡ የአላህ እጅ (ኀይሉ) ከእጆቻቸው በላይ ነው፡፡ ያፈረሰም ሰው የሚያፈርሰው በነፍሱ ላይ ብቻ ነው፡፡ በእርሱ ላይ አላህን ቃል ኪዳን የተጋባበትን የሞላም ሰው ታላቅ ምንዳን በእርግጥ ይሰጠዋል፡፡ 48|11|ከአዕራብ ሰዎች እነዚያ (ከዘመቻ) ወደ ኋላ የቀሩት ለአንተ «ገንዘቦቻችንና ቤተሰቦቻችን አስቸገሩን፤ ስለዚህ ምሕረትን ለምንልን፤» ይሉሃል፡፡ በልቦቻቸው ውስጥ የሌለውን ነገር በምላሶቻቸው ይናገራሉ፡፡ (አላህ) «በእናንተ ላይ ጉዳትን ቢሻ ወይም በእናንተ መጥቀምን ቢሻ ከአላህ (ለማገድ) ለእናንተ አንዳችን የሚችል ማነው? በእውነቱ አላህ፤በምትሠሰሩት ሁሉ ውስጥ ዐዋቂ ነው» በላቸው፡፡ 48|12|ይልቁንም መልክተኛውና ምእመናኖቹ ወደ ቤተሰቦቻቸው ፈጽሞ አለመመለሳቸውን ጠረጠራችሁ፡፡ ይህም በልቦቻችሁ ውስጥ ተሸለመላችሁ፡፡ መጥፎንም መጠርጠር ጠረጠራችሁ፡፡ ጠፊዎች ሕዝቦችም ኾናችሁ፡፡ 48|13|በአላህና በመልክተኛው ያላመነም ሰው እኛ ላከሓዲዎች እሳትን አዘጋጅተናል፡፡ 48|14|የሰማያትና የምድር ንግሥናም የአላህ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው ይምራል፤ የሚሻውንም ይቀጣል፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 48|15|ወደ ዘረፋዎች ልትይዟት በኼዳችሁ ጊዜ እነዚያ ወደ ኋላ የቀሩት ሰዎች «ተዉን እንከተላችሁ» ይሏችኋል፡፡ (በዚህም) የአላህን ቃል ሊለውጡ ይፈልጋሉ፡፡ «ፈጽሞ አትከተሉንም፡፡ ይህን (ቃል) ከዚህ በፊት አላህ ብሏል» በላቸው፡፡ ይልቁንም «ትመቀኙናላችሁ» ይላሉም፡፡ በእውነት እነርሱ ጥቂትን እንጅ የማያውቁ ነበሩ፡፡ 48|16|ከአዕራቦች ወደ ኋላ ለቀሩት በላቸው፡- «የብርቱ ጭካኔ ባለቤት ወደ ኾኑ ሕዝቦች (ውጊያ) ወደ ፊት ትጥጠራላችሁ፡፡ ትጋደሏቸዋላችሁ፤ ወይም ይሰልማሉ፡፡ ብትታዘዙም አላህ መልካም ምንዳን ይሰጣችኋል፡፡ ከአሁን በፊት እንደ ሸሻችሁ ብትሸሹም አሳማሚን ቅጣት ይቀጣችኋል፡፡» 48|17|በዕውር ላይ (ከዘመቻ በመቅቱ) ኃጢአት የለበትም፡፡ በአንካሳም ላይ ኃጢአት የለበትም፡፡ በበሽተኛም ላይ ኃጢአት የለበትም፡፡ አላህንና መልክተኛውንም የሚታዘዝ ሰው ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች ያገባዋል፡፡ የሚሸሸውንም ሰው አሳማሚውን ቅጣት ይቀጣዋል፡፡ 48|18|ከምእምናኖቹ በዛፊቱ ሥር ቃል ኪዳን በሚጋቡህ ጊዜ አላህ በእርግጥ ወደደ፡፡ በልቦቻቸውም ውስጥ ያለውን ዐወቀ፡፡ በእነርሱም ላይ እርጋታን አወረደ፡፡ ቅርብ የኾነንም መክፈት መነዳቸው፡፡ 48|19|ብዙዎች ዘረፋዎችንም የሚወስዷቸው የኾኑን (መነዳቸው)፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡ 48|20|አላህ ብዙዎችን ዘረፋዎች የምትወስዷቸው የኾኑን ተስፋ አደረገላችሁ፡፡ ይህችንም ለእናንተ አስቸኮለላችሁ፡፡ ከእናንተም የሰዎችን እጆች ከለከለላችሁ፡፡ (ልታመሰግኑትና) ለምእምናንም ምልክት እንድትኾን ቀጥተኛውን መንገድ ይመራችሁም ዘንድ (ይህንን ሠራላችሁ)፡፡ 48|21|ሌላይቱንም በእርሷ ላይ ገና ያልቻላችኋትን አላህ ያወቃትን (ለእናንተ አዘጋጃት)፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 48|22|እነዚያም የካዱት (የመካ ሰዎች በሑደይቢያ) በተወጉወችሁ ኖሮ ( ለሺሺት) ጀርባዎችን ባዞሩ ነበር፡፡ ከዚያም ዘመድም ረዳትም አያገኙም፡፡ 48|23|አላህ ያችን ከዚህ በፊት በእርግጥ ያለፈችውን ልማድ ደነገገ፡፡ ለአላህም ልማድ ለውጥን አታገኝም፡፡ 48|24|እርሱም ያ በመካ ውስጥ በእነርሱ ላይ ካስቻለችሁ በኋላ እጆቻቸውን ከእናንተ ላይ እጆቻችሁንም ከእነርሱ ላይ የከለከለ ነው፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 48|25|እነርሱ እነዚያ የካዱ፣ ከተከበረው መስጊድም የከለከሏችሁ፣ መስዋእቱንም የታሰረ ሲኾን በስፍራው እንዳይደርስ (የከለከሉ) ናቸው፡፡ የማታውቋቸው የኾኑ ምእመናን ወንዶችና ምእምናት ሴቶች (ከከሓዲዎቹ ጋር) ባልነበሩ ያለ ዕውቀት እነርሱን መርገጣችሁና ከእነረሱ (በኩል) መከፋት የሚነካችሁ ባልኾነ ኖሮ (እጆቻችሁን ባላገድን ነበር) አላህ የሚሻውን ሰው በእዝነቱ ውስጥ ያገባ ዝንድ (እጆቻችሁን አገደ)፡፡ በተለዩ ኖሮ እነዚያን ከእነርሱ ውስጥ የካዱትን አሳማሚን ቅጣት በቀጣናቸው ነበር፡፡ 48|26|እነዚያ የካዱት ደራይቱን የመሀይምነቲቱን ደራ በልቦቻቸው ውስጥ ባደረጉ ጊዜ (በቀጣናቸው ነበር)፡፡ አላህም በመልክተኛው ላይና በምእምናኖቹ ላይ እርጋታውን አወረደ፡፡ መጥጠበቂያይቱንም ቃል አስያዛቸው፡፡ በእርሷም ተገቢዎች ባለቤቶችዋም ነበሩ፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 48|27|አላህ ለመልክተኛው ሕልሙን እውነተኛ ሲኾን አላህ የሻ እንደ ኾነ ጸጥተኞች ኾናችሁ ራሶቻችሁን ላጭታችሁ፣ አሳጥራችሁም የማትፈሩ ስትኾኑ የተከበረውን መስጊድ በእርግጥ ትገባላችሁ፤ ያለውን በእርግጥ እውነት አደረገለት፡፡ (ከእርቁ) ያላወቃችሁትንም ነገር ዐወቀ፡፡ ከዚህም በፊት ቅርብን መክፈት አደረገ፡፡ 48|28|እርሱ ያ መልክተኛውን በመሪ መጽሐፍና በእውነተኛ ሃይማኖት በሃይማኖት ሁሉ ላይ ሊያልቀው የላከ ነው፡፡ መስካሪም በአላህ በቃ፡፡ 48|29|የአላህ መልክተኛ ሙሐመድ እነዚያም ከእርሱ ጋር ያሉት (ወዳጆቹ) በከሓዲዎቹ ላይ ብርቱዎች በመካከላቸው አዛኞች ናቸው፡፡ አጎንባሾች፣ ሰጋጆች ኾነው ታያቸዋለህ፡፡ ከአላህ ችሮታንና ውዴታን ይፈልጋሉ፡፡ ምልክታቸው ከስግደታቸው ፈለግ ስትኾን በፊቶቻቸው ላይ ናት፡፡ ይህ በተውራት (የተነገረው) ጠባያቸው ነው፡፡ በኢንጂልም ውስጥ ምሳሌያቸው ቀንዘሉን አንደአወጣ አዝመራና፣ (ቀንዘሉ) እንዳበረታው፣ እንደወፈረምና፣ ገበሬዎቹን የሚያስደንቅ ኾኖ በአገዳዎቹ ላይ ተስተካክሎ እንደ ቆመ (አዝመራ) ነው፡፡ (ያበረታቸውና ያበዛቸው) ከሓዲዎችን በእነርሱ ሊያስቆጭ ነው፡፡ አላህም እነዚያን ያመኑትንና ከእነርሱ በጎዎችን የሠሩትን ምሕረትንና ታላቅ ምንዳን ተስፋ አድርጎላቸዋል፡፡ 49|1|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በአላህና በመልክተኛው ፊት (ነፍሶቻችሁን) አታስቀድሙ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ ሰሚ ዐዋቂ ነውና፡፡ 49|2|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ድምጾቻችሁን ከነቢዩ ድምጽ በላይ ከፍ አታድርጉ፡፡ ከፊላችሁም ለከፊሉ እንደሚጮህ በንግግር ለርሱ አትጩሁ፡፡ እናንተ የማታውቁ ስትኾኑ ሥራዎቻችሁ እንዳይበላሹ (ተከልከሉ)፡፡ 49|3|እነዚያ በአላህ መልክተኛ ዘንድ ድምጾቻቸውን ዝቅ የሚያደርጉ እነዚህ እነዚያ አላህ ልቦቻቸውን ለፍርሃት የፈተናቸው ናቸው፡፡ ለእነርሱም ምሕረትና ታላቅ ምንዳ አላቸው፡፡ 49|4|እነዚያ ከክፍሎቹ ውጭ ኾነው የሚጠሩህ አብዛኞቻቸው አያውቁም፡፡ 49|5|ወደእነርሱም እስክትወጣ ድረስ እነርሱ በታገሱ ኖሮ ለእነርሱ በላጭ በኾነ ነበር፡፡ አላህም እጅግ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 49|6|እላንተ ያመናችሁ ሆይ! ነገረኛ ወሬን ቢያመጣላችሁ በስህተት ላይ ኾናችሁ ሕዝቦችን እንዳትጎዱና በሠራችሁት ነገር ላይ ተጸጸቾች እንዳትኾኑ አረጋግጡ፡፡ 49|7|በውስጣችሁም የአላህ መልክተኛ መኖሩን ዕወቁ፡፡ ከነገሩ በብዙው ቢከተላችሁ ኖሮ በእርግጥ በተቸገራችሁ ነበር፡፡ ግን አላህ አምነትን ወደናንተ አስወደደ፡፡ በልቦቻችሁም ውሰጥ አጌጠው፡፡ ክህደትንና አመጽንም እንቢተኛነትንም ወደናንተ የተጠላ አደረገ፡፡ እነዚያ (እምነትን የወደዱና ክሕደተን የጠሉ) እነርሱ ቅኖቹ ናቸው፡፡ 49|8|ከአላህ በኾነው ችሮታና ጸጋ (ቅኖች ናቸው)፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 49|9|ከምዕምናንም የኾኑ ሁለት ጭፍሮች ቢጋደሉ በመካከላቸው አስታርቁ፡፡ ከሁለቱ አንደኛይቱም በሌላይቱ ላይ ወሰን ብታልፍ ያችን ወሰን የምታልፈውን ወደ አላህ ትዕዛዝ እስከምትመለስ ድረስ ተጋደሉ፡፡ ብትመለስም በመካከላቸው በትክክል አስታርቁ፡፡ በነገሩ ሁሉ አስተካክሉም፡፡ አላህ አስተካካዮችን ይወዳልና፡፡ 49|10|ምእመናኖች ወንድማመቾች ናቸው፡፡ በሁለት ወንድሞቻችሁም መካከል አስታርቁ፡፡ ይታዘንላችሁም ዘንድ አላህን ፍሩ፡፡ 49|11|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ወንዶች ከወንዶች አይቀልዱ፡፡ ከእነርሱ የበለጡ ሊኾኑ ይከጀላልና፡፡ ሴቶችም ከሴቶች (አይሳለቁ)፡፡ ከእነርሱ የበለጡ ሊኾኑ ይከጀላልና፡፡ ነፍሶቻችሁንም አታነውሩ፡፡ በመጥፎ ስሞችም አትጠራሩ፡፡ ከእምነት በኋላ የማመጽ ስም ከፋ፡፡ ያልተጸጸተም ሰው እነዚያ እነርሱ በዳዮቹ ናቸው፡፡ 49|12|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከጥርጣሬ ብዙውን ራቁ፤ ከጥርጣሬ ከፊሉ ኃጢአት ነውና፡፡ ነውርንም አትከታተሉ፡፡ ከፊላችሁም ከፊሉን አይማ፡፡ አንደኛችሁ የወንድሙን ስጋ የሞተ ኾኖ ሊበላው ይወዳልን? (መብላቱን) ጠላችሁትም፤ (ሐሜቱንም ጥሉት)፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ነውና፡፡ 49|13|እናንተ ሰዎች ሆይ! እኛ ከወንድና ከሴት ፈጠርናችሁ፡፡ እንድትተዋወቁም ጎሳዎችና ነገዶች አደረግናችሁ፡፡ አላህ ዘንድ በላጫችሁ በጣም አላህን ፈሪያችሁ ነው፡፡ አላህ ግልጽን ዐዋቂ ውስጥንም ዐዋቂ ነው፡፡ 49|14|የዐረብ ዘላኖች «አምነናል» አሉ፡፡ «አላመናችሁም፤ ግን ሰልመናል በሉ፡፡ «እምነቱም በልቦቻችሁ ውስጥ ገና (ጠልቆ) አልገባም፡፡ አላህንና መልክተኛውንም ብትታዘዙ ከሥራዎቻችሁ ምንንም አያጎድልባችሁም፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና» በላቸው፡፡ 49|15|(እውነተኛዎቹ) ምእምናን እነዚያ በአላህና በመልእከተኛው ያመኑት ከዚያም ያልተጠራጠሩት በገንዘቦቻቸውና በነፍሶ ቻቸውም በአላህ መንገድ የታገሉት ብቻ ናቸው፡፡ እነዚያ እነሱ እውነተኞቹ ናቸው፡፡ 49|16|«አላህ በሰማያት ውስጥ ያለውንና በምድር ውስጥ ያለውን ሁሉ የሚያውቅ ሲኾን አላህን በሃይማኖታችሁ ታስታውቁ ታላችሁን?» በላቸው፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 49|17|በመስለማቸው በአንተ ላይ ይመጻደቃሉ «በስልምናችሁ በኔ ላይ አትመጻደቁ፤ ይልቁንም አላህ ወደ እምነት ስለ መራችሁ ይመጸደቅባችኋል፤ እውነተኞች ብትኾኑ» (መመጻደቅ ለአላህ ነው) በላቸው፡፡ 49|18|አላህ የሰማያትንና የምድርን ሩቅ ምሰጢር ያውቃል፤ አላህም የምትሰሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 50|1|ቀ (ቃፍ) በተከበረው ቁርኣን እምላለሁ (በሙሐመድ አላመኑም)፡፡ 50|2|ይልቁንም ከነሱ ጎሳ የኾነ አስፈራሪ ስለ መጣላቸው ተደነቁ፡፡ ከሓዲዎቹም «ይህ አስደናቂ ነገር ነው» አሉ፡፡ 50|3|«በሞትንና ዐፈር በኾን ጊዜ (እንመለሳለን?) ይህ ሩቅ የኾነ መመለስ ነው፤» (አሉ)፡፡ 50|4|ከእነርሱ (አካል) ምድር የምታጎድለውን በእርግጥ ዐውቀናል፡፡ እኛም ዘንድ ጠባቂ መጽሐፍ አልለ፡፡ 50|5|(አልተመለከቱም)፡፡ ይልቁንም በቁርኣን በመጣላቸው ጊዜ አስተባበሉ፡፡ እነርሱም በተማታ ነገር ውሰጥ ናቸው፡፡ 50|6|ወደ ሰማይም ከበላያቸው ስትኾን ለእርሷ ምንም ቀዳዳዎች የሌሏት ኾና እንዴት እንደ ገነባናትና (በከዋክብት) እንዳጌጥናት አልተመለከቱምን? 50|7|ምድርንም ዘረጋናት፡፡ በእርሷም ውስጥ ጋራዎችን ጣልንባት፡፡ በውስጧም ከሚያስደስት ዓይነት ሁሉ አበቀልን፡፡ 50|8|(ይህንን ያደረግነው) ተመላሽ ለኾነ ባሪያ ሁሉ ለማሳየትና ለማስገንዘብ ነው፡፡ 50|9|ከሰማይም ብሩክን ውሃ አወረድን፡፡ በእርሱም አትክልቶችንና የሚታጨድን (አዝመራ) ፍሬ አበቀልን፡፡ 50|10|ዘምባባንም ረዣዢም ለእርሷ የተደራረበ እንቡጥ ያላት ስትኾን (አበቀልን)፡፡ 50|11|ለባሮቹ ሲሳይ ትኾን ዘንድ (አዘጋጀናት)፡፡ በእርሱም የሞተችን አገር ሕያው አደረግንበት፡፡ (ከመቃብር) መውጣትም እንደዚሁ ነው፡፡ 50|12|ከእነርሱ በፊት የኑሕ ሕዝቦችና የረሰስ ሰዎች፤ ሰሙድም አስተባበሉ፡፡ 50|13|ዓድም ፈርዖንም፤ የሉጥ ወንድሞችም፤ 50|14|የአይከት ሰዎችም የቱብበዕ ሕዝቦችም ሁሉም መልከተኞቹን አስተባበሉ፡፡ ዛቻዬም ተረጋገጠባቸው፡፡ 50|15|በፊተኛው መፍጠር ደከምን? በእውነቱ እነርሱ ከአዲስ መፍጠር በመጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ 50|16|ሰውንም ነፍሱ (በሐሳቡ) የምታጫውተውን የምናውቅ ስንኾን በእርግጥ ፈጠርነው፤ እኛም ከደም ጋኑ ጅማት ይበልጥ ወደርሱ ቅርብ ነን፡፡ 50|17|ሁለቱ ቃል ተቀባዮች (መላእክት) ከቀኝና ከግራ ተቀማጮች ኾነው በሚቀበሉ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ 50|18|ከቃል ምንም አይናገርም በአጠገቡ ተጠባባቂና ዝግጁ የኾኑ (መላእክት) ያሉበት ቢኾን እንጅ፡፡ 50|19|የሞትም መከራ እውነቱን ነገር ታመጣለች፡፡ (ሰው ሆይ)፡- «ይህ ያ ከርሱ ትሸሸው የነበርከው ነው» (ይባላል)፡፡ 50|20|በቀንዱም ውስጥ ይንነፋል፡፡ ያ (ቀን) የዛቻው (መፈጸሚያ) ቀን ነው፡፡ 50|21|ነፍስም ሁሉ ከእርሷ ጋር ነጂና መስካሪ ያለባት ኾና ትመጣለች፡፡ 50|22|«ከዚህ ነገር በእርግጥ በዝንጋቴ ውስጥ ነበርክ፡፡ ሺፋንህንም ካንተ ላይ ገለጥንልህ፡፡ ስለዚህ ዛሬ ዓይንህ ስለታም ነው» (ይባላል)፡፡ 50|23|ቁራኛውም (መልአክ) «ይህ ያ እኔ ዘንድ ያለው ቀራቢ ነው» ይላል፡፡ 50|24|«ሞገደኛ ከሓዲን ሁሉ በገሀነም ውስጥ ጣሉ፡፡» 50|25|«ለበጎ ሥራ ከልካይ፣ በዳይ፣ ተጠራጣሪ የኾነን ሁሉ፤» (ጣሉ)፡፡ 50|26|«ያንን ከአላህ ጋር ሌላን አምላክ ያደረገውን በብርቱ ቅጣት ውስጥ ጣሉት፤» (ይባላል)፡፡ 50|27|ቁራኛው (ሰይጣን) «ጌታችን ሆይ! እኔ አላሳሳትኩትም፡፡ ግን (ራሱ) በሩቅ ስሕተት ውስጥ ነበር» ይላል፡፡ 50|28|(አላህ) «ወደእናንተ ዛቻን በእርግጥ ያስቀደምኩ ስኾን እኔ ዘንድ አትጨቃጨቁ» ይላቸዋል፡፡ 50|29|«ቃሉ እኔ ዘንድ አይለወጥም፡፡ እኔም ለባሮቼ ፈጽሞ በዳይ አይደለሁም» (ይላቸዋል)፡፡ 50|30|ለገሀነም «ሞላሽን? የምንልበትንና ጭማሪ አለን? የምትልበትን ቀን» (አስጠንቅቃቸው)፡፡ 50|31|ገነትም አላህን ለፈሩት እሩቅ ባልኾነ ስፍራ ትቅቀረባለች፡፡ 50|32|«ይህ ወደ አላህ ተመላሽና (ሕግጋቱን) ጠባቂ ለኾነ ሁሉ የተቀጠራችሁት ነው» (ይባላሉ)፡፡ 50|33|«አልረሕማንን በሩቁ ኾኖ ለፈራና በንጹሕ ልብ ለመጣ» (ትቅቀረባለች)፡፡ 50|34|«በሰላም ግቧት ይህ የመዘውተሪያ ቀን ነው» (ይባላሉ)፡፡ 50|35|ለነርሱ በውስጧ ሲኾኑ የሚሹት ሁሉ አልላቸው፡፡ እኛም ዘንድ ጭማሪ አልለ፡፡ 50|36|ከእነርሱም (ከቁረይሾች) በፊት ከክፍለ ዘመናት ሕዝቦች ብዙዎችን እነርሱ በኀያልነት ከእነርሱ ይበልጥ የበረቱ የኾኑትን (ማምለጫ ፍለጋ) በየአገሮቹም የመረመሩትን አጥፍተናል፡፡ ማምለጫ አለን? 50|37|በዚህ ውሰጥ ለእርሱ ልብ ላለው ወይም እርሱ (በልቡ) የተጣደ ኾኖ (ወደሚነበብለት) ጆሮውን ለጣለ ሰው ግሳጼ አለበት፡፡ 50|38|ሰማያትንና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ በስድስት ቀናት ውስጥ በእርግጥ ፈጠርን፡፡ ድካምም ምንም አልነካንም፡፡ 50|39|በሚሉትም ላይ ታገሥ፤ ጌታህንም ከማመስገን ጋር ፀሐይ ከመውጣቷ በፊት ከመግባቷም በፊት አወድሰው፡፡ 50|40|ከሌሊቱም አወድሰው ከስግደቶችም በኋላዎች (አወድሰው)፡፡ 50|41|(የሚነገርህን) አዳምጥም፡፡ ጠሪው ከቅርብ ስፍራ በሚጠራበት ቀን (ከመቃብራቸው ይወጣሉ)፡፡ 50|42|ጩኸቲቱን በእውነት የሚሰሙበት ቀን ያ (ከመቃብር) የመውጫው ቀን ነው፡፡ 50|43|እኛ እኛው ሕያው እናደርጋለን፡፡ እንገድላለንም፡፡ መመለሻም ወደእኛ ብቻ ነው፡፡ 50|44|የሚፈጥኑ ኾነው ምድር ከእነርሱ ላይ የምትሰነጣጠቅበት ቀን (የመውጫው ቀን ነው)፡፡ ይህ በእኛ ላይ ገር የኾነ መሰብሰብ ነው፡፡ 50|45|እኛ የሚሉትን ሁሉ ዐዋቂ ነን፡፡ አንተም በእነርሱ ላይ አስገዳጅ አይደለህም፡፡ ስለዚህ ዛቻየን የሚፈራን ሰው በቁርኣን አስታውስ፡፡ 51|1|መበተንን በታኞች በኾኑት (ነፋሶች)፡፡ 51|2|ከባድ (ዝናምን) ተሸካሚዎች በኾኑትም (ደመናዎች)፡፡ 51|3|ገር (መንሻለልን) ተንሻላዮች በኾኑትም (መርከቦች)፡፡ 51|4|ነገርን ሁሉ አከፋፋዮች በኾኑትም (መላእክት) እምላለሁ፡፡ 51|5|የምትቀጠሩት (ትንሣኤ) እውነት ነው፡፡ 51|6|(እንደየሥራው) ዋጋን ማግኘትም፤ ኋኝ ነው፤ (የማይቀር ነው)፡፡ 51|7|የ(ከዋክብት) መንገዶች ባለቤት በኾነችው ሰማይ እምላለሁ፡፡ 51|8|እናንተ (የመካ ሰዎች) በተለያየ ቃል ውስጥ ናችሁ፡፡ 51|9|ከርሱ የሚዝዞር ሰው ይዝዞራል፡፡ 51|10|በግምት የሚናገሩ ውሸታሞች ተረገሙ፡፡ 51|11|እነዚያ እነርሱ በሚሸፍን ስሕተተ ውስጥ ዘንጊዎች የኾኑት፡፡ 51|12|የዋጋ መስጫው ቀን መቼ እንደ ኾነ ይጠይቃሉ፡፡ 51|13|(እነርሱ) በእሳት ላይ በሚፈተኑበት ቀን ነው፡፡ 51|14|«መከራችሁን ቅመሱ፤ ይህ ያ በእርሱ ትቻኮሉበት የነበራችሁት ነው» (ይባላሉ)፡፡ 51|15|አላህን ፈሪዎቹ በአትክልቶችና በምንጮች ውስጥ ናቸው፡፡ 51|16|ያንን ጌታቸው የሰጣቸውን ተቀባዮች ኾነው፤ (በገነት ውስጥ ይኾናሉ)፡፡ እነርሱ ከዚህ በፊት መልካም ሰሪዎች ነበሩና፡፡ 51|17|ከሌሊቱ ጥቂትን ብቻ ይተኙ ነበሩ፡፡ 51|18|በሌሊቱ መጨረሻዎችም እነርሱ ምሕረትን ይለምናሉ፡፡ 51|19|በገንዘቦቻቸውም ውስጥ ለለማኝና (ከልመና) ለተከለከለም (በችሮታቸው) መብት አልለ፡፡ 51|20|በምድርም ውስጥ ለሚያረጋግጡ ሰዎች ምልክቶች አልሉ፡፡ 51|21|በነፍሶቻችሁም ውስጥ (ምልክቶች አልሉ)፤ ታዲያ አትመለከቱምን?› 51|22|ሲሳያችሁም የምትቀጠሩትም (ፍዳና ምንዳ) በሰማይ ውስጥ ነው፡፡ 51|23|በሰማይና በምድር ጌታም እምላለሁ፡፡ እርሱ እናንተ እንደምትናገሩት ብጤ እርግጠኛ ነው፡፡ 51|24|የተከበሩት የኢብራሂም እንግዶች ወሬ መጥቶሃልን? 51|25|በእርሱ ላይ በገቡና «ሰለም» ባሉ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ «ሰላም ያልታወቃችሁ ሕዝቦች ናችሁ፤» አላቸው፡፡ 51|26|ወደ ቤተሰቡም ተዘነበለ፤» ወዲያውም የሰባ ወይፈንን አመጣ፡፡ 51|27|ወደእነርሱም (አርዶና ጠብሶ) አቀረበው፡፡ «አትበሉም ወይ?» አላቸው፡፡ 51|28|ከእነርሱ መፍራትንም በልቡ አሳደረ፡፡ «አትፍራ» አሉት፡፡ በዐዋቂ ወጣት ልጅም አበሰሩት፡፡ 51|29|ሚስቱም እየጮኸች መጣች፡፡ ፊቷንም መታች፡፡ «መካን አሮጊት ነኝ» አለችም፡፡ 51|30|እንደዚህ ጌታሽ ብሏል፡፡ «እነሆ እርሱ ጥበባ ዐዋቂ ነውና» አሏት፡፡ 51|31|«እናንተ መልክተኞች ሆይ! ታዲያ ነገራችሁ ምንድን ነው?» አላቸው፡፡ 51|32|(እነርሱም) አሉ፡- «እኛ ወደ አመጸኞች ሕዝቦች ተልከናል፡፡» 51|33|በእነርሱ ላይ ከጭቃ የኾኑን ድንጋዮች ልንለቅባቸው (ተላክን)፡፡ 51|34|በጌታህ ዘንድ ለድንበር አላፊዎቹ (በየስማቸው) ምልክት የተደረገባት ስትኾን፡፡ 51|35|ከምእምናንም፤ በእርሷ (በከተማቸው) ውስጥ የነበሩትን አወጣን፡፡ 51|36|በውስጧም ከሙስሊሞች ከአንድ ቤት (ቤተሰቦች) በስተቀር አላገኘንም፡፡ 51|37|በውስጧም ለእነዚያ አሳማሚውን ቅጣት ለሚፈሩት ምልክትን አስቀረን፡፡ 51|38|በሙሳም (ወሬ) ውስጥ ወደ ፈርዖን በግልጽ ማስረጃ በላክነው ጊዜ (ምልክትን አደረግን)፡፡ 51|39|ከድጋፉ (ከሰራዊቱ) ጋርም (ከእምነት) ዞረ፡፡ (እርሱ) «ድግምተኛ ወይም ዕብድ ነው» አለም፡፡ 51|40|እርሱንም ሰራዊቱንም ያዝናቸው፡፡ እርሱ ተወቃሽ ሲኾን በባሕር ውስጥም ጣልናቸው፡፡ 51|41|በዓድም በእነርሱ ላይ መካንን ነፋስ በላክን ጊዜ (ምልክት አልለ)፡፡ 51|42|በላዩ ላይ የመጣችበትን ማንኛውንም ነገር እንደ በሰበሰ አጥንት ያደረገችው ብትኾን እንጂ አትተወውም፡፡ 51|43|በሰሙድም ለእነርሱ «እስከ ጊዜ (ሞታችሁ) ድረስ ተጣቀሙ» በተባሉ ጊዜ (ምልክት አልለ)፡፡ 51|44|ከጌታቸው ትዕዛዝም ኮሩ፡፡ እነርሱም እያዩ ጩኸት ያዘቻቸው፡፡ 51|45|መቆምንም ምንም አልቻሉም፡፡ የሚርረዱም አልነበሩም፡፡ 51|46|የኑሕንም ሕዝቦች ከዚህ በፊት (አጠፋን)፡፡ እነርሱ አመጸኞች ሕዝቦች ነበሩና፡፡ 51|47|ሰማይንም በኀይል ገነባናት፡፡ እኛም በእርግጥ ቻዮች ነን፡፡ 51|48|ምድርንም ዘረጋናት፡፡ ምን ያማርንም ዘርጊዎች (ነን!) 51|49|ትገነዘቡም ዘንድ ከነገሩ ሁሉ ሁለት (ተቃራኒ) ዓይነትን ፈጠርን፡፡ 51|50|«ወደ አላህም ሽሹ፤ እኔ ለእናንተ ከርሱ ግልጽ አስጠንቃቂ ነኝና» (በላቸው)፡፡ 51|51|ከአላህም ጋር ሌላን አምላክ አታድርጉ፡፡ እኔ ለእናንተ ከእርሱ (የተላክሁ) ግልጽ አስፈራሪ ነኝና፡፡ 51|52|(ነገሩ) እንደዚሁ ነው፡፡ እነዚያን ከእነርሱ በፊት የነበሩትን ከመልክተኛ ማንም አልመጣቸውም፡፡ (እርሱ) «ድግምተኛ ወይም ዕብድ ነው» ያሉ ቢኾኑ እንጂ፡፡ 51|53|በእርሱ (በዚህ ቃል) አደራ ተባብለዋልን? አይደለም፤ እነርሱ ጥጋበኞች ሕዝቦች ናቸው፡፡ 51|54|ከእነርሱም (ክርክር) ዘወር በል፤ (ተዋቸው)፡፡ አንተ ምንም ተወቃሽ አይደለህምና፡፡ 51|55|ገሥጽም፤ ግሣጼ ምእመናንን ትጠቅማለችና፡፡ 51|56|ጋኔንንና ሰውንም ሊግገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም፡፡ 51|57|ከነርሱም ምንም ሲሳይ አልፈልግም፡፡ ሊመግቡኝም አልሻም፡፡ 51|58|አላህ እርሱ ሲሳይን ሰጪ የብርቱ ኀይል ባለቤት ነው፡፡ 51|59|ለእነዚያም ለበደሉት እንደ ጓደኞቻቸው ፋንታ ብጤ (የቅጣት) ፋንታ አልላቸው፡፡ ስለዚህ አያስቸኩሉኝ፡፡ 51|60|ለነዚያም ለካዱት ከዚያ ከሚቀጠሩት ቀናቸው ወዮላቸው፡ 52|1|በጡር (ጋራ) እምላለሁ፡፡ 52|2|በተጻፈው መጽሐፍም፡፡ 52|3|በተዘረጋ ብራና ላይ፤ (በተጻፈው)፡፡ 52|4|በደመቀው ቤትም፡፡ 52|5|ከፍ በተደረገው ጣራም፡፡ 52|6|በተመላው ባሕርም እምላለሁ፡፡ 52|7|የጌታህ ቅጣት በእርግጥ ወዳቂ ነው፤ (የማይቀር ነው)፡፡ 52|8|ለእርሱ ምንም ገፍታሪ የለውም፡፡ 52|9|ሰማይ ብርቱ መዞርን በምትዞርበት ቀን (ይኾናል)፡፡ 52|10|ተራራዎችም መኼድን በሚኼዱበት (ቀን)፡፡ 52|11|ለአስተባባዮችም ያን ጊዜ ወዮላቸው፡፡ 52|12|ለእነዚያ እነርሱ በውሸት ውስጥ የሚጫወቱ ለኾኑት፡፡ 52|13|ወደ ገሀነም እሳት በኀይል መግገፍተርን በሚግገፈተሩበት ቀን፡፡ 52|14|ይህቺ ያቺ በእርሷ ታስተባብሉባት የነበራችሁት እሳት ናት፡፡ 52|15|ይህ (ፊት ትሉ እንደነበራችሁት) ድግምት ነውን? ወይስ እናንተ አታዩምን? 52|16|ግቧት ታገሱም ወይም አትታገሡ በእናንተ ላይ እኩል ነው፡፡ የምትምመነዱት ትሠሩት የነበራችሁትን (ፍዳ) ብቻ ነው (ይባላሉ)፡፡ 52|17|አላህን ፈሪዎቹ በእርግጥ በገነቶችና በጸጋ ውስጥ ናቸው፡፡ 52|18|ጌታቸው በሰጣቸው ጸጋ ተደሳቾች ኾነው (በገነት ውስጥ ናቸው)፡፡ የገሀነምንም ስቃይ ጌታቸው ጠበቃቸው፡፡ 52|19|«ትሠሩት በነበራችሁት ምክንያት ተደሳቾች ኾናችሁ ብሉ፤ ጠጡም፤» (ይባላሉ)፡፡ 52|20|በተደረደሩ አልጋዎች ላይ ተደጋፊዎች ኾነው (በገነት ይኖራሉ)፡፡ ዓይናማዎች በኾኑ ነጫጭ ሴቶችም እናጠናዳቸዋለን፡፡ 52|21|እነዚያም ያመኑትና ዝርያቸውም በእምነት የተከተለቻቸው ዝርያቸውን በእነርሱ እናስጠጋለን፡፡ ከሥራቸውም ምንም አናጎድልባቸውም፡፡ ሰው ሁሉ በሠራው ሥራ ተያዢ ነው፡፡ 52|22|ከሚሹትም ሁሉ እሸትንና ስጋን እንጨምርላቸዋለን፡፡ 52|23|በውስጧ መጠጥን ይሰጣጣሉ፡፡ በውስጧ ውድቅ ንግግርና መውወንጀልም የለም፡፡ 52|24|ለነርሱም የኾኑ ወጣቶች ልክ የተሸፈነ ሉል መስለው በእነርሱ ላይ (ለማሳለፍ) ይዘዋወራሉ፡፡ 52|25|የሚጠያየቁ ኾነውም ከፊላቸው በከፊሉ ላይ ይዞራል፡፡ 52|26|«እኛ ፊት በቤተሰቦቻችን ውስጥ (ከቅጣት) ፈሪዎች ነበርን» ይላሉ፡፡ 52|27|«አላህም በእኛ ላይ ለገሰ፡፡ የመርዛም እሳት ቅጣትንም ጠበቀን፡፡ 52|28|«እኛ ከዚህ በፊት እንለምነው ነበርን፡፡ እነሆ እርሱ በጎ ዋይ አዛኝ ነውና» (ይላሉ)፡፡ 52|29|(ሰዎችን) አስታውስም፡፡ አንተም በጌታህ ጸጋ ምክንያት ጠንቋይም ዕብድም አይደለህም፡፡ 52|30|ይልቁንም የሞትን አደጋ በእርሱ የምንጠባበቅበት የኾነ ባለ ቅኔ ነው ይላሉን? 52|31|«ተጠባበቁ፤ እኔም ከእናንተ ጋር ከሚጠባበቁት ነኝ» በላቸው፡፡ 52|32|አእምሮዎቻቸው በዚህ ያዟቸዋልን? አይደለም በእውነቱ እነርሱ ወሰን አላፊዎች ሕዝቦች ናቸው፡፡ 52|33|ወይም «ቀጠፈው ይላሉን?» አይደለም፤ በእውነቱ አያምኑም፡፡ 52|34|እውነተኞችም ቢኾኑ መሰሉ የኾነን ንግግር ያምጡ፡፡ 52|35|ወይስ ያለ አንዳች (ፈጣሪ) ተፈጠሩን? ወይስ እነርሱ ፈጣሪዎች ናቸውን? 52|36|ወይስ ሰማያትንና ምድርን ፈጠሩን? አይደለም አያረጋግጡም፡፡ 52|37|ወይስ የጌታህ ግምጃ ቤቶች እነርሱ ዘንድ ናቸውን? ወይስ እነርሱ አሸናፊዎች ናቸውን? 52|38|ወይስ ለእነርሱ በእርሱ ላይ (ከሰማይ) የሚያዳምጡበት መሰላል አላቸውን? አድማጫቸውም (ሰማሁ ቢል) ግልጽን አስረጅ ያምጣ፡፡ 52|39|ወይስ ለእርሱ ሴቶች ልጆች አሉትን? ለእናንተም ወንዶች ልጆች አሏችሁን? 52|40|ወይስ ዋጋን ትጠይቃቸዋለህን? ስለዚህ እነርሱ ከዕዳው የተከበዱ ናቸውን? 52|41|ወይስ ሩቁ ምስጢር እነርሱ ዘንድ ነውን? ስለዚህ እነርሱ ይጽፋሉን? 52|42|ወይስ ተንኮልን (ባንተ) ይሻሉን? እነዚያም የካዱት እነርሱ በተንኮል ተሸናፊዎች ናቸው፡፡ 52|43|ወይስ ለእነርሱ ከአላህ ሌላ አምላክ አላቸውን? አላህ ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ፡፡ 52|44|ከሰማይም ቁራጭን (በእነርሱ ላይ) ወዳቂ ኾኖ ቢያዩ ኖሮ «ይህ የተደራረበ ደመና ነው» ይሉ ነበር፡፡ 52|45|ያንንም በእርሱ የሚግገደሉበትን ቀናቸውን እስከሚገናኙ ድረስ ተዋቸው፡፡ 52|46|ተንኮላቸው ከእነርሱ ምንንም የማይጠቅማቸውንና እነርሱም የማይርረዱበትን ቀን (እስከ ሚገናኙ ተዋቸው)፡፡ 52|47|ለእነዚያ ለበደሉትም ከዚህ ሌላ ቅርብ ቅጣት አልላቸው፡፡ ግን አብዛኛዎቻቸው አያውቁም፡፡ 52|48|ለጌታህ ፍርድም ታገሥ፡፡ አንተ በጥበቃችን ውስጥ ነህና፡፡ ጌታህንም በምትነሳ ጊዜ ከማመስገን ጋር አወድሰው፡፡ 52|49|ከሌሊቱም አወድሰው፡፡ በከዋክብት መዳበቂያ ጊዜም (ንጋት ላይ አወድሰው)፡፡ 53|1|በኮከብ እምላለሁ በወደቀ (በገባ) ጊዜ፡፡ 53|2|ነቢያችሁ (ሙሐመድ) አልተሳሳተም፤ አልጠመመምም፡፡ 53|3|ከልብ ወለድም አይናገርም፡፡ 53|4|እርሱ (ንግግሩ) የሚወርረድ ራእይ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ 53|5|ኀይሎቹ ብርቱው (መልአክ) አስተማረው፡፡ 53|6|የዕውቀት ባለቤት የኾነው (አስተማረው፤ በተፈጥሮ ቅርጹ ኾኖ በአየር ላይ) ተደላደለም፡፡ 53|7|እርሱ በላይኛው አድማስ ኾኖ፡፡ 53|8|ከዚያም ቀረበ፤ ወረደም፡፡ 53|9|(ከእርሱ) የሁለት ደጋኖች ጫፍ ያህል ወይም (ከዚህ) ይበልጥ የቀረበ ኾነም፡፡ 53|10|ወደ ባሪያውም (አላህ) ያወረደውን አወረደ፡፡ 53|11|(ነቢዩም በዓይኑ) ያየውን ልቡ አልዋሸም፡፡ 53|12|ታዲያ በሚያየው ላይ ትከራከሩታላችሁን? 53|13|በሌላይቱም መውረድ ጊዜ በእርግጥ አይቶታል፡፡ 53|14|በመጨረሻይቱ ቁርቁራ አጠገብ፤ 53|15|እርሷ ዘንድ መኖሪያይቱ ገነት ያለች ስትኾን፡፡ 53|16|ቁርቁራይቱን የሚሸፍን ነገር በሚሸፍናት ጊዜ (አየው)፡፡ 53|17|ዓይኑ (ካየው) አልተዘነበለም፡፡ ወሰንም አላለፈም፡፡ 53|18|ከጌታው ታምራቶች ታላላቆቹን በእርግጥ አየ፡፡ 53|19|አል-ላትንና አል-ዑዛን አያችሁን? 53|20|ሦስተኛይቱንም አነስተኛዋን መናትን (አያችሁን? የምትግገዟቸው ኃይል አላቸውን?) 53|21|ለእናንተ ወንድ ለእርሱም ሴት (ልጅ) ይኖራልን? 53|22|ይህቺ ያን ጊዜ አድላዊ ክፍያ ናት፡፡ 53|23|እነርሱ እናንተና አባቶቻችሁ (አማልክት ብላችሁ) የጠራችኋቸው ስሞች ብቻ እንጅ ምንም አይደሉም፡፡ አላህ በእርሷ (መግገዛት) ምንም ማስረጃ አላወረደም፡፡ ከጌታቸውም መምሪያ የመጣላቸው ሲኾኑ ጥርጣሬንና ነፍሶች የሚዘነበሉበትን እንጅ ሌላ አይከተሉም፡፡ 53|24|ለሰው የተመኘው ሁሉ አለውን? 53|25|መጨረሻይቱም መጀመሪያይቱም (ዓለም) የአላህ ብቻ ናቸው፡፡ 53|26|በሰማያት ውስጥ ካለ መልአክም ብዙዎች (ሊማለዱለት) ለሚሻውና ለሚወደው ሰው ከፈቀደ በኋላ ቢኾን እንጅ ምልጃቸው ምንም አትጠቅምም፡፡ 53|27|እነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት መላእክትን በሴት አጠራር ይጠራሉ፡፡ 53|28|ለእነርሱም በእርሱ ምንም ዕውቀት የላቸውም፡፡ ጥርጣሬን እንጅ ሌላን አይከተሉም፡፡ ጥርጣሬም ከእውነት ምንም አያብቃቃም፡፡ 53|29|ከግሣጼያችንም (ከቁርኣን) ከሸሸና አነስተኛይቱን ሕይወት እንጅ ሌላን ከማይሻ ሰው ዙር (ተወው)፡፡ 53|30|ይህ (አነስተኛይቱን ሕይወት መምረጥ) ከዕውቀት ድካቸው ነው፡፡ ጌታህ እርሱ ከመንገዱ የተሳሳተውን በእርግጥ ዐዋቂ ነው፡፡ እርሱም የቀናውን ሰው ዐዋቂ ነው፡፡ 53|31|በሰማያት ያለውና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ እነዚያን ያጠፉትን በሠሩት ሊቀጣ እነዚያን ያሳመሩትንም በመልካሚቱ (ገነት) ሊመነዳ (የጠመመውንና የቀናውን ያውቃል)፡፡ 53|32|(እነርሱ) እነዚያ የኃጢኣትን ታላለቆችና አስጸያፊዎቹን የሚርቁ ናቸው፡፡ ግን ትናንሾቹ የሚማሩ ናቸው፡፡ ጌታህ ምሕረተ ሰፊ ነውና፡፡ ከምድር በፈጠራችሁ ጊዜ እናንተም በእናቶቻችሁ ሆዶች ውስጥ ሽሎች በኾናችሁ ጊዜ እርሱ በናንተ (ኹነታ) ዐዋቂ ነው፡፡ ነፍሶቻችሁንም አታወድሱ እርሱ የሚፈራውን ሰው ዐዋቂ ነው፡፡ 53|33|ያንን (ከእምነት) የዞረውን አየህን? 53|34|ጥቂትን የሰጠውንና ያቋረጠውንም (አየህን?) 53|35|የሩቁ ምስጢር ዕውቀት እርሱ ዘንድ አልለን? ስለዚህ እርሱ ያያልን? 53|36|ይልቁንም በዚያ በሙሳ ጽሑፎች ውስጥ ባለው ነገር አልተነገረምን? 53|37|በዚያም (የታዘዘውን) በፈጸመው በኢብራሂም (ጽሑፎች ውስጥ ባለው አልተነገረምን?) 53|38|(እርሱም ኃጢያት) ተሸካሚ ነፍስ የሌላይቱን ነፍስ ኃጢኣት አትሸከምም፡፡ 53|39|ለሰውም ሁሉ የሠራው እንጅ ሌላ የለውም፡፡ 53|40|ሥራውም ሁሉ ወደ ፊት ይታያል፡፡ 53|41|ከዚያም ሙሉውን ምንዳ ይመነዳዋል፡፡ 53|42|መጨረሻውም ወደ ጌታህ ብቻ ነው፡፡ 53|43|እነሆ እርሱም አስሳቀ፣ አስለቀሰም፡፡ 53|44|እነሆ እርሱም ገደለ፣ አስነሳም፡፡ 53|45|እርሱም ሁለቱን ዓይነቶች ወንድንና ሴትን ፈጠረ፡፡ 53|46|ከፍትወት ጠብታ (በማህጸን ውስጥ) በምትፈሰስ ጊዜ፡፡ 53|47|የኋለኛይቱም ማስነሳት በእርሱ ላይ ነው፡፡ 53|48|እነሆ እርሱም አከበረ፣ ጥሪተኛም አደረገ፡፡ 53|49|እነሆ እርሱም የሺዕራ ጌታ ነው፡፡ 53|50|እነሆ እርሱም የፊተኛይቱን ዓድ አጥፍቷል፡፡ 53|51|ሰሙድንም (አጥፍቷል)፤ አላስቀረምም፡፡ 53|52|በፊትም የኑሕን ሕዝቦች (አጥፍቷል)፡፡ እነርሱ በጣም በደለኞችና እጅግ የጠመሙ እነርሱ ነበሩና፡፡ 53|53|የተገለበጠችውንም ከተማ ደፋ፡፡ 53|54|ያለበሳትንም አለበሳት፡፡ 53|55|ከጌታህም ጸጋዎች በየትኛው ትጠራጠራለህ? 53|56|ይህ ከፊተኞቹ አስፈራሪዎች (ጎሳ) የኾነ አስፈራሪ ነው፡፡ 53|57|ቀራቢይቱ (ኅልፈተ ዓለም) ቀረበች፡፡ 53|58|ለእርሷ ከአላህ ሌላ ገላጭ የላትም፡፡ 53|59|ከዚህ ንግግር ትደነቃላችሁን? 53|60|ትስቃላችሁምን? አታለቅሱምን? 53|61|እናንተም ዘንጊዎች ናችሁ፡፡ 53|62|ለአላህም ስገዱ ተገዙትም፡፡ 54|1|ሰዓቲቱ (የትንሣኤ ቀን) ተቃረበች፤ ጨረቃም ተገመሰ፡፡ 54|2|ተዓምርንም ቢያዩ (ከእምነት) ይዞራሉ፡፡ (ይህ) «ዘውታሪ ድግምት ነውም» ይላሉ፡፡ 54|3|አስተባበሉም፡፡ ዝንባሌዎቻቸውንም ተከተሉ፡፡ ነገርም ሁሉ (ወሰን አለው)፤ ረጊ ነው፡፡ 54|4|ከዜናዎችም በእርሱ ውስጥ መገሰጥ ያለበት ነገር በእርግጥ መጣላቸው፡፡ 54|5|ሙሉ የኾነች ጥበብ (መጣቻቸው) ግን አስፈራሪዎቹ አያብቃቁም፡፡ 54|6|ከነርሱም ዙር፡፡ ጠሪው (መልአክ) ወደ አስደንጋጭ ነገር የሚጠራበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ 54|7|ዓይኖቻቸው ያቀረቀሩ ኾነው፤ ፍጹም የተበተነ አንበጣ መስለው ከመቃብሮቹ ይወጣሉ፡፡ 54|8|ወደ ጠሪው አንገቶቻቸውን ሳቢዎች ቸኳዮች ኾነው (ይወጣሉ)፡፡ ከሓዲዎቹ (ያን ጊዜ ምን ይላሉ?) «ይህ ብርቱ ቀን ነው» ይላሉ፡፡ 54|9|ከእነርሱ በፊት የኑሕ ነገድ አስተባበለች፡፡ ባሪያችንንም (ኑሕን) አስተባበሉ፡፡ «ዕብድ ነውም» አሉ፡፡ ተገላመጠም፡፡ 54|10|ጌታውንም «እኔ የተሸነፍኩ ነኝና እርዳኝ» ሲል ጠራ፡፡ 54|11|ወዲያውም የሰማይን ደጃፎች በሚንቧቧ ውሃ ከፈትን፡፡ 54|12|የምድርንም ምንጮች አፈነዳን፡፡ ውሃውም (የሰማዩና የምድሩ) በእርግጥ በተወሰነ ኹነታ ላይ ተገናኘ፡፡ 54|13|ባለ ሳንቃዎችና ባለሚስማሮች በኾነችም ታንኳ ላይ ጫንነው፡፡ 54|14|በጥበቃችን ስር ኾና ትንሻለላለች፡፡ ተክዶ ለነበረው ሰው ምንዳ (ይህንን ሠራን)፡፡ 54|15|ተዓምር አድርገንም በእርግጥ ተውናት፡፡ ከተገሳጭም አልለን? 54|16|ቅጣቴና ማስጠንቀቂያዎቼም እንዴት ነበሩ? 54|17|ቁርኣንንም ለመገንዘብ በእርግጥ አገራነው፡፡ ተገንዛቢም አልለን? 54|18|ዓድ አስተባበለች፡፡ ቅጣቴና ማስጠንቀቂያዎቼም እንዴት ነበሩ! 54|19|እኛ በእነርሱ ላይ ዘወትር መናጢ በኾነ ቀን በኀይል የምትንሻሻ ነፋስን ላክንባቸው፡፡ 54|20|ሰዎቹን ልክ ከሥሮቻቸው የተጎለሰሱ የዘንባባ ግንዶች መስለው (ከተደበቁበት) ትነቅላቸዋለች፡፡ 54|21|ቅጣቴና ማስጠንቀቂያዎቼም እንዴት ነበሩ? 54|22|ቁርኣንንም ለማስታወስ በእርግጥ አገራነው፡፡ ተገሳጭም አልለን? 54|23|ሰሙድ በአስፈራሪዎቹ አስተባበለች፡፡ 54|24|«ከእኛ የኾነን አንድን ሰው እንከተለዋለን? እኛ ያን ጊዜ በስህተትና በዕብደት ውስጥ ነን» አሉ፡፡ 54|25|«ከኛ መካከል በእርሱ ላይ (ብቻ) ማስገንዘቢያ (ራእይ) ተጣለለትን? አይደለም እርሱ ውሸታም ኩሩ ነው» (አሉ)፡፡ 54|26|ውሸታሙ ኩሩው ማን እንደኾነ ነገ በእርግጥ ያውቃሉ፡፡ 54|27|እኛ ሴት ግመልን ለእነርሱ መፈተኛ ትኾን ዘንድ ላኪዎች ነን፡፡ ተጠባበቃቸውም፡፡ ታገስም፡፡ 54|28|ውሃውንም በመካከላቸው የተከፈለ መኾኑን ንገራቸው፡፡ ከውሃ የኾነ ፋንታ ሁሉ (ተረኞቹ) የሚጣዱት ነው፡፡ 54|29|ጓደኛቸውንም ጠሩ፡፡ ወዲያውም (ሰይፍን) ተቀበለ፡፡ ወጋትም፡፡ 54|30|ቅጣቴና ማስጠንቀቂያዎቼም እንዴት ነበሩ? 54|31|እኛ በእነርሱ ላይ አንዲትን ጩኸት ላክንባቸው፡፡ ወዲያውም ከበረት አጣሪ (አጥር) እንደ ተሰባበረ ርግጋፊ ኾኑ፡፡ 54|32|ቁርኣንንም ለመገንዘብ አገራነው፡፡ ተገሳጭም አልለን? 54|33|የሉጥ ሕዝብ በአስፈራሪዎቹ አስተባበለች፡፡ 54|34|እኛ በእነርሱ ላይ ጠጠርን ያዘለች ነፋስን ላክን፡፡ የሉጥ ቤተሰቦች ብቻ ሲቀሩ (እነርሱንስ) በሌሊት መጨረሻ ላይ አዳንናቸው፡፡ 54|35|ከእኛ በኾነ ጸጋ (አዳንናቸው)፡፡ እንደዚሁ ያመሰገነን ሰው እንመነዳለን፡፡ 54|36|ብርቱይቱን አያያዛችንንም በእርግጥ አስጠነቀቃቸው፡፡ በማስጠንቀቂያዎቹም ተከራከሩ፡፡ 54|37|ከእንግዶቹም እንዲያስመቻቸው ደጋግመው ፈለጉት፡፡ ወዲያውም ዓይኖቻቸውን አበስን፡፡ «ቅጣቴንና ማስጠንቀቂያዎቼንም ቅመሱ» (አልናቸው)፡፡ 54|38|በማለዳም ዘውታሪ የኾነ ቅጣት በእርግጥ ማለደባቸው፡፡ 54|39|«ቅጣቴንና ማስጠንቀቂያዎቼንም ቅመሱ» (ተባሉ)፡፡ 54|40|ቁርኣንንም ለመገንዘብ በእርግጥ አገራነው፡፡ ተገሳጭም አልለን? 54|41|የፈርዖንንም ቤተሰቦች ማስጠንቀቂያዎች በእርግጥ መጡዋቸው፡፡ 54|42|በተዓምራቶቻችን በሁሏም አስተባበሉ፡፡ የብርቱ ቻይንም አያያዝ ያዝናቸው፡፡ 54|43|ከሓዲዎቻችሁ ከእነዚህ በላጮች ናቸውን? ወይስ ለናንተ በመጽሐፎች ውስጥ (የተነገረ) ነፃነት አላችሁን? 54|44|ወይስ «እኛ የተረዳን ክምቹዎች ነን» ይላሉን? 54|45|ክምቹዎቹ በእርግጥ ድል ይምመታሉ፡፡ ጀርባዎችንም ያዞራሉ፡፡ 54|46|ይልቁንም ሰዓቲቱ (ትንሣኤ) ቀጠሮዋቸው ናት፡፡ ሰዓቲቱም በጣም የከበደችና የመረረች ናት፡፡ 54|47|አመጸኞች በስህተትና በእሳቶች ውስጥ ናቸው፡፡ 54|48|በእሳት ውስጥ በፊቶቻቸው በሚጎተቱበት ቀን «የሰቀርን መንካት ቅመሱ» (ይባላሉ)፡፡ 54|49|እኛ ሁሉን ነገር በልክ ፈጠርነው፡፡ 54|50|ትእዛዛችንም እንደ ዓይን ቅጽበት አንዲት (ቃል) እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ 54|51|ብጤዎቻችሁንም በእርግጥ አጠፋን፡፡ ተገሳጭም አልለን? 54|52|የሠሩትም ነገር ሁሉ በመጽሐፎች ውስጥ ነው፡፡ 54|53|ትንሹም ትልቁም ሁሉ የተጻፈ ነው፡፡ 54|54|አላህን ፈሪዎቹ በአትክልቶችና በወንዞች ውስጥ ናቸው፡፡ 54|55|(እነርሱም ውድቅ ቃልና መውወንጀል በሌለበት) በእውነት መቀመጫ ውስጥ ቻይ የሆነው ንጉሥ ዘንድ ናቸው፡፡ 55|1|አል-ረሕማን፤ 55|2|ቁርኣንን አስተማረ፡፡ 55|3|ሰውን ፈጠረ፡፡ 55|4|መናገርን አስተማረው፡፡ 55|5|ፀሐይና ጨረቃ በተወሰነ ልክ (ይኼዳሉ)፡፡ 55|6|ሐረግና ዛፍም (ለእርሱ) ይሰግዳሉ፡፡ 55|7|ሰማይንም አጓናት፡፡ ትክክለኛነትንም ደነገገ፡፡ 55|8|በሚዛን (ስትመዝኑ) እንዳትበድሉ፡፡ 55|9|መመዘንንም በትክክል መዝኑ፡፡ ተመዛኙንም አታጉድሉ፡፡ 55|10|ምድርንም ለፍጡሩ አደላደላት፡፡ 55|11|በውስጧ እሸት ባለ ሺፋኖች የኾኑ ዘንባባዎችም ያሉባት ስትኾን፡፡ 55|12|የገለባ ባለቤት የኾነ ቅንጣትም፡፡ ባለ መልካም መዐዛ ቅጠሎችም (ያሉባት ስትኾን)፡፡ 55|13|(ሰዎችና ጋኔኖች ሆይ!) ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|14|ሰውን እንደ ሸክላ ከሚቅጨለጨል ደረቅ ጭቃ ፈጠረው፡፡ 55|15|ጃንንም ከእሳት ከኾነ ነበልባል ፈጠረው፡፡ 55|16|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|17|የሁለቱ ምሥራቆች ጌታ፤ የሁለቱ ምዕራቦችም ጌታ ነው፡፡ 55|18|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|19|ሁለቱን ባሕሮች የሚገናኙ ሲኾኑ ለቀቃቸው፡፡ 55|20|(እንዳይዋሐዱ) በመካከላቸው ጋራጅ አልለ፡፡ (አንዱ ባንዱ ላይ) ወሰን አያልፉም፡፡ 55|21|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታሰተባብላላችሁ?› 55|22|ሉልና መርጃን ከሁለቱ ይወጣል፡፡ 55|23|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|24|እንደ ጋራዎች ኾነው በባሕር ውስጥ የተሠሩት ተንሻለዮቹም (ታንኳዎች) የእርሱ ናቸው፡፡ 55|25|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|26|በእርሷ (በምድር) ላይ ያለው ሁሉ ጠፊ ነው፡፡ 55|27|የልቅናና የልግሥና ባለቤት የኾነው የጌታህ ፊትም ይቀራል፡፡ (አይጠፋም)፡፡ 55|28|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|29|በሰማያትና በምድር ውስጥ ያሉት ሁሉ ይለምኑታል፡፡ በየቀኑ ሁሉ እርሱ በሥራ ላይ ነው፡፡ 55|30|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታሰተባብላላችሁ?› 55|31|እናንተ ሁለት ከባዶች (ሰዎችና ጋኔኖች) ሆይ! ለእናንተ (መቆጣጠር) በእርግጥ እናስባለን፡፡ 55|32|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|33|የጋኔንና የሰው ጭፍሮች ሆይ! ከሰማያትና ከምድር ቀበሌዎች መውጣትን ብትችሉ ውጡ፡፡ በስልጣን እንጅ አትወጡም፡፡ (ግን ስልጣን የላችሁም) 55|34|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|35|በሁለታችሁም ላይ ከእሳት ነበልባል፣ ጭስም ይላክባችኋል፡፡ (ሁለታችሁም) አትርረዱምም፡፡ 55|36|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|37|ሰማይም በተሰነጠቀችና እንደ ጽጌረዳ፣ እንደታረበ ቆዳ በኾነች ጊዜ፤ (ጭንቁን ምን አበረታው)፡፡ 55|38|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|39|በዚያም ቀን ሰውም ጃንም ከኃጢኣቱ ገና አይጠየቅም፡፡ 55|40|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|41|ከሓዲዎች በምልክታቸው ይታወቃሉ፡፡ አናቶቻቸውንና ጫማዎቻቸውንም ይያዛሉ፡፡ 55|42|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ፡፡ 55|43|ይህቺ ያቺ አመጸኞች በእርሷ ያስተባብሉባት የነበረችው ገሀነም ናት (ይባላሉ)፡፡ 55|44|በእርሷና በጣም ሞቃት በኾነ ፍል ውሃ መካከል ይመላለሳሉ፡፡ 55|45|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|46|በጌታውም ፊት መቆምን ለፈራ ሰው ሁለት ገነቶች አልሉት፡፡ 55|47|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|48|የቀንዘሎች ባለ ቤቶች የኾኑ (ገነቶች አልሉት)፡፡ 55|49|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|50|በሁለቱ ውስጥ የሚፈስሱ ሁለት ምንጮች አልሉ፡፡ 55|51|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|52|በሁለቱ ውስጥ ከፍራፍሬዎች ሁሉ ሁለት ዓይነቶች (እርጥብና ደረቅ) አልሉ፡፡ 55|53|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|54|የውስጥ ጉስጉሳቸው ከወፍራም ሐር በኾኑ ምንጣፎች ላይ የተመቻቹ ሲኾኑ (ይንፈላሰሳሉ)፡፡ የሁለቱም ገነቶች ፍሬ (ለለቃሚ) ቅርብ ነው፡፡ 55|55|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|56|በውስጣቸው ከበፊታቸው (ከባሎቻቸው በፊት) ሰውም ጃንም ያልገሰሳቸው ዓይኖቻቸውን (በባሎቻቸው ላይ) አሳጣሪዎች (ሴቶች) አልሉ፡፡ 55|57|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|58|ልክ ያቁትና መርጃን ይመስላሉ፡፡ 55|59|ከጌታችሁም ጸጋዎቸ በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|60|የበጎ ሥራ ዋጋ በጎ እንጅ ሌላ ነውን? 55|61|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|62|ከሁለቱ ገነቶችም ሌላ ሁለት ገነቶች አልሉ፡፡ 55|63|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ?› 55|64|ከልምላሜያቸው የተነሳ ወደ ጥቁረት ያዘነበሉ ናቸው፡፡ 55|65|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|66|በውስጣቸው ሁለት የሚንፏፉ ምንጮች አልሉ፡፡ 55|67|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|68|በውስጣቸው ፍራፍሬ፣ ዘምባባም፣ ሩማንም አልለ፡፡ 55|69|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|70|በውስጣቸው ጠባየ መልካሞች መልክ ውቦች (ሴቶች) አልሉ፡፡ 55|71|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|72|በድንኳኖች ውስጥ የተጨጎሉ የዓይኖቻቸው ጥቁረትና ንጣት ደማቅ የኾኑ ናቸው፡፡ 55|73|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|74|ከነርሱ በፊት ሰውም ጃንም አልገሰሳቸውም፡፡ 55|75|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባበላላችሁ? 55|76|በሚያረገርጉ አረንጓዴ ምንጣፎችና በሚያማምሩ ስጋጃዎች ላይ የተደላደሉ ሲኾኑ (ይቀመጣሉ)፡፡ 55|77|ከጌታችሁም ጸጋዎች በየትኛው ታስተባብላላችሁ? 55|78|የግርማና የመክበር ባለቤት የኾነው ጌታህ ስም ተባረከ፡፡ 56|1|መከራይቱ በወደቀች ጊዜ፡፡ 56|2|ለመውደቋ አስተባባይ (ነፍስ) የለችም፡፡ 56|3|ዝቅ አድራጊና ከፍ አድራጊ ናት፡፡ 56|4|ምድር መናወጥን በተናወጠች ጊዜ፡፡ 56|5|ተራራዎችም መፍፈርፈርን በተፈረፈሩ ጊዜ (እንደተፈጨ ዱቄት በኾኑ ጊዜ)፡፡ 56|6|የተበተነ ብናኝ በኾኑም ጊዜ 56|7|ሦስት ዓይነቶችም በኾናችሁ ጊዜ (ታዋርዳለች፤ ታነሳለችም)፡፡ 56|8|የቀኝ ጓዶችም ምን (የተከበሩ) የቀኝ ጓዶች ናቸው፡፡ 56|9|የግራ ጓዶችም ምን (የተዋረዱ) የግራ ጓዶች ናቸው፡፡ 56|10|(ለበጎ ሥራ) ቀዳሚዎቹም (ለገነት) ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ 56|11|እነዚያ ባለሟሎቹ ናቸው፡፡ 56|12|በመጠቀሚያ ገነቶች ውስጥ ሲኾኑ፡፡ 56|13|ከፊተኞቹ ብዙ ጭፍሮች ናቸው፡፡ 56|14|ከኋለኞቹም ጥቂቶች ናቸው፡፡ 56|15|በተታቱ አልጋዎች ላይ ይኾናሉ፡፡ 56|16|በእርሷ ላይ የተመቻቹና ፊት ለፊት የተቅጣጩ ሲኾኑ፡፡ 56|17|በእነርሱ ላይ ሁል ጊዜ የማያረጁ ወጣቶች ልጆች ይዘዋወራሉ፡፡ 56|18|ከጠጅ ምንጭም በብርጭቆዎችና በኩስኩስቶች በጽዋም (በእነርሱ ላይ ይዝዞራሉ)፡፡ 56|19|ከእርሷ የራስ ምታት አያገኛቸውም፤ አይሰክሩምም፡፡ 56|20|ከሚመርጡትም ዓይነት በእሸቶች፡፡ 56|21|ከሚሹትም በኾነ የበራሪ ሥጋ (ይዞሩባቸዋል)፡፡ 56|22|ዓይናማዎች የኾኑ ነጫጭ ቆንጆዎችም አሏቸው፡፡ 56|23|ልክ እንደተሸፈነ ሉል መሰሎች የኾኑ፡፡ 56|24|በዚያ ይሠሩት በነበሩት ምክንያት ዋጋ ይኾን ዘንድ (ይህንን አደረግንላቸው)፡፡ 56|25|በውስጥዋ ውድቅ ንግግርንና መውወንጀልን አይሰሙም፡፡ 56|26|ግን ሰላም መባባልን (ይሰማሉ)፡፡ 56|27|የቀኝም ጓዶች ምንኛ (የከበሩ) የቀኝ ጓዶች! 56|28|በተቀፈቀፈ (እሾህ በሌለው) ቁርቁራ ውስጥ ናቸው፡፡ 56|29|(ፍሬው) በተነባበረ በሙዝ ዛፍም፡፡ 56|30|በተዘረጋ ጥላ ሥርም፡፡ 56|31|በሚንቧቧ ውሃ አጠገብም፡፡ 56|32|ብዙ (ዓይነት) በኾኑ ፍራፍሬዎችም፡፡ 56|33|የማትቋረጥም የማትከለከልም የኾነች፡፡ 56|34|ከፍ በተደረጉ ምንጣፎችም (ሴቶችም መካከል)፡፡ 56|35|እኛ አዲስ ፍጥረት አድርገን (ለእነርሱ) ፈጠርናቸው፡፡ 56|36|ደናግሎችም አደረግናቸው፡፡ 56|37|ለባሎቻቸው ተሽሞርሟሪዎች እኩያዎች (አደረግናቸው)፡፡ 56|38|ለቀኝ ጓዶች (አዘጋጀናቸው)፡፡ 56|39|ከፊተኞቹ ብዙ ጭፍሮች ናቸው፡፡ 56|40|ከኋለኞቹም ብዙ ጭፍሮች ናቸው፡፡ 56|41|የግራ ጓደኞችም ምንኛ (የተዋረዱ) የግራ ጓዶች! ናቸው፡፡ 56|42|በመርዛም ነፋስ በጣም በፈላ ውሃም ውስጥ ናቸው፡፡ 56|43|ከጥቁር ጭስም በኾነ ጥላ ውስጥ፡፡ 56|44|ቀዝቃዛም መልካምም ያልኾነ፡፡ 56|45|እነርሱ ከዚህ በፊት ቅምጥሎች ነበሩና፡፡ 56|46|በታላቅ ኀጢአትም ላይ ይዘወትሩ ነበሩና፡፡ 56|47|ይሉም ነበሩ፡- «በሞትንና ዐፈር፣ ዐጥንቶችም በኾን ጊዜ እኛ በእርግጥ የምንቀሰቀስ ነን? 56|48|«የፊተኞቹ አባቶቻችንም?» 56|49|በላቸው፡- «ፊተኞቹም ኋለኞቹም፡፡ 56|50|«በተወሰነ ቀን ቀጠሮ በእርግጥ ተሰብሳቢዎች ናቸው፡፡ 56|51|«ከዚያም እናንተ ጠማሞች አስተባባዮች ሆይ! 56|52|« ከዘቁም ዛፍ በእርግጥ በይዎች ናችሁ፡፡ 56|53|«ከእርሷም ሆዶቻችሁን ሞይዎች ናችሁ፡፡ 56|54|«በእርሱ ላይም ከፈላ ውሃ ጠጪዎች ናችሁ፡፡ 56|55|«የተጠሙንም ግመሎች አጠጣጥ ብጤ ጠጪዎች ናችሁ፡፡» 56|56|ይህ በፍርዱ ቀን መስተንግዷቸው ነው፡፡ 56|57|እኛ ፈጠርናችሁ አታምኑምን? 56|58|(በማኅፀኖች) የምታፈሱትን አያችሁን? 56|59|እናንተ ትፈጥሩታላችሁን? ወይስ እኛ ፈጣሪዎቹን ነን? 56|60|እኛ ሞትን (ጊዜውን) በመካከላችሁ ወሰንን፡፡ እኛም ተሸናፊዎች አይደለንም፡፡ 56|61|ብጤዎቻችሁን በመለወጥና በዚያ በማታውቁትም (ቅርጽ) እናንተን በመፍጠር ላይ (አንሸነፍም)፡፡ 56|62|የፊተኛይቱንም አፈጣጠር በእርግጥ ዐውቃችኋል፡፡ አትገነዘቡምን? 56|63|የምትዘሩትንም አያችሁን? 56|64|እናንተ ታበቅሉታላችሁን? ወይስ እኛ አብቃዮቹ ነን? 56|65|ብነሻ ኖሮ ደረቅ ስብርብር ባደረግነውና የምትደነቁም በኾናችሁ ነበር፡፡ 56|66|«እኛ በዕዳ ተያዦች ነን፡፡ 56|67|«በእርግጥም እኛ (ከመጠቀም) የተከለከልን ነን» (ትሉ ነበር)፡፡ 56|68|ያንንም የምትጠጡትን ውሃ አየችሁን? 56|69|እናንተ ከደመናው አወረዳችሁትን? ወይስ እኛ አውራጆቹ ነን? 56|70|ብንሻ ኖሮ መርጋጋ ባደረግነው ነበር፡፡ አታመሰግኑምን? 56|71|ያቺንም የምትሰብቋትን እሳት አያችሁን? 56|72|እናንተ ዛፏን ፈጠራችሁን? ወይስ እኛ ፈጣሪዎችዋ ነን? 56|73|እኛ (ለገሀናም) ማስታወሻ ለመንገደኞችም መጠቀሚያ አደረግናት፡፡ 56|74|የታላቁን ጌታህንም ስም አወድስ፡፡ 56|75|በከዋክብትም መጥለቂያዎች እምላለሁ፡፡ 56|76|እርሱም ብታወቁ ታላቅ መሓላ ነው፡፡ 56|77|እርሱ የከበረ ቁርኣን ነው፡፡ 56|78|በተጠበቀ መጽሐፍ ውስጥ ነው፡፡ 56|79|የተጥራሩት እንጅ ሌላ አይነካውም፡፡ 56|80|ከዓለማት ጌታ የተወረደ ነው፡፡ 56|81|በዚህ ንግግር እናንተ ቸልተኞች ናችሁን? 56|82|ሲሳያችሁንም (ዝናምን) እናንተ የምታስተባብሉት ታደርጋላችሁን? 56|83|(ነፍስ) ጉረሮንም በደረሰች ጊዜ፡፡ 56|84|እናንተ ያን ጊዜ የምታዩ ስትኾኑ፡፡ 56|85|እኛም ግን አታዩም እንጅ ከእናንተ ይልቅ ወደእርሱ የቀረብን ስንኾን፡፡ 56|86|የማትዳኙም ከኾናችሁ፡፡ 56|87|እውነተኞች እንደ ኾናችሁ (ነፍሲቱን ወደ አካሉ) ለምን አትመልሷትም፡፡ 56|88|(ሟቹ) ከባለሟሎቹ ቢኾንማ፡፡ 56|89|(ለእርሱ) ዕረፍት፣ መልካም ሲሳይም፣ የመጠቀሚያ ገነትም አልለው፡፡ 56|90|ከቀኝ ጓዶችም ቢኾንማ፡፡ 56|91|ከቀኝ ጓዶች ስለ ኾንክ ላንተ ሰላም አልለህ (ይባላል)፡፡ 56|92|ከሚያስዋሹት ጠማማዎችም ቢኾንማ፡፡ 56|93|ከፈላ ውሃ የኾነ መስተንግዶ አልለው፡፡ 56|94|በገሀነም መቃጠልም (አልለው)፡፡ 56|95|ይህ እርሱ እርግጠኛ እውነት ነው፡፡ 56|96|የታላቁንም ጌታህን ስም አወድስ፡፡ 57|1|በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ ለአላህ አሞገሰ፡፡ እርሱም ሁሉን አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 57|2|የሰማያትና የምድር ንግሥና የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ሕያው ያደርጋል፤ ይገድላልም፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 57|3|እርሱ ፊትም ያለ፣ ኋላም ቀሪ፣ ግልጽም፣ ስውርም ነው፡፡ እርሱም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 57|4|እርሱ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀናት ውስጥ የፈጠረ፤ ከዚያም በዙፋኑ ላይ (ስልጣኑ) የተደላደለ ነው፡፡ በምድር ውስጥ የሚገባውን፣ ከእርሷም የሚወጣውን፣ ከሰማይም የሚወርደውን በእርሷም ውስጥ የሚያርገውን ያውቃል፡፡ እርሱም የትም ብትኾኑ ከእናንተ ጋር ነው፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 57|5|የሰማያትና የምድር ንግሥና የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ነገሮችም (ሁሉ) ወደ አላህ ብቻ ይመለሳሉ፡፡ 57|6|ሌሊትን በቀን ውስጥ ያስገባል፡፡ ቀንንም በሌሊት ውስጥ ያስገባል፡፡ እርሱም በልቦች ውስጥ የተደበቁትን ዐዋቂ ነወ፡፡ 57|7|በአላህና በመልክተኛው እመኑ፡፡ (አላህ) በእርሱ ተተኪዎች ባደረጋችሁም ገንዘብ ለግሱ፡፡ እነዚያም ከእናንተ ውስጥ ያመኑትና የለገሱት ለእነርሱ ታላቅ ምንዳ አልላቸው፡፡ 57|8|መልክተኛው በጌታችሁ እንድታምኑ የሚጠራችሁ ሲኾን (ጌታችሁ) ኪዳናችሁንም የያዘባችሁ ሲኾን በአላህ የማታምኑት ለእናንተ ምን አልላችሁ? የምታምኑ ብትኾኑ (ወደ እምነት ቸኩሉ)፡፡ 57|9|እርሱ ከጨለማዎች ወደ ብርሃን ሊያወጣችሁ ያ ግልጾች የኾኑን አንቀጾች በበሪያው ላይ የሚያወርድ ነው፡፡ አላህም ለእናንተ በእርግጥ ርኅሩህ አዛኝ ነው፡፡ 57|10|የሰማያትና የምድር ውርስ ለአላህ ሲኾን በአላህ መንገድ የማትለግሱትም ለእናንተ ምን አልላችሁ? ከእናንተ ውስጥ (መካን) ከመክፈት በፊት የለገሰና የተጋደለ ሰው (ከተከፈተች በኋላ ከለገሰና ከተጋደለ ጋር) አይስተካከልም፡፡ ከእነዚያ በኋላ ከለገሱትና ከተጋደሉት እነዚህ በደረጃ በጣም የላቁ ናቸው፡፡ ሁሉንም አላህ መልካሚቱን ተስፋ ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 57|11|ያ ለአላህ መልካም ብድርን የሚያበድር ለእርሱም (አላህ) የሚያነባብርለት ሰው ማነው? ለእርሱም መልካም ምንዳ አልለው፡፡ 57|12|ምእመናንንና ምእምናትን በስተፊቶቻቸው፣ በቀኞቻቸውም ብርሃናቸው የሚሮጥ ሲኾን በምታያቸው ቀን (ምንዳ አልላቸው)፡፡ ዛሬ ብስራታችሁ በውስጦቻቸው ዘውታሪዎች ስትኾኑ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈስሱባቸው ገነቶች ናቸው (ይባላሉ)፡፡ ይህ እርሱ ታላቁ ዕድል ነው፡፡ 57|13|መናፍቃንና መናፍቃት ለእነዚያ ለአመኑት «ተመልከቱን፤ ከብርሃናችሁ እናበራለንና» የሚሉበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ «ወደ ኋላችሁ ተመለሱ፡፡ ብርሃንንም ፈልጉ» ይባላሉ፡፡ ግቢው በውስጡ ችሮታ (ገነት) ያለበት ውጭውም ከበኩሉ ስቃይ (እሳት) ያለበት የኾነ (ደጃፍ ባለው አጥር)፡፡ 57|14|«ከእናንተ ጋር አልነበርንምን?» በማለት ይጠሩዋቸዋል፡፡ «እውነት ነው፡፡ ግን እናንተ ነፍሶቻችሁን አጠፋችሁ፡፡ (በነቢዩ አደጋዎችን) ተጠባበቃችሁም፡፡ ተጠራጠራችሁም፡፡ የአላህም ትዕዛዝ እስከ መጣ ድረስ ከንቱ ምኞቶች አታለሏችሁ፡፡ አታላዩም (ሰይጣን) በአላህ (መታገስ) ሸነገላችሁ፤» ይሏቸዋል፡፡ 57|15|«ዛሬም ከእናንተ ቤዛ አይወስድም፡፡ ከእነዚያ ከካዱትም፡፡ መኖሪያችሁ እሳት ናት፡፡ እርሷ ተገቢያችሁ ናት፡፡ ምን ትከፋም መመለሻ!» (ይሏቸዋል)፡፡ 57|16|ለነዚያ ለአመኑት ለአላህ ተግሳጽና ከቁርኣንም ለወረደው ልቦቻቸው ሊፈሩ እንደእነዚያም በፊት መጽሐፍን እንደ ተሰጡትና በእነርሱ ላይ ጊዜ እንደረዘመባቸው ልቦቻቸውም እንደ ደረቁት ላይኾኑ (ጊዜው) አልቀረበምን? ከእነርሱም ብዙዎቹ አመጸኞች ናቸው፡፡ 57|17|አላህ ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው የሚያደርጋት መኾኑን ዕወቁ፡፡ ታወቁ ዘንድ አንቀጾችን ለእናንተ በእርግጥ አብራራንላችሁ፡፡ 57|18|የመጸወቱ ወንዶችና፣ የመጸወቱ ሴቶች፣ ለአላህም መልካምን ብድር ያበደሩ ለእነርሱ መልካም ምንዳ አልላቸው፡፡ 57|19|እነዚያም በአላህና በመልክተኞቹ ያመኑት እነዚያ እነርሱ በጣም እውነተኞቹ በጌታቸውም ዘንድ መስካሪዎቹ ናቸው፡፡ ለእነርሱ ምንዳቸው ብርሃናቸውም አልላቸው፡፡ እነዚያም የካዱት በአንቀጾቻችንም ያስተባበሉት እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ 57|20|ቅርቢቱ ሕይወት ጨዋታና ዛዛታ፣ ማጌጫም፣ በመካከላችሁም መፎካከሪያ፣ በገንዘቦችና በልጆችም ብዛት መበላለጫ ብቻ መኾንዋን ዕወቁ፡፡ (እርሷ) በቃዩ ገበሬዎችን እንደሚያስደስት ዝናም፣ ከዚያም በቃዩ እንደሚደርቅና ገርጥቶ እንደምታየው፣ ከዚያም የተሰባበረ እንደሚኾን ብጤ ናት፣ በመጨረሻይቱም ዓለም ብርቱ ቅጣት ከአላህም ምሕረትና ውዴታ አልለ፡፡ የቅርቢቱም ሕይወት የመታለያ ጥቅም እንጅ ሌላ አይደለችም፡፡ 57|21|ከጌታችሁ ወደ ኾነች ምሕረት፣ ወርዷ እደ ሰማይና ምድር ወርድ ወደ ሆነችም ገነት ተሽቀዳደሙ፡፡ ለእነዚያ በአላህና በመልክተኞቹ ላመኑት ተዘጋጅታለች፡፡ ይህ የአላህ ችሮታ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው ይሰጠዋል፡፡ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 57|22|በምድርም በነፍሶቻችሁም መከራ (ማንንም) አትነካም ሳንፈጥራት በፊት በመጽሐፍ የተመዘገበች ብትኾን እንጅ፡፡ ይህ በአላህ ላይ ገር ነው፡፡ 57|23|(ይህ ማሳወቃችን) ባመለጣችሁ ጸጋ ላይ እንዳታዝኑ አላህም በሰጣችሁ ነገር (በትዕቢት) እንዳትደሰቱ ነው፡፡ አላህም ኩራተኛን ጉረኛን ሁሉ አይወድም፡፡ 57|24|(እነርሱም) እነዚያ የሚሰስቱና ሰዎችንም በስስት የሚያዝዙ ናቸው፡፡ (ከእውነት) የሚሸሽም ሰው (ጥፋቱ በራሱ ላይ ነው)፡፡ አላህም እርሱ ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡ 57|25|መልክተኞቻችንን በግልጽ ማስረጃዎች በእርግጥ ላክን፡፡ ሰዎችም በትክክል ቀጥ እንዲሉ መጽሐፎችንና ሚዛንን ወደእነርሱ አወረድን፤ ብረትንም በውስጡ ብርቱ ኀይልና ለሰዎችም መጠቃቀሚያዎች ያልሉበት ሲኾን አወረድን፡፡ (እንዲጠቀሙበት) አላህም ሃይማኖቱንና መልክተኞቹን በሩቅ ኾኖ የሚረዳውን ሰው ሊያውቅ (ሊገልጽ አወረደው)፡፡ አላህ ብርቱ አሸናፊ ነውና፡፡ 57|26|ኑሕን፣ ኢብራሂምንም በእርግጥ ላክን፡፡ በዘሮቻቸውም ውስጥ ነቢይነትንና መጽሐፎችን አደረግን፡፡ ከእነርሱም ቅን አልለ፡፡ ከእነርሱም ብዙዎቹ አመጸኞች ናቸው፡፡ 57|27|ከዚያም በዱካዎቻቸው ላይ መልክተኞቻችንን አስከታተልን፡፡ የመርየምን ልጅ ዒሳንም አስከተልን፡፡ ኢንጂልንም ሰጠነው፡፡ በእነዚያም በተከተሉት (ሰዎች) ልቦች ውሰጥ መለዘብንና እዝነትን፣ አዲስ የፈጠሩዋትንም ምንኩስና አደረግን፡፡ በእነርሱ ላይ (ምንኩስናን) አልጻፍናትም፡፡ ግን የአላህን ውዴታ ለመፈለግ ሲሉ (ፈጠሩዋት)፡፡ ተገቢ አጠባበቋንም፤ አልጠበቋትም፡፡ ከእነርሱም ለእነዚያ ላመኑት ምንዳቸውን ሰጠናቸው፡፡ ከእነርሱም ብዙዎቹ አመጸኞች ናቸው፡፡ 57|28|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ፡፡ በመልእክተኛውም እመኑ፡፡ ከችሮታው ሁለትን ክፍሎች ይሰጣችኋልና፡፡ ለእናንተም በእርሱ የምትኼዱበት የኾነ ብርሃንን ያደርግላችኋል፡፡ ለእናንተም ይምራል፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 57|29|(ይህም) የመጽሐፉ ሰዎች ከአላህ ችሮታ በምንም ላይ የማይችሉ መኾናቸውን ችሮታም በአላህ እጅ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው ይሰጠዋል ማለትን እንዲያውቁ ነው፤ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 58|1|አላህ የዚያችን በባሏ (ነገር) የምተከራከርህንና ወደ አላህ የምታሰሙተውን (ሴት) ቃል በእርግጥ ሰማ፡፡ አላህም (በንግግር) መመላለሳችሁን ይሰማል፡፡ አላህ ሰሚ ተመልካች ነውና፡፡ 58|2|እነዚያ ከእናንተ ውስጥ ከሚስቶቻቸው እንደናቶቻችን ጀርባዎች ይኹኑብን በማለት የሚምሉ እነርሱ እናቶቻቸው አይደሉም፡፡ እናቶቻቸው እኒያ የወለዱዋቸው ብቻ ናቸው፡፡ እነርሱም (በዚህ ቃል) ከንግግር የተጠላንና ውሸትን በእርግጥ ይናገራሉ፡፡ አላህም (ለሚጸጸት) ይቅር ባይ መሓሪ ነው፡፡ 58|3|እነዚያም ከሚስቶቻቸው እንደናቶቻችን ጀርባዎች ኹኑብን በማለት የሚምሉ ከዚያም ወደ ተናገሩት የሚመለሱ ሳይነካኩ በፊት ጫንቃን ነጻ ማውጣት በነርሱ ላይ አለባቸው፡፡ እነሆ በእርሱ ትገሰጹበታለችሁ፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጥ ዓዋቂ ነው፡፡ 58|4|ያላገኘም ሰው ከመነካከታቸው በፊት ሁለት የተከታተሉ ወሮችን መጾም አለበት፡፡ ያልቻለም ሰው ስድሳ ድኾችን ማብላት (አለበት)፡፡ ይህ በአላህና በመልክተኛው እንድታምኑ ነው፡፡ ይህችም የአላህ ሕግጋት ናት፡፡ ለከሓዲዎችም አሳማሚ ቅጣት አልላቸው፡፡ 58|5|ግልጾች ማስረጃዎችን ያወረድን ስንኾን እነዚያ አላህንና መልክተኛውን የሚከራከሩ እነዚያ ከእነርሱ በፊት የነበሩት እንደተዋረዱ ይዋረዳሉ፡፡ ለከሓዲዎችም አዋራጅ ቅጣት አልላቸው፡፡ 58|6|አላህ ሁላቸውንም በሚቀስቃሳቸው ቀን (ይቀጣቸዋል)፡፡ የሠሩትንም ሁሉ ይነግራቸዋል፡፡ የረሱት ሲኾኑ አላህ ዐውቆታል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ዐዋቂ ነው፡፡ 58|7|አላህ በሰማያት ውስጥ ያለውን በምድርም ውሰጥ ያለውን ሁሉ የሚያውቅ መኾኑን አታይምን? ከሦስት ሰዎች መሾካሾክ አይኖርም እርሱ አራተኛቸው ቢኾን እንጅ፡፡ ከአምስትም (አይኖርም) እርሱ ስድስተኛቸው ቢኾን እንጅ፡፡ ከዚያ ያነሰም የበዛም (አይኖርም) እርሱ የትም ቢኾኑ እንጂ፡፡ ከዚያም በትንሣኤ ቀን የሠሩትን ሁሉ ይነግራቸዋል፡፡ አላህ ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 58|8|ወደእነዚያ (በመጥፎ) ከመሾካሾክ ወደ ተከለከሉት፣ ከዚያም ከእርሱ ወደ ተከለከሉት ነገር ወደሚመለሱት፣ በኃጢአትና ድንበር በማለፍ መልክተኛውን በመቃወም ወደሚንሾካሾኩት አላየህምን? (ሰላም ሊሉ) በመጡህም ጊዜ አላህ በእርሱ ባላናገረህ ቃል ያናግሩሃል፡፡ በነፍሶቻቸውም ውስጥ (ነቢይ ከኾንክ) «በምንለው ነገር አላህ አይቀጣንም ኖሮአልን?» ይላሉ፡፡ ገሀነም የሚገቧት ሲኾኑ በቂያቸው ናት፡፡ ምን ትከፋም መመለሻ! 58|9|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በተንሾካሾካችሁ ጊዜ በኃጢአትና ወሰንን በማለፍ፣ መልክተኛውንም በመቃወም አትንሾካሾኩ፡፡ ግን በበጎ ሥራና አላህን በመፍራት ተወያዩ፡፡ ያንንም ወደእርሱ የምትሰበሰቡበትን አላህን ፍሩ፡፡ 58|10|(በመጥፎ) መንሾካሾክ ከሰይጣን ብቻ ነው፡፡ እነዚያ ያመኑት ያዝኑ ዘንድ (ይቀሰቅሰዋል)፡፡ በአላህ ፈቃድ ካልኾነ በቀር በምንም አይጎዳቸውም፡፡ በአላህ ላይም አማኞች ይጠጉ፡፡ 58|11|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ለእናንተ በመቀመጫዎች ስፍራ ተስፋፉ በተባላችሁ ጊዜ (ስፍራን) አስፉ፡፡ አላህ ያሰፋላችኋልና፡፡ ተነሱ በተባላችሁም ጊዜ ተነሱ፡፡ አላህ ከናንተ እነዚያን ያመኑትንና እነዚያንም ዕውቀትን የተሰጡትን በደረጃዎች ከፍ ያደርጋል፡፡ አላህም በምትሰሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 58|12|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! መልክተኛውን በተወያያችሁ ጊዜ ከመወያየታችሁ በፊት ምጽዋትን አስቀድሙ፡፡ ይህ ለእናንተ መልካም ነው፡፡ አጥሪም ነው፡፡ ባታገኙም አላህ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 58|13|ከውይይታችሁ በፊት ምጽዋቶችን ከማስቀደም (ድህነትን) ፈራችሁን? ባልሠራችሁም ጊዜ አላህ ከእናንተ ጸጸትን የተቀበለ ሲኾን ሶላትን ስገዱ፡፡ ዘካንም ስጡ፡፡ አላህንና መልክተኛውንም ታዘዙ፡፡ አላህም ውስጥ ዐዋቂ ነው፡፡ 58|14|ወደእነዚያ አላህ በእነርሱ ላይ የተቆጣባቸውን ሕዝቦች ወደ ተወዳጁት (መናፍቃን) አላየኽምን? እነርሱ ከእናንተ አይደሉም፡፡ ከእነርሱም አይደሉም፡፡ እነርሱም የሚያውቁ ሲኾኑ በውሸት ላይ ይምላሉ፡፡ 58|15|አላህ ለእነርሱ ብርቱን ቅጣት አዘጋጀ፡፡ እነርሱ ይሠሩት የነበሩት ሥራ ምንኛ ከፋ! 58|16|መሓሎቻቸውን ጋሻ አድርገው ያዙ፡፡ ከአላህም መንገድ አገዱ፡፡ ስለዚህ ለእነርሱ አዋራጅ ቅጣት አልላቸው፡፡ 58|17|ገንዘቦቻቸውና ልጆቻቸው ከአላህ (ቅጣት) ምንንም ከእነርሱ አያድኗቸውም፡፡ እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡ እነርሱ በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው፡፡ 58|18|አላህ የተሰበሰቡ ኾነው በሚያስነሳቸው ቀን ለእናንተ እንደሚምሉላችሁም እነርሱ (በሚጠቅም) ነገር ላይ መኾናቸውን የሚያስቡ ኾነው ለእርሱ በሚምሉበት ቀን (አዋራጅ ቅጣት አልላቸው)፡፡ ንቁ! እነርሱ ውሸታሞቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 58|19|በእነርሱ ላይ ሰይጣን ተሾመባቸው፡፡ አላህንም ማስታወስን አስረሳቸው፡፡ እነዚያ የሰይጣን ጭፍሮች ናቸው፡፡ ንቁ! የሰይጣን ጭፍሮች ከሳሪዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ 58|20|እነዚያ አላህንና መልክተኛውን የሚከራከሩት እነዚያ በጣም በወራዶቹ ውስጥ ናቸው፡፡ 58|21|አላህ፡- «እኔ በእርግጥ አሸንፋለሁ፣ መልክተኞቼም (ያሸንፋሉ)» ሲል፤ ጽፏል፡፡ አላህ ብርቱ አሸናፊ ነውና፡፡ 58|22|በአላህና በመጨረሻው ቀን የሚያምኑትን ሕዝቦች አላህንና መልክተኛውን የሚከራከሩትን ሰዎች፤ አባቶቻቸው፣ ወይም ልጆቻቸው፣ ወይም ወንድሞቻቸው፣ ወይም ዘመዶቻቸው ቢኾኑም እንኳ የሚወዳጁ ኾነው አታገኛቸውም፡፡ እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ እምነትን ጽፏል፡፡ ከእርሱም በኾነ መንፈስ ደግፏቸዋል፡፡ ከሥሮቻቸውም ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ ያገባቸዋል፡፡ አላህ ከእነርሱ ወዷል፡፡ ከእርሱም ወደዋል፡፡ እነዚያ የአላህ ሕዝቦች ናቸው፡፡ ንቁ! የአላህ ሕዝቦቸ እነርሱ ምኞታቸውን የሚያገኙ ናቸው፡፡ 59|1|በሰማያትና በምድር ውስጥ ያለው ሁሉ ለአላህ አሞገሰ፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 59|2|እርሱ ያ ከመጽሐፉ ሰዎች እነዚያን የካዱትን ከቤቶቻቸው ለመጀመሪያው ማውጣት ያወጣቸው ነው፡፡ መውጣታቸውን አላሰባችሁም፡፡ እነርሱም ምሽጎቻቸው ከአላህ (ኀይል) የሚከላከሉላቸው መኾናቸውን አሰቡ፡፡ አላህም ካላሰቡት ስፍራ መጣባቸው፡፡ በልቦቻቸውም ውስጥ መርበድበድን ጣለባቸው፡፡ ቤቶቻቸውን በእጆቻቸውና በምእምናኖቹ እጆች ያፈርሳሉ፡፡ አስተውሉም የአእምሮ ባለቤቶች ሆይ! 59|3|በእነርሱም ላይ አላህ ከአገር መውጣትን ባልጻፈ ኖሮ በቅርቢቱ ዓለም በቀጣቸው ነበር፡፡ ለእነርሱም በመጨረሻይቱ (ዓለም) የእሳት ቅጣት አልላቸው፡፡ 59|4|ይህ እነርሱ አላህንና መልክተኛውን በመከራከራቸው ነው፡፡ አላህንም የሚከራከር ሰው (ይቀጣዋል)፡፡ አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና፡፡ 59|5|ከዘንባባ (ከተምር ዛፍ) ማንኛዋም የቆረጣችኋት ወይም በግንዶቿ ላይ የቆመች ኾና የተዋችኋት በአላህ ፈቃድ ነው፡፡ አመጸኞቸንም ያዋርድ ዘንድ (በመቁረጥ ፈቀደ)፡፡ 59|6|ከእነርሱም (ገንዘብ) በመልእክተኛው ላይ አላህ የመለሰው በእርሱ ላይ ፈረሶችንና ግመሎችን አላስጋለባችሁበትም፡፡ ግን አላህ መልክተኞቹን በሚሻው ሰው ላይ ይሾማል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 59|7|አላህ ከከተሞቹ ሰዎች (ሀብት) በመልክተኛው ላይ የመለሰው (ሀብት) ከእናንተ ውስጥ በሀብታሞቹ መካከል ተዘዋዋሪ እንዳይኾን፡፡ ለአላህና ለመልክተኛው፣ ለዝምድና ባለቤትም፣ አባት ለሌላቸው ልጆችም፣ ለድኾችም፣ ለመንገደኛም (የሚስሰጥ) ነው፡፡ መልክተኛውም የሰጣችሁን (ማንኛውንም) ነገር ያዙት፡፡ ከእርሱም የከለከላችሁን ነገር ተከልከሉ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና፡፡ 59|8|ለእነዚያ የአላህን ችሮታና ውዴታውን የሚፈልጉ፣ አላህንና መልክተኛውንም የሚረዱ ኾነው ከአገሮቻቸውና ከገንዘቦቻቸው ለተወጡት ስደተኞች ድኾች (ይስሰጣል)፡፡ እነዚያ እነርሱ እውነተኞቹ ናቸው፡፡ 59|9|እነዚያም ከበፊታቸው አገሪቱን መኖሪያ ያደረጉት እምነትንም የለመዱት ወደእነርሱ የተሰደዱትን ሰዎች ይወዳሉ፡፡ (ስደተኞቹ) ከተሰጡትም ነገር በልቦቻቸው ውስጥ ቅሬታን አያገኙም፡፡ በእነርሱ ላይ ችግር ቢኖርባቸውም በነፍሶቻቸው ላይ ሌላውን ይመርጣሉ፡፡ የነፍሱንም ንፍገት የሚጠበቅ ሰው እነዚያ እነሱ ምኞታቸውን አግኚዎች ናቸው፡፡ 59|10|እነዚያም ከበኋላቸው የመጡት «ጌታችን ሆይ! ለእኛም ለእነዚያም በእምነት ለቀደሙን ወንድሞቻችን ምሕረት አድርግ፡፡ በልቦቻችንም ውስጥ ለእነዚያ ለአመኑት (ሰዎች) ጥላቻን አታድርግ፡፡ ጌታችን ሆይ! አንተ ርኅሩህ አዛኝ ነህና» ይላሉ፡፡ 59|11|ወደእነዚያ ወደ ነፈቁት አላየህምን? ከመጽሐፉ ሰዎች ውስጥ ለእነዚያ ለካዱት ወንድሞቻቸው (ከአገር) «ብትባረሩ አብረናችሁ እንወጣለን፡፡ በእናንተም (ጉዳይ) አንድንም በፍጹም አንታዘዝም፡፡ ብትገድሉም በእርግጥ እንረዳችኋለን» ይሏቸዋል፡፡ አላህም እነርሱ ውሸታሞች መኾናቸውን ይመሰክራል፡፡ 59|12|ቢወጥጡ አብረዋቸው አይወጡም፤ ቢገደሉም አይረዱዋቸውም፡፡ ቢረዷቸውም (ለሽሽት) ጀርባቸውን ያዞራሉ፡፡ ከዚያም እርዳታን አያገኙም፡፡ 59|13|እናንተ በልቦቻቸው ውስጥ በማስፈራት ከአላህ ይልቅ የበረታችሁ ናችሁ፡፡ ይህ እነርሱ የማያውቁ ሕዝቦች በመኾናቸው ነው፡፡ 59|14|በተመሸጉ ከተሞች ውስጥ ወይም ከአጥሮች ጀርባ ኾነው እንጅ፤ የተሰበሰቡ ኾነው አይዋጉዋችሁም፡፡ ኀይላቸው በመካከላቸው ብርቱ ነው፡፡ ልቦቻቸው የተበታተኑ ሲኾኑ የተሰበሰቡ ናቸው ብለህ ትጠረጥራቸዋለህ፡፡ ይህ እነሱ አእምሮ የሌላቸው ሕዝቦች በመኾናቸው ነው፡፡ 59|15|(ብጤያቸው) እንደእነዚያ ከእነሱ በፊት በቅርብ ጊዜ የነገራቸውን ቅጣት እንደቀመሱት ብጤ ነው፡፡ ለእነርሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡ 59|16|እንደ ሰይጣን ብጤ ለሰውየው «ካድ» ባለው ጊዜና በካደም ጊዜ «እኔ ከአንተ ንጹሕ ነኝ እኔ አላህን የዓለማትን ጌታ እፈራለሁ» እንዳለው ነው፡፡ 59|17|መጨረሻቸውም እነርሱ በውስጡ ዘውታሪዎች ሲኾኑ በእሳት ውስጥ መኾን ነው፡፡ ይህም የበዳዮች ዋጋ ነው፡፡ 59|18|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ፡፡ ማንኛይቱም ነፍስ ለነገ ያስቀደመችውን ትመልከት፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 59|19|እንደነዚያም አላህን እንደረሱትና ነፍሶቻቸውን እንዳስረሳቸው (ሰዎች) አትኹኑ፡፡ እነዚያ እነርሱ አመጸኞቹ ናቸው፡፡ 59|20|የእሳት ጓዶችና የገነት ጓዶች አይተካከሉም፡፡ የገነት ጓዶች እነርሱ ምኞታቸውን አግኚዎች ናቸው፡፡ 59|21|ይህንን ቁርኣን በተራራ ላይ ባወረድነው ኖሮ ከአላህ ፍራቻ (የተነሳ) ተዋራጅ ተሰንጣቂ ኾኖ ባየኸው ነበር፡፡ ይህችንም ምሳሌ ይገመግሙ ዘንድ ለሰዎች እንገልፃለን፡፡ 59|22|እርሱ አላህ ነው፤ ያ ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ የሌለ፣ ሩቁንና ቅርቡን ዐዋቂ የኾነ ነው፡፡ እርሱ እጅግ በጣም ርኅሩህ በጣም አዛኝ ነው፡፡ 59|23|እርሱ አላህ ነው፡፡ ያ ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ የሌለ፣ ንጉሡ ከጉድለት ሁሉ የጠራው፣ የሰላም ባለቤቱ፣ ጸጥታን ሰጪው፣ ባሮቹን ጠባቂው፣ አሸናፊው፣ ኀያሉ፣ ኩሩው ነው፡፡ አላህ ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ፡፡ 59|24|እርሱ አላህ ፈጣሪው (ከኢምንት) አስገኚው፣ ቅርጽን አሳማሪው ነው፡፡ ለእርሱ መልካሞች ስሞች አልሉት፡፡ በሰማያትና በምድርም ያለው ሁሉ ለእርሱ ያሞግሳል፡፡ እርሱም 60|1|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ጠላቶቼንና ጠላቶቻችሁን ወዳጆች አድርገችሁ አትያዙ፡፡ ከእውነቱ የመጣላችሁን ሃይማኖት በእርግጥ የካዱ ሲኾኑ ውዴታን ወደእነርሱ ታደርሳላችሁ፡፡ መልክተኛውንና እናንተን በአላህ በጌታችሁ ስላመናችሁ (ከመካ) ያወጣሉ፡፡ በመንገዴ ለመታገልና ውዴታዬን ለመፈለግ የወጣችሁ እንደኾናችሁ (ወዳጆች አድርጋችሁ አትያዙዋቸው)፡፡ እኔ የምትደብቁትንና የምትገልጹትን ሁሉ የማውቅ ስኾን ወደእነርሱ በፍቅር ትመሳጠራላችሁ፡፡ ከእናንተም (ይህንን) የሚሠራ ሰው ቀጥተኛውን መንገድ በእርግጥ ተሳሳተ፡፡ 60|2|ቢያሸንፏችሁ ለእናንተ ጠላቶች ይኾናሉ፡፡ እጆቻቸውንና ምላሶቻቸውንም ወደእናንተ በክፉ ይዘረጋሉ፡፡ ብትክዱም ተመኙ፡፡ 60|3|ዘመዶቻችሁም፣ ልጆቻችሁም በትንሣኤ ቀን አይጠቅሟችሁም፤ (አላህ) በመካከላችሁ ይለያል፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 60|4|በኢብራሂምና በእነዚያ ከእርሱ ጋር በነበሩት (ምእምናን) መልካም መከተል አለቻችሁ፡፡ ለሕዝቦቻቸው «እኛ ከእናንተ ከአላህ ሌላ ከምትግገዙትም ንጹሖች ነን፡፡ በእናንተ ካድን፡፡ በአላህ አንድ ብቻ ሲኾን እስከምታምኑ ድረስ በእኛና በእናንተ መካከል ጠብና ጥላቻ ዘወትር ተገለጸ፡፡» ባሉ ጊዜ (መልካም መከተል አለቻችሁ)፡፡ ኢብራሂም ለአባቱ «እኔ ለአንተ ከአላህ (ቅጣት) ምንም የማልጠቅም ስኾን ለአንተ በእርግጥ ምሕረትን እለምንልኻለሁ» ማለቱ ብቻ ሲቀር፡፡ «ጌታችን ሆይ! በአንተ ላይ ተመካን፡፡ ወደ አንተም ተመለስን መመለሻም ወደ አንተ ብቻ ነው፤» (ባለው ተከተሉት)፡፡ 60|5|ጌታችን ሆይ! ለእነዚያ ለካዱት ሰዎች መሞከሪያ አታድርገን፡፡ ለእኛም ምሕረት አድርግልን፡፡ ጌታችን ሆይ! አንተ አሸናፊው ጥበበኛው አንተ ብቻ ነህ፡፡ 60|6|ለእናንተ አላህንና የመጨረሻውን ቀን ለሚፈራ ሰው በእነርሱ መልካም መከተል አልላችሁ፡፡ የሚዞርም ሰው (ራሱን ይጎዳል)፡፡ አላህ ተብቃቂው ምስጉኑ እርሱ ብቻ ነውና፡፡ 60|7|በናንተና በእነዚያ ከእነርሱ ጋር በተጣላችሁት ሰዎች መካከል አላህ መፋቀርን ሊያደርግ ይቻላል፡፡ አላህም ቻይ ነው፡፡ አላህም በጣም አዛኝ ነው፡፡ 60|8|ከእነዚያ በሃይማኖት ካልተጋደሏችሁ ከአገሮቻችሁም ካላወጡዋችሁ (ከሓዲዎች) መልካም ብትውሉላቸውና ወደእነርሱ ብታስተካክሉ አላህ አይከለክላችሁም፡፡ አላህ ትክክለኞችን ይወዳልና፡፡ 60|9|አላህ የሚከለክላችሁ ከእነዚያ በሃይማኖት ከተጋደሉዋችሁ፣ ከቤቶቻችሁም ካወጡዋችሁ፣ እናንተም በማውጣት ላይ ከረዱት (ከሓዲዎች) እንዳትወዳጁዋቸው ብቻ ነው፡፡ ወዳጅ የሚያደርጓቸውም ሰዎች እነዚያ እነርሱ በዳዮቹ ናቸው፡፡ 60|10|እላንተ ያመናችሁ ሆይ! ምእምናት ስደተኞች ኾነው በመጧችሁ ጊዜ (ለሃይማኖት መሰደዳቸውን) ፈትኑዋቸው፡፡ አላህ በእምነታቸው ይበልጥ ዐዋቂ ነው፡፡ አማኞችም መኾናቸውን ብትውቁ ወደ ከሓዲዎቹ አትመልሱዋቸው፡፡ እነርሱ (ሴቶቹ) ለእነርሱ የተፈቀዱ አይደሉምና፡፡ እነርሱም (ወንዶቹ) ለእነርሱ አይፈቀዱምና፡፡ ያወጡትንም ገንዘብ ስጧቸው፡፡ መህራቸውንም በሰጣችኋቸው ጊዜ ብታገቡዋቸው በእናንተ ላይ ኃጢአት የለባችሁም፡፡ የከሓዲዎቹንም ሴቶች የጋብቻ ቃል ኪዳኖች አትያዙ፤ ያወጣችሁትንም ገንዘብ ጠይቁ፡፡ ያወጡትንም ይጠይቁ፡፡ ይህ የአላህ ፍርድ ነው፡፡ በመካከላችሁ ይፈርዳል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡ 60|11|ከሚስቶቻችሁም ወደ ከሓዲዎቹ አንዳቸው ቢያመልጧችሁ ቀጥሎም ብትዘምቱባቸው ለእነዚያ ሚስቶቻቸው ለኼዱባቸው (ሰዎች) ያወጡትን ብጤ ስጧቸው፡፡ ያንንም እናንተ በርሱ ያመናችሁበትን አላህን ፍሩ፡፡ 60|12|አንተ ነቢዩ ሆይ! ምእምናቶቹ በአላህ ምንንም ላያጋሩ፣ ላይሰርቁም ላያመነዝሩም፣ ልጆቻቸውን ላይገድሉም፣ በእጆቻቸውና በእግሮቻቸው መካከልም የሚቀጣጥፉት የኾነን ኃጢኣት ላያመጡ (ላይሠሩ) በበጎም ሥራ ትዕዛዝህን ላይጥሱ ቃል ኪዳን ሊገቡልህ በመጡህ ጊዜ ኪዳን ተጋባቸው፡፡ ለእነርሱም አላህን ምሕረት ለምንላቸው፡፡ አላህ በጣም መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 60|13|እላንተ ያመናቸሁ ሆይ! አላህ በእነርሱ ላይ የተቆጣባቸውን ሕዝቦች አትወዳጁ፡፡ ከሓዲዎች ከመቃብር ሰዎች ተስፋ እንደቆረጡ ከመጨረሻይቱ ዓለም (ምንዳ) በእርግጥ ተስፋ ቆርጠዋል፡፡ 61|1|በሰማያት ውስጥ ያለው በምድርም ውስጥ ያለው ሁሉ ለአላህ አሞገሠ፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 61|2|እላንተ ያመናችሁ ሆይ! የማትሠሩትን ነገር ለምን ትናገራላችሁ? 61|3|የማትሠሩን ነገር መናገራችሁ አላህ ዘንድ መጠላቱ ተለቀ፡፡ 61|4|አላህ እነዚያን እነርሱ ልክ እንደ ተናሰ ግንብ የተሰለፉ ኾነው በመንገዱ (በሃይማኖቱ) የሚጋደሉትን ይወዳል፡፡ 61|5|ሙሳም ለሕዝቦቹ «ሕዝቦቼ ሆይ! እኔ ወደእናንተ የአላህ መልክተኛ መኾኔን በእርግጥ የምታውቁ ስትኾኑ ለምን ታሰቃዩኛላችሁ?» ባለ ጊዜ (አስታውስ፡፡ ከእውነት) በተዘነበሉም ጊዜ አላህ ልቦቻቸውን አዘነበላቸው፡፡ አላህም አመጸኞችን ሕዝቦች አያቀናም፡፡ 61|6|የመርየም ልጅ ዒሳም፡- «የእስራኤል ልጆች ሆይ! እኔ ከተውራት በፊቴ ያለውን የማረጋግጥና ከእኔ በኋላ በሚመጣው መልክተኛ ስሙ አሕመድ በኾነው የማበስር ስኾን ወደእናንተ (የተላክሁ) የአላህ መልክተኛ ነኝ» ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ በግልጽ ተዓምራቶች በመጣቸውም ጊዜ «ይህ ግልጽ ድግምት ነው» አሉ፡፡ 61|7|እርሱ ወደ ኢስላም የሚጥጠራ ሲኾን በአላህ ላይ ውሸትን ከቀጣጠፈ ሰውም ይበልጥ በደለኛ ማን ነው? አላህም በዳዮችን ሕዝቦች አይመራም፡፡ 61|8|የአላህን ብርሃን በአፎቻቸው ሊያጠፉ ይሻሉ፡፡ አላህም ከሓዲዎቹ ቢጠሉም እንኳ ብርሃኑን ገላጭ ነው፡፡ 61|9|እርሱ ያ አጋሪዎቹ ቢጠሉም መልክተኛውን በመምሪያ (መጽሐፍ) በእውነተኛው ሃይማኖትም (በኢስላም) ከሃይማኖት ሁሉ በላይ ይፋ ሊያደርገው የላከ ነው፡፡ 61|10|«እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከአሳማሚ ቅጣት የምታድናችሁ የኾነችን ንግድ ላመላክታችሁን?» (በላቸው)፡፡ 61|11|(እርሷም) በአላህና በመልክተኛው ታምናላችሁ፣ በአላህ መንገድም በገንዘቦቻችሁ በነፍሶቻችሁም ትታገላላችሁ፣ ይህ የምታውቁ ብትኾኑ ለእናንተ የተሻለ ነው፡፡ 61|12|ኃጢኣቶቻችሁን ለእናንተ ይምራል፡፡ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውንም ገነቶች ያገባችኋል፡፡ በመኖሪያ ገነቶችም በሚያማምሩ ቤቶች ውስጥ (ያስቀምጣችኋል)፡፡ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ 61|13|ሌላይቱንም የምትወዷትን (ጸጋ ይሰጣችኋለ)፡፡ ከአላህ የኾነ እርዳታና ቅርብ የኾነ የአገር መክፈት ነው፡፡ ምእምናንንም አብስር፡፡ 61|14|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! የመርየም ልጅ ዒሳ ለሐዋርያቶቹ «ወደ አላህ ረዳቴ ማነው?» እንዳለ ሐወርያቶቹም «እኛ የአላህ ረዳቶች ነን» እንዳሉት የአላህ ረዳቶች ኹኑ፡፡ ከእስራኤልም ልጆች አንደኛዋ ጭፍራ አመነች፡፡ ሌላይቱም ጭፍራ ካደች፡፡ እነዚያን ያመኑትንም በጠላታቸው ላይ አበረታናቸው፤ አሸናፊዎችም ኾኑ፡፡ 62|1|በሰማያት ያለው በምድርም ያለው ሁሉ ለአላህ ንጉሥ፣ ቅዱስ፣ አሸናፊ፣ ጥበበኛ ለኾነው ያሞግሳል፡፡ 62|2|እርሱ ያ በመሃይሞቹ ውስጥ አንቀጾቹን (ቁርኣንን) በእነርሱ ላይ የሚያነብላቸው፣ (ከማጋራት) የሚያጠራቸውም፣ መጽሐፍንና ጥበብን የሚያስተምራቸውም የኾነን መልክተኛ (ሙሐመድን) ከእነርሱው ውስጥ የላከ ነው፡፡ እነርሱም ከእርሱ በፊት በግልጽ ስሕተት ውስጥ ነበሩ፡፡ 62|3|ከነሱም ሌሎች ገና ያልተጠጉዋቸው በኾኑት ላይ (የላከው ነው)፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 62|4|ይህ የአላህ ችሮታ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው ይሰጠዋል፡፡ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡ 62|5|የእነዚያ ተውራትን የተጫኑትና ከዚያም ያልተሸከሟት (ያልሠሩባት) ሰዎች ምሳሌ መጽሐፎችን እንደሚሸከም አህያ ብጤ ነው፡፡ የእነዚያ በአላህ አንቀጾች ያስተባበሉት ሕዝቦች ምሳሌ ከፋ፡፡ አላህም በዳዮችን ሕዝቦች አይመራም፡፡ 62|6|«እናንተ አይሁዳውያን የኾናችሁ ሆይ! ከሰው ሁሉ በስተቀር እናንተ ብቻ ለአላህ ወዳጆች ነን ብትሉ እውነተኞች እንደኾናችሁ ሞትን ተመኙ» በላቸው፡፡ 62|7|እጆቻቸውም ባስቀደሙት ኃጢአት ምክንያት በፍጹም አይመኙትም፡፡ አላህም በዳዮቹን ዐዋቂ ነው፡፡ 62|8|«ያ ከእርሱ የምትሸሹት ሞት እርሱ በእርግጥ አግኛችሁ ነው፡፡ ከዚያም ሩቁንና ቅርቡን ዐዋቂ ወደ ኾነው ጌታ ትመለሳላችሁ፡፡ ትሠሩትም የነበራችሁትን ሁሉ ይነግራችኋል» በላቸው፡፡ 62|9|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በዐርብ ቀን ለስግደት ጥሪ በተደረገ ጊዜ ወደ አላህ ማውሳት ኺዱ፡፡ መሸጥንም ተዉ፡፡ ይህ የምታውቁ ብትኾኑ ለእናንተ በጣም የተሻለ ነወ፡፡ 62|10|ሶለቲቱም በተፈጸመች ጊዜ በምድር ላይ ተበተኑ፡፡ ከአላህም ችሮታ ፈልጉ፡፡ አላህንም በብዙ አውሱ፡፡ ልትድኑ ይከጀላልና፡፡ 62|11|ንግድን ወይም ዛዛታን ባዩ ጊዜም ቆመህ የተዉህ ሲኾኑ ወደእርሷ ይበተናሉ፡፡ አላህ ዘንድ ያለው ዋጋ ከዛዛታም ከንግድም በላጭ ነው፡፡ «አላህም ከሰጪዎቹ ሁሉ ይበልጥ ሲሳይን ሰጭ ነው» በላቸው፡፡ 63|1|መናፍቃን በመጡህ ጊዜ «አንተ የአላህ መልክተኛ መኾንህን በእርግጥ (ምለን) እንመሰክራለን» ይላሉ፡፡ አላህም አንተ በእርግጥ መልክተኛው መኾንህን ያውቃል፡፡ አላህም መናፍቃን (ከልብ እንመሰክራለን በማለታቸው) ውሸታሞች መኾናቸውን ይመሰክራል፡፡ 63|2|መሓሎቻቸውን ጋሻ አድርገው ያዙ፡፡ ከአላህም መንገድ ከለከሉ፡፡ እነርሱ ይሠሩት የነበሩት ነገር ከፋ፡፡ 63|3|ይህ እነርሱ (በምላስ) ያመኑ ከዚያም (በልብ) የካዱ በመኾናቸው ነው፡፡ በልቦቻቸውም ላይ ታተመባቸው፤ ስለዚህ እነርሱ አያውቁም፡፡ 63|4|ባየሃቸውም ጊዜ አካሎቻቸው (ግዙፍነታቸው) ያስደንቁሃል፡፡ ቢናገሩም ለንግግራቸው ታዳምጣለህ፤ (ከዕውቀት ባዶ በመኾን)፡፡ እነርሱ ልክ በግድግዳ የተጠጉ ግንዶችን ይመስላሉ፡፡ ጩኸትን ሁሉ በእነርሱ ላይ ነው ብለው ያስባሉ፡፡ እነርሱ ጠላቶች ናቸውና ተጠንቀቃቸው፡፡ አላህ ይጋደላቸው፤ (ከእምነት) እንዴት ይመለሳሉ! 63|5|ለእነሱም ፡- «ኑ የአላህ መልክተኛ ለእናንተ ምሕረትን ይለምንላችኋል፤» በተባሉ ጊዜ ራሶቻቸውን ያዞራሉ፡፡ እነርሱም ትዕቢተኞች ኾነው ሲሸሹ ታያቸዋለህ፡፡ 63|6|ምሕረትን ብትለምንላቸው ወይም ምሕረትን ባትለምንላቸው በእነርሱ ላይ እኩል ነው፡፡ አላህ ለእነርሱ በፍጹም አይምርም፡፡ አላህ አመጸኞችን ሕዝቦች አየመራምና፡፡ 63|7|እነርሱ እነዚያ ፡- «አላህ መልክተኛ ዘንድ ላሉት ሰዎች እስከሚበታተኑ ድረስ አትቀልቡ» የሚሉ ናቸው፡፡ የሰማያትና የምድር ድልቦችም የአላህ ናቸው፡፡ ግን መናፍቃን አያውቁም፡፡ 63|8|«ወደ መዲና ብንመለስ አሸናፊው ወራዳውን በእርግጥ ከእርሷ ያወጣል» ይላሉ፡፡ አሸናፊነትም ለአላህ፣ ለመልክተኛውና ለምእምናን ነው፡፡ ግን መናፍቃን አያውቁም፡፡ 63|9|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ገንዘቦቻችሁና ልጆቻችሁ አላህን ከማስታወስ አያታሉዋችሁ፡፡ ይህንንም የሚሠሩ ሰዎች እነዚያ እነርሱ ከሳሪዎች ናቸው፡፡ 63|10|አንዳችሁንም ሞት ሳይመጣውና ጌታዬ ሆይ! እንድመጸውትና ከደጋጐቹም ሰዎች እንድኾን ወደ ጥቂት ጊዜ ብታቆየኝ ኖሮ እመኛለሁ ከማለቱ በፊት ከሰጠናችሁ ሲሳይ ለግሱ፡፡ 63|11|ማንኛይቱም ነፍስ የሞት ጊዜዋ በመጣበት ጊዜ አላህ በፍጹም አያቆያትም፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡ 64|1|በሰማያት ውስጥ ያለው በምድርም ውስጥ ያለው ሁሉ ለአላህ ያሞግሳል፡፡ ንግሥናው የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ምስጋናም ለእርሱ ነው፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 64|2|እርሱ ያ የፈጠራችሁ ነው፡፡ ከእናንተም ከሓዲ አልለ፡፡ ከእናንተም አማኝ አልለ፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 64|3|ሰማያትንና ምድርን በእውነት ፈጠረ፡፡ ቀረጻችሁም ቅርጻችሁንም አሳመረ፡፡ መመለሻችሁም ወደእርሱ ነው፡፡ 64|4|በሰማያትና በምድር ውስጥ ያለውን ሁሉ ያውቃል፡፡ የምትደብቁትንም የምትገልጡትንም ያውቃል፡፡ አላህም በልቦች ውስጥ ያለውን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 64|5|የእነዚያ ከአሁን በፊት የካዱትና የክሕደታቸውን ቅጣት ቅመሱ የተባሉት ሕዝቦች ወሬ አልመጣላችሁምን? ለእነሱም አሳማሚ ቅጣት አልላቸው፡፡ 64|6|ይህ (ቅጣት) እርሱ መልክተኞቻቸው በአስረጂዎች ይመጡባቸው ስለ ነበሩ «ሰዎችም ይመሩናልን?» ስላሉና ስለካዱ (ከእምነት) ስለ ዞሩም ነው፡፡ አላህም (ከእነሱ እምነት) ተብቃቃ፡፡ አላህም ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡ 64|7|እነዚያ የካዱትን በፍጹም የማይቀሰሱ መኾናቸውን አሰቡ፡፡ «አይደለም በጌታዬ እምላለሁ፡፡ በእርግጥ ትቀሰቀሳላችሁ፡፡ ከዚያም በሠራችሁት ሁሉ ትነገራላችሁ፡፡ ይህም በአላህ ላይ ቀላል ነው፡፡» በላቸው፡፡ 64|8|በአላህና በመልክተኛውም፡፡ በዚያም ባወረድነው ብርሃን እመኑ፡፡ «አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው» (በላቸው)፡፡ 64|9|ለመሰብሰቢያ ቀን የሚሰበስብባችሁን ቀን (አስታውሱ)፤ ይህ የመጎዳዳት (መግለጫ) ቀን ነው፡፡ በአላህም የሚያምን ሰው መልካምንም የሚሠራ ከርሱ ኃጢአቶቹን ይሰርይለታል፤ (ይፍቅለታል)፤ ከሥሮቻቸውም ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘለዓለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ ያገባዋል፤ ይህ ታላቅ ማግኘት ነው፡፡ 64|10|እነዚያም የካዱና በአንቀጾቻችን ያስተባበሉ እነዚያ በውስጡ ዘውታሪዎች ሲኾኑ የእሳት ጓዶች ናቸው፤ መመለሻቸውም ከፋ! 64|11|ከመከራም (ማንንም) አይነካም በአላህ ፈቃድ ቢኾን እንጅ፤ በአላህም የሚያምን ሰው ልቡን (ለትዕግስት) ይመራዋል፤ አላህም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 64|12|አላህንም ተገዙ፤ መልክተኛውንም ታዘዙ፤ ብትዞሩም (መልክተኛውን አትጎዱም)፤ በመልክተኛውም ላይ ያለበት ግልጽ ማድረስ ብቻ ነው፡፡ 64|13|አላህ ከርሱ በቀር አምላክ የለም፤ በአላህም ላይ አማኞቹ ይመኩ፡፡ 64|14|እላንተ ያመናችሁ ሆይ! ከሚስቶቻችሁና ከልጆቻችሁ (ከአላህ መንገድ በማስተጓጎል) ለናንተ ጠላቶች የኾኑ አልሉ፤ ስለዚህ ተጠንቀቋቸው፤ ይቅርታ ብታደርጉ ብታልፏቸውም ብተምሩዋቸውም አላህ በጣም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 64|15|ገንዘቦቻችሁና ልጆቻችሁ ለናንተ መፈተኛ ብቻ ናቸው፤ አላህም እርሱ ዘንድ ታላቅ ምንዳ አልለ፡፡ 64|16|አላህንም የቻላችሁትን የክል ፍሩት፤ ትዕዛዙን ስሙም፤ ታዘዙም፤ ለግሱም፤ ለነፍሶቻችሁ መልካምን (ይሰጣችኋልና)፤ የነፍሱንም ንፍገት የሚጠበቅ ሰው እነዚያ እነሱ ፍላጎታቸውን የሚያገኙ ናቸው፡፡ 64|17|ለአላህ መልካም ብድርን ብታበድሩ (ምንዳውን) ለናንተ ይደራርበዋል፤ ለናንተም ይምራል፤ አላህም አመስጋኝ ታጋሽ ነው፡፡ 64|18|ሩቁን ምስጢር ግልጹንም ሁሉ ዐዋቂው አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡ 65|1|አንተ ነቢዩ ሆይ! ሴቶችን መፍታት ባሰባችሁ ጊዜ፤ ለዒዳቸው ፍቱዋቸው፡፡ ዒዳንም ቁጠሩ፡፡ አላህንም ጌታችሁን ፍሩ፡፡ ግልጽ የኾነችን ጠያፍ ካልሠሩ በስተቀር ከቤቶቻቸው አታውጡዋቸው፤ አይውጡም፡፡ ይህችም የአላህ ሕግጋት ናት፡፡ የአላህንም ሕግጋት የተላለፈ ሰው በእርግጥ ነፍሱን በደለ፡፡ ከዚህ (ፍች) በኋላ አላህ (የመማለስ) ነገርን ምናልባት ያመጣ እንደኾነ አታውቅም፡፡ 65|2|ጊዜያቸውንም ለመዳረስ በተቃረቡ ጊዜ በመልካም ያዙዋቸው፡፡ ወይም በመልካም ተለያዩዋቸው፡፡ ከእናንተም ውስጥ ሁለት የትክክለኛነት ባለቤቶችን አስመስክሩ፡፡ ምስክርነትንም ለአላህ አስተካክሉ፡፡ ይህ በአላህና በመጨረሻው ቀን የሚያምን የኾነ ሰው ሁሉ በእርሱ ይገሰጽበታል፡፡ አላህንም የሚፈራ ሰው ለእርሱ መውጫን ያደርግለታል፡፡ 65|3|ከማያስበውም በኩል ሲሳየን ይሰጠዋል፡፡ በአላህም ላይ የሚጠጋ ሰው እርሱ በቂው ነው፡፡ አላህ ፈቃዱን አድራሽ ነው፡፡ አላህ ለነገሩ ሁሉ የተወሰነ ጊዜን በእርግጥ አድርጓል፡፡ 65|4|እኒያም ከሴቶቻቸው ከአደፍ ያቋረጡት (በዒዳቸው ሕግ) ብትጠራጠሩ ዒዳቸው ሦስት ወር ነው፡፡ እኒያም ገና አደፍን ያላዩት (ዒዳቸው እንደዚሁ ነው)፡፡ የእርግዝና ባለቤቶችም ጊዜያቸው እርጉዛቸውን መውለድ ነው፡፡ አላህንም የሚፈራ ሰው ከነገሩ ሁሉ ለርሱ መግራትን ያደርግለታል፡፡ 65|5|ይህ የአላህ ፍርድ ነው፡፡ ወደእናንተ አወረደው፡፡ አላህንም የሚፈራ ሰው ኀጢኣቶቹን ከእርሱ ይሰርይለታል፡፡ ምንዳንም ለእርሱ ያተልቅለታል፡፡ 65|6|ከችሎታችሁ ከተቀመጣችሁበት ስፍራ አስቀምጧቸው፡፡ በእነርሱም ላይ ልታጣብቡ አትጉዷቸው፡፡ የእርግዝና ባለቤቶችም ቢኾኑ እርጉዛቸውን እስኪወልዱ ድረስ በእነርሱ ላይ ቀልቡ፡፡ ለእናንተም (ልጆቻችሁን) ቢያጠቡላችሁ ምንዳዎቻቸውን ስጧቸው፡፡ በመካከላችሁም በመልካም ነገር ተመካከሩ፡፡ ብትቸጋገሩም ለእርሱ ሌላ (ሴት) ታጠባለታለች፡፡ 65|7|የችሎታ ባለቤት ከችሎታው ይቀልብ፡፡ በእርሱም ላይ ሲሳዩ የተጠበበበት ሰው አላህ ከሰጠው ይቀልብ አላህ ነፍስን የሰጣትን እንጅ አያስገድድም፡፡ አላህ ከችግር በኋላ ምቾትን በእርግጥ ያደርጋል፡፡ 65|8|ከከተማም ከጌታዋ ትዕዛዝ ከመልክተኞቹም ያመጸች፣ ብርቱንም ቁጥጥር የተቆጣጠርናት፣ መጥፎንም ቅጣት የቀጣናት ብዙ ናት፡፡ 65|9|የነገርዋንም ቅጣት ቀመሰች፡፡ የነገርዋም መጨረሻ ከሳራ ኾነ፡፡ 65|10|አላህ ለእነርሱ ብርቱን ቅጣት አዘጋጀ፡፡ እናንተም የአእምሮ ባለቤቶች ሆይ! አላህን ፍሩ፡፡ እነዚያ ያመኑ (ሆይ)! አላህ ወደናንተ ግሳጼን በእርግጥ አወረደ፡፡ መልክተኛን (ላከ)፡፡ 65|11|እነዚያን ያመኑትንና መልካሞችን የሠሩትን ከጨለማዎች ወደ ብርሃን ያወጣ ዘንድ የአላህን አንቀጾች ገላጮች ሲኾኑ በእናንተ ላይ የሚያነብላችሁን (ላከ)፡፡ በአላህም አንቀጾች የሚያምን፣ መልካምን ሥራ የሚሠራም ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈስሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘለዓለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ ያገባዋል፡፡ አላህ ለእርሱ ሲሳይን በእርግጥ አሳመረ፡፡ 65|12|አላህ ያ ሰባትን ሰማያት የፈጠረ ነው፡፡ ከምድርም መሰላቸውን (ፈጥሮአል)፤ በመካከላቸው ትእዛዙ ይወርዳል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ መኾኑን አላህም በነገሩ ሁሉ በዕውቀት ያካበበ መኾኑን በዕውቀት ያካበበ መኾኑን ታወቁ ዘንድ (ይህንን አሳወቃችሁ)፡፡ 66|1|አንተ ነቢዩ ሆይ! አላህ ለአንተ የፈቀደልህን ነገር ሚስቶችህን ማስወደድን የምትፈልግ ስትኾን (ባንተ ላይ) ለምን እርም ታደርጋለህ? አላህም እጅግ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡ 66|2|አላህ ለእናንተ የመሓሎቻችሁን መፍቻ ደነገገላችሁ፡፡ አላህም ረዳታችሁ ነው፡፡ እርሱም ዐዋቂው ጥበበኛው ነው፡፡ 66|3|ነቢዩ ከሚስቶቹ ወደ አንዷ ወሬን በመሰጠረ ጊዜ (አስታውስ)፡፡ እርሱንም በነገረችና አላህ እርሱን (ማውራትዋን) ባሳወቀው ጊዜ ከፊሉን አስታወቀ፡፡ ከፊሉንም ተወ፡፡ በእርሱም ባወራት ጊዜ «ይህን ማን ነገረህ?» አለች፡፡ «ዐዋቂው ውስጠ ዐዋቂው ነገረኝ» አላት፤ 66|4|ወደ አላህ ብትመለሱ ልቦቻችሁ በእርግጥ ተዘንብለዋልና (ትስማማላችሁ)፡፡ በእርሱም ላይ ብትረዳዱ አላህ እርሱ ረዳቱ ነው፡፡ ጂብሪልም ከምእምናንም መልካሙ ከዚህም በኋላ መላእክቱ ረዳቶቹ ናቸው፡፡ 66|5|(መላችሁንም) ቢፈታችሁ ከእናንተ የበለጡ ሚስቶችን ሙስሊሞች፣ አማኞች፣ ታዛዦች፣ ተጸጻቾች፣ (ለአላህ) ተገዢዎች፣ ጾመኛዎች ፈቶች፣ ደናግልም የኾኑትን ጌታው ሊለውጠው ይከጀላል፡፡ 66|6|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ነፍሶቻችሁንና ቤተሰቦቻችሁን መቀጣጠያዋ ሰዎችና ደንጋዮች ከኾነች እሳት ጠብቁ፡፡ በእርሷ ላይ ጨካኞች፣ ኀይለኞች የኾኑ መላእክት አልሉ፡፡ አላህን ያዘዛቸውን ነገር (በመጣስ) አያምጹም፡፡ የሚታዘዙትንም ሁሉ ይሠራሉ፡፡ 66|7|እላንተ የካዳችሁ ሆይ! ዛሬ አታመካኙ፡፡ የምትመነዱት ያንን ትሠሩት የነበራችሁትን ብቻ ነው (ይባላሉ)፡፡ 66|8|እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ንጹሕ የኾነችን ጸጸት በመጸጸት ወደ አላህ ተመለሱ፡፡ ጌታችሁ ከእናንተ ኀጢኣቶቻችሁን ሊሰርይላችሁ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውንም ገነቶች ሊያስገባችሁ ይከጀላልና፡፡ አላህ ነቢዩን፣ እነዚያንም ከእርሱ ጋር ያመኑትን በማያሳፍርበት ቀን ብርሃናቸው በፊቶቻቸውና በቀኞቻቸው የሚሮጥ ሲኾን «ጌታችን ሆይ! ብርሃናችንን ሙላልን፣ ለእኛ ምሕረትም አድርግልን፣ አንተ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነህና» ይላሉ፡፡ 66|9|አንተ ነቢዩ ሆይ! ከሓዲዎችንና መናፍቃንን ታገል፡፡ በእነርሱም ላይ በርታ፡፡ መኖሪያቸውም ገሀነም ናት፡፡ ምን ትከፋም መመለሻ! 66|10|አላህ ለእነዚያ ለካዱት ሰዎች የኑሕን ሴትና የሉጥን ሴት ምሳሌ አደረገ፡፡ ከባሮቻችን ከኾኑ ሁለት መልካም ባሪያዎች ሥር ነበሩ፡፡ ከዱዋቸውም፡፡ ከአላህም (ቅጣት ኑሕና ሉጥ) ከሚስቶቻቸው ምንም አልገፈተሩላቸውም፡፡ ከገቢዎቹም ጋር «እሳትን ግቡ» ተባሉ፡፡ 66|11|ለእነዚያ ለአመኑትም የፈርኦንን ሴት አላህ ምሳሌ አደረገ፡፡ «ጌታዬ ሆይ! አንተ ዘንድ በገነት ውስጥ ለእኔ ቤትን ገንባልኝ፡፡ ከፈርዖንና ከሥራውም አድነኝ፡፡ ከበደለኞቹ ሕዝቦችም አድነኝ» ባለች ጊዜ፡፡ 66|12|የዒምራንን ልጅ መርየምንም ያችን ብልቷን የጠበቀችውን (ምሳሌ አደረገ)፡፡ በእርሱም ውስጥ ከመንፈሳችን ነፍፋን፡፡ በጌታዋ ቃላትና በመጻሕፍቱም አረጋገጠች፡፡ ከታዛዦቹም ነበረች፡፡ 67|1|ያ ንግሥና በእጁ የኾነው አምላክ ችሮታው በዛ፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡ 67|2|ያ የትኛችሁ ሥራው ይበልጥ ያማረ መኾኑን ሊሞክራችሁ ሞትንና ሕይወትን የፈጠረ ነው፡፡ እርሱም አሸናፊው መሓሪው ነው፡፡ 67|3|ያ ሰባትን ሰማያት የተነባበሩ ኾነው የፈጠረ ነው፡፡ በአልረሕማን አፈጣጠር ውስጥ ምንም መዛነፍን አታይም፡፡ ዓይንህንም መልስ፡፡ «ከስንጥቆች አንዳችን ታያለህን?» 67|4|ከዚያም ብዙ ጊዜ ዓይንህን መላልስ፡፡ ዓይንህ ተዋርዶ እርሱም የደከመ ኾኖ ወዳንተ ይመለሳል፡፡ 67|5|ቅርቢቱን ሰማይም በእርግጥ በመብራቶች (በከዋክብት) አጌጥናት፡፡ ለሰይጣናትም መቀጥቀጫዎች አደረግናት፡፡ ለእነርሱም (ለሰይጣኖች) የእሳትን ቅጣት አዘጋጀን፡፡ 67|6|ለእነዚያም በጌታቸው ለካዱት የገሀነም ቅጣት አልላቸው፡፡ መመለሻይቱም ከፋች! 67|7|በውስጧ በተጣሉ ጊዜ፤ እርሷ የምትፈላ ስትኾን ለእርሷ (እንደ አህያ) ማናፋትን ይሰማሉ፡፡ 67|8|ከቁጭትዋ የተነሳ ልትቆራረጥ ትቀርባለች፡፡ በውስጧ ጭፍሮች በተጣሉ ቁጥር ዘበኞችዋ «አስፈራሪ (ነቢይ) አልመጣችሁምን?» በማለት ይጠይቋቸዋል፡፡ 67|9|«አይደለም በእርግጥ አስፈራሪ መጥቶናል፡፡ አስተባበልንም፡፡ አላህም ምንንም አላወረደ እናንተ (አውርዷል ስትሉ) በትልቅ ስህተት ውስጥ እንጅ አይደላችሁም አልን» ይላሉ፡፡ 67|10|«የምንሰማ ወይም የምናስብ በነበርንም ኖሮ በነዳጅ እሳት ጓዶች ውስጥ ባልኾን ነበር» ይላሉ፡፡ 67|11|በኀጢኣታቸውም ያምናሉ ለእሳት ጓዶችም (ከእዝነት) መራቅ ተገባቸው፡፡ 67|12|እነዚያ ጌታቸውን በሩቁ የሚፈሩ ለእነርሱ ምሕረትና ታላቅ ምንዳ አልላቸው፡፡ 67|13|(ሰዎች ሆይ!) ቃላችሁንም መስጥሩ፡፡ ወይም በእርሱ ጩሁ፡፡ እርሱ በልቦች ውስጥ ያለን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡ 67|14|የፈጠረ አምላክ እርሱ ዕውቀት ረቂቁ፣ ውስጥ ዐዋቂው ሲኾን (ምስጢርን ሁሉ) አያውቅምን? 67|15|እርሱ ያ ምድርን ለእናንተ የተገራች ያደረገላችሁ ነው፡፡ በጋራዎችዋና በመንገዶችዋም ኺዱ፡፡፡ ከሲሳዩም ብሉ፡፡ (ኋላ) መመለሻውም ወደእርሱ ብቻ ነው፡፡ 67|16|በሰማይ ውስጥ ያለን (ሰራዊት) በእናንተ ምድርን ቢደረባባችሁ ወዲያውም እርሷ የምታረገርግ ብትኾን ትተማመናላችሁን? (አትፈሩምን?) 67|17|ወይም በሰማይ ውስጥ ያለን በእናንተ ላይ ጠጠርን ያዘለች ነፋስን ቢልክባችሁ ትተማመናላችሁን? (አትፈሩምን?) ማስጠንቀቄም እንዴት እንደኾነ ወደፊት ታውቃላችሁ፡፡ 67|18|እነዚያም ከእነርሱ በፊት የነበሩት በእርግጥ አስተባበሉ፡፡ ጥላቻዬም እንዴት ነበር! 67|19|ወደ አእዋፍ ከበላያቸው ክንፎቻቸውን ዘርግተው ተንሳፋፊዎች የሚሰበሰቡም ሲኾኑ አላዩምን? ከአልረሕማን በቀር (ባየር ላይ) የሚይዛቸው የለም፡፡ እርሱ በነገሩ ሁሉ ተመልካች ነው፡፡ 67|20|በእውነቱ ያ እርሱ ከአልረሕማን ሌላ የሚረዳችሁ ለእናንተ የኾነ ሰራዊት ማነው? ከሓዲዎች በመታለል ውስጥ እንጅ በሌላ ላይ አይደሉም፡፡ 67|21|ወይም ሲሳዩን ቢይዝባችሁ ያ ሲሳይን የሚሰጣችሁ ማነው? በእውነቱ እነርሱ በሞገድና በመደንበር ውስጥ ችክ አሉ፡፡ 67|22|በፊቱ ላይ ተደፍቶ የሚኼድ ሰው ይበልጥ የቀና ነውን? ወይስ በቀጥተኛ መንገድ ላይ ተስተካክሎ የሚኼድ? 67|23|«እርሱ ያ የፈጠራችሁ ለእናንተም መስሚያና ማያዎችን፣ ልቦችንም ያደረገላችሁ ነው፡፡ ጥቂትንም አታመስግኑም» በላቸው፡፡ 67|24|«እርሱ ያ በምድር ላይ የበተናቸሁ ነው፡፡ ወደእርሱም ትሰበሰባላችሁ» በላቸው፡፡ 67|25|«እውነተኞችም እንደኾናችሁ ይህ ቀጠሮ መቼ ነው?» ይላሉ፡፡ 67|26|«ዕውቀቱ አላህ ዘንድ ብቻ ነው፡፡ እኔ ግልጽ አስፈራሪ እንጅ ሌላ አይደለሁም» በላቸው፡፡ 67|27|(ቅጣቱን) ቅርብ ኾኖ ባዩትም ጊዜ የእነዚያ የካዱት ሰዎች ፊቶች ይክከፋሉ፡፡ «ይህ ያ በእርሱ ትከራከሩበት የነበራችሁት ነው» ይባላሉም፡፡ 67|28|«አያችሁን? አላህ ቢገድለኝ ከእኔ ጋር ያሉትንም (እንደዚሁ) ወይም (በማቆየት) ቢያዝንልን ከሓዲዎችን ከአሳማሚ ቅጣት የሚያድን ማን ነው?» በላቸው፡፡ 67|29|«እርሱ (እመኑበት የምላችሁ) አልረሕማን ነው፡፡ (እኛ) በእርሱ አመንን፡፡ በርሱም ላይ ተጠጋን፡፡ ወደ ፊትም በግልጽ መሳሳት ውስጥ የኾነው እርሱ ማን አንደ ኾነ በእርግጥ ታውቃላችሁ» በላቸው፡፡ 67|30|«አያችሁን? ውሃችሁ ሠራጊ ቢኾን ፈሳሺን ውሃ የሚያመጣላቸሁ ማን ነው?» በላቸው፡፡ (አላህ የዓለማት ጌታ ያመጣዋል)፡፡ 68|1|ነ.(ኑን)፤ በብርእ እምላለሁ በዚያም (መልአኮች) በሚጽፉት፡፡ 68|2|አንተ በጌታህ ጸጋ የተጎናጸፍክ ስትኾን ዕብድ አይደለህም፡፡ 68|3|ላንተም (ከጌታህ) የማይቋረጥ ዋጋ በእርግጥ አልለህ፡፡ 68|4|አንተም በታላቅ ጠባይ ላይ ነህ፡፡ 68|5|ወደፊትም ታያለህ፤ ያያሉም፡፡ 68|6|ዕብደት በማንኛችሁ እንዳልለ፡፡ 68|7|ጌታህ እርሱ ከመንገዱ የተሳሳተውን ሰው ዐዋቂ ነው፡፡ እርሱም ተመሪዎቹን ዐዋቂ ነው፡፡ 68|8|ለአስተባባዮችም አትታዝዙ፡፡ 68|9|ብትመሳሰላቸውና ቢመሳሰሉህ ተመኙ፡፡ 68|10|ወራዳንም ሁሉ አትታዘዝ፡፡ 68|11|ሰውን አነዋሪንና በማሳበቅ ኼያጅን፡፡ 68|12|ለበጎ ነገር በጣም ከልካይን፣ ወሰን አላፊን፣ ኃጢአተኛን፤ 68|13|ልበ ደረቅን፣ ከዚህ በኋላ ዲቃላን (ሁሉ አትታዘዝ)፡፡ 68|14|የገንዘብና የልጆች ባለቤት በመኾኑ (ያስተባብላል)፡፡ 68|15|በእርሱ ላይ አንቀጾቻችን በሚነበቡ ጊዜ «የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ተረቶች ናቸው» ይላል፡፡ 68|16|በአፍንጫው ላይ በእርግጥ (የሚነወርበት) ምልክት እናደርግበታለን፡፡ 68|17|እኛ የአትክልቲቱን ባለቤቶቸ እንደ ሞከርን (የመካን ሰዎች) ሞከርናቸው፡፡ ማልደው (ፍሬዋን) ሊለቅሟት በማሉ ጊዜ፡፡ 68|18|(በመሓላቸው) አያስቀሩምም፡፡ 68|19|እነርሱ የተኙ ኾነውም ሳሉ ከጌታህ የኾነ ዟሪ በእርሷ ላይ ዞረባት፡፡ 68|20|እንደ ሌሊት ጨለማም ኾና አነጋች፤ (ከሰለች)፡፡ 68|21|ያነጉም ኾነው ተጠራሩ፡፡ 68|22|«ቆራጮች እንደ ኾናችሁ በእርሻቸሁ ላይ ማልዱ» በማለት፡፡ 68|23|እነርሱ የሚንሾካሾኩ ኾነው ኼዱም፡፡ 68|24|ዛሬ በእናንተ ላይ ድኻ እንዳይገባት በማለት፡፡ 68|25|(ድኾችን) በመከልከልም ላይ (በሐሳባቸው) ቻዮች ኾነው ማለዱ፡፡ 68|26|(ተቃጥላ) ባዩዋትም ጊዜ «እኛ በእርግጥ ተሳሳቾች ነን» አሉ፡፡ 68|27|«ይልቁንም እኛ የተከለከልን ነን» አሉ፡፡ 68|28|ትክክለኛቸው «ለእናንተ አላህን ለምን አታጠሩም አላልኳችሁምን?» አላቸው፡፡ 68|29|«ጌታችን ጥራት ይገባው፡፡ እኛ በዳዮች ነበርን፤» አሉ፡፡ 68|30|የሚወቃቀሱም ኾነው ከፊሎቻቸው በከፊሉ ላይ መጡ፡፡ 68|31|«ዋ ጥፋታችን! እኛ ድንበር አላፊዎች ነበርን፤» አሉ፡፡ 68|32|«ጌታችን ከእርሷ የተሻለን (አትክልት) ሊለውጠን ይከጀላል፡፡ እኛ ወደ ጌታችን ከጃዮች ነን፤» (አሉ)፡፡ 68|33|ቅጣቱ እንደዚሁ ነው፡፡ የመጨረሻይቱም ዓለም ቅጣት ታላቅ ነው፡፡ የሚያውቁት በኾኑ ኖሮ (በተጠነቀቁ ነበር)፡፡ 68|34|ለጥንቁቆቹ በጌታቸው ዘንድ መጠቀሚያ ገነቶች አሏቸው፡፡ 68|35|ሙስሊሞቹን እንደ ከሓዲዎች እናደርጋለን? 68|36|ለእናንተ ምን (አስረጅ) አላችሁ? እንዴት ትፈርዳላችሁ፡፡ 68|37|በእውነቱ ለእናንተ በእርሱ የምታጠኑበት መጽሐፍ አላችሁን? 68|38|በውስጡ ለእናንተ የምትመርጡት አላችሁ (የሚል) 68|39|ወይስ ለእናንተ የምትፈርዱት አላችሁ በማለት (ቃል ኪዳን የገባንላችሁ) እስከ ትንሣኤ ቀን ደራሽ የኾኑ መሓላዎች ለእናንተ በእኛ ላይ አሏችሁን? 68|40|በዚህ ማንኛቸው ተያያዥ እንደ ኾነ ጠይቃቸው፡፡ 68|41|ወይስ ለእነርሱ (በፍርዳቸው ተስማሚ) «ተጋሪዎች» አሏቸውን? እውነተኞችም እንደኾኑ «ተጋሪዎቻቸውን» ያምጡ፡፡ 68|42|ባት የሚገለጥበትን (ከሓዲዎች) ወደ መስገድም የሚጥጠሩበትንና የማይችሉበት ቀን (አስታውስ)፡፡ 68|43|ዓይኖቻቸው የፈሩ ውርደት የምትሸፍናቸው ሲኾኑ፤ (ወደ ስግደት የሚጠሩበትን)፤ እነርሱም (በምድረ ዓለም) ደህና ኾነው ሳሉ ወደ ስግደት በእርግጥ ይጠሩ ነበሩ፡፡ 68|44|በዚህም ንግግር ከሚያስተባብሉት ሰዎች ጋር ተዎኝ፡፡ (እነርሱን እኔ እበቃሃለሁ)፡፡ ከማያውቁት ስፍራ አዘናግተን እንይዛቸዋለን፡፡ 68|45|እነርሱንም አዘገያለሁ፡፡ ዘዴዬ ብርቱ ነውና፡፡ 68|46|በእውነቱ ዋጋን ትጠይቃቸዋለህን? ስለዚህ እነርሱ ከዕዳ የተከበዱ ናቸውን? 68|47|ወይስ እነርሱ ዘንድ የሩቁ ምስጢር ዕውቀት አልለን? ስለዚህ እነርሱ ይጽፋሉን? 68|48|ለጌታህም ፍርድ ታገሥ፤ (በመበሳጨትና ባለ መታገሥ) እንደ ዓሣው ባለቤትም (እንደ ዮናስ) አትኹን፡፡ እርሱ በጭንቀት የተመላ ኾኖ (ጌታውን) በተጣራ ጊዜ፡፡ 68|49|ከጌታው የኾነ ጸጋ ባላገኘው ኖሮ በምድረ በዳ ተወቃሽ ኾኖ በተጣለ ነበር፡፡ 68|50|ጌታውም (በነቢይነት) መረጠው፡፡ ከደጋጎቹም አደረገው፡፡ 68|51|እነሆ እነዚያም የካዱት ሰዎች ቁርኣኑን በሰሙ ጊዜ በዓይኖቻቸው ሊጥሉህ (ሊያጠፉህ) ይቀርባሉ፡፡ «እርሱም በእርግጥ ዕብድ ነው» ይላሉ፡፡ 68|52|ግን እርሱ (ቁርኣን) ለዓለማት መገሰጫ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ 69|1|እውነትን አረጋጋጪቱ (ትንሣኤ)፡፡ 69|2|አረጋጋጪቱም (እርሷ) ምንድን ናት! 69|3|አረጋጋጪቱም ምን እንደኾነች ምን አሳወቀህ? 69|4|ሰሙድና ዓድ በቆርቋሪይቱ (ትንሣኤ) አስተባበሉ፡፡ 69|5|ሠሙድማ ወሰን በሌላት ጩኸት ተጠፋ፤ (ተወደሙ)፡፡ 69|6|ዓድማ በኀይል በምትንሻሻ ብርቱ ነፋስ ተጠፉ፡፡ 69|7|ተከታታይ በኾኑ ሰባት ሌሊቶችና ስምንት መዓልቶች ውስጥ በእነርሱ ላይ ለቀቃት፡፡ ሕዝቦቹንም፤ በውስጧ የተጣሉ ኾነው ልክ ክፍት የኾኑ የዘንባባ ግንዶች መስለው ታያቸዋለህ፡፡ 69|8|ለእነርሱም ቀሪን ታያለህን? 69|9|ፈርዖን ከበፊቱ የነበሩትም ሰዎች ተገልባጮቹም (ከተሞች) በኀጢአት (ሥራዎች) መጡ፡፡ 69|10|የጌታቸውንም መልእክተኛ ትዕዛዝ ጣሱ፡፡ የበረታችንም አያያዝ ያዛቸው፡፡ 69|11|እኛ ውሃው ባየለ ጊዜ በተንሻላይቱ ታንኳ ውስጥ ጫንናችሁ፡፡ 69|12|ለእናንተ መገሰጫ ልናደርጋት አጥኒ የኾነችም ጆሮ ታጠናት ዘንድ፡፡ 69|13|በቀንዱም አንዲት መንነፋት በተነፋች ጊዜ፡፡ 69|14|ምድርና ጋራዎችም (ከስፍራቸው) በተነሱና አንዲትን መሰባበር በተሰባበሩ ጊዜ፡፡ 69|15|በዚያ ቀን ኋኝቱ (ትንሣኤ) ትኾናለች፡፡ 69|16|ሰማይም ትቀደዳለች፡፡ ስለዚህ እርሷ በዚያ ቀን ደካማ ናት፡፡ 69|17|መላእክትም በየጫፎችዋ ላይ ይኾናሉ፡፡ የጌታህንም ዐርሽ በዚያ ቀን ስምንት መላእክት ከበላያቸው ይሸከማሉ፡፡ 69|18|በዚያ ቀን ከእናንተ ተደባቂ (ነገሮች) የማይደበቁ ሲኾኑ ትቅቀረባላችሁ፡፡ 69|19|መጽሐፉን በቀኙ የተሰጠ ሰውማ (ለጓደኞቹ) «እንኩ፤ መጽሐፌን አንብቡ» ይላል፡፡ 69|20|«እኔ ምርመራየን የምገናኝ መኾኔን አረጋገጥኩ፤» (ተዘጋጀሁም ይላል)፡፡ 69|21|እርሱም በተወደደች ኑሮ ውሰጥ ይኾናል፡፡ 69|22|በከፍተኛይቱ ገነት ውስጥ፡፡ 69|23|ፍሬዎችዋ ቅርቦች የኾኑ፡፡ 69|24|በአለፉት ቀናት ውስጥ (በምድረ ዓለም) ባስቀደማችሁት ምክንያት ብሉ፤ ጠጡም፤ (ይባላሉ)፡፡ 69|25|መጽሐፉንም በግራው የተሰጠማ «ዋ ጥፋቴ! ምነው መጽሐፌን ባልተሰጠሁ» ይላል፡፡ 69|26|«ምርመራየንም ምን እንደኾነ ባላወቅኩ፡፡ 69|27|«እርሷ (ሞት ሕይወቴን) ምነው ፈጻሚ በኾነች፡፡ 69|28|«ገንዘቤ ከእኔ ምንንም አላብቃቃኝ፤ (አልጠቀመኝም)፡፡ 69|29|«ኀይሌ ከእኔ ላይ ጠፋ» (ይላል)፡፡ 69|30|«ያዙት፤ እሰሩትም፡፡ 69|31|«ከዚያም በእሳት ውሰጥ አግቡት፡፡ 69|32|«ከዚያም ርዝመቷ ሰባ ክንድ በኾነች ሰንሰለት ውስጥ አግቡት፡፡» 69|33|እርሱ ታላቅ በኾነው አላህ አያምንም ነበርና፡፡ 69|34|ድኾችንም በማብላት ላይ አያግባባም ነበርና፡፡ 69|35|ለእርሱም ዛሬ እዚህ ዘመድ የለውም፡፡ 69|36|ምግብም ከእሳት ሰዎች ቁስል እጣቢ (እዥ) በስተቀር የለውም፡፡ 69|37|ኀጢኣተኞች እንጅ ሌላ አይበላውም፤ (ይባላል)፡፡ 69|38|በምታዩትም ነገር እምላለሁ፡፡ 69|39|በማታዩትም ነገር፡፡ 69|40|እርሱ (ቁርኣን) የተከበረ መልክተኛ ቃል ነው፡፡ 69|41|እርሱም የባለቅኔ ቃል (ግጥም) አይደለም፡፡ ጥቂትን ብቻ ታምናላችሁ፡፡ 69|42|የጠንቋይም ቃል አይደለም፡፡ ጥቂትን ብቻ ታስታውሳላችሁ፡፡ 69|43|ከዓለማት ጌታ የተወረደ ነው፡፡ 69|44|በእኛ ላይም ከፊልን ቃላት (ያላልነውን) በቀጠፈ ኖሮ፤ 69|45|በኀይል በያዝነው ነበር፡፡ 69|46|ከዚያም ከእርሱ የልቡን ሥር (የተንጠለጠለበትን ጅማት) በቆረጥን ነበር፡፡ 69|47|ከእናንተም ውስጥ ከእርሱ ላይ ከልካዮች ምንም አይኖሩም፡፡ 69|48|እርሱም (ቁርኣን) ለጥንቁቆቹ መገሠጫ ነው፡፡ 69|49|እኛም ከእናንተ ውስጥ አስተባባዮች መኖራቸውን በእርግጥ እናውቃለን፡፡ 69|50|እርሱም (ቁርኣን) በከሓዲዎቹ ላይ ጸጸት ነው፡፡ 69|51|እርሱም የተረጋገጠ እውነት ነው፡፡ 69|52|የታላቁን ጌታህንም ስም አወድስ፡፡ 70|1|ወዳቂ ከኾነው ቅጣት ጠያቂ ጠየቀ፡፡ 70|2|በከሓዲዎች ላይ (ወዳቂ ከኾነው) ለእርሱ መላሽ የለውም፡፡ 70|3|የ(ሰማያት) መሰላሎች ባለቤት ከኾነው አላህ (መላሽ የለውም)፡፡ 70|4|መላእክቱና መንፈሱም ልኩ አምሳ ሺሕ ዓመት በኾነ ቀን ውስጥ ወደእርሱ ያርጋሉ፤ (ይወጣሉ)፡፡ 70|5|መልካምንም ትዕግስት ታገሥ፡፡ 70|6|እነርሱ (ያንን ቀን) ሩቅ አድርገው ያዩታል፡፡ 70|7|እኛም ቅርብ ኾኖ እናየዋለን፡፡ 70|8|ሰማይ እንደ ዘይት አተላ በምትኾንበት ቀን፡፡ 70|9|ጋራዎችም በተለያዩ ቀለማት እንደ ተነከረ ሱፍ (ነፋስ እንደሚያበረው) በሚኾኑበት ቀን፡፡ 70|10|ዘመድም ዘመድን በማይጠይቅበት ቀን፤ (መላሽ የለውም)፡፡ 70|11|(ዘመዶቻቸውን) ያዩዋቸዋል፡፡ አመጸኛው ከዚያ ቀን ስቃይ (ነፍሱን) በልጆቹ ሊበዥ ይመኛል፡፡ 70|12|በሚስቱም በወንድሙም፡፡ 70|13|በዚያችም በምታስጠጋው ጎሳው፡፡ 70|14|በምድርም ላይ ባለው ሁሉ (ሊበዥ) ከዚያም ሊያድነው (ይመኛል)፡፡ 70|15|ይተው! እርሷ (እሳቲቱ) ለዟ ናት፡፡ 70|16|የራስን ቅል ቆዳ የምትሞሽልቅ ስትኾን፡፡ 70|17|(ከእምነት) የዞረንና የሸሸን ሰው (ወደእርሷ) ትጠራለች፡፡ 70|18|ገንዘብን የሰበሰበንና (ዘካውን ሳይሰጥ) የቆጠረንም፤ (ትጠራለች)፡፡ 70|19|ሰው ቅጠ ቢስ ኾኖ ተፈጠረ፡፡ 70|20|ክፉ ነገር ባገኘው ጊዜ ብስጪተኛ፡፡ 70|21|መልካምም ነገር (ድሎት) ባገኘ ጊዜ ከልካይ (ኾኖ ተፈጠረ)፡፡ 70|22|ሰጋጆቹ ብቻ ሲቀሩ፡፡ 70|23|እነዚያ እነርሱ በስግደታቸው ላይ ዘውታሪዎች የኾኑት፡፡ 70|24|እነዚያም በገንዘቦቻቸው ላይ የታወቀ መብት ያለባቸው የኾኑት፡፡ 70|25|ለለማኝ ከልመና ለሚከለከልም (መብት ያለባቸው የኾኑት)፡፡ 70|26|እነዚያም በፍርዱ ቀን እውነት የሚሉት (የሚያረጋግጡት)፡፡ 70|27|እነዚያም እነርሱ ከጌታቸው ቅጣት ፈሪዎች የኾኑት፡፡ 70|28|የጌታቸው ቅጣት (መምጣቱ) የማያስተማምን ነውና፡፡ 70|29|እነዚያም እነርሱ ብልቶቻቸውን ጠባቂዎች የኾኑት፡፡ 70|30|በሚስቶቻቸው ወይም እጆቻቸው በያዙዋቸው (ባሪያዎች) ላይ ሲቀር፡፡ እነርሱ (በእነዚህ) የማይወቀሱ ናቸውና፡፡ 70|31|ከዚያም ወዲያ የፈለገ ሰው እነዚያ እነሱ ድንበር አላፊዎች ናቸው፡፡ 70|32|እነዚያም እነርሱ አደራዎቻቸውንና ቃል ኪዳናቸውን ጠባቂዎች የኾኑት፡፡ 70|33|እነዚያም እነርሱ በምስክርነታቸው ትክክለኞች የኾኑት፡፡ 70|34|እነዚያም እነርሱ በሶላቶቻቸው ላይ የሚጠባበቁት፡፡ 70|35|እነዚህ (ከዚህ በላይ የተወሱት ሁሉ) በገነቶች ውስጥ የሚከበሩ ናቸው፡፡ 70|36|ለእነዚያም ለካዱት ወደ አንተ በኩል አንገቶቻቸውን መዝዘው የሚያተኩሩት ምን አላቸው? 70|37|ከቀኝና ከግራ ክፍልፍል ጭፍሮች ሲኾኑ፡፡ 70|38|ከእነርሱ እያንዳንዱ ሰው የጸጋይቱን ገነት መግባትን ይከጅላልን? 70|39|ይከልከል፤ እኛ ከሚያውቁት ነገር (ከፍቶት ጠብታ) ፈጠርናቸው፡፡ 70|40|በምሥራቆችና በምዕራቦችም ጌታ እምላለሁ፡፡ እኛ በእርግጥ ቻዮች ነን፡፡ 70|41|ከእነርሱ የተሻለን በመለወጥ ላይ፡፡ እኛም ተሸናፊዎች አይደለንም፡፡ 70|42|ያንንም የሚስፈራሩበትን ቀናቸውን እስከሚገናኙ ድረስ ተዋቸው፡፡ ይዋኙ ይጫወቱም፡፡ 70|43|ወደ ጣዖቶች እንደሚሽቀዳደሙ ኾነው ከመቃብሮቻቸው ፈጥነው የሚወጡበትን ቀን (እስከሚገናኙ ድረስ ተዋቸው)፡፡ 70|44|ዓይኖቻቸው ያፈሩ ኾነው ውርደት ትሸፍናቸዋለች፡፡ ይህ ቀን ያ ይስፈራሩበት የነበሩት ነው፡፡ 71|1|እኛ ኑሕን «ሕዝቦችህን አሳማሚ ቅጣት ሳይመጣባቸው በፊት አስጠንቅቅ በማለት ወደ ሕዝቦቹ ላክነው፡፡» 71|2|(እርሱም) አለ «ሕዝቦቼ ሆይ! እኔ ለእናንተ ገላጭ የኾንኩ አስጠንቃቂ ነኝ፡፡ 71|3|«አላህን ተገዙት፣ ፍሩትም፣ ታዘዙኝም በማለት፤ (አስጠንቃቂ ነኝ)፡፡ 71|4|«ለእናንተ ከኀጢኣቶቻችሁ ይምራልና፡፡ ወደተወሰነው ጊዜም ያቆያችኋል፡፡ የአላህ (የወሰነው) ጊዜ በመጣ ወቅት አይቆይም፡፡ የምታውቁት ብትኾኑ ኖሮ (በታዘዛችሁ ነበር)፡፡» 71|5|(ስለ ተቃወሙትም) «አለ ጌታዬ ሆይ! እኔ ሌሊትም ቀንም ሕዝቦቼን ጠራሁ፡፡ 71|6|«ጥሪየም መሸሽን እንጅ ሌላ አልጨመረላቸውም፡፡ 71|7|«እኔም ለእነርሱ ትምር ዘንድ (ወደ እምነት) በጠራኋቸው ቁጥር ጣቶቻቸውን በጆሮዎቻቸው ውስጥ አደረጉ፡፡ ልብሶቻቸውንም ተከናነቡ፡፡ (በመጥፎ ሥራቸው ላይ) ዘወተሩም፡፡ (ያለ ልክ) መኩራትንም ኮሩ፡፡ 71|8|«ከዚያም እኔ በጩኸት ጠራኋቸው፡፡ 71|9|«ከዚያም እኔ ለእነርሱ ገለጽኩ፡፡ ለእነርሱም መመስጠርን መሰጠርኩ 71|10|«አልኳቸውም፡- ጌታችሁን ምሕረትን ለምኑት፡፡ እርሱ በጣም መሐሪ ነውና፡፡ 71|11|«በእናንተ ላይ ዝናምን ተከታታይ አድርጎ ይልካል፡፡ 71|12|«በገንዘቦችና በልጆችም ይለግሰላችኋል፡፡ ለእናንተም አትክልቶችን ያደርግላችኋል፡፡ ለእናንተም ወንዞችን ያደርግላችኋል፡፡» 71|13|ለአላህ ልቅናን የማትሹት ለእናንተ ምን አላችሁ? 71|14|በልዩ ልዩ ኹኔታዎች በእርግጥ የፈጠራችሁ ሲኾን፡፡ 71|15|አላህ ሰባትን ሰማያት አንዱ ካንዱ በላይ ሲኾን እንዴት እንደፈጠረ አታዩምን? 71|16|በውስጣቸውም ጨረቃን አብሪ አደረገ፡፡ ፀሐይንም ብርሃን አደረገ፡፡ 71|17|አላህም ከምድር ማብቀልን አበቀላችሁ፡፡ 71|18|ከዚያም በውስጧ ይመልሳችኋል፡፡ ማውጣትንም ያወጣችኋል፡፡ 71|19|አላህም ምድርን ለእናንተ ምንጣፍ አደረጋት፡፡ 71|20|ከእርሷ ሰፋፊዎችን መንገዶች ትገቡ ዘንድ፡፡ 71|21|ኑሕ አለ፡- «ጌታዬ ሆይ! እነሱ አምመጹብኝ፡፡ ገንዘቡና ልጁም ከጥፋት በስተቀር ያልጨመረለትን ሰው ተከተሉ፡፡ 71|22|«ታላቅንም ተንኮል የመከሩትን ሰዎች» (ተከተሉ)፡፡ 71|23|አሉም «አምላኮቻችሁን አትተዉ፡፡ ወድንም፣ ሱዋዕንም፣ የጉሥንም፣ የዑቅንም ነስርንም አትተው፡፡ 71|24|«በእርግጥም ብዙዎችን አሳሳቱ፡፡ ከሓዲዎችንም ጥመትን እንጅ ሌላን አትጨምርላቸው» (አለ)፡፡ 71|25|በኀጢኣቶቻቸው ምክንያት ተሰጠሙ፡፡ እሳትንም እንዲገቡ ተደረጉ፡፡ ለእነርሱም ከአላህ ሌላ የኾኑ ረዳቶችን አላገኙም፡፡ 71|26|ኑሕም አለ «ጌታዬ ሆይ! ከከሓዲዎቹ በምድር ላይ አንድንም አትተው፡፡ 71|27|«አንተ ብትተዋቸው ባሮችህን ያሳስታሉና፡፡ ኀጢኣተኛ ከሓዲንም እንጅ ሌላን አይወልዱም፡፡ 71|28|«ጌታዬ ሆይ! ለእኔም ለወላጆቼም ምእመን ኾኖ በቤቴ ለገባም ሰው ሁሉ ለምእመናንና ለምእምናትም ምሕረት አድርግ፡፡ ከሓዲዎችንም ከጥፋት በቀር አትጨምርላቸው፤» (አለ)፡፡ 72|1|(ሙሐመድ ሆይ!) በል «እነሆ ከጂን የኾኑ ጭፈሮች (ቁርኣንን) አዳመጡ፡፡‹እኛ አስደናቂ የኾነን ቁርኣን ሰማንም› አሉ ማለት ወደእኔ ተወረደ፡፡ 72|2|‹ወደ ቀጥታ መንገድ የሚመራን (ቁርአን ሰማን)፡፡ በእርሱም አመንን፡፡ በጌታችንም አንድንም አናጋራም፡፡› 72|3|‹እነሆም የጌታችን ክብር ላቀ፡፡ ሚስትንም ልጅንም አልያዘም፡፡› 72|4|‹እነሆም ቂላችን በአላህ ላይ ወሰን ያለፈን (ውሸት) ይናገር ነበር፡፡› 72|5|‹እኛም ሰዎችና ጋኔኖች በአላህ ላይ ውሸትን (ቃል) አይናገሩም ማለትን ጠረጠርን፡፡› 72|6|‹እነሆም ከሰዎች የኾኑ ወንዶች በጋኔን ወንዶች ይጠበቁ ነበሩ፡፡ ኩራትንም ጨመሩዋቸው፡፡› 72|7|‹እነርሱም አላህ አንድንም አይቀሰቅስም ማለትን እንደጠረጠራችሁ ጠረጠሩ፡፡› 72|8|‹እኛም ሰማይን (ለመድረስ) ፈለግን፡፡ ብርቱ ጠባቂዎችንና ችቦዎችንም ተሞልታ አገኘናት፡፡ 72|9|‹እኛም ከእርሷ (ወሬን) ለማደመጥ በመቀመጫዎች እንቀመጥ ነበርን፡፡ አሁን ግን የሚያዳምጥ ሰው ለእርሱ ተጠባባቂ ችቦን ያገኛል፡፡ 72|10|‹እኛም በምድር ውስጥ ባልሉ ሰዎች ክፉ ተሽቷል? ወይስ በእነርሱ ጌታቸው ደግን ነገር ሽቷል? ማለትን አናውቅም፡፡ 72|11|‹እኛም ከእኛ ውስጥ ደጎች አልሉ፡፡ ከኛም ከዚህ ሌላ የኾኑ አልሉ፡፡ የተለያዩ መንገዶች (ባለ ቤቶች) ነበርን፡፡ 72|12|‹እኛም አላህን በምድር ውስጥ ፈጽሞ የማናቅተው፤ ሸሽተንም ፈጽሞ የማናመልጠው መኾናችንን አረጋገጥን፡፡ 72|13|‹እኛም መሪውን በሰማን ጊዜ በርሱ አመንን፡፡ በጌታውም የሚያምን ሰው መግጎደልንም መጭጨመርንም አይፈራም፡፡ 72|14|«እኛም ከእኛ ውስጥ ሙስሊሞች አልሉ፡፡ ከእኛም ውስጥ በዳዮች አልሉ፡፡ የሰለሙም ሰዎች እነዚያ ቅንን መንገድ መረጡ፡፡» 72|15|በዳዮቹማ ለገሀነም ማገዶ ኾኑ፡፡ 72|16|እነሆም በመንገዲቱ ላይ ቀጥ ባሉ ኖሮ ብዙ ዝናምን ባጠጣናቸው ነበር (ማለትም ተወረደልኝ)፡፡ 72|17|በእርሱ ልንሞክራቸው (ባጠጣናቸው ነበር)፡፡ ከጌታውም ማስታወሻ የሚያፈገፍግ ሰው አስቸጋሪን ቅጣት ያገባዋል፡፡ 72|18|እነሆ መስጊዶችም የአላህ ብቻ ናቸው፡፡ (በውስጣቸው) ከአላህ ጋር አንድንም አትገዙ (ማለትም)፡፡ 72|19|እነሆም የአላህ ባሪያ (ሙሐመድ አላህን) የሚጠራው ኾኖ በተነሳ ጊዜ (ጋኔኖች) በእርሱ ላይ ድርብርቦች ሊኾኑ ቀረቡ (ማለትም)፡፡ 72|20|«እኔ የምግገዛው ጌታየን ብቻ ነው፡፡ በእርሱም አንድንም አላጋራም» በል፡፡ 72|21|«እኔ ለእናንተ ጉዳትንም ቀጥታንም አልችልም» በላቸው፡፡ 72|22|«እኔ ከአላህ (ቅጣት) አንድም አያድነኝም፡፡ ከእርሱም ሌላ መጠጊያን አላገኝም» በላቸው፡፡ 72|23|«ከአላህ የኾነ ማድረስን መልክቶቹንም በስተቀር (አልችልም)፡፡ አላህንና መልክተኛውንም የሚያምጽ ሰው ለእርሱ የገሀነም እሳት አልለው፡፡ በውስጧ ዘላለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ፡፡» 72|24|የሚስፈራሩበትንም ባዩ ጊዜ ረዳቱ ደካማ፣ ቁጥሩም አነስተኛ የኾነው ማን እንደኾነ በእርግጥ ያውቃሉ፡፡ 72|25|«የምትስፈራሩበት ነገር ቅርብ ወይም ጌታየ ለእርሱ የተወሰነ ጊዜን የሚያደርግለት (ሩቅ) መኾኑን አላውቅም» በላቸው፡፡ 72|26|«(እርሱ) ሩቁን ምስጢር ዐዋቂ ነው፡፡ በምስጢሩም ላይ አንድንም አያሳውቅም፡፡» 72|27|ከመልክተኛ ለወደደው ቢኾን እንጅ (ለሌላ አይገልጽም)፡፡ እርሱም ከስተፊቱም ከስተኋላውም ጠባቂዎችን ያደርግለታል፡፡ 72|28|እነርሱ ዘንድ ባለው ነገር ዕውቀቱ የከበበና ነገሩንም ሁሉ በቁጥር ያጠቃለለ ሲኾን የጌታቸውን መልክቶች ያደረሱ መኾናቸውን ያውቅ ዘንድ (ጠባቂ ያደርጋል)፡፡ 73|1|አንተ ተከናናቢው ሆይ፡፡ 73|2|ሌሊቱን ሁሉ ጥቂት ሲቀር ቁም፤ (ስገደ)፡፡ 73|3|ግማሹን (ቁም)፤ ወይም ከርሱ ጥቂትን ቀንስ፡፡ 73|4|ወይም በእርሱ ላይ ጨምር፡፡ ቁርኣንንም በዝግታ ማንበብን አንብብ፡፡ 73|5|እኛ ባንተ ላይ ከባድ ቃልን እንጥላለንና፡፡ 73|6|የሌሊት መነሳት እርሷ (ሕዋሳትንና ልብን) ለማስማማት በጣም ብርቱ ናት፡፡ ለማንበብም ትክክለኛ ናት፡፡ 73|7|ላንተ በቀን ውስጥ ረዥም መዘዋወር አልለህ፡፡ 73|8|የጌታህንም ስም አውሳ፤ ወደእርሱም (መግገዛት) መቋረጥን ተቋረጥ ፡፡ 73|9|(እርሱም) የምሥራቅና የምዕራብ ጌታ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ መጠጊያ አድርገህም ያዘው፡፡ 73|10|(ከሓዲዎች) በሚሉትም ላይ ታገሥ፡፡ መልካምንም መተው ተዋቸው፡፡ 73|11|የድሎት ባለቤቶችም ከኾኑት አስተባባዮች ጋር ተዎኝ፡፡ ጥቂትንም ጊዜ አቆያቸው፡፡ 73|12|እኛ ዘንድ ከባድ ማሰሪያዎች እሳትም አልለና፡፡ 73|13|የሚያንቅ ምግብም፤ አሳማሚ ቅጣትም (አልለ) 73|14|ምድርና ገራዎች በሚርገፈገፉበት፣ ጋራዎችም ፈሳሽ የአሸዋ ክምር በሚኾኑበት ቀን፡፡ 73|15|እኛ በእናንተ ላይ መስካሪ መልክተኛን ወደእናንተ ላክን፡፡ ወደ ፈርዖን መልክተኛን እንደላክን፡፡ 73|16|ፈርዖንም መልክተኛውን አመጸ፤ ብርቱ መያዝንም ያዝነው፡፡ 73|17|ብትክዱ ልጆችን ሸበቶዎች የሚያደርገውን ቀን (ቅጣት) እንዴት ትጠበቃላችሁ፡፡ 73|18|ሰማዩ በርሱ (በዚያ ቀን) ተሰንጣቂ ነው፡፡ ቀጠሮው ተፈጻሚ ነው፡፡ 73|19|ይህቺ መገሠጫ ናት፡፡ (መዳንን) የሻም ሰው ወደ ጌታው መንገድን ይይዛል፡፡ 73|20|አንተ ከሌሊቱ ሁለት እጅ ያነሰን ግማሹንም ሲሶውንም የምትቆም መኾንህን ጌታህ በእርግጥ ያውቃል፡፡ ከእነዚያም አብረውህ ካሉት ከፊሎች (የሚቆሙ መኾናቸውን ያውቃል)፡፡ አላህም ሌሊትንና ቀንን ይለክካል፡፡ (ሌሊቱን) የማታዳርሱት መኾናችሁን ዐወቀ፡፡ በእናንተ ላይም (ወደ ማቃለል) ተመለሰላችሁ፡፡ ስለዚህ ከቁርኣን (በስግደት) የተቻላችሁን አንብቡ፡፡ ከእናንተ ውስጥ በሽተኞች፣ ሌሎችም ከአላህ ችሮታ ለመፈለግ በምድር ላይ የሚጓዙ፣ ሌሎችም በአላህ መንገድ (ሃይማኖት) የሚጋደሉ እንደሚኖሩ ዐወቀ፡፡ (አቃለለላቸውም)፡፡ ከእርሱም የተቻለችሁን አንብቡ፡፡ ሶላትንም ስገዱ፡፡ ዘካንም ስጡ፡፡ ለአላህም መልካም ብደርን አበድሩ፡፡ ከመልካም ሥራም ለነፍሶቻችሁ የምታስቀድሙትን ሁሉ እርሱ የተሻለና በምንዳም ታላቅ ኾኖ አላህ ዘንድ ታገኙታላችሁ፡፡ አላህንም ምሕረትን ለምኑት፡፡ አላህ በጣም መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡ 74|1|አንተ (ልብስህን) ደራቢው ሆይ! 74|2|ተነሳ አስጠንቅቅም፡፡ 74|3|ጌታህንም አክብር፡፡ 74|4|ልብስህንም አጥራ፡፡ 74|5|ጣዖትንም ራቅ፡፡ 74|6|ማብዛትንም የምትፈልግ ኾነህ፤ (በረከትን) አትለግስለለ 74|7|ለጌታህም (ትዕዛዝ) ታገሥ፡፡ 74|8|በቀንዱም በተነፋ ጊዜ (ነገሩ ይበረታል)፡፡ 74|9|ይህም (ጊዜ) ያ ቀን አስቸጋሪ ቀን ነው፡፡ 74|10|በከሓዲዎች ላይ ገር ያልኾነ ነው፡፡ 74|11|አንድ ኾኖ ከፈጠርኩት ሰው ጋር ተዎኝ (እኔ እበቃሃለሁ)፡፡ 74|12|ለእርሱም የተዘረጋን ገንዘብ (በያይነቱ) ያደረግሁለት፡፡ 74|13|(በያደባባዩ) ተገኝዎች የኾኑ ወንዶች ልጆችንም፡፡ 74|14|ለእርሱም (ኑሮውን) መዘርጋትን የዘረጋሁለት (ከኾነ ሰው ገር ተዎኝ)፡፡ 74|15|ከዚያም ልጨምርለት ይከጅላል፡፡ 74|16|ይከልከል፤ እርሱ ለአንቀጾቻችን በእርግጥ ተቃዋሚ ነበር፡፡ 74|17|በእርግጥ ችግርን አስገድደዋለሁ፡፡ 74|18|እርሱ (በቁርኣን ነገር) ሐሰበ፤ ገመተም፡፡ 74|19|ተረገመም፤ እንዴት ገመተ! 74|20|ከዚያም (ከሞት በኋላ) ተረገመ፡፡ እንዴት ገመተ! 74|21|ከዚያም እንደ ገና (በቁርኣኑ ነገር) ተመለከተ፡፡ 74|22|ከዚያም ፊቱን አጨፈገገ፤ አኮማተረም፡፡ 74|23|ከዚያም (ከማመን) ዞረ፤ ኮራም፡፡ 74|24|አለም «ይህ (ከሌላ) የሚቀዳ ድግምት እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ 74|25|«ይህ የሰው ቃል እንጅ ሌላ አይደለም፡፡» 74|26|በሰቀር ውስጥ በእርግጥ አገባዋለሁ፡፡ 74|27|ሰቀር ምን እንደኾነች ምን አሳወቀህ? 74|28|(ያገኘችውን ሁሉ) አታስቀርም አትተውምም፡፡ 74|29|ቆዳን በጣም አክሳይ ናት፡፡ 74|30|በእርሷም ላይ አሥራ ዘጠኝ (ዘበኞች) አሉባት፡፡ 74|31|የእሳትንም ዘበኞች መላእክት እንጅ ሌላ አላደረግንም፡፡ ቁጥራቸውንም ለእነዚያ ለካዱት መፈተኛ እንጅ አላደረግንም፡፡ እነዚያ መጽሐፍን የተሰጡት እንዲያረጋግጡ፣ እነዚያም ያመኑት እምነትን እንዲጨምሩ፣ እነዚያም መጽሐፍን የተሰጡትና ምእምናኖቹ እንዳይጠራጠሩ፣ እነዚያም በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ያለባቸው (መናፍቃን)፣ ከሓዲዎችም አላህ በዚህ (ቁጥር) ምን ምሳሌ ሽቷል? እንዲሉ (እንጅ አላደረግንም)፡፡ እንደዚሁ አላህ የሚሻውን ያጠምማል፡፡ የሚሻውንም ያቀናል፡፡ የጌታህንም ሰራዊት (ልክ) ከርሱ በቀር ማንም አያውቅም፡፡ እርሷም (የሰቀር እሳት) ለሰዎች መገሰጫ እንጅ ሌላ አይደለችም፡፡ 74|32|(ከክህደት) ይከልከሉ፡፡ በጨረቃ እምላለሁ፡፡ 74|33|በሌሊቱም በኼደ ጊዜ፡፡ 74|34|በንጋቱም ባበራ ጊዜ፡፡ 74|35|እርሷ (ሰቀር) ከታላላቆቹ (አደጋዎች) አንዷ ናት፡፡ 74|36|ለሰዎች አስፈራሪ ስትኾን፡፡ 74|37|ከእናንተ (ወደ በጎ ነገር) መቅደምን ወይም ወደ ኋላ መቅረትን ለሻ ሰው (አስፈራሪ ስትኾኑ)፡፡ 74|38|ነፍስ ሁሉ በሠራችው ሥራ ተያዥ ናት፡፡ 74|39|የቀኝ ባለቤቶች ብቻ ሲቀሩ፡፡ 74|40|(እነርሱስ) በገነቶች ውስጥ ይጠያየቃሉ፡፡ 74|41|ከአመጸኞቹ ኹነታ፡፡ 74|42|(ይሏቸዋልም) «በሰቀር ውስጥ ምን አገባችሁ?» 74|43|(እነርሱም) ይላሉ «ከሰጋጆቹ አልነበርንም፡፡ 74|44|«ለድኾችም የምናበላ አልነበርንም፡፡ 74|45|«ከዘባራቂዎቹም ጋር እንዘባርቅ ነበርን፡፡ 74|46|«በፍርዱ ቀንም እናስተባብል ነበርን፡፡ 74|47|«እርግጠኛው (ሞት) እስከ መጣን ድረስ፡፡» 74|48|የአማላጆችም ምልጃ አትጠቅማቸውም፡፡ 74|49|ከግሣጼዬም (ከቁርኣን) የሚያፈገፍጉት ለእነርሱ ምን አልላቸው? 74|50|እነርሱ ልክ ደንባሪዎች የሜዳ አህዮች ይመስላሉ፡፡ 74|51|ከዐንበሳ የሸሹ፡፡ 74|52|ይልቁንም ከእነርሱ እያንዳንዱ ሰው ሁሉ የተዘረጉ ጽሑፎችን እንዲስሰጥ ይፈልጋል፡፡ 74|53|ይከልከሉ፡፡ ይልቁንም የመጨረሻይቱን ዓለም (ቅጣት) አይፈሩም፡፡ 74|54|ይከልከሉ፡፡ እርሱ (ቁርኣን) መገሠጫ ነው፡፡ 74|55|ስለዚህ የሻ ሰው ይገሰጽበታል፡፡ 74|56|አላህም ካልሻ በስተቀር አይገሠጹም፡፡ እርሱ (አላህ) የመፈራት ባለቤት የምሕረትም ባለቤት ነው፡፡ 75|1|(ነገሩ ከሓዲዎች እንደሚሉት) አይደለም፡፡ በትንሣኤ ቀን እምላለሁ፡፡ 75|2|(ራሷን) ወቃሽ በኾነች ነፍስም እምላለሁ፡፡ (በእርግጥ ትቀሰቀሳላችሁ)፡፡ 75|3|ሰው አጥንቶቹን አለመሰብሰባችንን ያስባልን? 75|4|አይደለም ጣቶቹን (ፊት እንደ ነበሩ) በማስተካከል ላይ ቻዮች ስንኾን (እንሰበስባቸዋለን)፡፡ 75|5|ይልቁንም ሰው በፊቱ ባለው ነገር (በትንሣኤ) ሊያስተባብል ይፈልጋል፡፡ 75|6|«የትንሣኤው ቀን መቼ ነው?» ሲል ይጠይቃል፡፡ 75|7|ዓይንም በዋለለ ጊዜ፡፡ 75|8|ጨረቃም በጨለመ ጊዜ፡፡ 75|9|ፀሐይና ጨረቃም በተሰበሰቡ ጊዜ፡፡ 75|10|«ሰው በዚያ ቀን መሸሻው የት ነው?» ይላል፡፡ 75|11|ይከልከል፤ ምንም መጠጊያ የለም፡፡ 75|12|በዚያ ቀን መርጊያው ወደ ጌታህ ብቻ ነው፡፡ 75|13|ሰው በዚያ ቀን ባስቀደመውና ባስቆየው ሁሉ ይነገራል፡፡ 75|14|በእርግጥም ሰው በነፍሱ ላይ አስረጅ ነው፡፡ (አካሎቹ ይመሰክሩበታል)፡፡ 75|15|ምክንያቶቹን ሁሉ ቢያመጣም እንኳ (አይሰማም)፡፡ 75|16|በእርሱ (በቁርኣን ንባብ) ልትቸኩል ምላስህን በእርሱ አታላውስ፡፡ 75|17|(በልብህ ውስጥ) መሰብሰቡና ማንበቡ በእኛ ላይ ነውና፡፡ 75|18|ባነበብነውም ጊዜ (ካለቀ በኋላ) ንባቡን ተከተል፡፡ 75|19|ከዚያም ማብራራቱ በእኛ ላይ ነው፡፡ 75|20|(ከመጣደፍ) ተከልከል፡፡ ይልቁንም (ሰዎች) ፈጣኒቱን (ዓለም) ትወዳላችሁ፡፡ 75|21|መጨረሻይቱንም (ዓለም) ትተዋላችሁ፡፡ (አትዘጋጁላትም)፡፡ 75|22|ፊቶች በዚያ ቀን አብሪዎች ናቸው፡፡ 75|23|ወደ ጌታቸው ተመልካቾች ናቸው፡፡ 75|24|ፊቶችም በዚያ ቀን ጨፍጋጊዎች ናቸው፡፡ 75|25|በርሳቸውም ዐደጋ እንደሚሠራባቸው ያረጋግጣሉ፡፡ 75|26|ንቁ (ነፍስ) ብሪዎችን በደረሰች ጊዜ፤ 75|27|«አሻሪው ማነው?» በተባለም ጊዜ፡፡ 75|28|(ሕመምተኛው) እርሱ (የሰፈረበት ነገር ከዚህ ዓለም) መልለየት መኾኑን ባረጋገጠም ጊዜ፡፡ 75|29|ባትም በባት በተጣበቀች ጊዜ፡፡ 75|30|በዚያ ቀን መነዳቱ ወደ ጌታህ (ፍርድ) ነው፡፡ 75|31|አላመነምም አልሰገደምም፡፡ 75|32|ግን አስተባበለ፤ (ከእምነት) ዞረም፡፡ 75|33|ከዚያም እየተንጎባለለ ወደ ቤተሰቡ ኼደ፡፡ 75|34|የምትጠላውን ነገር (አላህ) ያስከትልህ፡፡ ለአንተ ተገቢህም ነው፡፡ 75|35|ከዚያም ጥፋት ይጠጋህ ለአንተ የተገባህም ነው፡፡ 75|36|ሰው ስድ ኾኖ መትተውን ይጠረጥራልን? 75|37|የሚፈሰስ ከኾነ የፍትወት ጠብታ አልነበረምን? 75|38|ከዚያም የረጋ ደም ኾነ (አላህ ሰው አድርጎ) ፈጠረውም፡፡ አስተካከለውም፡፡ 75|39|ከእርሱም ሁለት ዓይነቶችን ወንድና ሴትን አደረገ፡፡ 75|40|ይህ (ጌታ) ሙታንን ሕያው በማድረግ ላይ ቻይ አይደለምን? 76|1|በሰው ላይ የሚታወስ ነገር ሳይኾን ከዘመናት የተወሰነ ጊዜ በእርግጥ አልፎበታል፡፡ 76|2|እኛ ሰውን (በሕግ ግዳጅ) የምንሞከረው ስንኾን ቅልቅሎች ከኾኑ የፍትወት ጠብታ ፈጠርነው፡፡ ሰሚ ተመልካችም አደረግነው፡፡ 76|3|እኛ ወይ አመስጋኝ ወይም ከሓዲ ሲኾን መንገዱን መራነው፤ (ገለጽንለት)፡፡ 76|4|እኛ ለከሓዲዎች ሰንሰሎቶችንና እንዛዝላዎችን፣ እሳትንም አዘጋጅተናል፡፡ 76|5|በጎ አድራጊዎች መበረዣዋ ካፉር ከኾነች ጠጅ ይጠጣሉ፡፡ 76|6|ከእርሷ የአላህ ባሮች የሚጠጡላት (ወደፈለጉበት) ማንቧቧትን የሚያንቧቧት ከኾነች ምንጭ (ይጠጣሉ)፡፡ 76|7|(ዛሬ) በስለታቸው ይሞላሉ፡፡ መከራው ተሰራጪ የኾነንም ቀን ይፈራሉ፡፡ 76|8|ምግብንም ከመውደዳቸው ጋር ለድኻ፣ ለየቲምም፣ ለምርኮኛም ለእስረኛም ያበላሉ፡፡ 76|9|«የምናበላችሁ ለአላህ ውዴታ ብቻ ነው፡፡ ከእናንተ ዋጋንም ማመስገንንም አንፈልግም፡፡ 76|10|«እኛ (ፊትን) የሚያጨፈግግን ብርቱ ቀን ከጌታችን እንፈራለንና፤» (ይላሉ)፡፡ 76|11|አላህም የዚያን ቀን ክፋት ጠበቃቸው፡፡ (ፊታቸው) ማማርንና መደሰትንም ገጠማቸው፡፡ 76|12|በመታገሣቸውም ገነትንና የሐር ልብስን መነዳቸው፡፡ 76|13|በውስጧ በባለ አጎበር አልጋዎች ላይ ተደጋፊዎች በውስጧ ፀሐይንም ጨረቃንም የማያዩ ሲኾኑ፡፡ 76|14|ዛፎችዋም በእነርሱ ላይ የቀረበች፣ ፍሬዎችዋም (ለለቃሚዎች) መግገራትን የተገራች ስትኾን (ገነትን መነዳቸው)፡፡ 76|15|በእነርሱም ላይ ከብር በኾኑ ዕቃዎች (ሰሐኖች) የብርጭቆዎች በኾኑ ኩባያዎችም ይዝዞርባቸዋል፡፡ 76|16|መለካትን የለኳቸው በኾኑ የብር ብርጭቆዎች (ይዝዞርባቸዋል)፡፡ 76|17|በእርሷም መበረዣዋ ዘንጀቢል የኾነችን ጠጅ ይጠጣሉ፡፡ 76|18|በውስጧ ያለችውን ሰልሰቢል ተብላ የምትጠራውን ምንጭ፡፡ 76|19|በእነርሱም ላይ (ባሉበት ኹነታ) የሚዘወትሩ ወጣት ልጆች ይዘዋወራሉ፡፡ ባየሃቸው ጊዜ የተበተነ ሉል ናቸው ብለህ ታስባቸዋለህ፡፡ 76|20|እዚያም በተመለከትክ ጊዜ ጸጋንና ታላቅ ንግሥናን ታያለህ፡፡ 76|21|አረንጓዴዎች የኾኑ የቀጭን ሐር ልብሶችና ወፍራም ሐርም በላያቸው ላይ አልለ፡፡ ከብር የኾኑ አንባሮችንም ይሸለማሉ፡፡ ጌታቸውም አጥሪ የኾነን መጠጥ ያጠጣቸዋል፡፡ 76|22|«ይህ በእርግጥ ለእናንተ ዋጋ ኾነ፡፡ ሥራችሁም ምስጉን ኾነ፤» (ይባላሉ)፡፡ 76|23|እኛ ቁርኣንን ባንተ ላይ ማውረድን እኛው አወረድነው፡፡ 76|24|ለጌታህ ፍርድም ታገሥ፡፡ ከእነርሱም ኀጢአተኛን ወይም ከሓዲን አትታዘዝ፡፡ 76|25|የጌታህንም ስም በጧትና ከቀትር በላይ አውሳ፡፡ 76|26|ከሌሊቱም ለእርሱ ስገድ፡፡ በረዢም ሌሊትም አወድሰው፡፡ 76|27|እነዚያ ፈጣኒቱን ዓለም ይወዳሉ፡፡ ከባድን ቀንም በስተፊታቸው ኾኖ ይተዋሉ፡፡ 76|28|እኛ ፈጠርናቸው፡፡ መለያልያቸውንም አጠነከርን፡፡ በሻንም ጊዜ መሰሎቻቸውን መለወጥን እንለውጣለን፡፡ 76|29|ይህቺ መገሠጫ ናት፡፡ የሻም ሰው ወደ ጌታው መንገድን ይይዛል፡፡ 76|30|አላህም ካልሻ በስተቀር አትሹም፡፡ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡ 76|31|የሚሻውን ሰው በእዝነቱ ውስጥ ያገባዋል፡፡ በዳዮቹንም (ዝቶባቸዋል)፡፡ ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣትን አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ 77|1|ተከታታይ ኾነው በተላኩት፣ 77|2|በኀይል መንፈስን ነፋሾች በኾኑትም፣ 77|3|መበተንን በታኞች በኾኑትም፤ (ነፋሶች)፣ 77|4|መለየትን ለይዎች በኾኑትም፣ 77|5|መገሠጫን (ወደ ነቢያት) ጣይዎች በኾኑትም፣ 77|6|ምክንያትን ለማስወገድ ወይም ለማስፈራራት (ጣይዎች በኾኑት መላእክት) እምላለሁ፡፡ 77|7|ያ የምትስፈራሩበት (ትንሣኤ) በእርግጥ ኋኝ ነው፡፡ 77|8|ከዋክብትም (ብርሃንዋ) በታበሰች ጊዜ፡፡ 77|9|ሰማይም በተከፈተች ጊዜ፡፡ 77|10|ጋራዎችም በተንኮተኮቱ ጊዜ፡፡ 77|11|መልክተኞቹም ወቅት በተደረገላቸው ጊዜ፡፡ 77|12|ለየትኛው ቀን ተቀጠሩ (የሚባል ሲኾን)፤ 77|13|ለመለያው ቀን (በተባለ ጊዜ፤ በፍጡሮች መካከል ይፈረዳል)፡፡ 77|14|የመለያውም ቀን ምን እንደኾነ ምን አሳወቀህ? 77|15|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|16|የፊተኞቹን (ሕዝቦች) አላጠፋንምን? 77|17|ከዚያም የኋለኞቹን እናስከትላቸዋለን፡፡ 77|18|በአመጸኞች ሁሉ እንደዚሁ እንሠራለን፡፡ 77|19|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|20|ከደካማ ውሃ አልፈጠርናችሁምን? 77|21|በተጠበቀ መርጊያ ውስጥም (በማሕፀን) አደረግነው፡፡ 77|22|እስከ ታወቀ ልክ ድረስ፡፡ መጠንነውም፤ ምን ያማርንም 77|23|መጣኞች ነን! 77|24|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|25|ምድርን ሰብሳቢ አላደረግናትምን? 77|26|ሕያዋን ኾናችሁ ሙታንም ኾናችሁ፡፡ 77|27|በውስጧም ከፍተኛዎችን ተራራዎች አደረግን፡፡ ጣፋጭ ውሃንም አጠጣናችሁ፡፡ 77|28|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|29|«ወደዚያ በእርሱ ታስተባብሉ ወደ ነበራችሁት (ቅጣት) አዝግሙ፡፡ 77|30|«ባለ ሦስት ቅርንጫፎች ወደ ኾነው ጥላ አዝግሙ፤» (ይባላሉ)፡፡ 77|31|አጠላይ ያልኾነ ከእሳቱም ላንቃ የማያድን ወደ ኾነው (አዝግሙ)፡፡ 77|32|እርሷ እንደ ታላላቅ ሕንጻ የኾኑን ቃንቄዎች ትወረውራለች፡፡ 77|33|(ቃንቄውም) ልክ ዳለቻዎች ግመሎችን ይመስላል፡፡ 77|34|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|35|ይህ የማይናገሩበት ቀን ነው፡፡ 77|36|ይቅርታም ይጠይቁ ዘንድ፤ ለእነርሱ አይፈቀድላቸውም፡፡ 77|37|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|38|ይህ መለያው ቀን ነው፡፡ እናንተንም የፊተኞቹንም ሰብሰብናችሁ፡፡ 77|39|ለናንተም (ለማምለጥ) ብልሃት እንዳላችሁ ተተናኮሉኝ፡፡ 77|40|ላስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|41|ጥንቁቆቹ በጥላዎችና በምንጮች ውስጥ ናቸው፡፡ 77|42|ከሚከጅሉትም ሁሉ በፍራፍሬዎች ውስጥ ናቸው፡፡ 77|43|«ትሠሩት በነበራችሁት ዋጋ የምትደሰቱ ኾናችሁ ብሉ፣ ጠጡም፤» (ይባላሉ)፡፡ 77|44|እኛ እንደዚሁ መልካም ሠሪዎችን ሁሉ እንመነዳለን፡፡ 77|45|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|46|ብሉ፤ ጥቂትንም (ጊዜ) ተጠቀሙ፡፡ እናንተ አመጸኞች ናችሁና፡፡ 77|47|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|48|«ለእነርሱ ስገዱም» በተባሉ ጊዜ አይሰግዱም፡፡ 77|49|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 77|50|ከእርሱም ሌላ በየትኛው ንግግር ያምናሉ? 78|1|ከምን ነገር ይጠያየቃሉ? 78|2|ከታላቁ ዜና (ከቁርኣን ይጠያየቃሉ)፡፡ 78|3|ከዚያ እነርሱ በእርሱ የተለያዩበት ከኾነው፡፡ 78|4|ይከልከሉ፤ ወደፊት (የሚደርስበቸውን) በእርግጥ ያውቃሉ፡፡ 78|5|ከዚያም ይከልከሉ፤ ወደፊት ያውቃሉ፡፡ 78|6|ምድርን ምንጣፍ አላደረግንምን? 78|7|ጋራዎችንም ችካሎች አላደረግንምን? 78|8|ብዙ ዓይነቶችም አድርገን ፈጠርናችሁ፡፡ 78|9|እንቅልፋችሁንም ዕረፍት አደረግን፡፡ 78|10|ሌሊቱንም ልባስ አደረግን፡፡ 78|11|ቀኑንም (ለኑሮ) መስሪያ አደረግን፡፡ 78|12|ከበላያችሁም ሰባትን ብርቱዎች (ሰማያት) ገነባን፡፡ 78|13|አንጸባራቂ ብርሃንንም አደረግን፡፡ 78|14|ከአረገዙት ደመናዎችም ተንቧቢ ውሃን አወረድን፡፡ 78|15|በእርሱ እኽልንና ቅጠላ ቅጠልን እናወጣ ዘንድ (አወረድን)፡፡ 78|16|የተቆላለፉ አትክልቶችንም፡፡ 78|17|የመለያው ቀን የተወሰነ ጊዜ ነው፡፡ 78|18|በቀንዱ በሚነፋና የተለያዩ ጭፍሮች ኾናችሁ በምትመጡ ቀን ነው፡፡ 78|19|ሰማይም በምትከፈትና (ባለ) ደጃፎችም በምትኾንበት፡፡ 78|20|ጋራዎችም በሚነዱበት (እንደ) ሲሪብዱም በሚኾኑበት (ቀን) ነው፡፡ 78|21|ገሀነም መጠባበቂያ (ስፍራ) ናት፡፡ 78|22|ለሕግ ተላላፊዎች መመለሻ ስትኾን፡፡ 78|23|በውስጧ ብዙን ዘመናት ነዋሪዎች ሲኾኑ፤ 78|24|በውስጧ ቅዝቃዜንም መጠጥንም አይቀምሱም፡፡ 78|25|ግን ሙቅ ውሃንና እዥን (ይቀምሳሉ)፡፡ 78|26|ተስማሚን ምንዳ ይምመነዳሉ፡፡ 78|27|እነርሱ ምርመራን የማይፈሩ ነበሩና፡፡ 78|28|በአንቀጾቻችንም ማስተባበልን አስተባበሉና፡፡ 78|29|ነገሩንም ሁሉ የተጻፈ ሲኾን አጠቃለልነው፡፡ 78|30|ቅመሱም ቅጣትንም እንጅ (ሌላን) አንጨምራችሁም (ይባላሉ)፡፡ 78|31|ለጥንቁቆቹ መዳኛ ስፍራ አልላቸው፡፡ 78|32|አትክልቶችና ወይኖችም፡፡ 78|33|እኩያዎች የኾኑ ጡተ ጉቻማዎችም፡፡ 78|34|የተሞሉ ብርጭቆዎችም፡፡ 78|35|በውስጧ ትርፍ ቃልንም ማስዋሸትንም አይሰሙም፡፡ 78|36|ከጌታህ የኾነን ምንዳ በቂ ስጦታን (ተሰጡ)፡፡ 78|37|የሰማያትና የምድር በመካከላቸውም ያለው ሁሉ ጌታ በጣም አዛኝ ከኾነው (ተመነዱ)፡፡ ከእርሱ ጋር መነጋገርን አይችሉም፡፡ 78|38|መንፈሱ (ጂብሪል) መላእክቶቹም የተሰለፉ ኾነው በሚቆሙ ቀን አል-ረሕማን ለእርሱ የፈቀደለትና ትክክለኛን ቃል ያለ ሰው ቢኾን እንጅ (መነጋገርን አይችሉም)፡፡ 78|39|ይህ የተረጋገጠው ቀን ነው፡፡ የሻም ሰው ወደ ጌታው መመለስን ይይዛል፡፡ 78|40|እኛ ሰው ሁሉ እጆቹ ያስቀደሙትን በሚያይበትና ከሓዲውም ዋ ምኞቴ! ምንነው ዐፈር በኾንኩ በሚልበት ቀን ቅርብ የኾነን ቅጣት አስጠነቀቅናችሁ፡፡ 79|1|በኃይል አውጪዎች በኾኑት፤ 79|2|በቀስታ መምዘዝንም መዘዦች በኾኑት፤ 79|3|መዋኘትም ዋኚዎች በኾኑት፤ 79|4|መቅደምንም ቀዳሚዎች በኾኑት፤ 79|5|ነገርንም አስተናባሪዎች በኾኑት (መላእክት) እምላለሁ፡፡ (በእርግጥ ትቀሰቀሳላችሁ)፡፡ 79|6|ተርገፍጋፊይቱ (ምድር) በምትርገፈገፍበት ቀን፤ 79|7|ለጣቂይቱ የምትከተላት ስትኾን (ትቀሰቀሳላችሁ)፡፡ 79|8|በዚያ ቀን ልቦች ተሸባሪዎች ናቸው፡፡ 79|9|ዓይኖቻቸው ተዋራጆች (አቀርቃሪዎች) ናቸው፡፡ 79|10|«እኛ ወደ መጀመሪያይቱ ኹነታ ተመላሾች ነን?» ይላሉ፡፡ 79|11|«የበሰበሱ አጥንቶች በኾን ጊዜ (እንቀሰቀሳለን?)» 79|12|«ይህቺ ያን ጊዜ ባለ ከሳራ መመለስ ናት» ይላሉ፡፡ 79|13|እርሷም አንዲት ጩኸት ብቻ ናት፡፡ 79|14|ወዲያውኑም እነርሱ እንቅልፍ በሌለባት (ምድር) ላይ ይኾናሉ፡፡ 79|15|የሙሳ ወሬ መጣልህን? 79|16|ጌታው በተቀደሰው ሸለቆ በጡዋ በጠራው ጊዜ፤ 79|17|ወደ ፈርዖን ኺድ፡፡ እርሱ ወሰን አልፏልና፡፡ 79|18|በለውም፡- «ወደ መጥራራትህ ላንተ (መንገድ) አለህን?» 79|19|«ወደ ጌታህም ልመራህ ትፈራውም ዘንድ፤ (መንገድ አለህን?)» አለው፡፡ 79|20|ታላቂቱንም ተዓምር አሳየው፡፡ 79|21|አስተባበለም፤ አመጸም፡፡ 79|22|ከዚያም (ለማጥፋት) የሚተጋ ኾኖ ዞረ፡፡ 79|23|(ሰራዊቶቹን) ሰበሰበም፤ ተጣራም፡፡ 79|24|አለም፡- «እኔ ታላቁ ጌታችሁ ነኝ፡፡» 79|25|አላህም በኋለኛይቱና በፊተኛይቱ (ቃል) ቅጣት ያዘው፡፡ 79|26|በዚህ ውስጥ ለሚፈራ ሰው በእርግጥ መገምገሚያ አለበት፡፡ 79|27|ባፈጣጠር እናንተ ይበልጥ የበረታችሁ ናችሁን? ወይንስ ሰማይ? (አላህ) ገነባት፡፡ 79|28|ከፍታዋን አጓነ፤ አስተካከላትም፡፡ 79|29|ሌሊቷንም አጨለመ፡፡ ቀንዋንም ገለጸ፡፡ 79|30|ምድርንም ከዚህ በኋላ ዘረጋት፡፡ 79|31|ውሃዋንና ግጦሿን ከእርሷ አወጣ፡፡ 79|32|ጋራዎችንም አደላደላቸው፡፡ 79|33|ለእናንተና ለእንስሶቻችሁ መጣቀሚያ ይኾን ዘንድ (ይህን አደረገ)፡፡ 79|34|ታላቂቱም መዐት በመጣች ጊዜ፣ 79|35|ሰው ሁሉ የሠራውን በሚያስታውስበት ቀን፣ 79|36|ገሀነምም ለሚያይ ሰው በተገለጠች ጊዜ፣ 79|37|የካደ ሰውማ፣ 79|38|ቅርቢቱንም ሕይወት የመረጠ፣ 79|39|ገሀነም እርሷ በእርግጥ መኖሪያው ናት፡፡ 79|40|በጌታው ፊት መቆምን የፈራ ሰውማ ነፍሱንም ከዝንባሌዋ የከለከለ 79|41|ገነት እርሷ በእርግጥ መኖሪያው ናት፡፡ 79|42|«ከሰዓቲቱ መቼ ነው መኾኛዋ?» ሲሉ ይጠይቁሃል፡፡ 79|43|አንተ እርሷን ከማስታወስ በምን ውስጥ ነህ? 79|44|(የዕውቀት) መጨረሻዋ ወደ ጌታህ ብቻ ነው፡፡ 79|45|አንተ የሚፈራትን ሰው አስፈራሪ ብቻ ነህ፡፡ 79|46|እነርሱ በሚያዩዋት ቀን ያንዲት ቀን ምሽትን ወይም ረፏዷን እንጅ ያልቆዩ ይመስላሉ፡፡ 80|1|ፊቱን አጨፈገገ፤ ዞረም፡፡ 80|2|ዕውሩ ስለ መጣው፡፡ 80|3|ምን ያሳውቅሃል? (ከኀጢአቶቹ) ሊጥራራ ይከጀላል፡፡ 80|4|ወይም ሊገሠጽ ግሠጼይቱም ልትጠቅመው (ይከጀላል)፡፡ 80|5|የተብቃቃው ሰውማ፤ 80|6|አንተ ለእርሱ (ለእምነቱ በመጓጓት) በፈገግታ ትቀበለዋለህ፡፡ 80|7|ባይጥራራ (ባያምን) ባንተ ላይ ምንም የሌለብህ ስትኾን፡፡ 80|8|እየገሰገሰ የመጣህ ሰውማ፤ 80|9|እርሱ (አላህን) የሚፈራ ሲኾን፤ 80|10|አንተ ከእርሱ ትዝዘናጋለህ፡፡ 80|11|ተከልከል፡፡ እርሷ ማስገንዘቢያ ናት፡፡ 80|12|የሻም ሰው (ቁርኣኑን) ያስታውሰዋል፡፡ 80|13|በተከበሩ ጽሑፎች ውስጥ ነው፡፡ 80|14|ከፍ በተደረገች ንጹሕ በተደረገች (ጽሑፍ ውስጥ ነው)፡፡ 80|15|በጸሐፊዎቹ (መላእክት) እጆች (ንጹሕ የተደረገች)፡፡ 80|16|የተከበሩና ታዛዦች በኾኑት (ጸሐፊዎች እጆች)፡፡ 80|17|ሰው ተረገመ፤ ምን ከሓዲ አደረገው? 80|18|(ጌታው) በምን ነገር ፈጠረው? (አያስብምን?) 80|19|ከፍትወት ጠብታ ፈጠረው፤ መጠነውም፡፡ 80|20|ከዚያም (መውጫ) መንገዱን አገራው፡፡ 80|21|ከዚያም ገደለው፤ እንዲቀበርም አደረገው፡፡ 80|22|ከዚያም (ማንሳቱን) በሻ ጊዜ ያስነሳዋል፡፡ 80|23|በእውነት ያንን (ጌታው) ያዘዘውን ገና አልፈጸመም፡፡ 80|24|ሰውም ወደ ምግቡ ይመልከት፡፡ 80|25|እኛ ውሃን ማንቧቧትን ያንቧቧን መኾናችንን፡፡ 80|26|ከዚያም ምድርን (በደካማ ቡቃያ) መሰንጠቅን የሰነጠቅን፤ 80|27|በውስጧም እኽልን ያበቀልን፤ 80|28|ወይንንም፤ እርጥብ ያበቀልን፤ 80|29|የዘይት ወይራንም ዘንባባንም፤ 80|30|ጭፍቆች አትክልቶችንም፤ 80|31|ፍራፍሬንም ገለባንም፤ (ያበቀልን መኾናችንን ይመልከት)፡፡ 80|32|ለእናንተም ለእንስሶቻችሁም መጠቀሚያ ይኾን ዘንድ (ይህን ሠራን)፡፡ 80|33|አደንቋሪይቱም (መከራ) በመጣች ጊዜ፤ 80|34|ሰው ከወንድሙ በሚሸሽበት ቀን፤ 80|35|ከናቱም ካባቱም፤ 80|36|ከሚስቱም ከልጁም፤ 80|37|ከእነርሱ ለየሰው ሁሉ በዚያ ቀን (ከሌላው) የሚያብቃቃው ኹነታ አልለው፡፡ 80|38|ፊቶች በዚያ ቀን አብሪዎች ናቸው፤ 80|39|ሳቂዎችም ተደሳቾችም ናቸው፡፡ 80|40|ፊቶችም በዚያ ቀን በላያቸው ላይ ትቢያ አልለባቸው፤ 80|41|ጥቁረት ትሸፍናቸዋለች፤ 80|42|እነዚያ እነሱ ከሓዲዎቹ አመጸኞቹ ናቸው፡፡ 81|1|ፀሐይ በተጠቀለለች ጊዜ፤ 81|2|ከዋክብትም በረገፉ ጊዜ፤ 81|3|ተራራዎችም በተነዱ ጊዜ፤ 81|4|የዐሥር ወር እርጉዞች ግመሎችም (ያለጠባቂ) በተተዉ ጊዜ፤ 81|5|እንስሳትም ሁሉ በተሰበሰቡ ጊዜ፤ 81|6|ባሕሮችም በተቃጠሉ ጊዜ፤ 81|7|ነፍሶችም (በየአካሎቻቸው) በተቆራኙ ጊዜ፤ 81|8|በሕይወቷ የተቀበረችውም ሴት ልጅ በተጠየቀች ጊዜ፤ 81|9|በምን ወንጀል እንደ ተገደለች፤ 81|10|ጽሑፎችም በተዘረጉ ጊዜ፤ 81|11|ሰማይም በተገሸለጠች ጊዜ፤ 81|12|ገሀነምም በተነደደች ጊዜ፤ 81|13|ገነትም በተቀረበች ጊዜ፤ 81|14|ነፍስ ሁሉ (ከሥራ) ያቀረበችውን ታውቃለች፤ 81|15|ተመላሾችም በኾኑት (ዐዋድያት) እምላለሁ፡፡ 81|16|ኺያጆች ገቢዎች በኾኑት (ከዋክብት)፡፡ 81|17|በሌሊቱም (ጨለማውን) በጠነሰሰ ጊዜ፤ 81|18|በንጋቱም (በብርሃን) በተነፈሰ ጊዜ፤ (እምላለሁ)፡፡ 81|19|እርሱ (ቁርኣን) የክቡር መልክተኛ ቃል ነው፡፡ 81|20|የኀይል ባለቤት በዙፋኑ ባለ ቤት ዘንድ ባለሟል የኾነ፡፡ 81|21|በዚያ ስፍራ ትእዛዙ ተሰሚ፤ ታማኝ የኾነ (መልክተኛ ቃል) ነው፡፡ 81|22|ነቢያችሁም በፍጹም ዕብድ አይደለም፡፡ 81|23|በግልጹ አድማስም በእርግጥ አይቶታል፡፡ 81|24|እርሱም በሩቁ ወሬ ላይ ሰሳች (ንፉግ) አይደለም፡፡ 81|25|እርሱም (ቁርኣን) የእርጉም ሰይጣን ቃል አይደለም፡፡ 81|26|ታዲያ ወዴት ትኼዳላችሁ? 81|27|እርሱ የዓለማት መገሠጫ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡ 81|28|ከናንተ ቀጥተኛ መኾንን ለሻ ሰው (መገሰጫ ነው)፡፡ 81|29|የዓለማት ጌታ አላህ ካልሻም አትሹም፡፡ 82|1|ሰማይ በተሰነጠቀች ጊዜ፤ 82|2|ከዋክብትም ተበታትነው በወደቁ ጊዜ፤ 82|3|ባሕሮችም በተከፈቱና በተደበላለቁ ጊዜ፤ 82|4|መቃብሮችም በተገለባበጡና (ሙታን) በተነሱ ጊዜ፤ 82|5|ማንኛይቱም ነፍስ ያስቀደመችውንና ያቆየችውን ታውቃለች፡፡ 82|6|አንተ ሰው ሆይ! በቸሩ ጌታህ ምን አታለለህ? 82|7|በዚያ በፈጠረህ አካለ ሙሉም ባደረገህ ባስተካከለህም፡፡ 82|8|በማንኛውም በሻው ቅርፅ በገጣጠመህ (ጌታህ ምን አታለለህ)፡፡ 82|9|ተከልከሉ፤ በእውነቱ በፍርዱ ቀን ታስተባብላላችሁ፡፡ 82|10|በእናንተ ላይ ተጠባባቂዎች ያሉባችሁ፤ ስትኾኑ፤ 82|11|የተከበሩ ጸሐፊዎች የኾኑ፤ (ተጠባባቂዎች)፡፡ 82|12|የምትሠሩትን ሁሉ የሚያውቁ፡፡ 82|13|እውነተኞቹ ምእምናን በእርግጥ በገነት ውስጥ ናቸው፡፡ 82|14|ከሓዲዎቹም በእርግጥ በገሀነም ውስጥ ናቸው፡፡ 82|15|በፍርዱ ቀን ይገቧታል፡፡ 82|16|እነርሱም ከርሷ ራቂዎች አይደሉም፡፡ 82|17|የፍርድ ቀን ምን እንደኾነ ምን አሳወቀህ? 82|18|ከዚያም የፍርዱ ቀን ምን እንደኾነ ምን አሳወቀህ? 82|19|(እርሱ) ማንኛይቱም ነፍስ ለሌላይቱ ነፍስ ምንም ማድረግን የማትችልበት ቀን ነው፡፡ ነገሩም ሁሉ በዚያ ቀን ለአላህ ብቻ ነው፡፡ 83|1|ለሰላቢዎች ወዮላቸው፡፡ 83|2|ለእነዚያ ከሰዎች ባስሰፈሩ ጊዜ የሚያስሞሉ፡፡ 83|3|ለእነርሱም (ለሰዎቹ) በሰፈሩ ወይም በመዘኑላቸው ጊዜ የሚያጎድሉ (ለኾኑት)፡፡ 83|4|እነዚያ እነርሱ ተቀስቃሾች መኾናቸውን አያውቁምን? 83|5|በታላቁ ቀን፡፡ 83|6|ሰዎች ሁሉ ለዓለማት ጌታ (ፍርድ)፤ በሚቆሙበት ቀን (ተቀስቃሾች መኾናቸውን)፡፡ 83|7|በእውነት የከሓዲዎቹ (የሰላቢዎቹ) መጽሐፍ በእርግጥ በሲጂን ውስጥ ነው፡፡ 83|8|ሲጂንም ምን እንደ ኾነ ምን አሳወቀህ? 83|9|የታተመ መጽሐፍ ነው፡፡ 83|10|ለአስተባባዮች በዚያ ቀን ወዮላቸው፡፡ 83|11|ለእነዚያ በፍርዱ ቀን ለሚያስተባብሉት፡፡ 83|12|በእርሱም ወሰን አላፊ ኀጢአተኛ ሁሉ እንጅ ሌላ አያስተባብልም፡፡ 83|13|አንቀጾቻችን በእርሱ ላይ በተነበቡ ጊዜ «የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ተረቶች ናቸው» ይላል፡፡ 83|14|ይከልከል፤ ይልቁንም በልቦቻቸው ላይ ይሠሩት የነበሩት (ኀጢአት) ደገደገባቸው፡፡ 83|15|ይከልከሉ፤ እነርሱ በዚያ ቀን ከጌታቸው (ማየት) ተጋራጆች ናቸው፡፡ 83|16|ከዚያም እነርሱ በእርግጥ ገሀነምን ገቢዎች ናቸው፡፡ 83|17|ከዚያም «ይህ ያ በእርሱ ታስተባብሉበት የነበራችሁት ነው» ይባላሉ፡፡ 83|18|በእውነቱ የእውነተኞቹ ምእምናን መጽሐፍ በዒሊዮን ውስጥ ነው፡፡ 83|19|ዒሊዮንም ምን እንደ ኾነ ምን አሳወቀህ? 83|20|የታተመ መጽሐፍ ነው፡፡ 83|21|ባለሟልዎቹ ይጣዱታል፡፡ 83|22|እውነተኞቹ ምእምናን በእርግጥ በድሎት (ገነት) ውስጥ ናቸው፡፡ 83|23|በባለ አጎበር አልጋዎች ላይ ኾነው ይመለከታሉ፡፡ 83|24|በፊቶቻቸው ላይ የድሎትን ውበት ታውቃለህ፡፡ 83|25|ተጣርቶ ከታተመ ጠጅ ይጠጣሉ፡፡ 83|26|ማተሚያው ምስክ ከኾነ፤ በዚህም ተሽቀዳዳሚዎች ይሽቀዳደሙ፡፡ 83|27|መበረዣውም ከተስኒም ነው፡፡ 83|28|ባለሟሎቹ ከእርሷ የሚጠጡላት ምንጭ ናት፡፡ 83|29|እነዚያ ያምመጹት በእነዚያ ባመኑት በእርግጥ ይስቁ ነበሩ፡፡ 83|30|በእነርሱም ላይ ባለፉ ጊዜ ይጠቃቀሱ ነበር፡፡ 83|31|ወደ ቤተሰቦቻቸውም በተመለሱ ጊዜ (በመሳለቃቸው) ተደሳቾች ኾነው ይመለሱ ነበር፡፡ 83|32|ባዩዋቸውም ጊዜ «እነዚህ በእርግጥ ተሳሳቾች ናቸው» ይሉ ነበር፡፡ 83|33|በነርሱ ላይ ተጠባባቂዎች ተደርገው ያልተላኩ ሲኾኑ፡፡ 83|34|ዛሬ (በትንሣኤ ቀን) እነዚያ ያመኑት በከሓዲዎቹ ይስቃሉ፡፡ 83|35|በባለ አጎበር አልጋዎች ላይ ኾነው የሚመለከቱ ሲኾኑ (ይስቃሉ)፡፡ 83|36|ከሓዲዎች ይሠሩት የነበሩትን (ዋጋ) ተመነዱን? (ይላሉ)፡፡ 84|1|ሰማይ በተቀደደች ጊዜ፤ 84|2|ለጌታዋም (ትዕዛዝ) በሰማች ጊዜ፤ (ልትሰማ) ተገባትም፤ 84|3|ምድርም በተለጠጠች ጊዜ፤ 84|4|በውስጧ ያለውንም ሁሉ በጣለችና ባዶ በኾነች ጊዜ፤ 84|5|ለጌታዋም በሰማች ጊዜ፤ (መስማት) ተገባትም፤ (ሰው ሁሉ ሥራውን ይገናኛል)፡፡ 84|6|አንተ ሰው ሆይ! አንተ ጌታህን (በሞት) እስከምትገናኝ ድረስ ልፋትን ለፊ ነህ፤ ተገናኚውም ነህ፡፡ 84|7|መጽሐፉን በቀኙ የተሰጠ ሰውማ፤ 84|8|በእርግጥ ቀላልን ምርመራ ይመረመራል፡፡ 84|9|ወደ ቤተሰቦቹም ተደሳች ኾኖ ይመለሳል፡፡ 84|10|መጽሐፉን በጀርባው ኋላ የተሰጠ ሰውማ፤ 84|11|(ዋ! ጥፋቴ በማለት) ጥፋትን በእርግጥ ይጠራል፡፡ 84|12|የተጋጋመች እሳትንም ይገባል፡፡ 84|13|እርሱ በቤተሰቡ ውስጥ ተደሳች ነበርና፡፡ 84|14|እርሱ (ወደ አላህ) የማይመለስ መኾኑን አስቧልና፡፡ 84|15|አይደለም (ይመለሳል)፡፡ ጌታው በእርሱ (መመለስ) ዐዋቂ ነበር፤ (ነውም)፡፡ 84|16|አትካዱ፤ በወጋገኑ እምላለሁ፡፡ 84|17|በሌሊቱም በሰበሰውም ሁሉ፤ 84|18|በጨረቃውም በሞላ ጊዜ (እምላለሁ)፡፡ 84|19|ከኹነታ በኋላ ወደ ሌላ ኹነታ ትለዋወጣላችሁ፡፡ 84|20|የማያምኑት ለእነርሱ ምን አላቸው? 84|21|በእነርሱም ላይ ቁርኣን በተነበበ ጊዜ የማይሰግዱት፤ (ምንአላቸው?) 84|22|በእርግጡ እነዚያ የካዱት (በትንሣኤ) ያስተባብላሉ፡፡ 84|23|አላህም (በልቦቻቸው) የሚቆጥሩትን ዐዋቂ ነው፡፡ 84|24|በአሳማሚ ቅጣትም አብስራቸው፡፡ 84|25|ግን እነዚያ ያመኑና መልካሞችን የሠሩ ለእነርሱ የማይቆረጥ ምንዳ አልላቸው፡፡ 85|1|የቡርጆች ባለቤት በኾነችው ሰማይ እምላለሁ፡፡ 85|2|በተቀጠረው ቀንም፤ 85|3|በተጣጅና በሚጣዱትም፤ (እምላለሁ)፡፡ 85|4|የጉድቡ ባለቤቶች ተረገሙ፡፡ 85|5|የማገዶ ባለቤት የኾነቺው እሳት (ባለቤቶች)፡፡ 85|6|እነርሱ በርሷ (አፋፍ) ላይ ተቀማጮች በኾኑ ጊዜ፤ (ተረገሙ)፡፡ 85|7|እነርሱም በምእምናኖቹ በሚሠሩት (ማሰቃየት) ላይ መስካሪዎች ናቸው፡፡ 85|8|ከእነርሱም በአላህ አሸናፊው፣ ምስጉኑ በኾነው (ጌታ) ማመናቸውን እንጅ ሌላ ምንም አልጠሉም፡፡ 85|9|በእዚያ የሰማያትና የምድር ንግሥና ለእርሱ ብቻ በኾነው (አላህ ማመናቸውን)፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ መስካሪ ነው፡፡ 85|10|እነዚያ ምእምንንና ምእምናትን ያሰቃዩ፣ ከዚያም ያልተጸጸቱ ለእነርሱ የገሀነም ቅጣት አልላቸው፡፡ ለእነርሱም የመቃጠሉ ስቃይ አልላቸው፡፡ 85|11|እነዚያ ያመኑና መልካም ሥራዎችንም የሠሩ ለእነርሱ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶች አሏቸው፡፡ ይህ ታላቅ ማግኘት ነው፡፡ 85|12|የጌታህ በኀይል መያዝ ብርቱ ነው፡፡ 85|13|እነሆ እርሱ መፍጠርን ይጀምራል፤ ይመልሳልም፡፡ 85|14|እርሱም ምሕረተ ብዙ ወዳድ ነው፡፡ 85|15|የዙፋኑ ባለቤት የላቀው ነው፡፡ 85|16|የሚሻውን ሁሉ ሠሪ ነው፡፡ 85|17|የሰራዊቶቹ ወሬ መጣልህን? 85|18|የፈርዖንና የሰሙድ፤ (ወሬ)፡፡ 85|19|በእውነቱ እነዚያ የካዱት በማስተባበል ውስጥ ናቸው፡፡ 85|20|አላህም በዙሪያቸው (በዕውቀቱ) ከባቢ ነው፡፡ 85|21|ይልቁንም እርሱ የከበረ ቁርኣን ነው፡፡ 85|22|የተጠበቀ በኾነ ሰሌዳ ውስጥ ነው፡፡ 86|1|በሰማዩ በሌሊት መጪውም እምላለሁ፡፡ 86|2|የሌሊት መጪውም ምን እንደ ኾነ ምን አሳወቀህ? 86|3|ጨለማን ቀዳጁ ኮከብ ነው፡፡ 86|4|ነፍስ ሁሉ በእርሷ ላይ ጠባቂ ያለባት እንጅ ሌላ አይደለችም፡፡ 86|5|ሰውም ከምን እንደተፈጠረ ይመልከት፡፡ 86|6|ከተስፈንጣሪ ውሃ ተፈጠረ፡፡ 86|7|ከጀርባና ከእርግብግብቶች መካከል የሚወጣ ከኾነ (ውሃ)፡፡ 86|8|እርሱ (አላህ) በመመለሱ ላይ በእርግጥ ቻይ ነው፡፡ 86|9|ምስጢሮች በሚገለጡበት ቀን፡፡ 86|10|ለእርሱም (ለሰው) ኀይልና ረዳት ምንም የለውም፡፡ 86|11|የመመለስ ባለቤት በኾነችው ሰማይም እምላለሁ፡፡ 86|12|(በበቃይ) የመሰንጠቅ ባለቤት በኾነችው ምድርም፤ 86|13|እርሱ (እውነትን ከውሸት) የሚለይ ቃል ነው፡፡ 86|14|እርሱም ቀልድ አይደለም፡፡ 86|15|እነርሱ በእርግጥ ተንኮልን ይሠራሉ፡፡ 86|16|(እኔ) ተንኮልንም እመልሳለሁ፡፡ 86|17|ከሓዲዎችንም ቀን ስጣቸው፡፡ ጥቂትን ጊዜ አቆያቸው፡፡ 87|1|ከሁሉ በላይ የኾነውን ጌታህን ስም አሞግሥ፡፡ 87|2|የዚያን (ሁሉን ነገር) የፈጠረውን ያስተካከለውንም፡፡ 87|3|የዚያንም የወሰነውን፡፡ (ለተፈጠረለት ነገር) የመራውንም፡፡ 87|4|የዚያንም ግጦሽን (ለምለም አድርጎ) ያወጣውን፡፡ 87|5|(ከዚያ) ደረቅ ጥቁር ያደረገውንም (አምላክ ስም አሞግስ)፡፡ 87|6|(ቁርኣንን) በእርግጥ እናስነብብሃለን፤ አትረሳምም፡፡ 87|7|አላህ ከሻው ነገር በስተቀር፡፡ እርሱ ግልጹን የሚሸሸገውንም ሁሉ ያውቃልና፡፡ 87|8|ለገሪቱም (ሕግጋት) እንገጥምሃለን፡፡ 87|9|ግሣጼይቱ ብትጠቅም (ሰዎችን) ገሥጽም፡፡ 87|10|(አላህን) የሚፈራ ሰው በእርግጥ ይገሠጻል፡፡ 87|11|መናጢውም ይርቃታል፡፡ 87|12|ያ ታላቂቱን እሳት የሚገባው፡፡ 87|13|ከዚያም በእርሷ ውስጥ አይሞትም ሕያውም አይኾንም፡፡ 87|14|የተጥራራ ሰው በእርግጥ ዳነ፡፡ 87|15|የጌታውንም ስም ያወሳና የሰገደ፡፡ 87|16|ይልቁንም ቅርቢቱን ሕይወት ትመርጣላችሁ፡፡ 87|17|መጨረሻይቱ (ሕይወት) በላጭ ሁል ጊዜ ዘውታሪም ስትኾን፡፡ 87|18|ይህ በፊተኞቹ መጻሕፍት ውስጥ ያልለ ነው፡፡ 87|19|በኢብራሂምና በሙሳ ጽሑፎች ውስጥ፡፡ 88|1|የሸፋኝቱ (ትንሣኤ) ወሬ መጣህን? 88|2|ፊቶች በዚያ ቀን ተዋራጆች ናቸው፡፡ 88|3|ሠሪዎች ለፊዎች ናቸው፡፡ 88|4|ተኳሳን እሳት ይገባሉ፡፡ 88|5|በጣም ከፈላች ምንጭ ይጋታሉ፡፡ 88|6|ለእነርሱ ዶሪዕ ከሚባል (እሾሃም) ዛፍ እንጅ ሌላ ምግብ የላቸውም፡፡ 88|7|የማያሰባ ከረኃብም የማያብቃቃ ከኾነው፡፡ 88|8|ፊቶች በዚያ ቀን ተቀማጣዮች ናቸው፡፡ 88|9|ለሥራቸው ተደሳቾች ናቸው፡፡ 88|10|በከፍተኛ ገነት ውስጥ ናቸው፡፡ 88|11|በውስጧ ውድቅን ነገር አይሰሙም፡፡ 88|12|በውስጧ ፈሳሾች ምንጮች አልሉ፡፡ 88|13|በውስጧ ከፍ የተደረጉ አልጋዎች አልሉ፡፡ 88|14|በተርታ የተኖሩ ብርጭቆዎችም፡፡ 88|15|የተደረደሩ መከዳዎችም፡፡ 88|16|የተነጠፉ ስጋጃዎችም (አልሉ)፡፡ 88|17|(ከሓዲዎች) አይመለከቱምን? ወደ ግመል እንዴት እነደተፈጠረች! 88|18|ወደ ሰማይም እንዴት ከፍ እንደ ተደረገች! 88|19|ወደ ተራራዎችም እንዴት እንደ ተቸከሉ! 88|20|ወደ ምድርም እንዴ እንደተዘረጋች (አይመለከቱምን?) 88|21|አስታውስም፤ አንተ አስታዋሽ ብቻ ነህና፡፡ 88|22|በእነርሱ ላይ ተሿሚ (አስገዳጅ) አይደለህም፡፡ 88|23|ግን (ከእውነት) የዞረና የካደ ሰው፤ 88|24|አላህ ታላቁን ቅጣት ይቀጣዋል፡፡ 88|25|መመለሻቸው ወደእኛ ብቻ ነው፡፡ 88|26|ከዚያም ምርመራቸው በእኛ ላይ ብቻ ነው፡፡ 89|1|በጎህ እምላለሁ፡፡ 89|2|በዐሥር ሌሊቶችም፡፡ 89|3|በጥንዱም በነጠላውም፡፡ 89|4|በሌሊቱም በሚኼድ ጊዜ፡፡ 89|5|በዚህ (መሓላ) ለባለ አእምሮ ታላቅ መሓላ አለበትን? 89|6|ጌታህ በዓድ እንዴት እንደ ሠራ አታውቅምን? 89|7|በኢረም በባለ ረዣዢሚቱ አዕማድ፡፡ 89|8|በዚያች ብጤዋ በአገሮች ውስጥ ያልተፈጠረ በኾነችው፡፡ 89|9|በሰሙድም በእነዚያ በሸለቆው ቋጥኝን የቆረጡ በኾኑት፡፡ 89|10|በፈርዖንም ባለ ችካሎች በኾነው፡፡ 89|11|በእነዚያ በአገሮች ላይ ግፍ የሠሩ፡፡ 89|12|በእርሷም ውስጥ ጥፋትን ያበዙ በኾኑት (እንዴት እንደሠራ አታውቅምን?) 89|13|በእነርሱ ላይም ጌታህ የቅጣትን አለንጋ አወረደባቸው፡፡ 89|14|ጌታህ በመጠባበቂያ ላይ ነውና፡፡ 89|15|ሰውማ ጌታው በሞከረው ጊዜ፣ ባከበረውና ባጣቀመውም (ጊዜ) «ጌታዬ አከበረኝ (አበለጠኝ)» ይላል፡፡ 89|16|በሞከረውና በእርሱ ላይ ሲሳዩን ባጠበበ ጊዜማ «ጌታዬ አሳነሰኝ» ይላል፡፡ 89|17|ይከልከል፤ ይልቁንም የቲምን አታከብሩም፡፡ 89|18|ድኻንም በማብላት ላይ አትታዘዙም፡፡ 89|19|የውርስንም ገንዘብ የመሰብሰብን አበላል ትበላላችሁ፡፡ 89|20|ገንዘብንም ብዙን መውደድ ትወዳላችሁ፡፡ 89|21|ተዉ፤ ምድር ደጋግማ በተሰባበረች ጊዜ፤ 89|22|መላእክትም ሰልፍ ሰልፍ ኾነው ጌታህ (ትዕዛዙ) በመጣ ጊዜ፤ 89|23|ገሀነምም በዚያ ቀን በተመጣች ጊዜ በዚያ ቀን ሰው (ጥፋቱን) ይገነዘባል፡፡ መገንዘብም ለእርሱ ከየቱ? 89|24|«ዋ እኔ! ምነው በሕይወቴ (መልካምን ሥራ) ባስቀደምኩ ኖሮ» ይላል፡፡ 89|25|በዚያ ቀንም የርሱን አቀጣጥ አንድም አይቀጣም፡፡ 89|26|የእርሱንም አስተሳሰር አንድም አያስርም፡፡ 89|27|(ለአመነች ነፍስም) «አንቺ የረካሺው ነፍስ ሆይ! 89|28|«ወዳጅ ተወዳጅ ኾነሽ ወደ ጌታሽ ተመለሺ፡፡ 89|29|«በባሮቼም ውስጥ ግቢ፡፡ 89|30|ገነቴንም ግቢ፤» (ትባላለች)፡፡ 90|1|በዚህ አገር (በመካ) እምላለሁ፡፡ 90|2|አንተ በዚህ አገር ሰፋሪ ስትኾን፡፡ 90|3|በወላጂም በወለዳቸውም ሰዎች (በአዳምና በዘሮቹ ሁሉ እምላለሁ)፡፡ 90|4|ሰውን ሁሉ በእርግጥ በልፋት ውስጥ ኾኖ ፈጠርነው፡፡ 90|5|በእርሱ ላይ አንድም የማይችል መኾኑን ይጠረጥራልን? 90|6|«ብዙን ገንዘብ አጠፋሁ» ይላል፡፡ 90|7|አንድም ያላየው መኾኑን ያስባልን? 90|8|ለእርሱ ሁለት ዓይኖችን አላደረግንለትምን? 90|9|ምላስንና ሁለት ከንፈሮችንም፡፡ 90|10|ሁለትን መንገዶችም አልመራነውምን? 90|11|ዓቀበቲቱንም አልወጣም፡፡ 90|12|ዓቀበቲቱም (መውጣቷ) ምን እንደኾነች ምን አሳወቀህ? 90|13|(እርሱ) ጫንቃን መልቀቅ ነው፡፡ 90|14|ወይም የረኃብ ባለቤት በኾነ ቀን ማብላት፡፡ 90|15|የዝምድና ባለቤት የኾነን የቲም፤ 90|16|ወይም የዐፈር ባለቤት የኾነን ድኻ (ማብላት ነው)፡፡ 90|17|(ዐቀበቲቱን አልወጣም)፡፡ ከዚያም ከነዚያ ከአመኑትና በመታገስ አደራ ከተባባሉት፣ በማዘንም አደራ ከተባባሉት ሰዎች አልኾነም፡፡ 90|18|እነዚያ (ይህንን የፈጸሙ) የቀኝ ጓዶች ናቸው፡፡ 90|19|እነዚያም በአንቀጾቻችን የካዱት እነርሱ የግራ ጓዶች ናቸው፡፡ 90|20|በእነርሱ ላይ የተዘጋች እሳት አልለች፡፡ 91|1|በፀሐይና በብርሃኗ እምላለሁ፡፡ 91|2|በጨረቃም በተከተላት ጊዜ፤ 91|3|በቀኑም (ፀሐይን) በገለጻት ጊዜ፤ 91|4|በሌሊቱም በሸፈናት ጊዜ፤ 91|5|በሰማይቱም በገነባትም (ጌታ)፤ 91|6|በምድሪቱም በዘረጋትም፤ 91|7|በነፍስም ባስተካከላትም፤ 91|8|አመጽዋንና ፍርሃትዋንም ባሳወቃት (አምላክ እምላለሁ)፡፡ 91|9|(ከኀጢኣት) ያጠራት ሰው ፍላጎቱን በእርግጥ አገኘ፡፡ 91|10|(በኀጢኣት) የሸፈናትም ሰው በእውነት አፈረ፡፡ 91|11|ሠሙድ ወሰን በማለፍዋ አስተባበለች፡፡ 91|12|ጠማማዋ በተንቀሳቀሰ ጊዜ፡፡ 91|13|ለእነርሱም የአላህ መልክተኛ (ሷሊህ) «የአላህን ግመል የመጠጥ ተራዋንም (ተጠንቀቁ)» አላቸው፡፡ 91|14|አስተባበሉትም፡፡ (ቋንጃዋን) ወጓትም፡፡ በኀጢኣታቸውም ምክንያት ጌታቸው (ቅጣትን) በእነርሱ ላይ ደመደመባቸው፤ አስተካከላትም፡፡ 91|15|ፍጻሜዋንም (የምታስከትለውን) አያፈራም፡፡ 92|1|በሌሊቱ እምላለሁ (በጨለማው) በሚሸፍን ጊዜ፡፡ 92|2|በቀኑም፤ በተገለጸ ጊዜ፡፡ 92|3|ወንድንና ሴትን በፈጠረውም (አምላክ እምላለሁ)፡፡ 92|4|ሥራችሁ በእርግጥ የተለያየ ነው፡፡ 92|5|የሰጠ ሰውማ ጌታውን የፈራም፡፡ 92|6|በመልካሚቱም (እምነት) ያረጋገጠ፤ 92|7|ለገሪቱ ሥራ እናዘጋጀዋለን፡፡ 92|8|የሰሰተ ሰውማ የተብቃቃም፤ (በራሱ የተመካ)፤ 92|9|በመልካሚቱ (እምነት) ያሰተባበለም፤ 92|10|ለክፉይቱ ሥራ እናዘጋጀዋለን፡፡ 92|11|በወደቀም ጊዜ ገንዘቡ ከእርሱ ምንም አይጠቅመውም፡፡ 92|12|ቅኑን መንገድ መግለጽ በእኛ ላይ አለብን፡፡ 92|13|መጨረሻይቱም መጀመሪያይቱም ዓለም የእኛ ናቸው፡፡ 92|14|የምትንቀለቀልንም እሳት አስጠነቀቅኳችሁ (በላቸው)፡፡ 92|15|ከጠማማ በቀር ሌላ የማይገባት የኾነችን፡፡ 92|16|ያ ያስተባበለና ከትዕዛዝ የሸሸው፡፡ 92|17|አላህን በጣም ፈሪውም በእርግጥ ይርቃታል፡፡ 92|18|ያ የሚጥራራ ኾኖ ገንዘቡን (ለድኾች) የሚሰጠው፡፡ 92|19|ለአንድም ሰው እርሱ ዘንድ የምትመለስ ውለታ የለችም፡፡ 92|20|ግን የታላቅ ጌታውን ውዴታ ለመፈለግ (ይህንን ሠራ)፡፡ 92|21|ወደፊትም በእርግጥ ይደሰታል፡፡ 93|1|በረፋዱ እምላለሁ፡፡ 93|2|በሌሊቱም ጸጥ ባለ ጊዜ፤ 93|3|ጌታህ አላሰናበተህም፤ አልጠላህምም፡፡ 93|4|መጨረሻይቱም (ዓለም) ከመጀመሪያይቱ ይልቅ ላንተ በላጭ ናት፡፡ 93|5|ጌታህም ወደ ፊት (ብዙን ስጦታ) በእርግጥ ይሰጥሃል፡፡ ትደሰታለህም፡፡ 93|6|የቲም ኾነህ አላገኘህምና አላስጠጋህምን? (አስጠግቶሃል)፡፡ 93|7|የሳትክም ኾነህ አገኘህ መራህም፡፡ 93|8|ድኻም ኾነህ አገኘህ፤ አከበረህም፡፡ 93|9|የቲምንማ አትጨቁን፡፡ 93|10|ለማኝንም አትገላምጥ፡፡ 93|11|በጌታህም ጸጋ አውራ፤ (ግለጻት)፡፡ 94|1|ልብህን ለአንተ አላሰፋንልህምን? (አስፍተንልሃል)፡፡ 94|2|ሸክምህንም ካንተ አውርደንልሃል፡፡ 94|3|ያንን ጀርባህን ያከበደውን (ሸክም)፡፡ 94|4|መወሳትህንም ላንተ ከፍ አድርገንልሃል፡፡ 94|5|ከችግርም ጋር ምቾት አልለ፡፡ 94|6|ከችግር ጋር በእርግጥ ምቾት አልለ፡፡ 94|7|በጨረስክም ጊዜ ልፋ፡፡ (ቀጥል)፡፡ 94|8|ወደ ጌታህም ብቻ ከጅል፡፡ 95|1|በበለስና በዘይት ወይራ እምላለሁ፡፡ 95|2|በሲኒን ተራራም፤ 95|3|በዚህ በጸጥተኛው አገርም (እምላለሁ)፡፡ 95|4|ሰውን በጣም በአማረ አቋም ላይ ፈጠርነው፡፡ 95|5|ከዚያም (ከፊሉን) ከዝቅተኞች ሁሉ በታች አድርገን መለስነው፡፡ 95|6|ግን እነዚያ ያመኑት መልካሞችንም የሠሩት ለእነርሱ ተቆራጭ ያልኾነ ምንዳ አልላቸው፡፡ 95|7|ታዲያ ከዚህ በኋላ በፍርዱ ምን አስተባባይ አደረገህ? 95|8|አላህ ከፈራጆች ሁሉ ይበልጥ ፈራጅ አይደለምን? (ነው)፡፡ 96|1|አንብብ በዚያ (ሁሉን) በፈጠረው ጌታህ ስም፡፡ 96|2|ሰውን ከረጋ ደም በፈጠረው (ጌታህ ስም)፡፡ 96|3|አንብብ፤ ጌታህ በጣም ቸር ሲኾን፤ 96|4|ያ በብርዕ ያስተማረ፡፡ 96|5|ሰውን ያላወቀውን ሁሉ ያሳወቀ ሲኾን፡፡ 96|6|በእውነቱ ሰው ወሰንን ያልፋል፡፡ 96|7|ራሱን የተብቃቃ (ባለ ሀብት) ኾኖ ለማየቱ፡፡ 96|8|መመለሻው ወደ ጌታህ ብቻ ነው፡፡ 96|9|አየህን? ያንን የሚከለክለውን፡፡ 96|10|ባሪያን በሰገደ ጊዜ፤ 96|11|አየህን? ንገረኝ (ተከልካዩ) በትክክለኛ መንገድ ላይ ቢኾን፤ 96|12|ወይም (ፈጣሪውን) በመፍራት ቢያዝ፤ 96|13|አየህን? ንገረኝ (ከልካዩ) ቢያስተባብልና (ከእምነት) ቢሸሽ፤ 96|14|አላህ የሚያይ መኾኑን አያውቅምን? 96|15|ይተው ባይከለከል አናቱን ይዘን እንጎትተዋለን፡፡ 96|16|ውሸታም ስሕተተኛ የኾነችውን አናቱን፡፡ 96|17|ሸንጎውንም ይጥራ፡፡ 96|18|(እኛም) ዘበኞቻችንን እንጠራለን፡፡ 96|19|ይከልከል አትታዘዘው፡፡ ስገድም፤ (ወደ አላህ) ተቃረብም፡፡ 97|1|እኛ (ቁርኣኑን) በመወሰኛይቱ ሌሊት አወረድነው፡፡ 97|2|መወሰኛይቱም ሌሊተ ምን እንደ ኾነች ምን አሳወቀህ? 97|3|መወሰኛይቱ ሌሊት ከሺሕ ወር በላጭ ናት፡፡ 97|4|በርሷ ውስጥ መላእክትና መንፈሱ በጌታቸው ፈቃድ በነገሩ ሁሉ ይወርዳሉ፡፡ 97|5|እርስዋ እስከ ጎህ መውጣት ድረስ ሰላም ብቻ ናት፡፡ 98|1|እነዚያ ከመጽሐፉ ባለቤቶች ከአጋሪዎቹም የካዱት ግልጹ አስረጅ እስከ መጣላቸው ድረስ (ከነበሩበት ላይ) ተወጋጆች አልነበሩም፡፡ 98|2|(አስረጁም) ከአላህ የኾነ መልክተኛ የተጥራሩን መጽሐፎች የሚያነብ ነው፡፡ 98|3|በውስጧ ቀጥተኛ የኾኑ ጽሑፎች ያሉባት የኾነችን፡፡ 98|4|እነዚያም መጽሐፉን የተሰጡት ሰዎች ግልጽ አስረጅ ከመጣላቸው በኋላ እንጅ አልተለያዩም፡፡ 98|5|አላህን ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ አጥሪዎች፣ ቀጥተኞች ኾነው ሊግገዙት፣ ሶላትንም አስተካክለው ሊሰግዱ ዘካንም ሊሰጡ እንጅ ያልታዘዙ ሲኾኑ (ተለያዩ)፡፡ ይህም የቀጥተኛይቱ (ሃይማኖት) ድንጋጌ ነው፡፡ 98|6|እነዚያ ከመጽሐፉ ሰዎች የካዱት፣ አጋሪዎቹም በገሀነም እሳት ውስጥ ናቸው፤ በውስጧ ዘውታሪዎች ሲኾኑ እነዚያ እነርሱ ከፍጥረት ሁሉ ክፉ ናቸው፡፡ 98|7|እነዚያ ያመኑትና መልካሞችንም የሠሩት፣ እነዚያ እነርሱ ከፍጥረት ሁሉ በላጭ ናቸው፡፡ 98|8|በጌታቸው ዘንድ ምንዳቸው ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው የመኖሪያ ገነቶች ነው፡፡ በውስጣቸው ዘለዓለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ (ይገቡባቸወል)፡፡ አላህ ከእነርሱ ወደደ፡፡ ከእርሱም ወደዱ፡፡ ይህ ጌታውን ለፈራ ሰው ነው፡፡ 99|1|ምድር (በኀይል) መንቀጥቀጥዋን በተንቀጠቀጠች ጊዜ፤ 99|2|ምድር ሸክሞችዋን ባወጣችም ጊዜ፤ 99|3|ሰውም ምን ኾነች? ባለ ጊዜ፤ 99|4|በዚያ ቀን ወሬዎችዋን ትናገራለች፡፡ 99|5|ጌታህ ለእርሷ በማሳወቁ ምክንያት፡፡ 99|6|በዚያ ቀን ሰዎች ሥራዎቻቸውን (ምንዳዋን) እንዲያዩ ይደረጉ ዘንድ (እንደየሥራቸው) የተለያዩ ኾነው (ከመቆሚያው ስፍራ) ይመለሳሉ፡፡ 99|7|የብናኝ ክብደት ያክልም መልካምን የሠራ ሰው ያገኘዋል፡፡ 99|8|የብናኝ ክብደት ያክልም ክፉን የሠራ ሰው ያገኘዋል፡፡ 100|1|እያለከለኩ ሩዋጮች በኾኑት (ፈረሶች) እምላለሁ፡፡ 100|2|(በሰኮናቸው) እያጋጩ እሳትን አውጪዎች በኾኑትም፤ 100|3|በማለዳ ወራሪዎች በኾኑትም፤ 100|4|በእርሱ አቧራን በቀሰቀሱትም፤ 100|5|በ(ጠላት) ክቢ መካከል በእርሱ (በጧት) በተጋፈጡትም እምላለሁ፡፡ 100|6|ሰው ለጌታው ብርቱ ከሓዲ ነው፡፡ 100|7|እርሱም በዚህ ላይ መስካሪ ነው፡፡ 100|8|እርሱም ገንዘብን ለመውደድ በጣም ብርቱ ነው፡፡ 100|9|(ሰው) አያውቅምን? በመቃብሮች ያሉት (ሙታን) በተቀሰቀሱ ጊዜ፤ 100|10|በልቦች ውስጥ ያለውም ሁሉ በተገለጸ ጊዜ (እንዴት እንደሚኾን)፡፡ 100|11|ጌታቸው በዚያ ቀን በእነርሱ (ነገር) በእርግጥ ውስጠ አዋቂ ነው፡፡ 101|1|ቆርቋሪይቱ (ጩኸት)፤ 101|2|ምን አስደናቂ ቆርቋሪ ናት! 101|3|ቆርቋሪይቱም ምን እንደኾነች ምን አሳወቀህ? 101|4|ሰዎች እንደ ተበታተነ ቢራቢሮ (ወይም ኩብኩባ) በሚኾኑበት ቀን፤ 101|5|ጋራዎችም እንደ ተነደፈ ሱፍ በሚኾኑበት (ቀን ልቦችን በድንጋጤ ትቆረቁራለች፡፡) 101|6|ሚዛኖቹ የከበዱለት ሰውማ፤ 101|7|እርሱ በምትወደድ ኑሮ ውስጥ ይኾናል፡፡ 101|8|ሚዛኖቹም የቀለሉበት ሰውማ፤ 101|9|መኖሪያው ሃዊያህ ናት 101|10|እርሷም ምን እንደ ኾነች ምን አሳወቀህ? 101|11|(እርሷ) በጣም ተኳሳ እሳት ናት፡፡ 102|1|በብዛት መፎካከር (ጌታችሁን ከመገዛት) አዘነጋችሁ፡፡ 102|2|መቃብሮችን እስከ ጎበኛችሁ ድረስ፡፡ 102|3|ተከልከሉ፤ ወደፊት (ውጤቱን) ታውቃላችሁ፡፡ 102|4|ከዚያም ተከልከሉ፤ ወደ ፊት ታውቃላችሁ፡፡ 102|5|በእውነቱ (የሚጠብቃችሁን) እርግጠኛ ዕውቀትን ብታውቁ ኖሮ፤ (ባልዘናጋችሁ ነበር)፡፡ 102|6|ገሀነምን በእርግጥ ታያላችሁ፡፡ 102|7|ከዚያም እርግጠኛን ማየት ታዩዋታላችሁ፡፡ 102|8|ከዚያም ከድሎታችሁ ሁሉ በዚያ ቀን ትጠየቃላችሁ፡፡ 103|1|በጊዜያቱ እምላለሁ፡፡ 103|2|ሰው ሁሉ በእርግጥ በከሳራ ውስጥ ነው፡፡ 103|3|እነዚያ ያመኑትና መልካሞችን የሠሩት፣ በእውነትም አደራ የተባባሉት፣ በመታገስም አደራ የተባባሉት ብቻ ሲቀሩ፡፡ 104|1|ለሃሜተኛ ለዘላፊ ሁሉ ወዮለት፡፡ 104|2|ለዚያ ገንዘብን የሰበሰበና የቆጣጠረው (ያደለበውም) ለኾነ ፤(ወዮለት)፡፡ 104|3|ገንዘቡ የሚያዘወትረው መኾኑን ያስባል፡፡ 104|4|ይከልከል፤ በሰባሪይቱ (እሳት) ውስጥ በእርግጥ ይጣላል፡፡ 104|5|ሰባሪይቱም ምን እንደ ኾነች ምን አሳወቀህ? 104|6|የተነደደችው የአላህ እሳት ናት፡፡ 104|7|ያቺ በልቦች ላይ የምትዘልቅ የኾነችው፡፡ 104|8|እርሷ በእርግጥ በእነርሱ ላይ የተዘጋጀች ናት፡፡ 104|9|በተዘረጋች አዕማድ ውስጥ (የተዘጋች ናት)፡፡ 105|1|በዝሆኑ ባለቤቶች ጌታህ እንዴት እንደሠራ አላወቅህምን? 105|2|ተንኮላቸውን በጥፋት ውስጥ (ከንቱ) አላደረገምን? (አድርጓል)፡፡ 105|3|በእነርሱም ላይ መንጎች የኾኑን ዎፎች ላከ፡፡ 105|4|ከተጠበሰ ጭቃ በኾነ ድንጋይ የምትወረውርባቸው የኾነችን፤ (አዕዋፍ)፡፡ 105|5|ቅጠሉ እንደ ተበላ አዝመራም አደረጋቸው፡፡ 106|1|ቁረይሽን ለማላመድ (ባለዝሆኖቹን አጠፋ)፡፡ 106|2|የብርድና የበጋን ወራት ጉዞ ሊያላምዳቸው ይህንን ሠራ፡፡ 106|3|ስለዚህ የዚህን ቤት (የከዕባን) ጌታ ይግገዙ፡፡ 106|4|ያንን ከረኃብ ያበላቸውን ከፍርሃትም ያረካቸውን (ጌታ ያምልኩ)፡፡ 107|1|ያንን በምርመራው የሚያስተባብለውን አየህን? (ዐወቅከውን?) 107|2|ይህም ያ የቲምን በኀይል የሚገፈትረው፤ 107|3|ድኻንም በማብላት ላይ የማያግባባው ሰው ነው፡፡ 107|4|ወዮላቸው ለሰጋጆች፡፡ 107|5|ለእነዚያ እነርሱ ከስግደታቸው ዘንጊዎች ለኾኑት፤ (ሰጋጆች)፡፡ 107|6|ለእነዚያ እነርሱ ይዩልኝ ባዮች ለኾኑት፡፡ 107|7|የዕቃ ትውስትንም (ሰዎችን) የሚከለክሉ ለኾኑት (ወዮላቸው)፡፡ 108|1|እኛ በጣም ብዙ በጎ ነገሮችን ሰጠንህ፡፡ 108|2|ስለዚህ ለጌታህ ስገድ፤ (በስሙ) ሰዋም፡፡ 108|3|ጠይህ (የሚጠላህ) እርሱ በእርግጥ (ዘሩ) የተቆረጠው ነው፡፡ 109|1|በላቸው «እናንተ ከሓዲዎች ሆይ! 109|2|«ያንን የምትግገዙትን (ጣዖት አሁን) አልግገዛም፡፡ 109|3|«እናንተም እኔ የምግገዛውን (አምላክም አሁን) ተገዢዎች አይደላችሁም፡፡ 109|4|«እኔም ያንን የተገዛችሁትን (ወደፊት) ተገዢ አይደለሁም፡፡ 109|5|«እናንተም እኔ የምግገዛውን (ወደፊት) ተገዢዎች አይደላችሁም፡፡ 109|6|«ለእናንተ ሃይማኖታችሁ አልላችሁ፡፡ ለእኔም ሃይማኖቴ አለኝ፡፡ 110|1|የአላህ እርዳታና (መካን) መክፈት በመጣ ጊዜ፤ 110|2|ሰዎችንም ጭፍሮች እየኾኑ፤ በአላህ ሃይማኖት ውስጥ ሲገቡ ባየህ ጊዜ፤ 110|3|ጌታህን ከማመስገን ጋር አጥራው፡፡ ምሕረትንም ለምነው፡፡ እርሱ ጸጸትን በጣም ተቀባይ ነውና፡፡ 111|1|የአቡ ለሀብ ሁለት እጆች ከሰሩ (ጠፉ፤ እርሱ) ከሰረም፡፡ 111|2|ከእርሱ ገንዘቡና ያም ያፈራው ሁሉ ምንም አልጠቀመውም፡፡ 111|3|የመንቀልቀል ባለቤት የኾነችን እሳት በእርግጥ ይገባል፡፡ 111|4|ሚስቱም (ትገባለች)፤ እንጨት ተሸካሚ ስትኾን፡፡ 111|5|በአንገትዋ ላይ ከጭረት የኾነ ገመድ ያለባት ስትኾን፡፡ 112|1|በል «እርሱ አላህ አንድ ነው፡፡ 112|2|«አላህ (የሁሉ) መጠጊያ ነው፡፡ 112|3|«አልወለደም፤ አልተወለደምም፡፡ 112|4|«ለእርሱም አንድም ብጤ የለውም፡፡» 113|1|በል «በተፈልቃቂው ጎህ ጌታ እጠበቃለሁ፡፡ 113|2|«ከፈጠረው ፍጡር ሁሉ ክፋት፡፡ 113|3|«ከሌሊትም ክፋት ባጨለመ ጊዜ፤ 113|4|«በተቋጠሩ (ክሮች) ላይ ተፊዎች ከኾኑት (ደጋሚ) ሴቶችም ክፋት፡፡ 113|5|«ከምቀኛም ክፋት በተመቀኘ ጊዜ፤ (እጠበቃለሁ በል)፡፡» 114|1|በል «በሰዎች ፈጣሪ እጠበቃለሁ፡፡ 114|2|«የሰዎች ሁሉ ንጉሥ በኾነው፡፡ 114|3|«የሰዎች አምላክ በኾነው፡፡ 114|4|«ብቅ እልም ባይ ከኾነው ጎትጓች (ሰይጣን) ክፋት፡፡ 114|5|«ከዚያ በሰዎች ልቦች ውስጥ የሚጎተጉት ከኾነው፡፡ 114|6|«ከጋኔኖችም ከሰዎችም (ሰይጣናት እጠበቃለሁ በል)፡፡» # -------------------------------------------------------------------- # # Quran Translation # Name: ሳዲቅ & ሳኒ ሐቢብ # Translator: Muhammed Sadiq and Muhammed Sani Habib # Language: Amharic # ID: am.sadiq # Last Update: August 3, 2012 # Source: Tanzil.net # # --------------------------------------------------------------------